Debre Edom St. Mary Ethiopian Orthodox Tewahedo Church

Debre Edom St. Mary Ethiopian Orthodox Tewahedo Church This page is dedicated to information regarding the religious and social and services of Debre Edom St. [email protected] Tel. 210-920-0871

Mary Ethiopian Orthodox Tewahido Church in San Antonio Texas.

«ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት፣ ወነበረ በየማነ አቡሁ» (በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ፣ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ)========( አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ እንደጻፉት)​መግቢያ፦ የትንፋሻች...
05/21/2026

«ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት፣ ወነበረ በየማነ አቡሁ» (በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ፣ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ)
========
( አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ እንደጻፉት)

​መግቢያ፦ የትንፋሻችን ልዕልና ወደ አርያም
​ሰውነትን ከተዋረደበት የዕዳ ማዕበል አውጥቶ፣ ልቡናን በተመስጦ ወደ ሰማየ ሰማያት የሚያሻግር አንድ ታላቅ ምሥጢር ቢኖር እርሱ የበዓለ ዕርገት ምሥጢር ነው። ይህ ዕለት ምድርና ሰማይ ፍጹም የታረቁበት፣ ከአፈር የተገኘው የሰነፍ አዳም ባሕርይ ከኪሩቤልና ከሱራፌል በላይ ከፍ ብሎ የከበረበት የድኅነታችን ማኅተም ነው።

​ለመሆኑ «ዐርገ» (ወጣ) ስንል ወዴት ወጣ? የትስ ነበረ? እርሱ ለመውጣት ስፍራ የማይሻ፣ ለመውረድም ክንድ የማይጎድለው ምሉዕ በኩለሔ አምላክ ነው። ነገር ግን እኛን ፍለጋ ወደ ታችኛው የምድር ክፍል የወረደው ያው የባሕርይ አምላክ፣ ዛሬ በእኛ ሥጋ፣ በእኛ ደምና በእኛ ተፈጥሮ ወደ ቀደመ ክብሩ በታላቅ ምስጋና ተመለሰ።

​ይህ ትምህርት እንዲሁ የታሪክ ድርሳን ሳይሆን፣ የሰው ልጅ ተፈጥሮ እስከ እግዚአብሔር ቀኝ ድረስ የተጓዘበትን ሰማያዊ ጉዞ የሚያስረዳ የብርሃን መንገድ ነው። አሁን ልባችንን ከተንኰለኛው ዓለም ሐሳብ አርቀን፣ ዓይነ ሕሊናችንን ወደ ደብረ ዘይት ተራራ አንጋጠን፣ ይህንን ድንቅ መለኮታዊ ምሥጢር በክፍል በክፍል እንቃኘዋለን።

ክፍል አንድ፦ መውረድና መውጣት፣ የሥጋና የቃል ዕርገት፣ የክርስቶስ የማዳን ጉዞ
​«አረገ» (ወጣ) ለመባል አስቀድሞ «ወረደ» መባሉ ግድ ነው። ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በኤፌሶን መልእክቱ ላይ፦ «ወደ ላይ ወጣ ሲል፥ አስቀድሞ ወደ ምድር ታችኛው ክፍል ደግሞ ወረደ ማለት ካልሆነ ምን ማለት ነው? ይህ የወረደው ሁሉን ይሞላ ዘንድ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው ያው ነው» (ኤፌ ፬፥፱) በማለት እንደገለጠው፣ የክርስቶስ ዕርገት መሠረቱ መውረዱ ነው።

​ነገር ግን እዚህ ላይ መመልከት የሚያሻን በመጀመሪያ መውጣትና መወረድ ለማይስማማው፣ በምሉዕነቱ ሰማይና ምድርን ለሞላው ለእግዚአብሔር ወልድ «ወረደ» ማለት ምን ማለት ነው? እርሱ ከሰማይ ሲወርድ ሰማይ አልጎደለችም፣ ወደ ምድርም ሲመጣ ምድር አልጠበበችውም። መውረዱ የቦታ መለዋወጥ ሳይሆን፣ የማይታየው ባሕርዩ በሥጋ መገለጡ (ዕሩቅ ብእሲን መዋሐዱ) ነው፤ መውጣቱም ሥጋን ይዞ የባሕርይ ክብሩን መግለጡ ነው።

​የሥጋና የቃል ዕርገት (በማኅፀንና በዓርባ ቀን)
​ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን በአንድምታ ትርጓሜያቸው ይህንን ምሥጢር በሁለት ከፍለው ያሳዩናል፦

​የቃል ዕርገት በማኅፀን፦ ቃል ሥጋን ከመዋሐዱ (ከተዋሕዶ) አስቀድሞ፣ መለኮት በቅድስናውና በልዕልናው ከፍ ያለ ነበር። ነገር ግን በፍቅሩ ምክንያት ወደ ድንግል ማርያም ማኅፀን ወረደ። በማኅፀን ሳለ ግን ያ የቃል (የመለኮት) ልዕልና አልጠፋም፤ በታናሽነቱ ውስጥ ታላቅነቱ፣ በውርደቱ ውስጥ ክብሩ ነበረ
የቃል ገንዘብ ለሥጋ ሆነ ሉዓላዊ ቃል ምድራዊ ሆነ
የሥጋ ገንዘብ ለቃል ሆነ ምድራዊ ሥጋ ሉዓላዊ ሰማያዊ ሆነ

​የሥጋ ዕርገት በዓርባ ቀን፦ ጌታችን ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ በአርባኛው ቀን ሥጋን ይዞ ወደ ቀደመ ክብሩ ወጣ። ይህ የአርባ ቀን ዕርገት የቃል ዕርገት ይባላል። ምክንያቱም የወረደው መለኮት ከቶም ከሰማይ ከዙፋኑ ባይናወጥም የሥጋን ውሱኑነት ገንዘቡ ስላደረገ በማኅፀነ ወረደ ተባለ በአርባ ቀን ዐረገ ተባለ ፤ ስለዚህ ከዐፈር የተገኘው፣ መከራ የተቀበለው፣ የሞተውና የተነሣው የሰውነታችን (የሥጋችን) ባሕርይ ከሁሉ በላይ ከፍ ከፍ አለ

​ከማኅፀን እስከ ቀራንዮ፤ ከትንሣኤ እስከ በዝግ ቤት እስከ መግባት
​ይህ ከሰማይ የወረደው የባሕርይ አምላክ፣ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በነሳው ሥጋ በጥቂት በጥቂቱ አደገ። በሥጋዌው ምሥጢር ፍጹም ሰው ሆነ። በሠላሳ ዘመኑ በዮርዳኖስ ወንዝ በእደ ዮሐንስ ተጠመቀ፤ ይህ የተደረገው ለኃጢአት ሳይሆን የእኛን የዕዳ ደብዳቤ ለመቅደድና የልጅነትን ምሥጢር ለመመሥረት ነበር።

​ከጥምቀት በኋላ ወደ ገዳመ ቆሮንቶስ በመሄድ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾመ፣ ጸለየ፤ ጠላታችን ዲያብሎስን ድል ነሳልን። ከዚያም ለሦስት ዓመት ከሦስት ወር በዚህች ምድር ላይ እየተዘዋወረ የሕይወትን ወንጌል አስተማረ፣ ሙታንን አስነሳ፣ ዕውራንን አበራ፣ ለምጻሞችን አነጻ።
​ትምህርቱ ከምር ሲረዳለት፣ ምሥጢሩ በደቀ መዛሙርቱ ልብ ሲታተም፣ ለድኅነተ ዓለም (ዓለምን ለማዳን) ራሱን መሥዋዕት አድርጎ አቀረበ።

በቀራንዮ አደባባይ በእንጨት መስቀል ላይ ተሰቅሎ፣ በሃይለ መለኮቱ ሕያው ሆኖ በሥጋ ሞተ። በፈሰሰው ቅዱስ ደሙ ዓለምን ከዲያብሎስ ባርነት ዋጃት። ሙስና መቃብርን አጥፍቶ (መቃብርን አሸንፎ) በሦስተኛው ቀን በታላቅ ኃይልና ሥልጣን ተነሣ።

​ትንሣኤው በግልጥ የታየ፣ መቃብሩ ባዶ መሆኑ የተረጋገጠ ነበር። ለደቀ መዛሙርቱ በተለያዩ ጊዜያት እየተገለጠ ትንሣኤውን በተጨባጭ እንዲረዱት አደረጋቸው፤ ጎኑን አሳያቸው፣ ከእነርሱም ጋር በላ፣ ጠጣ። ይህ የሆነው ትንሣኤው መንፈሳዊ ቅዠት ሳይሆን እውነተኛ፣ ሥጋና አጥንት ያለው መሆኑን ደቀ መዛሙርቱ አምነው እንዲረዱትና ለዓለም እንዲመሰክሩ ነው።

​ክፍል ሁለት፦ አርባ ቀን የት ቆየ? ለምንስ በዕለተ ትንሣኤው ወዲያው አላረገም?
​ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ፣ ወዲያውኑ በዚያኑ ዕለት ወደ ሰማይ አላረገም። በምድር ላይ አርባ ቀን ሙሉ ቆየ። ሐዋርያው ቅዱስ ሉቃስ በግብረ ሐዋርያት መጽሐፉ ላይ፦ «እነርሱም ደግሞ አርባ ቀን እየታያቸው ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት ነገር እየነገራቸው፥ በብዙ ማስረጃ ከሕማማቱ በኋላ ሕያው ሆኖ ለነሱ ራሱን አሳያቸው» (ሐዋ ፩፥፫) በማለት ይህንን እውነት አስፍሮታል።

​ለመሆኑ እነዚህን አርባ ቀናት የት ቆየ? ለምንስ ዕለቱን አላረገም? የቤተክርስቲያን ሊቃውንት ይህንን ምሥጢር በአራት አበይት ምክንያቶች ይተነትኑታል።

