05/21/2026
«ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት፣ ወነበረ በየማነ አቡሁ» (በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ፣ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ)
========
( አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ እንደጻፉት)
መግቢያ፦ የትንፋሻችን ልዕልና ወደ አርያም
ሰውነትን ከተዋረደበት የዕዳ ማዕበል አውጥቶ፣ ልቡናን በተመስጦ ወደ ሰማየ ሰማያት የሚያሻግር አንድ ታላቅ ምሥጢር ቢኖር እርሱ የበዓለ ዕርገት ምሥጢር ነው። ይህ ዕለት ምድርና ሰማይ ፍጹም የታረቁበት፣ ከአፈር የተገኘው የሰነፍ አዳም ባሕርይ ከኪሩቤልና ከሱራፌል በላይ ከፍ ብሎ የከበረበት የድኅነታችን ማኅተም ነው።
ለመሆኑ «ዐርገ» (ወጣ) ስንል ወዴት ወጣ? የትስ ነበረ? እርሱ ለመውጣት ስፍራ የማይሻ፣ ለመውረድም ክንድ የማይጎድለው ምሉዕ በኩለሔ አምላክ ነው። ነገር ግን እኛን ፍለጋ ወደ ታችኛው የምድር ክፍል የወረደው ያው የባሕርይ አምላክ፣ ዛሬ በእኛ ሥጋ፣ በእኛ ደምና በእኛ ተፈጥሮ ወደ ቀደመ ክብሩ በታላቅ ምስጋና ተመለሰ።
ይህ ትምህርት እንዲሁ የታሪክ ድርሳን ሳይሆን፣ የሰው ልጅ ተፈጥሮ እስከ እግዚአብሔር ቀኝ ድረስ የተጓዘበትን ሰማያዊ ጉዞ የሚያስረዳ የብርሃን መንገድ ነው። አሁን ልባችንን ከተንኰለኛው ዓለም ሐሳብ አርቀን፣ ዓይነ ሕሊናችንን ወደ ደብረ ዘይት ተራራ አንጋጠን፣ ይህንን ድንቅ መለኮታዊ ምሥጢር በክፍል በክፍል እንቃኘዋለን።
ክፍል አንድ፦ መውረድና መውጣት፣ የሥጋና የቃል ዕርገት፣ የክርስቶስ የማዳን ጉዞ
«አረገ» (ወጣ) ለመባል አስቀድሞ «ወረደ» መባሉ ግድ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በኤፌሶን መልእክቱ ላይ፦ «ወደ ላይ ወጣ ሲል፥ አስቀድሞ ወደ ምድር ታችኛው ክፍል ደግሞ ወረደ ማለት ካልሆነ ምን ማለት ነው? ይህ የወረደው ሁሉን ይሞላ ዘንድ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው ያው ነው» (ኤፌ ፬፥፱) በማለት እንደገለጠው፣ የክርስቶስ ዕርገት መሠረቱ መውረዱ ነው።
ነገር ግን እዚህ ላይ መመልከት የሚያሻን በመጀመሪያ መውጣትና መወረድ ለማይስማማው፣ በምሉዕነቱ ሰማይና ምድርን ለሞላው ለእግዚአብሔር ወልድ «ወረደ» ማለት ምን ማለት ነው? እርሱ ከሰማይ ሲወርድ ሰማይ አልጎደለችም፣ ወደ ምድርም ሲመጣ ምድር አልጠበበችውም። መውረዱ የቦታ መለዋወጥ ሳይሆን፣ የማይታየው ባሕርዩ በሥጋ መገለጡ (ዕሩቅ ብእሲን መዋሐዱ) ነው፤ መውጣቱም ሥጋን ይዞ የባሕርይ ክብሩን መግለጡ ነው።
የሥጋና የቃል ዕርገት (በማኅፀንና በዓርባ ቀን)
ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን በአንድምታ ትርጓሜያቸው ይህንን ምሥጢር በሁለት ከፍለው ያሳዩናል፦