​፩ኛ. የትንሣኤውን እውነተኝነት ፍጹም ለማረጋገጥ
​ጌታችን ወዲያውኑ በትንሣኤው ዕለት ዐርጎ ቢሆን ኖሮ፣ አይሁድና ክፉዎች «ትንሣኤው እውነት አይደለም፤ አልተነሣም፣ ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ሰረቁት እንጂ» የሚሉትን አጉል ወሬ ይበልጥ ባናፈሱት ነበር። ደቀ መዛሙርቱም ቢሆኑ በድንጋጤና በፍርሃት ውስጥ ስለነበሩ፣ ትንሣኤውን እንደ መንፈስ ወይም እንደ ቅዠት ሊቆጥሩት ይችሉ ነበር።

​ስለዚህ አርባ ቀን ሙሉ በተለያየ ስፍራና ጊዜ እየተገለጠ፦
​ከእነርሱ ጋር በማዕድ ተቀመጠ፣ ዓሳና ማር በላ (ሥጋዊ ፍላጎት ኖሮት ሳይሆን ሥጋዊ ትንሣኤውን ለማረጋገጥ)።
​ቅዱስ ቶማስን «ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን» (ዮሐ ፳፥፳፯) በማለት በጥበብ አረጋገጠለት።
ይህ ሁሉ የሆነው ትንሣኤው ፍጹም የተረጋገጠና ሊታበል የማይችል ዐለት መሆኑን ለመመሥረት ነው።

​፪ኛ. አርባ ቀን የት ቆየ? (የሥርዓተ ቤተክርስቲያን ጉባኤ)
​በእነዚህ አርባ ቀናት ጌታችን በሥጋዊ ሕይወት እዚህም እዚያም እንደሚንከራተት ሰው አልነበረም። ታዲያ የት ነበረ? ሊቃውንቱ «ኢየሩሳሌም በዘጋጉት ቤት (በማርቆስ እናት ቤት)፣ በገሊላ ባህር አጠገብ፣ በደብረ ዘይት ተራራ» እያሉ ደቀ መዛሙርቱ ባሉበት ስፍራ ሁሉ ይገኝ እንደነበር ይናገራሉ። ነገር ግን ዋነኛው ምሥጢር በእነዚህ ቀናት የሰማይና የምድር ጌታ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር የምሥጢራትና የሥርዓት ጉባኤ ማድረጉ ነው።

​ቤተክርስቲያን የምትመራበትን ሥርዓተ ቀኖና፣ ምሥጢረ ጥምቀትን፣ ምስጢረ ቁርባንን፣ የክህነትን ሥልጣን (ዮሐ ፳፥፳፪) የሰጣቸውና ያስተማራቸው በእነዚህ አርባ ቀናት ውስጥ ነው። ለዚህ ነው በትርጓሜ መጻሕፍት «ኪዳን» እና «አስተስርዮ» የሚባሉት ሰማያዊ መጻሕፍት በዚህ ጊዜ ለሐዋርያት የተሰጡ የሥርዓት መጻሕፍት ተደርገው የሚቆጠሩት።

​፫ኛ. አዳም በገነት የቆየበትን ዕድሜ ለመካስ (የቀናት ምሥጢር)
​በትርጓሜ ሊቃውንት ዘንድ ሌላው ጥልቅ ምሥጢር የቀናት ቁጥር ነው። አዳም በተፈጠረ በመጀመሪያው ሳምንት ወደ ገነት አልገባም፤ አርባ ቀን ከሆነው በኋላ ነው ወደ ገነት የገባው (መጽሐፈ ኩፋሌን ይመለከቷል)። በገነትም ሳለ ሕጉን አፍርሶ ወጣ።

​ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ ደግሞ በበደለኛው አዳም ምትክ ሆኖ፣ አዳም ሳይቀደስበትና ሳይኖርበት የቀረውን ያንን የአርባ ቀን ምስጢር እርሱ በትንሣኤው ሕያው ሆኖ በምድር ላይ በመቆየት ቀደሰው። አዳም ከአርባ ቀን በኋላ ወደ ገነት እንደገባ፣ ክርስቶስም ከአርባ ቀን ቆይታ በኋላ ወደ ሰማያዊቷ ገነት ወደ አባቱ ቀኝ ገባ።

​፬ኛ. የመንፈስ ቅዱስን ተስፋ ለመስጠትና ልባቸውን ለማጽናት
​ደቀ መዛሙርቱ ጌታቸው ጥሏቸው ፈጥኖ ቢሄድ ኖሮ እንደ እረኛ እንደሌላቸው በጎች ይበተኑ ነበር። ስለዚህ አርባ ቀን ሙሉ እያስተማረ፣ እየመገበ፣ ፍርሃታቸውን እያራቀ ካዘጋጃቸው በኋላ «ከኢየሩሳሌም አትውጡ፣ ከአብ የተሰጠውን የተስፋ ቃል ጠብቁ» (ሐዋ ፩፥፬) በማለት የመንፈስ ቅዱስን መውረድ (ጰራቅሊጦስን) ተስፋ ሰጣቸው። ይህ ቆይታ ደቀ መዛሙርቱን ከፍርሃት ወደ ድፍረት፣ ከጥርጣሬ ወደ ፍጹም እምነት ያሻገረበት ድልድይ ነበር።

​ክፍል ሦስት፦ ስለ ዕርገት የተነገሩ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች፣
​የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት በድንገት የተደረገ ሳይሆን፣ አስቀድሞ በብሉይ ኪዳን በነቢያት አንደበት የተነገረ፣ በሐዲስ ኪዳንም በሐዋርያት የተመሰከረ ታላቅ ምሥጢር ነው። የትርጓሜ መምህራን እነዚህን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች በታሪክ፣ በአማናዊነትና በምሥጢር እንዲህ ይተረጉሟቸዋል፦

​፩ኛ. የቅዱስ ዳዊት ትንቢት (መዝሙር ፵፮፥፭)
​«ዐርገ እግዚአብሔር በይባቤ ወእግዚእነ በቃለ ቀርን»
(እግዚአብሔር በእልልታ፥ ጌታችን በመለከት ድምፅ ዐረገ።)
​ትርጓሜውና ምሥጢሩ፦ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት ይህንን የተናገረው ከክርስቶስ ልደት አንድ ሺህ ዘመን አስቀድሞ ነው። «በእልልታና በመለከት» ማረጉ ምን ማለት ነው? በሊቃውንት ትርጓሜ፣ እልልታና መለከት የድል አድራጊነት ምልክቶች ናቸው። ንጉሥ በጦርነት ጠላቱን ድል አድርጎ ሲመለስ በሕዝቡ ዘንድ እልልታና መለከት ይነፋል።

ክርስቶስም ሞትን ድል አድርጎ፣ ዲያብሎስን ማርኮ፣ ሲዖልን በርብሮ ወደ ሰማይ ሲያርግ ቅዱሳን መላእክት በሰማያዊ እልልታና በምስጋና መለከት ተቀብለውታል።
​አንድምታው፦ «እግዚአብሔር» ያለው መለኮቱን ሲሆን፣ «ጌታችን» ያለው ደግሞ እኛን ለማዳን የተዋሐደውን ሥጋውን ነው። ስለዚህ መለኮትና ሥጋ በተዋሕዶ ከብረው በታላቅ ምስጋና ዐረጉ ማለት ነው።

​፪ኛ. የቅዱስ ዳዊት ትንቢት (መዝሙር ፷፯፥፲፰)
​«ዐረገ ውስተ አርያም ጼዋውከ ጼዋዌ ወወሀብከ ጸጋከ ለዕጓለ እመሕያው»
(ወደ ላይ ዐረግህ፥ ምርኮን ማረክህ፥ ስጦታዎችንም ለሰዎች ሰጠህ።)

​ትርጓሜውና ምሥጢሩ፦ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በኤፌሶን ፬፥፰ ላይ ይህንን ጥቅስ በማምጣት የክርስቶስ ዕርገት መሆኑን አረጋግጧል። «ምርኮን ማረክህ» ማለት አዳምና ልጆቹ በአጋንንት ተማርከው በሲዖል ነበሩ። ክርስቶስ ግን በሞቱና በትንሣኤው እነዚያን የዲያብሎስ ምርኮኞች የነበሩትን ነፍሳት ነጻ አውጥቶ፣ ወደ ገነትና ወደ ሰማያዊው ክብር ይዟቸው ዐረገ (ምርኮኛውን መልሶ ማረከው)።

​«ለሰዎች ሥጦታን ሰጠህ» የሚለው ደግሞ ከዕርገቱ በኋላ በጥቂት ቀናት (በዓሥረኛው ቀን) ለሐዋርያት ያወረደላቸውን የመንፈስ ቅዱስን ጸጋና ልዩ ልዩ ሀብታትን (ሃብተ ክህነትን፣ሀብተ ፈወስንና ሃብተ ትንቢትን) ያመለክታል።

​፫ኛ. የቅዱስ ዳዊት ትንቢት (መዝሙር ፳፫፥፯)
​«አርኅዉ ኆኃተ መኳንንት፣ ወይትረኃዋ ኆኃት እለ እምፍጥረት፣ ወይባእ ንጉሠ ስብሐት»
(መኳንንት በሮችን ክፈቱ፥ የዘላለም በሮችም ይከፈቱ፥ የክብር ንጉሥ ይግባ።)

​ትርጓሜውና ምሥጢሩ፦ ይህ ጥቅስ የትርጓሜ መምህራን በሰፊው የሚያመሰጥሩት ድንቅ ክፍል ነው። ጌታችን ሥጋን ለብሶ ወደ ሰማይ ሲያርግ፣ በሰማይ ያሉ መላእክት በሁለት ክፍል ቆመው ነበር። የታችኞቹ (ወደ ምድር የቀረቡት) መላእክት ለበላዮቹ «በሮችን ክፈቱ፣ የክብር ንጉሥ ይግባ» አሉ። የበላዮቹ መላእክት ደግሞ «ይህ የክብር ንጉሥ ማን ነው?» አሉ። ምክንያቱም ከዚህ ቀደም የሰው ሥጋ ለብሶ፣ በችንካር ተወግቶ፣ የሞተና የተነሣ አምላክ ወደ ሰማይ ሲያርግ አይተው አያውቁምና።
​የታችኞቹ መላእክትም መልሰው፦ «እርሱ በውጊያ ብርቱና ኃያል የሆነው፣ ሰይጣንንና ሞትን ድል ያደረገው እግዚአብሔር ነው» ብለው መለሱላቸው። በዚህም የሰው ልጅ ተፈጥሮ (ሥጋ) ለመጀመሪያ ጊዜ የሰማይን በሮች ከፍቶ መግባቱ ተገለጠ።