የቃል ዕርገት በማኅፀን፦ ቃል ሥጋን ከመዋሐዱ (ከተዋሕዶ) አስቀድሞ፣ መለኮት በቅድስናውና በልዕልናው ከፍ ያለ ነበር። ነገር ግን በፍቅሩ ምክንያት ወደ ድንግል ማርያም ማኅፀን ወረደ። በማኅፀን ሳለ ግን ያ የቃል (የመለኮት) ልዕልና አልጠፋም፤ በታናሽነቱ ውስጥ ታላቅነቱ፣ በውርደቱ ውስጥ ክብሩ ነበረ
የቃል ገንዘብ ለሥጋ ሆነ ሉዓላዊ ቃል ምድራዊ ሆነ
የሥጋ ገንዘብ ለቃል ሆነ ምድራዊ ሥጋ ሉዓላዊ ሰማያዊ ሆነ
የሥጋ ዕርገት በዓርባ ቀን፦ ጌታችን ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ በአርባኛው ቀን ሥጋን ይዞ ወደ ቀደመ ክብሩ ወጣ። ይህ የአርባ ቀን ዕርገት የቃል ዕርገት ይባላል። ምክንያቱም የወረደው መለኮት ከቶም ከሰማይ ከዙፋኑ ባይናወጥም የሥጋን ውሱኑነት ገንዘቡ ስላደረገ በማኅፀነ ወረደ ተባለ በአርባ ቀን ዐረገ ተባለ ፤ ስለዚህ ከዐፈር የተገኘው፣ መከራ የተቀበለው፣ የሞተውና የተነሣው የሰውነታችን (የሥጋችን) ባሕርይ ከሁሉ በላይ ከፍ ከፍ አለ
ከማኅፀን እስከ ቀራንዮ፤ ከትንሣኤ እስከ በዝግ ቤት እስከ መግባት
ይህ ከሰማይ የወረደው የባሕርይ አምላክ፣ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በነሳው ሥጋ በጥቂት በጥቂቱ አደገ። በሥጋዌው ምሥጢር ፍጹም ሰው ሆነ። በሠላሳ ዘመኑ በዮርዳኖስ ወንዝ በእደ ዮሐንስ ተጠመቀ፤ ይህ የተደረገው ለኃጢአት ሳይሆን የእኛን የዕዳ ደብዳቤ ለመቅደድና የልጅነትን ምሥጢር ለመመሥረት ነበር።
ከጥምቀት በኋላ ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ በመሄድ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾመ፣ ጸለየ፤ ጠላታችን ዲያብሎስን ድል ነሳልን። ከዚያም ለሦስት ዓመት ከሦስት ወር በዚህች ምድር ላይ እየተዘዋወረ የሕይወትን ወንጌል አስተማረ፣ ሙታንን አስነሳ፣ ዕውራንን አበራ፣ ለምጻሞችን አነጻ።
ትምህርቱ ከምር ሲረዳለት፣ ምሥጢሩ በደቀ መዛሙርቱ ልብ ሲታተም፣ ለድኅነተ ዓለም (ዓለምን ለማዳን) ራሱን መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ።
በቀራንዮ አደባባይ በእንጨት መስቀል ላይ ተሰቅሎ፣ በሃይለ መለኮቱ ሕያው ሆኖ በሥጋ ሞተ። በፈሰሰው ቅዱስ ደሙ ዓለምን ከዲያብሎስ ባርነት ዋጃት። ሙስና መቃብርን አጥፍቶ (መቃብርን አሸንፎ) በሦስተኛው ቀን በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ተነሣ።
ትንሣኤው በግልጥ የታየ፣ መቃብሩ ባዶ መሆኑ የተረጋገጠ ነበር። ለደቀ መዛሙርቱ በተለያዩ ጊዜያት እየተገለጠ ትንሣኤውን በተጨባጭ እንዲረዱት አደረጋቸው፤ ጎኑን አሳያቸው፣ ከእነርሱም ጋር በላ፣ ጠጣ። ይህ የሆነው ትንሣኤው መንፈሳዊ ቅዠት ሳይሆን እውነተኛ፣ ሥጋና አጥንት ያለው መሆኑን ደቀ መዛሙርቱ አምነው እንዲረዱትና ለዓለም እንዲመሰክሩ ነው።
ክፍል ሁለት፦ አርባ ቀን የት ቆየ? ለምንስ በዕለተ ትንሣኤው ወዲያው አላረገም?
ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ፣ ወዲያውኑ በዚያኑ ዕለት ወደ ሰማይ አላረገም። በምድር ላይ አርባ ቀን ሙሉ ቆየ። ሐዋርያው ቅዱስ ሉቃስ በግብረ ሐዋርያት መጽሐፉ ላይ፦ «እነርሱም ደግሞ አርባ ቀን እየታያቸው ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት ነገር እየነገራቸው፥ በብዙ ማስረጃ ከሕማማቱ በኋላ ሕያው ሆኖ ለነሱ ራሱን አሳያቸው» (ሐዋ ፩፥፫) በማለት ይህንን እውነት አስፍሮታል።
ለመሆኑ እነዚህን አርባ ቀናት የት ቆየ? ለምንስ ዕለቱን አላረገም? የቤተክርስቲያን ሊቃውንት ይህንን ምሥጢር በአራት አበይት ምክንያቶች ይተነትኑታል።
፩ኛ. የትንሣኤውን እውነተኝነት ፍጹም ለማረጋገጥ
ጌታችን ወዲያውኑ በትንሣኤው ዕለት ዐርጎ ቢሆን ኖሮ፣ አይሁድና ክፉዎች «ትንሣኤው እውነት አይደለም፤ አልተነሣም፣ ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ሰረቁት እንጂ» የሚሉትን አጉል ወሬ ይበልጥ ባናፈሱት ነበር። ደቀ መዛሙርቱም ቢሆኑ በድንጋጤና በፍርሃት ውስጥ ስለነበሩ፣ ትንሣኤውን እንደ መንፈስ ወይም እንደ ቅዠት ሊቆጥሩት ይችሉ ነበር።
ስለዚህ አርባ ቀን ሙሉ በተለያየ ስፍራና ጊዜ እየተገለጠ፦
ከእነርሱ ጋር በማዕድ ተቀመጠ፣ ዓሳና ማር በላ (ሥጋዊ ፍላጎት ኖሮት ሳይሆን ሥጋዊ ትንሣኤውን ለማረጋገጥ)።
ቅዱስ ቶማስን «ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን» (ዮሐ ፳፥፳፯) በማለት በጥበብ አረጋገጠለት።
ይህ ሁሉ የሆነው ትንሣኤው ፍጹም የተረጋገጠና ሊታበል የማይችል ዐለት መሆኑን ለመመሥረት ነው።
፪ኛ. አርባ ቀን የት ቆየ? (የሥርዓተ ቤተክርስቲያን ጉባኤ)
በእነዚህ አርባ ቀናት ጌታችን በሥጋዊ ሕይወት እዚህም እዚያም እንደሚንከራተት ሰው አልነበረም። ታዲያ የት ነበረ? ሊቃውንቱ «ኢየሩሳሌም በዘጋጉት ቤት (በማርቆስ እናት ቤት)፣ በገሊላ ባህር አጠገብ፣ በደብረ ዘይት ተራራ» እያሉ ደቀ መዛሙርቱ ባሉበት ስፍራ ሁሉ ይገኝ እንደነበር ይናገራሉ። ነገር ግን ዋነኛው ምሥጢር በእነዚህ ቀናት የሰማይና የምድር ጌታ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር የምሥጢራትና የሥርዓት ጉባኤ ማድረጉ ነው።
ቤተክርስቲያን የምትመራበትን ሥርዓተ ቀኖና፣ ምሥጢረ ጥምቀትን፣ ምስጢረ ቁርባንን፣ የክህነትን ሥልጣን (ዮሐ ፳፥፳፪) የሰጣቸውና ያስተማራቸው በእነዚህ አርባ ቀናት ውስጥ ነው። ለዚህ ነው በትርጓሜ መጻሕፍት «ኪዳን» እና «አስተስርዮ» የሚባሉት ሰማያዊ መጻሕፍት በዚህ ጊዜ ለሐዋርያት የተሰጡ የሥርዓት መጻሕፍት ተደርገው የሚቆጠሩት።
፫ኛ. አዳም በገነት የቆየበትን ዕድሜ ለመካስ (የቀናት ምሥጢር)
በትርጓሜ ሊቃውንት ዘንድ ሌላው ጥልቅ ምሥጢር የቀናት ቁጥር ነው። አዳም በተፈጠረ በመጀመሪያው ሳምንት ወደ ገነት አልገባም፤ አርባ ቀን ከሆነው በኋላ ነው ወደ ገነት የገባው (መጽሐፈ ኩፋሌን ይመለከቷል)። በገነትም ሳለ ሕጉን አፍርሶ ወጣ።
ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ ደግሞ በበደለኛው አዳም ምትክ ሆኖ፣ አዳም ሳይቀደስበትና ሳይኖርበት የቀረውን ያንን የአርባ ቀን ምስጢር እርሱ በትንሣኤው ሕያው ሆኖ በምድር ላይ በመቆየት ቀደሰው። አዳም ከአርባ ቀን በኋላ ወደ ገነት እንደገባ፣ ክርስቶስም ከአርባ ቀን ቆይታ በኋላ ወደ ሰማያዊቷ ገነት ወደ አባቱ ቀኝ ገባ።
፬ኛ. የመንፈስ ቅዱስን ተስፋ ለመስጠትና ልባቸውን ለማጽናት
ደቀ መዛሙርቱ ጌታቸው ጥሏቸው ፈጥኖ ቢሄድ ኖሮ እንደ እረኛ እንደሌላቸው በጎች ይበተኑ ነበር። ስለዚህ አርባ ቀን ሙሉ እያስተማረ፣ እየመገበ፣ ፍርሃታቸውን እያራቀ ካዘጋጃቸው በኋላ «ከኢየሩሳሌም አትውጡ፣ ከአብ የተሰጠውን የተስፋ ቃል ጠብቁ» (ሐዋ ፩፥፬) በማለት የመንፈስ ቅዱስን መውረድ (ጰራቅሊጦስን) ተስፋ ሰጣቸው። ይህ ቆይታ ደቀ መዛሙርቱን ከፍርሃት ወደ ድፍረት፣ ከጥርጣሬ ወደ ፍጹም እምነት ያሻገረበት ድልድይ ነበር።
ክፍል ሦስት፦ ስለ ዕርገት የተነገሩ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች፣
የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት በድንገት የተደረገ ሳይሆን፣ አስቀድሞ በብሉይ ኪዳን በነቢያት አንደበት የተነገረ፣ በሐዲስ ኪዳንም በሐዋርያት የተመሰከረ ታላቅ ምሥጢር ነው። የትርጓሜ መምህራን እነዚህን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በታሪክ፣ በአማናዊነትና በምሥጢር እንዲህ ይተረጉሟቸዋል፦
፩ኛ. የቅዱስ ዳዊት ትንቢት (መዝሙር ፵፮፥፭)
«ዐርገ እግዚአብሔር በይባቤ ወእግዚእነ በቃለ ቀርን»
(እግዚአብሔር በእልልታ፥ ጌታችን በመለከት ድምፅ ዐረገ።)
ትርጓሜውና ምሥጢሩ፦ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ይህንን የተናገረው ከክርስቶስ ልደት አንድ ሺህ ዘመን አስቀድሞ ነው። «በእልልታና በመለከት» ማረጉ ምን ማለት ነው? በሊቃውንት ትርጓሜ፣ እልልታና መለከት የድል አድራጊነት ምልክቶች ናቸው። ንጉሥ በጦርነት ጠላቱን ድል አድርጎ ሲመለስ በሕዝቡ ዘንድ እልልታና መለከት ይነፋል።
ክርስቶስም ሞትን ድል አድርጎ፣ ዲያብሎስን ማርኮ፣ ሲዖልን በርብሮ ወደ ሰማይ ሲያርግ ቅዱሳን መላእክት በሰማያዊ እልልታና በምስጋና መለከት ተቀብለውታል።
አንድምታው፦ «እግዚአብሔር» ያለው መለኮቱን ሲሆን፣ «ጌታችን» ያለው ደግሞ እኛን ለማዳን የተዋሐደውን ሥጋውን ነው። ስለዚህ መለኮትና ሥጋ በተዋሕዶ ከብረው በታላቅ ምስጋና ዐረጉ ማለት ነው።
፪ኛ. የቅዱስ ዳዊት ትንቢት (መዝሙር ፷፯፥፲፰)
«ዐረገ ውስተ አርያም ጼዋውከ ጼዋዌ ወወሀብከ ጸጋከ ለዕጓለ እመሕያው»
(ወደ ላይ ዐረግህ፥ ምርኮን ማረክህ፥ ስጦታዎችንም ለሰዎች ሰጠህ።)
ትርጓሜውና ምሥጢሩ፦ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በኤፌሶን ፬፥፰ ላይ ይህንን ጥቅስ በማምጣት የክርስቶስ ዕርገት መሆኑን አረጋግጧል። «ምርኮን ማረክህ» ማለት አዳምና ልጆቹ በአጋንንት ተማርከው በሲዖል ነበሩ። ክርስቶስ ግን በሞቱና በትንሣኤው እነዚያን የዲያብሎስ ምርኮኞች የነበሩትን ነፍሳት ነጻ አውጥቶ፣ ወደ ገነትና ወደ ሰማያዊው ክብር ይዟቸው ዐረገ (ምርኮኛውን መልሶ ማረከው)።