​፬ኛ. በሐዲስ ኪዳን (የሉቃስ ወንጌል ፳፬፥፶-፶፩ እና የሐዋርያት ሥራ ፩፥፱)
​«ይህንን ካለ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው።»

​ትርጓሜውና ምሥጢሩ፦ ወንጌላዊው ሉቃስ የታሪኩን እውነተኝነት ያስረግጣል። «እያዩት» ማለቱ በድብቅ ወይም በሕልም ሳይሆን በግልጽ፣ በአካል፣ ዐይናቸው እያየ መሆኑን ለማሳየት ነው። ደመና መቀበሏ ደግሞ እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ መሆኑን፣ ደመናትን እንደ ሠረገላ የሚጠቀምባት የባሕርይ አምላክ መሆኑን ለማስመስከር ነው።

​ክፍል አራት፦ የሄኖክ መሠወር፣ የኤልያስ ዕርገት እና የጻድቃን ዕርገት ከክርስቶስ ዕርገት ጋር በንጽጽር እንመልከተው
​በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ውስጥ ከምድር ወደ ላይ የወጡ (የሄዱ) ቅዱሳን አሉ። እነርሱም ሄኖክና ኤልያስ ናቸው። ወደፊትም በትንሣኤ ዘጉባኤ ጻድቃን ሁሉ ይነጠቃሉ። ነገር ግን የእነርሱ መሄድና የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት ሰማይና ምድር ያህል የተራራቁ ናቸው።

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት «ዐርገ እግዚአብሔር ከመ ያለቡ ዕርገተ ጻድቃን» (የጻድቃንን ዕርገት ያስረዳ ዘንድ እግዚአብሔር ዐረገ) እያሉ ምሥጢሩን ከማጣቀሻ ጋር እንዲህ ያነጻጽሩታል፦

​፩ኛ. የሄኖክ መሠወር (ኦሪት ዘፍጥረት ፭፥፳፬)
​«ሄኖክም አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር አደረገ፤ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም።»
(በሐዲስ ኪዳንም፦ «ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ፥ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም» ዕብ ፲፩፥፭)ይላል

​ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሄኖክ ሲናገር «ወሰደው» (አሻገረው) ነው የሚለው እንጂ «በራሱ ሥልጣን ዐረገ» አይልም። ሄኖክ ፍጡር ነው፤ መሄዱም በራሱ ኃይል ሳይሆን በእግዚአብሔር ረዳትነትና ፈቃድ ነው።

​ምስጢራዊ ልዩነቱ፦ ሄኖክ የተወሰደው «ሞትን እንዳያይ» ነው (ለጊዜው ከሞት ቢያመልጥም በኋላ ግን በዓለም ፍጻሜ መጥቶ ይሞታል)። ጌታችን ግን ሞትን አይቶ፣ ሞትን በሞቱ ቀጥቅጦ፣ ተነሥቶ ነው ያረገው። ሄኖክ የተሰወረው በእግዚአብሔር ኃይል ሲሆን፣ ክርስቶስ ግን አሳራጊ ሳይሻ በገዛ የባሕርይ ሥልጣኑ ዐረገ።

​፪ኛ. የነቢዩ ኤልያስ ዕርገት (፪ኛ ነገሥት ፪፥፲፩)
​«እነሆም፥ የእሳት ሠረገላና የእሳት ፈረሶች በመካከላቸው ተለዩ፥ ኤልያስም በዐውሎ ንፋስ ወደ ሰማይ ወጣ።»

ነቢዩ ኤልያስ ወደ ሰማይ የወጣው በሁለት ነገሮች ተደግፎ ነው፦ አንደኛ በእሳት ሠረገላ፣ ሁለተኛ ደግሞ በዐውሎ ንፋስ ኃይል። ይህ የሚያሳየው ኤልያስ ተሸካሚ፣ አሳራጊና ደጋፊ የሚሻ ደካማ ፍጡር መሆኑን ነው።

የት ነው የሄደው ቢሉ ወደ ሰማየ ሰማያት (ወደ አባቱ ቀኝ) አልወጣም፤ «ወደ ብሔረ ሕያዋን» (የሕያዋን ምድር) ተወሰደ እንጂ።

​ምሥጢራዊ ልዩነቱ፦ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ወደ ሰማይ ሲያርግ ምንም ዓይነት የእሳት ሠረገላ ወይም የነፋሳት አውታር አልፈለገም። እርሱ «ገብአ ኀበ ዘትካት ሕላዌሁ» (ወደ ቀደመው የባሕርይ መኖሪያው ተመለሰ) እንደተባለ፣ የሚያሳርገው ሳይሻ በራሱ መለኮታዊ ኃይል ዐረገ። ደመና ተቀበለችው የሚለውም የደብረ ታቦር ደመናና የዕርገት ደመና የባሕሪ ክብሩ መገለጫ ነው
ኤልያስ የተወሰደው ወደ ፍጡር ቦታ (ብሔረ ሕያዋን) ሲሆን፣ ክርስቶስ ግን ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ወደሆነው ወደ ባሕርይ አባቱ ቀኝ ወጣ

​፫ኛ. የጻድቃን ዕርገት (፩ኛ ተሰሎንቄ ፬፥፲፯)
​«ከዚያም በኋላ እኛ ሕያዋን ሆነን የምንቀረው፥ ጌታን በአየር ላይ ለመቀበል ከእነርሱ ጋር በደመና እንነጠቃለን፤ እንዲሁም ሁልጊዜ ከጌታ ጋር እንሆናለን።»

​ ጻድቃን በዕለተ ምጽአት ወደ ሰማይ የሚነጠቁት (የሚያርጉት) በራሳቸው ኃይል ሳይሆን በጌታ ጥሪና በመላእክት ሰብሳቢነት ነው። የጻድቃን ዕርገት የተረጋገጠውና ትርጉም ያገኘው በክርስቶስ ዕርገት ነው።

​«ዐርገ እግዚአብሔር ከመ ያለቡ ዕርገተ ጻድቃን» የሚለው የምሥጢር ትርጓሜው ይህ ነው፦ ክርስቶስ የሰውን ሥጋ ለብሶ ቀዳሚ (በኩር) ሆኖ ወደ ሰማይ ባያርግ ኖሮ፣ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ወደ ሰማይ መውጣት እንደሚችል አይታወቅም ነበር። እርሱ ግን የሰውን ሥጋ ለብሶ በመውጣቱ፣ እኛም የሰው ልጆች (ጻድቃን) በትንሣኤ ዘጉባኤ ሰማይን መውረስ እንደምንችል በተግባር አሳየን፤ መንገዱን ከፈተልን። ስለዚህ የጻድቃን ዕርገት የክርስቶስ ዕርገት ፍሬና ውጤት ነው።

መለኪያ ሄኖክ / ኤልያስ ጻድቃን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ
የማረግ ኃይል በእግዚአብሔር ሰጪነት (በሠረገላ) በጌታ ኃይል (በነጠቃ) ነው

እርሱ ግን በገዛ የባሕርይ ሥልጣኑ (በራሱ)
እነርሱ የሄዱበት ቦታ ብሔረ ሕያዋን (የፍጡር ቦታ) ነው እርሱ ግን ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ወደ ቀደመው ክብሩ (በአባቱ ቀኝ) ተቀመጠ
የእነርሱ የመሄዳቸው ምሠሰጢር ለአምላክ ክብር ምስክር ለመሆን የደመወዛቸውን ዋጋ ለመቀበልነው
እርሱ ግን የሰውን ባሕርይ አክብሮ ወደ ሸደመ ክብሩ ለማስገባት ነው

​ክፍል አምስት፦ የደብረ ዘይት ምሥጢር፣ «እንዘ ይባርኮሙ ተረሐቆሙ »፣
​ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአርባኛው ቀን ደቀ መዛሙርቱን ይዟቸው ወደ ኢየሩሳሌም አቅራቢያ ወደምትገኘው ወደ ደብረ ዘይት (የወይራ ተራራ) ወጣ። ይህ ስፍራ እንዲሁ በአጋጣሚ የተመረጠ ሳይሆን፣ የጌታችን የሕማማቱ፣ የጸሎቱና የምሥጢራቱ ሁሉ መተላለፊያ ማዕከል ነበረ።

​፩ኛ. «እንዘ ይባርኮሙ ተረሐቆሙ» (እየባረካቸው ተለያቸው)
​ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ይህንን ታላቅ ምሥጢር ሲዘግብ፦ «እጆቹንም አንሥቶ ባረካቸው። ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ ወደ ሰማይም ዐረገ» (ሉቃ ፳፬፥፶-፶፩) ይላል።

ጌታችን እጆቹን አንሥቶ የባረካቸው ባርኮት «የስንብት» ሳይሆን «የሥልጣንና የጸጋ» ማኅተም ነው። እጆቹን ሲዘረጋላቸው፣ አዳም በዕፀ በለስ ምክንያት የተረገመውን ያንን የጥንት እርግማን ፈጽሞ ማጥፋቱንና በምትኩ ሰማያዊ በረከትን ማቅረቡን ለማሳየት ነው።

​«እየባረካቸው ወደ ላይ ከፍ ከፍ አለ» ሲል፣ ባርኮቱ እንዳልተቋረጠ፣ ያ ጸጋና ሰላም እስከ ዓለም ፍጻሜ ከቤተክርስቲያን ጋር አብሮ እንደሚኖር ለማሳየት ነው። ደቀ መዛሙርቱ ወደ ላይ አንጋጠው እያዩት ማረጉ ደግሞ፣ መሄዱ በምሥጢር ወይም ተደብቆ ሳይሆን ዐይናቸው እያየ ፍጹም እውነተኛ መሆኑን በልባቸው ለመቅረጽ ነው።

​፪ኛ. «ደመና ተቀበለችው» (የባሕርይ ክብሩ መገለጫ)
​«ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው» (ሐዋ ፩፥፱)። ሊቃውንቱ እዚህ ላይ «ደመና ለምን ተቀበለችው?» የሚለውን በጥልቀት ይተረጉማሉ።