«ለሰዎች ሥጦታን ሰጠህ» የሚለው ደግሞ ከዕርገቱ በኋላ በጥቂት ቀናት (በዓሥረኛው ቀን) ለሐዋርያት ያወረደላቸውን የመንፈስ ቅዱስን ጸጋና ልዩ ልዩ ሀብታትን (ሃብተ ክህነትን፣ሀብተ ፈወስንና ሃብተ ትንቢትን) ያመለክታል።
፫ኛ. የቅዱስ ዳዊት ትንቢት (መዝሙር ፳፫፥፯)
«አርኅዉ ኆኃተ መኳንንት፣ ወይትረኃዋ ኆኃት እለ እምፍጥረት፣ ወይባእ ንጉሠ ስብሐት»
(መኳንንት በሮችን ክፈቱ፥ የዘላለም በሮችም ይከፈቱ፥ የክብር ንጉሥ ይግባ።)
ትርጓሜውና ምሥጢሩ፦ ይህ ጥቅስ የትርጓሜ መምህራን በሰፊው የሚያመሰጥሩት ድንቅ ክፍል ነው። ጌታችን ሥጋን ለብሶ ወደ ሰማይ ሲያርግ፣ በሰማይ ያሉ መላእክት በሁለት ክፍል ቆመው ነበር። የታችኞቹ (ወደ ምድር የቀረቡት) መላእክት ለበላዮቹ «በሮችን ክፈቱ፣ የክብር ንጉሥ ይግባ» አሉ። የበላዮቹ መላእክት ደግሞ «ይህ የክብር ንጉሥ ማን ነው?» አሉ። ምክንያቱም ከዚህ ቀደም የሰው ሥጋ ለብሶ፣ በችንካር ተወግቶ፣ የሞተና የተነሣ አምላክ ወደ ሰማይ ሲያርግ አይተው አያውቁምና።
የታችኞቹ መላእክትም መልሰው፦ «እርሱ በውጊያ ብርቱና ኃያል የሆነው፣ ሰይጣንንና ሞትን ድል ያደረገው እግዚአብሔር ነው» ብለው መለሱላቸው። በዚህም የሰው ልጅ ተፈጥሮ (ሥጋ) ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማይን በሮች ከፍቶ መግባቱ ተገለጠ።
፬ኛ. በሐዲስ ኪዳን (የሉቃስ ወንጌል ፳፬፥፶-፶፩ እና የሐዋርያት ሥራ ፩፥፱)
«ይህንን ካለ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው።»
ትርጓሜውና ምሥጢሩ፦ ወንጌላዊው ሉቃስ የታሪኩን እውነተኝነት ያስረግጣል። «እያዩት» ማለቱ በድብቅ ወይም በሕልም ሳይሆን በግልጽ፣ በአካል፣ ዐይናቸው እያየ መሆኑን ለማሳየት ነው። ደመና መቀበሏ ደግሞ እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ መሆኑን፣ ደመናትን እንደ ሠረገላ የሚጠቀምባት የባሕርይ አምላክ መሆኑን ለማስመስከር ነው።
ክፍል አራት፦ የሄኖክ መሠወር፣ የኤልያስ ዕርገት እና የጻድቃን ዕርገት ከክርስቶስ ዕርገት ጋር በንጽጽር እንመልከተው
በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ውስጥ ከምድር ወደ ላይ የወጡ (የሄዱ) ቅዱሳን አሉ። እነርሱም ሄኖክና ኤልያስ ናቸው። ወደፊትም በትንሣኤ ዘጉባኤ ጻድቃን ሁሉ ይነጠቃሉ። ነገር ግን የእነርሱ መሄድና የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት ሰማይና ምድር ያህል የተራራቁ ናቸው።
የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት «ዐርገ እግዚአብሔር ከመ ያለቡ ዕርገተ ጻድቃን» (የጻድቃንን ዕርገት ያስረዳ ዘንድ እግዚአብሔር ዐረገ) እያሉ ምሥጢሩን ከማጣቀሻ ጋር እንዲህ ያነጻጽሩታል፦
፩ኛ. የሄኖክ መሠወር (ኦሪት ዘፍጥረት ፭፥፳፬)
«ሄኖክም አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር አደረገ፤ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም።»