​አማናዊ ምሥጢሩ፦ ደመና የተባለችው ጌታችንን ለመሸከም ወይም ደግፋ ወደ ላይ ለማውጣት የመጣች ፍጥረት አይደለችም። በብሉይ ኪዳን ታሪክ እግዚአብሔር ክብሩን በሚገልጥበት ጊዜ ሁሉ በደመና ውስጥ ሆኖ ይገለጥ ነበር (ለምሳሌ በሲና ተራራ፣ በደብረ ታቦር)። ስለዚህ ደመና መቀበሏ የባሕርይ ክብሩ (የመለኮቱ ኃይል) መግለጫ ነው። እርሱ ደመናትን መረገጫ የሚያደርግ፣ ነፋሳትን በቃሉ የሚያዝዝ የሰማይና የምድር ፈጣሪ መሆኑን ለማሳየት ደመና ለክብሩ አገለገለች።

​፫ኛ. በቅዱሳን መላእክት ዘንድ የታየው ታላቅ ደስታ
​ጌታችን የሰውን ሥጋ ለብሶ፣ ያንን በቀራንዮ የቆሰለውንና በችንካር የተቸነከረውን አካል ይዞ ወደ ሰማየ ሰማያት ሲያርግ በሰማያውያን መላእክት ዘንድ የሆነው ደስታና ድንጋጤ በሰው አንደበት ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም።
​ቅዱሳን መላእክት የሰውን ሥጋ ከኪሩቤልና ከሱራፌል በላይ፣ ከአብ ቀኝ ሲቀመጥ አዩት። ከዚህ ቀደም ከመንበሩ ወርዶ የነበረው ጌታ፣ አሁን ግን የሰውን ባሕርይ (ሥጋን) ይዞ ወደ መንበሩ ሲመለስ ታላቅ ሰማያዊ አምልኮና ምስጋና አቀረቡ።

​በደብረ ዘይት ተራራ ደቀ መዛሙርቱ ወደ ሰማይ አንጋጠው ሲያዩ፣ ነጫጭ ልብስ የለበሱ ሁለት መላእክት ተገልጠው፦ «የገሊላ ሰዎች ሆይ፥ ወደ ሰማይ እየተመለከታችሁ ስለ ምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁት፥ እንዲሁ ይመጣል» (ሐዋ ፩፥፲፩) አሏቸው። ይህ የመላእክት ምስክርነት የዕርገቱን ፍጻሜ ብቻ ሳይሆን፣ ዳግም በግርማ መለኮት ለፍርድ የሚመጣበትን የዕለተ ምጽአትን ምሥጢር ያበሰረ ነበር።

ዕርገት የድኅነታችን ማጠናቀቂያ ማኅተም ነው።
​ጌታችን ሰው ሆኖ ባይወለድ ኖሮ—ሰው አይቀደስም ነበር።
​ባይሰቀል ኖሮ—የዕዳ ደብዳቤአችን አይቀደድም ነበር።
​ባይነሣ ኖሮ—ሙስና መቃብር አይጠፋም ነበር።
​ባያርግ ኖሮ ደግሞ—የሰው ልጅ ተፈጥሮ ወደ ሰማይ ገብቶ ከአምላክ ቀኝ አይቀመጥም ነበር።

​ስለዚህ ዕርገት ማለት የሰው ልጅ ተፈጥሮ ከምድር ዐፈር ተነሥቶ፣ በክርስቶስ ኢየሱስ በኩል እስከ እግዚአብሔር አብ ቀኝ ድረስ የከበረበት፣ የሰማይና የምድር ሰላም የታወጀበት፣ ሰይጣን ፈጽሞ ያፈረረበት ታላቅ የምሥጢር ቀን ነው።

​«ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት፣ ወነበረ በየማነ አቡሁ»
ወስብሐት ለእግዚአብሔር።

​✍️​ ​“ለግሪክ ሰዎችና ላልተማሩም፥ ለጥበበኞችና ለማያስተውሉም ዕዳ አለብኝ፤”
በወንጌል አላፍርምና፤
አስቀድሞ ለአይሁዳዊ ደግሞም
ለግሪክ ሰው፥ ለሚያምኑ ሁሉ
የእግዚአብሔር ኃይል ለማዳን
ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎ እንደ ተጻፈ የእግዚአብሔር ጽድቅ ከእምነት ወደ እምነት በእርሱ ይገለጣልና። ሮሜ 1÷14

እግዚአብሔር ሆይ የሚሳንህ ነገር የለምና የራቀውን አቅርበህ የረቀቀውን አጉልተህ እየሰማነው ካለነው መርዶና ሰቀቀን ዕረፍተ ሥጋንና ዕረፍተ ነፍስን አትንሣን

ጸልዩ በእንተ ሰላም
ስለ ሰላም እንጸልይ
ስለ ሀገራችን እንጸልይ
ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንጸልይ
በጭንቅ በመከራ ስላሉት እንጸልይ
በረሀብ በስደት ስላሉት እንጸልይ
በጽኑ ሕመም ተይዘው ስለሚሰቃዩት እንጸልይ
ስለ ሃይማኖት መሪዎች አባቶቻችን እንጸልይ
ስለ ሀገር መሪዎች እንጸልይ
የሰላም የምህረት የቸርነት ባለቤት እግዚአብሔር ሰላሙን ምህረቱን ቸርነቱን አይንሳን

አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ፣
ዘዝዋይ ገዳም፣
ግንቦት 12/9/2018 ዓ.ም ✍️

+++ የትንሣኤ ፫ኛ እሑድ +++========መዝሙር፦ «ወበእሑድ ሰንበት ጌሠት ማርያም መግደላዊት በጽባሕ ኃበ መቃብር። እንዘ ዓዲ ጽልመት። ወረከበት እብነ ዕቱተ እመ አፈ መቃብር። ወበጽሐት...
04/26/2026

+++ የትንሣኤ ፫ኛ እሑድ +++
========
መዝሙር፦
«ወበእሑድ ሰንበት ጌሠት ማርያም መግደላዊት በጽባሕ ኃበ መቃብር። እንዘ ዓዲ ጽልመት። ወረከበት እብነ ዕቱተ እመ አፈ መቃብር። ወበጽሐት ኀበ ስምዖን ጴጥሮስ ወበኃበ ካልዕ ረድዕ ዘያፈቅሮ ኢየሱስ። ወትቤሎሙ ነሥእዎ ለእግዚእየ። ወኢየአምር ኃበ ወሰድዎ እንዘ ይረውጹ ክልዔሆሙ ኅቡረ። በደሮ ዝኩ ካልዕ ረድዕ ዘያፈቅሮ ኢየሱስ።»

ትርጉም:-
በእሑድ ሰንበት መግደላዊት ማርያም በማለዳ ገና ጨለማ ሳለ ወደ መቃብር ገሠገሠች ደንጊያው ከመቃብሩ አፍ ተወግዶ አገኘች ወደ ስምዖን ጴጥሮስና ኢየሱስ ወደሚወደው ወደ ሁለተኛው ደቀመዝሙር ደረሰች እንዲህም አለቻቸው ጌታዬን ከመቃብር ወስደዉታል ወዴት እንደወሰዱትም አላውቅም ሁለቱ በአንድ ላይ ሲሮጡ ኢየሱስ የሚወደው ሌላው ደቀመዝሙር ጴጥሮስን ቀደመው።
========

የዕለቱ_ግጻዌ (መልእክታት፥ ምስባክ፥ ወንጌል...)
+++++++++++

✞ መልእክታት፦
➊.
፪ኛ ቆሮንቶስ ፭ : ፲፩ - ፍጻሜ (5:11-ፍጻሜ)
========

➋.
፪ኛ ጴጥሮስ መል ፫ : ፲፬ - ፍጻሜ (3:14-ፍጻሜ)
=======


ግብረ ሐዋርያት ፳፩:፴፩-ፍጻሜ ምዕ (21:31-ፍጻሜ)
============

✞ ምስባክ ዘቅዳሴ

ይእዜ እትነሣእ ይቤ እግዚአብሔር።
እሬሲ መድኃኒተ ወአግህድ ቦቱ፣
ቃለ እግዚአብሔር ቃል ንጹሕ።
======

ትርጉም:-
እግዚአብሔር አሁን እነሣለሁ ይላል ፤
መድኃኒትን አደርጋለሁ፥ በላዩም እገልጣለሁ።
የእግዚአብሔር ቃላት የነጹ ቃላት ናቸው።
{ መዝ ፲፩ : ፭ /11:5 }
✞ ወንጌል ዘቅዳሴ
የሉቃስ ወንጌል ፳፬ : ፲፫ - ፴፫ (24:13-33)
======

✞ ቅዳሴ ~
** ዘዲዮስቆሮስ (እምቅድመ ዓለም) {በዕዝል ዜማ}
___

እንኳን አደረሳችሁ አደረሰን=====እሑድ፡ ዳግም ትንሣኤ (በመ/ር ጌታቸው በቀለ)የሰሙነ ትንሣኤ መጨረሻው ስምንተኛው ቀን ወይም ኹለተኛው እሑድ “ዳግም ትንሣኤ” ይባላል፡፡  ሰሙነ ሕማማትና ...
04/18/2026

እንኳን አደረሳችሁ አደረሰን
=====
እሑድ፡ ዳግም ትንሣኤ
(በመ/ር ጌታቸው በቀለ)
የሰሙነ ትንሣኤ መጨረሻው ስምንተኛው ቀን ወይም ኹለተኛው እሑድ “ዳግም ትንሣኤ” ይባላል፡፡
ሰሙነ ሕማማትና ሰሙነ ትንሣኤን እንድናከብር ቀደም ሲል በዲዲስቅልያ ኋላም በፍትሐ ነገሥት ታዝዟል፡፡

“እስመ ሰሙነ ዐብይ ሰሙነ ሕማማት እንተ ትተልዋሄ ሰሙነ ትንሣኤ ወዘይትፈቀድ ከመ ናእምር እስመ ዘሐመ ናሁ ትንሣአ” ሲል ይገኛል፡፡ /ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፲፱/፡፡ የሰሙነ ትንሣኤ መጨረሻው ስምንተኛው ቀን ዳግም ትንሣኤ ነው፡፡ ይኸው ዕለት ዳግም ትንሣኤ፣ “ፈጸምነ”፣ “አግብኦተ ግብር” በመባል ይጠራል፡፡
ዳግም ትንሣኤ ለምን ተባለ?
=== ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተነሣው አንድ ጊዜ ነው ዳግም ትንሣኤ ለምን ተባለ? መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሰው ልጆች ኃጢአት በመስቀል ላይ ተሰቅሎ የሞተው አንድ ጊዜ ብቻ እንደመኾኑ መጠን ሞትን ድል አድርጎ የተነሣውም እንዲሁ አንድ ጊዜ ብቻ ነው፡፡ ስለ ክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ በየዘመኑ የተነሡ ነቢያት ሁሉ በትንቢታቸው የተናገሩት፤ ክርስቶስ አንድ ጊዜ ብቻ ሞቶ እንደሚነሣ እንጂ፤ ክርስቶስ ኹለተኛ ሞትና ትንሣኤ እንዳለው የሚያመለክት ቃል ፈጽሞ አልተናገሩም፡፡
ዳግም ትንሣኤ የተባለበት ምክንያት በአከባበር በሥርዐት የመጀመሪያውን ትንሣኤ ስለሚመስል ነው፡፡ የትንሣኤ ዕለት የሚባለው ቃለ እግዚአብሔር ሳይለወጥ በሙሉ በዚህ ቀን ይደገማል፡፡ በ/ዮሐ. ፳÷፲፱—፳፪/፡፡ እንደተጻፈው በመጀመሪያው የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ዐሥሩ ደቀ መዛሙርት አይሁድን ፈርተው፣ ደጅ ዘግተው ተሰብስበው በነበሩበት ቦታ ጌታችን ለቅዱሳን ሐዋርያት በዝግ በር ገብቶ በመካከላቸው ተገኝቶ “ሰላም ለሁላችሁ ይሁን” ብሎ ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው፤ ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡ ቶማስ ከሔደበት ሲመጣ ጌታችን እንደተነሣ እና እንደተገለጸላቸው በደስታ ሲነግሩት “በኋላ እናንተ ዐየን ብላችሁ ልትመሰክሩ፣ ልታስተምሩ፣ እኔ ግን “ሰምቼአለሁ” ብዬ ልመሰክር፣ ላስተምር? አይሆንም እኔም ካላየሁ አላምንም” በማለቱ የሰውን ሁሉ፤ ይልቁንም የመረጣቸው ወዳጆቹን የልብ ሐሳብ ምክንያቱን ለይቶ የሚያውቀው፣ ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኀኔዓለም ክርስቶስ ልክ እንደ መጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት ሐዋርያት በአንድነት በተዘጋ ቤት እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ “ሰላም ለሁላችን ይሁን” በማለት በመካከላቸው ቆመ፤ ቶማስንም “ያመንክ እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን፡፡ እነሆ ጣትህን ወደዚህ አግባ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን፣ የተወጋ ጐኔንም ናና እይ” ብሎ አሳየው፡፡ እርሱም ምልክቱን በማየቱ፣ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደፍላጎቱ በመረዳቱ “ጌታዬ አምላኬ ብሎ መስክሮ” አመነ፡፡ መዳሰሱን ሲያይ “ጌታዬ” ማቃጠሉን ሲያይ “አምላኬ” አለ፡፡ የዳሰሰው ሥጋ መለኮት የተዋሐደው ነውና፡፡ ጌታም “ቶማስ ሆይ ብታየኝ አመንክን ሳያዩኝ የሚያምኑ ብፁዓን ናቸው” አለው /ዮሐ.፳፮.÷፴/፡፡ እንግዲህ ይህ የትንሣኤው ምስጢር ጌታችን ቶማስ ባለበት በዝግ ቤት ዳግመኛ ለኹለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት ስለሆነ፤ የትንሣኤው ሳምንት “ዳግም ትንሣኤ” ተብሎ ሰንበቱ ይጠራበታል፤ ይከበርበታል /ዮሐ. ፳÷፳፬—፴/፡፡
ምስጢሩ ግን ከእሑድ ከቀዳማይ ትንሣኤ ጀምረው ቢቆጥሩት ስምንት ቀን ይኾናል፡፡ አንድ ቀን እንደ አንድ ሺሕ ቆጥሮ ስምንት ሺሕ ይኾናል፡፡ ዳግማይነቱ ለትንነሣኤ ነውና በስምንተኛው ሺሕ ዘመን ዳግም በትንሣኤ ዘጉባኤ እንነሣለን ለማለት ዳግም ትንሣኤ ተባለ፡፡ አንድም ዳግም ትንሣኤ የምንለው ኋላ በትንሣኤ የምንነሣውን ነው፡፡ በመጀመሪያው ትንሣኤ ጽንሰቱን፣ ልደቱን፣ ጥምቀቱን፣ ሕማሙን፣ ስቅለቱን፣ ጾሙን፣ ሞቱን ትንሣኤውን ዕርገቱን አምነን በትንሣኤ ልቦና እንነሣለን፡፡ ኋላ የምንነሣው ትንሣኤ ለአሁኑ ትንሣኤ ልቦና “ዳግም ትንሣኤ” ይባላል፡፡ ጌታ ለእኛ የትንሣኤያችን በኵር ኾኖ ነው የተነሣው፡፡ እሱን ሞት ሊይዘው ቀርቶ ሊቀርበው አይችልም፡፡ ነገር ግን የትንሣኤያችን በኵር ለመኾን ለአርአያነት፣ ለቤዛነት እሱ ተበድሎ እኛን ለማዳን እሱ ካሰን፡፡ የተበደለውም የካሰውም እሱ ነው፡፡ በዚህ ዕለትም ትንሣኤ ልቦናን እና በኋላ በዳግም ምጽአት የምንነሣውን ትንሣኤ ዘጉባኤን እናስባለን፡፡
ዳግም ትንሣኤ ሌላ ሁለት መጠሪያ ስሞች አሉት፡፡ እነዚህም ፈጸምነ፣ አግብኦተ ግብር ይባላሉ፡፡
ፈጸምነ
===
“ፈጸምነ” ማለት ከእሑድ እስከ እሑድ ስለ አንድ ቀን ይቆጠራል፡፡ ፈጸምነ የተባለበትም የበዓሉን ቀን (የሰሙነ ትንሣኤን) በዓል አክብረን ጨረስን፣ ፈጸምን ማለት ነው፡፡ በሌላ በኩልም የተነገረው ትንቢት፣ የተመሰለው ምሳሌ አለቀ፣ ተፈጸመ ለማለት ነው፡፡ እንዲሁም ጌታችን የሰውነት ሥራውን ሲያከናውን ከቆየ በኋላ በፍጻሜ አካባቢ ለባሕርይ አባቱ ባቀረበው ጸሎት “እኔ ላደርገው የሰጠኸኝን ፈጽሜ በምድር አከበርኩህ” በማለት የጸለየውን አምላካዊ ጸሎት በተወሰነ ቀን ፈጸምነ ብለውታል /ዮሐ.፲፯÷፬/፡፡ በዚህ ቀን ጌታችን ከሙታን ተለይቶ ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ በዝግ ቤት ሳሉ በር ሳይከፈት ገብቶ በመካከላቸው በመገኘት ሰላም ለሁላችሁ ይሁን የአለበት ቀን ነው፡፡ ይህም ክርስቶስ የመጣበትን ዓላማ መፈጸሙን የሚያረጋግጥ ስም አጠራር ነው፡፡ በአጠቃላይ ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም የመጣበትን ዓላማ በመስቀል ላይ በሚያፈሰው ደሙ ሰዎችን ከኃጢአት ነጻ ለማውጣት በሞቱም ዘለዓለማዊ ሕይወትን ሰጥቶ፣ በትንሣኤው ለትንሣኤያችን በኵር ለመኾን በመኾኑም ይህንኑ ሥራውን ያጠናቀቀ መኾኑን ለማመልከት ነው፡፡
አግብኦተ ግብር
==.=. አግብኦተ ግብር (የግብር ማግባት) የኤማሁስን ማዕድ ነው፤ ግብር ማዕድ ማለት ነው፡፡ በማዕድ ተሰብስበው እንዳሉ ተገለጸላቸው /ሊቃ.፳፬÷፲፫/፡፡ “አግብኦተ ግብር” የተባለበትም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “አባ ወአቡየ ግብረ ዘወሀብከኒ ፈጸምኩ” - እኔ ልሠራው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጸምኩ” ያለውን ከቅዳሴ በኋላ ሊቃውንት በዚህ ቀን ስለሚዘምሩት የተሰጠው ስያሜ ነው፡፡ ምስጢሩ ግን ሥጋ የተገዢነት ሥራ ፈጸመ፡፡ ከእንግዲህ በአብ እሪና ተቀምጦ ይፈርዳል ለማለት ነው፡፡ /ዮሐ. ፲፯÷፬/፡፡
እንደ ማጠቃለያ
===== በአጠቃላይ በቅድስት ቤተክርስቲያን በሰሙነ ፋሲካ የሚፈጸመው መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት ሁሉ ልክ እንደ መጀመሪያው የትንሣኤ ሥርዐት ኾኖ ይከናወናል፡፡ በማኅበራዊ ኑሮም የፋሲካ ሳምንት ብዙ መንፈሳዊና ባሕላዊ ቁምነገሮች የሚፈጸሙበት ሳምንት ነው፡፡ ወገን ከወገን የሚገናኝበት፣ ጎረቤት ከጎረቤት ተጠራርቶ የሚገባበዝበት፣ ካህናትና ምእመናን በአንድነት ተገናኝተው መታሰቢያውን የሚያከብሩበት፣ በገብረ ሰላሙ ላይ ማኅሌተ ገንቦ የሚያሰሙበት፣ የተጣላ የሚታረቅበት፣ ጋብቻ ከጋብቻ ተጠራርቶ የሚገናኝበት፣ የሚገባበዙበት በጠቅላላው ሰላም የሰፈነበት መልካም የዕረፍት ሳምንት ነው፡፡
ለብርሃነ ትንሣኤው ያደረሰን አምላካችን ለብርሃነ ዕርገቱም በሰላም ያድርሰን፡፡ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዋቤ መጻሕፍት
✍️ መጽሐፍ ቅዱስ
✍️ ፍትሐ ነገሥት
✍️ ሃይማኖት አበው
✍️ መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ
✍️ ከስቅለት እስከ ትንሣኤ
በመ/ር ጌታቸው በቀለ