(በሐዲስ ኪዳንም፦ «ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ፥ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም» ዕብ ፲፩፥፭)ይላል
መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሄኖክ ሲናገር «ወሰደው» (አሻገረው) ነው የሚለው እንጂ «በራሱ ሥልጣን ዐረገ» አይልም። ሄኖክ ፍጡር ነው፤ መሄዱም በራሱ ኃይል ሳይሆን በእግዚአብሔር ረዳትነትና ፈቃድ ነው።
ምስጢራዊ ልዩነቱ፦ ሄኖክ የተወሰደው «ሞትን እንዳያይ» ነው (ለጊዜው ከሞት ቢያመልጥም በኋላ ግን በዓለም ፍጻሜ መጥቶ ይሞታል)። ጌታችን ግን ሞትን አይቶ፣ ሞትን በሞቱ ቀጥቅጦ፣ ተነሥቶ ነው ያረገው። ሄኖክ የተሰወረው በእግዚአብሔር ኃይል ሲሆን፣ ክርስቶስ ግን አሳራጊ ሳይሻ በገዛ የባሕርይ ሥልጣኑ ዐረገ።
፪ኛ. የነቢዩ ኤልያስ ዕርገት (፪ኛ ነገሥት ፪፥፲፩)
«እነሆም፥ የእሳት ሠረገላና የእሳት ፈረሶች በመካከላቸው ተለዩ፥ ኤልያስም በዐውሎ ንፋስ ወደ ሰማይ ወጣ።»
ነቢዩ ኤልያስ ወደ ሰማይ የወጣው በሁለት ነገሮች ተደግፎ ነው፦ አንደኛ በእሳት ሠረገላ፣ ሁለተኛ ደግሞ በዐውሎ ንፋስ ኃይል። ይህ የሚያሳየው ኤልያስ ተሸካሚ፣ አሳራጊና ደጋፊ የሚሻ ደካማ ፍጡር መሆኑን ነው።
የት ነው የሄደው ቢሉ ወደ ሰማየ ሰማያት (ወደ አባቱ ቀኝ) አልወጣም፤ «ወደ ብሔረ ሕያዋን» (የሕያዋን ምድር) ተወሰደ እንጂ።
ምሥጢራዊ ልዩነቱ፦ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ወደ ሰማይ ሲያርግ ምንም ዓይነት የእሳት ሠረገላ ወይም የነፋሳት አውታር አልፈለገም። እርሱ «ገብአ ኀበ ዘትካት ሕላዌሁ» (ወደ ቀደመው የባሕርይ መኖሪያው ተመለሰ) እንደተባለ፣ የሚያሳርገው ሳይሻ በራሱ መለኮታዊ ኃይል ዐረገ። ደመና ተቀበለችው የሚለውም የደብረ ታቦር ደመናና የዕርገት ደመና የባሕሪ ክብሩ መገለጫ ነው
ኤልያስ የተወሰደው ወደ ፍጡር ቦታ (ብሔረ ሕያዋን) ሲሆን፣ ክርስቶስ ግን ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ወደሆነው ወደ ባሕርይ አባቱ ቀኝ ወጣ
፫ኛ. የጻድቃን ዕርገት (፩ኛ ተሰሎንቄ ፬፥፲፯)
«ከዚያም በኋላ እኛ ሕያዋን ሆነን የምንቀረው፥ ጌታን በአየር ላይ ለመቀበል ከእነርሱ ጋር በደመና እንነጠቃለን፤ እንዲሁም ሁልጊዜ ከጌታ ጋር እንሆናለን።»
ጻድቃን በዕለተ ምጽአት ወደ ሰማይ የሚነጠቁት (የሚያርጉት) በራሳቸው ኃይል ሳይሆን በጌታ ጥሪና በመላእክት ሰብሳቢነት ነው። የጻድቃን ዕርገት የተረጋገጠውና ትርጉም ያገኘው በክርስቶስ ዕርገት ነው።
«ዐርገ እግዚአብሔር ከመ ያለቡ ዕርገተ ጻድቃን» የሚለው የምሥጢር ትርጓሜው ይህ ነው፦ ክርስቶስ የሰውን ሥጋ ለብሶ ቀዳሚ (በኩር) ሆኖ ወደ ሰማይ ባያርግ ኖሮ፣ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ወደ ሰማይ መውጣት እንደሚችል አይታወቅም ነበር። እርሱ ግን የሰውን ሥጋ ለብሶ በመውጣቱ፣ እኛም የሰው ልጆች (ጻድቃን) በትንሣኤ ዘጉባኤ ሰማይን መውረስ እንደምንችል በተግባር አሳየን፤ መንገዱን ከፈተልን። ስለዚህ የጻድቃን ዕርገት የክርስቶስ ዕርገት ፍሬና ውጤት ነው።
መለኪያ ሄኖክ / ኤልያስ ጻድቃን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ
የማረግ ኃይል በእግዚአብሔር ሰጪነት (በሠረገላ) በጌታ ኃይል (በነጠቃ) ነው
እርሱ ግን በገዛ የባሕርይ ሥልጣኑ (በራሱ)
እነርሱ የሄዱበት ቦታ ብሔረ ሕያዋን (የፍጡር ቦታ) ነው እርሱ ግን ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ወደ ቀደመው ክብሩ (በአባቱ ቀኝ) ተቀመጠ
የእነርሱ የመሄዳቸው ምሠሰጢር ለአምላክ ክብር ምስክር ለመሆን የደመወዛቸውን ዋጋ ለመቀበልነው
እርሱ ግን የሰውን ባሕርይ አክብሮ ወደ ሸደመ ክብሩ ለማስገባት ነው
ክፍል አምስት፦ የደብረ ዘይት ምሥጢር፣ «እንዘ ይባርኮሙ ተረሐቆሙ »፣
ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአርባኛው ቀን ደቀ መዛሙርቱን ይዟቸው ወደ ኢየሩሳሌም አቅራቢያ ወደምትገኘው ወደ ደብረ ዘይት (የወይራ ተራራ) ወጣ። ይህ ስፍራ እንዲሁ በአጋጣሚ የተመረጠ ሳይሆን፣ የጌታችን የሕማማቱ፣ የጸሎቱና የምሥጢራቱ ሁሉ መተላለፊያ ማዕከል ነበረ።
፩ኛ. «እንዘ ይባርኮሙ ተረሐቆሙ» (እየባረካቸው ተለያቸው)
ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ይህንን ታላቅ ምሥጢር ሲዘግብ፦ «እጆቹንም አንሥቶ ባረካቸው። ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ ወደ ሰማይም ዐረገ» (ሉቃ ፳፬፥፶-፶፩) ይላል።
ጌታችን እጆቹን አንሥቶ የባረካቸው ባርኮት «የስንብት» ሳይሆን «የሥልጣንና የጸጋ» ማኅተም ነው። እጆቹን ሲዘረጋላቸው፣ አዳም በዕፀ በለስ ምክንያት የተረገመውን ያንን የጥንት እርግማን ፈጽሞ ማጥፋቱንና በምትኩ ሰማያዊ በረከትን ማቅረቡን ለማሳየት ነው።
«እየባረካቸው ወደ ላይ ከፍ ከፍ አለ» ሲል፣ ባርኮቱ እንዳልተቋረጠ፣ ያ ጸጋና ሰላም እስከ ዓለም ፍጻሜ ከቤተክርስቲያን ጋር አብሮ እንደሚኖር ለማሳየት ነው። ደቀ መዛሙርቱ ወደ ላይ አንጋጠው እያዩት ማረጉ ደግሞ፣ መሄዱ በምሥጢር ወይም ተደብቆ ሳይሆን ዐይናቸው እያየ ፍጹም እውነተኛ መሆኑን በልባቸው ለመቅረጽ ነው።
፪ኛ. «ደመና ተቀበለችው» (የባሕርይ ክብሩ መገለጫ)
«ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው» (ሐዋ ፩፥፱)። ሊቃውንቱ እዚህ ላይ «ደመና ለምን ተቀበለችው?» የሚለውን በጥልቀት ይተረጉማሉ።
አማናዊ ምሥጢሩ፦ ደመና የተባለችው ጌታችንን ለመሸከም ወይም ደግፋ ወደ ላይ ለማውጣት የመጣች ፍጥረት አይደለችም። በብሉይ ኪዳን ታሪክ እግዚአብሔር ክብሩን በሚገልጥበት ጊዜ ሁሉ በደመና ውስጥ ሆኖ ይገለጥ ነበር (ለምሳሌ በሲና ተራራ፣ በደብረ ታቦር)። ስለዚህ ደመና መቀበሏ የባሕርይ ክብሩ (የመለኮቱ ኃይል) መግለጫ ነው። እርሱ ደመናትን መረገጫ የሚያደርግ፣ ነፋሳትን በቃሉ የሚያዝዝ የሰማይና የምድር ፈጣሪ መሆኑን ለማሳየት ደመና ለክብሩ አገለገለች።
፫ኛ. በቅዱሳን መላእክት ዘንድ የታየው ታላቅ ደስታ