ሆሣዕና በአርያም! Palm Sunday 🌿🌿 መድኃኒተ ፈነወ እግዚአብሔር ለሕዝቡ።God sent redemption unto His peopleእግዚአብሔር ለሕዝቡ መድኃኒትን ላከ። መዝ. ፻፲፥፱ (1...
03/31/2026

ሆሣዕና በአርያም! Palm Sunday
🌿🌿
መድኃኒተ ፈነወ እግዚአብሔር ለሕዝቡ።
God sent redemption unto His people
እግዚአብሔር ለሕዝቡ መድኃኒትን ላከ።
መዝ. ፻፲፥፱ (110፥9)

🌴 እንኳን አደረሳችሁ 🌴

እሑድ፣ በኒቆዲሞስ ሰንበት፣ ልዩ የበገና ምሥጋና ቀን=====** በደብረ ኤዶም ቅ/ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሳን አንቶኒዮ፤ ቴክሳስ** ከቅዳሴ በኋላ ....** አድራሻ፦ 8102 Midcrown ...
03/24/2026

እሑድ፣ በኒቆዲሞስ ሰንበት፣ ልዩ የበገና ምሥጋና ቀን
=====
** በደብረ ኤዶም ቅ/ማርያም ቤተ ክርስቲያን ሳን አንቶኒዮ፤ ቴክሳስ
** ከቅዳሴ በኋላ ....
** አድራሻ፦ 8102 Midcrown Dr, Windcrest, TX 78239

Zemari Yared Asrat Debre Edom St. Mary Ethiopian Orthodox Tewahedo Church Ephrem Eshete Ephrem

የበገና የምሥጋና ቀን || Harp of David Hymns day====You are cordially Invited. March 29, 2026Debre Edom St. Mary Ethiopian Ortho...
03/12/2026

የበገና የምሥጋና ቀን || Harp of David Hymns day
====
You are cordially Invited.
March 29, 2026

Debre Edom St. Mary Ethiopian Orthodox Tewahedo Church
** Address:
8102 Midcrown Dr, Windcrest, TX
78239
** For more information:- (210) 920-0871

02/04/2026

እንደ ነነዌ ሕዝብ ያለ ልብ ይስጠን
( በሊቀ ሊቃውንት የኔታ አባ አትናቴዎስ )

በትዕግስት ያንብቡት !

​​የልቦና ማዕበልና የነነዌ ተስፋ​

​(መድረኩ ጥቁር ጨርቅ ለብሷል፤ ይህም የዘመኑን ግራ መጋባትና ጨለማ ይወክላል። ቀስ ያለ፣ ልብ የሚነካ የጸሎት ድምፅ ከሩቅ ይሰማል። መብራቱ ሰማያዊ ሆኖ እየደመቀ ሲመጣ፣ አንድ አረጋዊ ረጅም ነጭ ልብስ ለብሶ፣ እጆቹን ወደ ሰማይ ዘርግቶ በተመስጦ ቆሞ ይታያል።)

​(ድምፁ በትዝታና በለቅሶ የታጀበ ነው) ወገኖቼ! ዛሬ በዚህ ግራ በተጋባ ዘመን፣ ማዕበሉ በበዛበት ዓለም ላይ ቆመን ሳለን፤ ፈጣሪ አንድ ትልቅ ነገር እንዲያድለን እንለምነዋለን። ዙሪያችንን ስናየው ጩኸቱ በዝቷል፣ የጥላቻው ማዕበል ከፍ ብሏል፣ የመቻቻላችን መርከብም ልትሰበር ተቃርባለች። በዚህ ጭንቅ ሰዓት ግን ጣታችንን ወደ ሌላ ከመቀሰራችን በፊት፣ እንዲህ ብለን ወደ ልባችን እንመለስ፦

​🌊 እንደ ዮናስ ያለ ነቢይ! ስጠን
​"ወገኖቼ፣ አምላክ እንደ ዮናስ ያለ አስተዋይ ነቢይ ይስጠን። እስቲ አስተውሉ! ዮናስ መጀመሪያ ከፈጣሪ ትእዛዝ ቢሸሽም፣ ባሕሩ ላይ ማዕበሉ ሲበረታ ግን የሸሸው ከሰው ሳይሆን ከራሱ ሕሊና እንደሆነ ተረዳ። ባሕሩ ሲቆጣ 'ለምን ይሄ ሆነ?' ብሎ ሌላውን አልከሰሰም፤ 'ለምን ነፋሱ መጣ?' ብሎ ተፈጥሮን አልረገመም። ወገኖቼ፣ ዛሬ እኮ እኛ ነፋሱን በመርገም፣ ማዕበሉን በመውቀስ ዕድሜያችንን ጨረስን።

​ዮናስ ግን ወደ ውስጡ ተመለከተ። በመርከቧ ውስጥ በፍርሃት ለተጨነቁት ምስኪኖች እንዲህ አለ፦ 'ጥፋቱ የእኔ ነው፤ እኔን ወደ ባሕሩ ጣሉኝና ማዕበሉ ይጥፋ'

​ወገኖቼ፣ እስቲ ቆም ብለን እናስብ! ዛሬ እኮ የጠፋነው 'ጥፋቱ የእኔ ነው' የሚል መሪ በማጣታችን ነው። ራሱን ተወቃሽ የሚያደርግ፣ ሌላው እንዲኖር ራሱን አሳልፎ የሚሰጥ፣ 'እኔ ከጠፋሁ ሕዝቡ ይተርፋል' የሚል የልቦና ጀግና ናፈቀን።

ዮናስን ወደ ባሕር የጣሉት መርከበኞቹ አይደሉም፤ ዮናስ ራሱ ነው ለሌሎች ሰላም ሲል ራሱን ለመስዋዕትነት ያቀረበው።

​የእውነትን ቃል ለመናገር የማይፈራ፣ ሕዝቡ እንዳይጠፋ 'ንሰሐ ግቡ' የሚል ድምፅ ያለው፣ ከራሱ በፊት ስለ መርከቧ ደኅንነት የሚጨነቅ መሪ ዛሬ ያስፈልገናል። እንዲህ ያለ መስዋዕትነት ያለው ልብ፣ እንዲህ ያለ አስተዋይ ነቢይ አምላክ ይስጠን!"

​(አረጋዊው በመድረኩ ላይ ወዲያና ወዲህ እያለ፣ በእጁ የመርከብን መናወጥ በሚያሳይ ምልክት ንግግሩን ይቀጥላል...)
​"ወገኖቼ፣ ዮናስ እኮ በዓሣ ሆድ ውስጥ ሆኖ 'የማዳን ሥራ የአምላክ ነው' ብሎ እስኪያምን ድረስ ትልቅ ትግል ውስጥ ነበር። ዛሬም እኛ ከገባንበት የማዕበል ሆድ ውስጥ እንድንወጣ፣ በመጀመሪያ የራሳችንን ስህተት አምነን የምንቀበልበትን የዮናስን ልቦና ይስጠን።

ሌላውን ሰው ከመጣል፣ ራሳችንን ዝቅ አድርገን ማዕበሉን የምናስታግስበትን ጥበብ አምላክ ይግለጥልን።"
​(መብራቱ ወደ ቀይ ይለወጣል... የነፋሱ ድምፅ ይጨምራል)
​ወገኖቼ፣ የዮናስ ታሪክ የሚጀምረው 'ጥፋቱ የእኔ ነው' ከሚል ንሰሐ ነው። ዛሬስ የእኛ መርከብ የምትተርፈው ማን 'ጥፋቱ የእኔ ነው' ሲል ይሆን?

​🟢​የመርከበኞቹ ማስተዋል (የጥበብ ጉዞ)
​(ድምፅ፦ ኃይለኛ የንፋስ ሽውሽውታ እና የውኃ መገላበጥ ይሰማል። መድረኩ ላይ ያሉት ተጓዦች መርከብ ላይ እንዳሉ ሆነው ግራና ቀኝ ይወዘወዛሉ። አንዱ ተጓዥ ወደ ተመልካቹ እየመጣ በታላቅ ተመስጦ ይናገራል)

​🟢 ወገኖቼ! ቆም ብለን እናስተውል። በመርከቧ ላይ የነበሩትን እነዚያን ተጓዦች በደንብ ተመልከቷቸው። እነርሱ እኮ ዮናስን አያውቁትም ነበር፤ አምላኩንም አያውቁትም። ነገር ግን ማዕበሉ መጥቶ መርከቧ ልትሰበር ስትቃረብ፣ ከመካከላቸው አንድም ሰው ሌላውን በጣት አልቀሰረም።
​"አንተ ነህ ያመጣህብን!" ብለው እርስ በርስ አልተጋደሉም። ይልቁንም መጀመሪያ ያደረጉት ነገር "ሸክሙን መጣል" ነበር።

​🟢​ወገኖቼ፣ አስተውሉ! መርከበኞቹ መጀመሪያ ሰውን አልጣሉም፣ መጀመሪያ እቃቸውን ጣሉ እንጂ። ዛሬ እኛ መርከባችን ስትወዘወዝ፣ ማዕበሉ ሲበረታብን መጀመሪያ የምንጥለው ወንድማችንን ነው። መጀመሪያ የምንጥለው ፍቅራችንን ነው። መርከበኞቹ ግን 'መርከቧ እንድትቀልልን' ያከማቹትን ሀብት፣ የድካማቸውን ውጤት ወደ ባሕር ጣሉ በቃ።

​🟢​ዛሬም አምላክ እንዲህ ያለውን አስተውሎት ይስጠን! ማዕበሉ ሲመጣብን፣ የችግሩ ምንጭ የሆነውን ትዕቢታችንን፣ ጥላቻችንን እና ክፉ ንግግራችንን ወደ ባሕር የምንጥልበት ልቦና ይስጠን።

​🟢​"እጣ ተጣጣሉ"
ተጓዦቹ እውነቱን ለማወቅ ጸለዩ። "እኛ ንጹሕ ነን" ብለው አልተታበዩም። "እጣው በማን ላይ እንደሚወጣ እንይ" አሉ። ይህ ማለት እኮ ራስን መመርመር ነው። ዛሬ እኛ ራሳችንን ከመመርመር ይልቅ ሌላው ላይ እጣ ለመጣል እንሮጣለን። መርከበኞቹ ግን እጣው በዮናስ ላይ ሲወጣ እንኳ፣ ወዲያው አላነቁትም፤ "ማን ነህ? ከየት መጣህ? አምላክህ ማነው?" ብለው ጠየቁት።

​🟢​ወገኖቼ፣ ማስተዋል ማለት እንዲህ ነው። ሰውን ከመፍረድ በፊት ማንነቱን መረዳት፣ ከመጣል በፊት ለመታደግ መሞከር ነው። ዮናስ "እኔን ወደ ባሕር ጣሉኝ" ሲላቸው እንኳ መጀመሪያ "አይሆንም" ብለው ለመቅዘፍ ሞክረው ነበር። የሰው ነፍስ እንዳይጠፋ መጨከን አቃታቸው።

​🟢​ዛሬም እኛ ወንድማችንን አሳልፈን ከመስጠት የምንቆጠብበት፣ ለሰው ነፍስ የምንሳሳበት፣ በችግር ጊዜ በጋራ የምንቆምበት እንደ መርከበኞቹ ያለ አስተውሎት አምላክ ይስጠን! ማዕበሉን የሚያቆመው ጩኸት ብቻ ሳይሆን፣ ለሰው ልጅ ያለን ጥልቅ ፍቅርና ራስን የመመርመር ጥበብ ነውና።

​(ተጓዡ በዝግታ ወደ መሬት ቁጭ ይላል፤ መብራቱ እየጠፋ ይሄዳል)
​ጸሎት፦ "አምላክ ሆይ! በመርከባችን ላይ ማዕበል ሲነሳ፣ ሰውን ከመጣል ሸክምን መጣልን አስተምረን። ሌላውን ከመወንጀል ራስን መመርመርን አድለን። በመከራ ውስጥ ሆነን ለሰው ነፍስ የምንራራበትን ያንን የመርከበኞቹን ማስተዋል ለሁላችንም አፍስስልን።"

​🟢​ የነነዌ መሪ ትሕትና (የዙፋን ንሰሐ)​🟢
​(መድረኩ ደመቅ ይላል። ከበስተጀርባ የከተማ ግርግርና የጭንቀት ድምፅ ይሰማል።

አንድ ሰው የንጉሥ ካባ የሚመስል ደርቦ፣ በግርማ ሞገስ መሃል ላይ ይቆማል። ዮናስ "ነነዌ ትጠፋለች!" ብሎ ሲጮኽ ይሰማል። ንጉሡ በድንገት ካባውን ማውለቅ ይጀምራል...)

አንድ አረጋዊ ባለ ግርማ ሞገስ (በዝግታና በጥልቅ ድምፅ) ወገኖቼ! እስቲ አሁን ደግሞ ዐይናችንን ወደ ነነዌ ቤተ-መንግሥት እናዙር። እንደ ነነዌ ንጉሥ ያለ መሪ ማግኘት እንዴት ያለ የታደለ ዘመን ነው!

​🟢​ዮናስ በከተማዋ አውራ ጎዳናዎች እየዞረ "በሦስት ቀን ውስጥ ነነዌ ትገለባበጣለች!" ብሎ ሲያውጅ፣ ዜናው ወደ ንጉሡ ዘንድ ደረሰ። ንጉሡ ምን አደረገ? "ይህንን ነቢይ በሰንሰለት እሰሩት! ክብሬን ነካ፣ መንግሥቴን አወከ" አላለም። ወታደሮቹን አላዘዘም፣ ኃይሉን አላሳየም።
​ይልቁንም፦

​🟢ወገኖቼ፣ አስተውሉ! ንጉሡ ከዙፋኑ ወረደ። ዙፋን እኮ የሥልጣን፣ የኩራትና የኃይል ምልክት ነው። እሱ ግን "ከአምላክ ቁጣ በታች ነኝ" ብሎ ራሱን ዝቅ አደረገ። የለበሰውን ያን የሚያምር የንግሥና ልብሱን አወለቀ፤ በምትኩም ሻካራ ማቅ ለበሰ። አክሊሉን ጥሎ በአመድ ላይ ተቀመጠ።

​🟢​ዛሬም አምላክ እንዲህ ያለውን ትሕትና ይስጠን!
"ጥፋቱ ከእኔ ነው፣ መከራው የመጣው በእኔ በደል ነው" ብሎ ራሱን ዝቅ የሚያደርግ፣ የሕዝቡን ዕንባ አይቶ ራሱ የሚያለቅስ፣ ለሕዝቡ ደኅንነት ሲል ክብሩን አሳልፎ የሚሰጥ መሪ ዛሬ ያስፈልገናል። መሪው ማቅ ሲለብስ ሕዝቡ ተስፋ ያደርጋል፤ መሪው ሲጸልይ ሰማይ ይከፈታል።
​ንጉሡ አዋጅ አስነገረ፦ "ሰውም ቢሆን እንስሳም ቢሆን ምንም አይቅመሱ፤ በኃይለኛውም ወደ አምላክ ይጮኹ" አለ። ወገኖቼ፣ እውነተኛ መሪ ሕዝቡን ወደ እግዚአብሔር የሚመራ እንጂ ራሱን እንደ አምላክ የሚያሳይ አይደለም።

​🟢 የነነዌ ንጉሥ "ምናልባት አምላክ ይራራልን ይሆናል" ብሎ በትንሽ ተስፋ ውስጥ ትልቅ ንሰሐን አሳየ።
​ዛሬም እኛ ማዕበሉን የምናልፈው እንዲህ ያለ መሪ ሲኖረን ነው። "እኔ አውቃለሁ" ከሚል ትዕቢት ወጥቶ፣ "አምላክ ሆይ ማረን" ወደሚል ትሕትና የሚመለስ መሪ አምላክ ይስጠን። የነነዌ ንጉሥ ዙፋኑን በመተው ከተማውን አዳነ። ዛሬም ጥቅምንና ክብርን በመተው ሀገርን የሚያድን ልቦና ለሁላችንም ይሁን!

​(አረጋዊው በጉልበቱ ተንበርክኮ፣ ንጉሣዊ ካባውን መሬት ላይ ጥሎ አንገቱን ይደፋል)
​ጸሎት፦ "አምላክ ሆይ! በየቤታችንም ይሁን በየመንግሥታችን፣ የትዕቢትን ካባ አውልቀን የንሰሐን ማቅ የምንለብስበትን ትሕትና ስጠን። ክብራችንን ላንተ ትተን፣ ሕዝብህን የምናድንበትን ብልሃት አድለን።"

​🟢​ የነነዌ ሕዝቦች ልቦና (የአንድነት ንሰሐ)​🟢
​(መድረኩ ሙሉ በሙሉ በደብዛዛና በጭጋጋማ ብርሃን ይሞላል። ከበስተጀርባ የብዙ ሰዎች የለቅሶና የጸሎት ድምፅ እንደ ንፋስ ሽውሽውታ ይሰማል። ተዋናዩ መድረኩ መሃል ላይ ቆሞ፣ ፊቱ ላይ በአመድ የተቀባ መስቀል ይታያል፤ ይህም የንስሐ ምልክት ነው።)

​🟢​አረጋዊው (በሚንቀጠቀጥና በተመስጦ ድምፅ) ወገኖቼ! አሁን ደግሞ ወደ ትልቁ ተዓምር እንምጣ። እንደ ነነዌ ሕዝቦች ያለ ለስላሳ ልቦና አምላክ ለሁላችንም ይስጠን! እስቲ አስቡት፤ ነነዌ ግዙፍ ከተማ ነበረች። በክፋቷና በኃጢአቷ ብዛት ጩኸቷ ወደ ሰማይ የደረሰ፣ በዓመፅ የሰከረች ከተማ ነበረች። ነገር ግን አንዲት የንስሐ ቃል ስትሰማ፣ ያ ያበጠ ልቧ እንደ በረዶ ቀለጠ።

​🔴 የእልከኝነት መለወጥ!
"ወገኖቼ፣ የነነዌ ሕዝብ 'ይህ ነቢይ ከየት መጣ? ማን ሰጠው ስልጣን?' ብለው አልተከራከሩም። ቃሉን ሲሰሙ 'እውነት ነው' አሉ። ዛሬ እኛ እውነት ሲነገረን የምንቆጣ፣ ስህተታችን ሲገለጥ የምናምፅ፣ ልባችን እንደ ድንጋይ የጠነከረብን ነን። የነነዌ ሕዝብ ግን ልባቸውን እንደ መሬት አላደረጉትም፤ እንደ ሰም አረገቡት እንጂ። የጥፋት ዐዋጁን ሲሰሙ 'እኛን አይመለከተንም' ሳይሉ፣ ወደ ራሳቸው ተመለከቱ።"

​⚪ ከአንድነት የመነጨ ንሰሐ!
"አስተውሉ ወገኖቼ! ከታላቁ እስከ ታናሹ፣ ከባለጸጋው እስከ ምስኪኑ፣ ከሽማግሌው እስከ ሕፃኑ በአንድ ቃል ተስማሙ። በመካከላቸው የዘር፣ የጎሳ ወይም የደረጃ ልዩነት አልነበረም። 'እኔ ንጹሕ ነኝ፣ እሱ ግን ኃጢአተኛ ነው' የሚል መካካድና ጣት መጠቆም አልነበረም። ሁሉም በአንድነት ማቅ ለበሱ። ማቅ መልበስ እኮ የምቾት መራቆት ብቻ አይደለም፤ 'ሁላችንም በአምላክ ፊት እኩል ድሆችና ምሕረት ፈላጊዎች ነን' ብሎ ራስን ማሳነስ እንጂ።"