ጌታችን የሰውን ሥጋ ለብሶ፣ ያንን በቀራንዮ የቆሰለውንና በችንካር የተቸነከረውን አካል ይዞ ወደ ሰማየ ሰማያት ሲያርግ በሰማያውያን መላእክት ዘንድ የሆነው ደስታና ድንጋጤ በሰው አንደበት ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም።
ቅዱሳን መላእክት የሰውን ሥጋ ከኪሩቤልና ከሱራፌል በላይ፣ ከአብ ቀኝ ሲቀመጥ አዩት። ከዚህ ቀደም ከመንበሩ ወርዶ የነበረው ጌታ፣ አሁን ግን የሰውን ባሕርይ (ሥጋን) ይዞ ወደ መንበሩ ሲመለስ ታላቅ ሰማያዊ አምልኮና ምስጋና አቀረቡ።
በደብረ ዘይት ተራራ ደቀ መዛሙርቱ ወደ ሰማይ አንጋጠው ሲያዩ፣ ነጫጭ ልብስ የለበሱ ሁለት መላእክት ተገልጠው፦ «የገሊላ ሰዎች ሆይ፥ ወደ ሰማይ እየተመለከታችሁ ስለ ምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁት፥ እንዲሁ ይመጣል» (ሐዋ ፩፥፲፩) አሏቸው። ይህ የመላእክት ምስክርነት የዕርገቱን ፍጻሜ ብቻ ሳይሆን፣ ዳግም በግርማ መለኮት ለፍርድ የሚመጣበትን የዕለተ ምጽአትን ምሥጢር ያበሰረ ነበር።
ዕርገት የድኅነታችን ማጠናቀቂያ ማኅተም ነው።
ጌታችን ሰው ሆኖ ባይወለድ ኖሮ—ሰው አይቀደስም ነበር።
ባይሰቀል ኖሮ—የዕዳ ደብዳቤአችን አይቀደድም ነበር።
ባይነሣ ኖሮ—ሙስና መቃብር አይጠፋም ነበር።
ባያርግ ኖሮ ደግሞ—የሰው ልጅ ተፈጥሮ ወደ ሰማይ ገብቶ ከአምላክ ቀኝ አይቀመጥም ነበር።
ስለዚህ ዕርገት ማለት የሰው ልጅ ተፈጥሮ ከምድር ዐፈር ተነሥቶ፣ በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል እስከ እግዚአብሔር አብ ቀኝ ድረስ የከበረበት፣ የሰማይና የምድር ሰላም የታወጀበት፣ ሰይጣን ፈጽሞ ያፈረረበት ታላቅ የምሥጢር ቀን ነው።
«ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት፣ ወነበረ በየማነ አቡሁ»
ወስብሐት ለእግዚአብሔር።
✍️ “ለግሪክ ሰዎችና ላልተማሩም፥ ለጥበበኞችና ለማያስተውሉም ዕዳ አለብኝ፤”
በወንጌል አላፍርምና፤
አስቀድሞ ለአይሁዳዊ ደግሞም
ለግሪክ ሰው፥ ለሚያምኑ ሁሉ
የእግዚአብሔር ኃይል ለማዳን
ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎ እንደ ተጻፈ የእግዚአብሔር ጽድቅ ከእምነት ወደ እምነት በእርሱ ይገለጣልና። ሮሜ 1÷14
እግዚአብሔር ሆይ የሚሳንህ ነገር የለምና የራቀውን አቅርበህ የረቀቀውን አጉልተህ እየሰማነው ካለነው መርዶና ሰቀቀን ዕረፍተ ሥጋንና ዕረፍተ ነፍስን አትንሣን
ጸልዩ በእንተ ሰላም
ስለ ሰላም እንጸልይ
ስለ ሀገራችን እንጸልይ
ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንጸልይ
በጭንቅ በመከራ ስላሉት እንጸልይ
በረሀብ በስደት ስላሉት እንጸልይ
በጽኑ ሕመም ተይዘው ስለሚሰቃዩት እንጸልይ
ስለ ሃይማኖት መሪዎች አባቶቻችን እንጸልይ
ስለ ሀገር መሪዎች እንጸልይ
የሰላም የምህረት የቸርነት ባለቤት እግዚአብሔር ሰላሙን ምህረቱን ቸርነቱን አይንሳን
አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ፣
ዘዝዋይ ገዳም፣
ግንቦት 12/9/2018 ዓ.ም ✍️