​🟢 ለእንስሳቱ እንኳ መራራት!
"ወገኖቼ፣ የነነዌ ሕዝብ ልቦና ምን ያህል እንደረገበ የሚያሳየው፣ እንስሳቶቻቸው እንኳ ሳይቀሩ እንዳይበሉና እንዳይጠጡ ማድረጋቸው ነው። ይህ ትልቅ ምስጢር አለው። 'መላው ተፈጥሮ በእኛ በደል ምክንያት እየታወከ ነው' ብሎ ማስተዋል ነው። ዛሬ እኛ ለወንድማችን ነፍስ በማንራራበት፣ ደም በከንቱ በሚፈስበት ዘመን፣ እነርሱ ግን ለእንስሳቶቻቸው ጭምር በመጨነቅ ወደ አምላክ ጮኹ። የፍጥረት ሁሉ ስቃይ ገባቸው።"

​⚫ ከክፉ መንገድ መመለስ!
"ወገኖቼ፣ ትልቁ ምልክት ግን ጩኸቱ ብቻ አይደለም፤ 'እያንዳንዱ ከክፉ መንገዱና በእጁ ካለው ግፍ ተመለሰ' ይላል መጽሐፉ። ዛሬም አምላክ እንዲህ ያለውን ልቦና ይስጠን! በደላችንን ተገንዝበን፣ የሰረቅነውን መልሰን፣ የበደልነውን ክሰን፣ የገፋነውን አንስተን ከክፉ መንገዳችን የምንመለስበትን ንጹሕ ልብ ይስጠን። ቃሉን መስማት ብቻ ሳይሆን፣ ወደ ተግባር የመለሱበት ያ ልብ ዛሬ ለእኛም መድኃኒት ነው።"

​(አረጋዊሰ እጆቹን ወደ ሰማይ ዘርግቶ፣ ድምፁን ከፍ ያደርጋል።)
​ወገኖቼ! ነነዌ የዳነችው በግንቧ ጥንካሬ ወይም በጦር መሣሪያዋ ብዛት ሳይሆን በሕዝቧ ልብ መለስለስ ነው። ዛሬም ምድራችንን የምናድነው በጠመንጃ ጩኸት ሳይሆን በንስሐ ዕንባ ነው። የነነዌ ሕዝቦች ዛሬ ለእኛ ታላቅ ምስክሮች ናቸው።

​🙏 ማጠቃለያ ጸሎት፦
"አምላክ ሆይ! በልባችን ያለውን የድንጋይ ግንብ አፍርሰው። የኩራትና የትዕቢት ካባችንን አውልቀን፣ በፍቅርና በይቅርታ የምንገናኝበትን የነነዌ ሕዝቦችን ልቦና ስጠን። ዮናስ ሲሰብክ እንደተመለሱ፣ እኛም ዛሬ ካለንበት የጥፋት መንገድ ተመልሰን ምሕረትህን የምናይበትን ዘመን አምጣልን! አሜን።"

( በሊቀ ሊቃውንት የኔታ ቆሞስ አባ አትናቴዎስ )
የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አበምኔት
የአራቱ ጉባዔያት መምህር
አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ

01/30/2026

Orthodox Tewahedo Liturgy in English, this Sunday.

This page is dedicated to information regarding the religious and social and services of Debre Edom St. Mary Ethiopian Orthodox Tewahido Church in San Antonio Texas.
[email protected] Tel. 210-920-0871

🙏 "ጊዜ ዕረፍታ ለሶልያና ወረደ ወልድ እምዲበ ልዕልና ጠሊሳነ ንግሥ ሶቤሃ ከደና"🙏 የአስተርእዮ ማርያም ትምህርት🙏==========(አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ)+++++🙏መግቢያ"ሰላም ...
01/28/2026

🙏 "ጊዜ ዕረፍታ ለሶልያና ወረደ ወልድ እምዲበ ልዕልና ጠሊሳነ ንግሥ ሶቤሃ ከደና"🙏 የአስተርእዮ ማርያም ትምህርት🙏
==========
(አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ)
+++++
🙏መግቢያ
"ሰላም ለኪ!" እያሉ መላእክት በሰማይ፣ ካህናት በምድር የሚያመሰግኗት፤ የሁላችን እናት፣ የዓለም ሁሉ እመቤት፣ የቅዱሳን መመኪያ፣ የኃጥአን ተስፋ... ዛሬ በመካከላችን ትገኛለች።

🙏ዛሬ የምንማረው ስለ አስደንጋጩ ሞት አይደለም፤
🙏ዛሬ የምናወራው ስለ ፍጡር መጥፋት አይደለም።
🙏ዛሬ የምንመለከተው... መለኮት እናቱን ሊቀበል ከሰማያዊ ዙፋኑ ሲወርድ ነው!
🙏ዛሬ የምንረዳው... ሞት በድንግል ማርያም ፊት ተንበርክኮ ‘ዕረፍት’ ተብሎ ሲሰየም ነው።
🙏የተከበራችሁ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች! እስኪ ለአፍታ ልባችሁን ሰብሰብ አድርጉና ወደ ኢየሩሳሌም፣ ወደ ዮሐንስ ቤት በመንፈስ እንሂድ።

🙏 ኑ! ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት በበገናው ሲዘምር እዩት፤ "ልጄ ሆይ ስሚ እዪ ጆሮሽንም ዘንበል አድርጊ" (መዝ. 44) እያለ በመሰንቆው ሲያመሰግን አድምጡት።
ኑ! ነቢያት በደስታ ሲሰበሰቡ እዩ፤
🙏ኢሳይያስ "ድንግል ትፀንሳለች" ያለው ትንቢት ተፈጽሞ፣
🙏ሕዝቅኤል "የተዘጋች በር" ያላት ታላቋ እመቤት ወደ ዘለዓለማዊ ሰላም ስትሸጋገር እዩ።
🙏 ነቢያት እጅ ለእጅ ተያይዘው እንደ ሐዋርያት በአንድነት ቆመው "ትንቢታችን በአንቺ ተፈጸመ" እያሉ ሲዘምሩ ተመልከቱ።
🙏 ኑ! ዓለምን የፈጠረ ጌታ፣ እናቱን "ወዳጄ ሆይ ተነሺ፤ ውበቴ ሆይ ነዪ፤ መጸው አልፏል ዝናቡም አልፎ ሄዷል" (መኃ. 2) እያለ በፍቅር ሲጠራት በልባችሁ ዐይን እዩ። ቅዱሳን ሐዋርያት በደመና ተጭነው፣ መላእክት በብርሃን ክንፍ አጅበው፣ ሰማይና ምድር በአንድነት የሰላምታ ዝማሬ ሲያቀርቡ እናስተውላለን።

🙏 ይህ ዕለት ‘አስተርእዮ ’ ይባላል። መገለጥ ነው! የእናትነት ፍቅር የተገለጠበት፣ የልጅነት ባለሟልነት የታየበት፣ ሞት ተሸንፎ ትንሣኤ የሰለጠነበት ታላቅ ምስጢር ነው። ቅኔው እንዲህ ይላል፦
"ጊዜ ዕረፍታ ለሶልያና፤
ወረደ ወልድ እምዲበ ልዕልና፤
ጠሊሳነ ንግሥ ሶቤሃ ከደና።"
የርግብየ የሰላሜ፣ የእመቤታችን የዕረፍቷ ጊዜ በደረሰ ጊዜ... ጌታ ከልዕልናው ወረደ፤ የንግሥና መጎናጸፊያም (የክብር ደመና) በዚያን ጊዜ ጋረዳት።
ኑ! ዛሬ በዚህ ድንቅ ትምህርት ውስጥ የእመቤታችንን 64 ዓመታት የቅድስና ጉዞ፣ የሐዋርያትን መከራና ሱባኤ፣ የተውፋንያን ፍርድና ምሕረት፣ የድንግልን ትንሣኤና ዕርገት በጥልቀት እንመልከት። ይህ ትምህርት ለነፍሳችን ምግብ፣ ለልባችን ተስፋ፣ ለሕይወታችን ደግሞ ብርሃን ይሁንልን።

🙏🙏 ርዕስ፦ "ጊዜ ዕረፍታ ለሶልያና ወረደ ወልድ እምዲበ ልዕልና ጠሊሳነ ንግሥ ሶቤሃ ከደና"

🙏🙏መለኮታዊ ጥሪና የቅድስት ነፍስ ዕረፍት

ምስጢር፦
"ሶልያና" (ርግብ/ሰላም) የተባለች እመቤታችን ዕረፍቷ "አስተርእዮ" (መገለጥ) ይባላል። ይህም ሞት ለቅዱሳን ጥፋት ሳይሆን ወደ ክብር መሸጋገሪያ መሆኑ የተገለጠበት ምስጢር ነው። መለኮት ከሰው ልጅ ጋር ባለው አንድነት፣ ሞት ድል ተመትቶ የክብር መግቢያ ሆኗል።

🙏🙏 እመቤታችን በምድር ላይ የቆየችባቸው 64 ዓመታት (3 ዓመት በወላጆቿ ቤት፣ 12 ዓመት በቤተ መቅደስ፣ 34 ዓመት ከልጇ ጋር፣ 15 ዓመት ከዮሐንስ ወንጌላዊ ጋር) የታሪክ ብቻ ሳይሆኑ የምስጢር ቁጥሮች ናቸው። ጥር 21 ቀን የዕረፍቷ ጊዜ ሲቃረብ፣ ቅዱስ ገብርኤል የክብርን ዜና ይዞ መጣ። ቅኔው "ወረደ ወልድ እምዲበ ልዕልና" እንደሚለው፣ ጌታችን የእናቱን ነፍስ ለሌላ መልአክ አሳልፎ አልሰጠም፤ ራሱ ወርዶ በክብር ተቀበላት። ይህ ክስተት እመቤታችን ከፍጥረት ሁሉ በላይ መሆኗንና የጌታ ልዩ ፍቅር በእርሷ ላይ መገለጡን ያሳያል። ነፍሷን በብርሃን ልብስ ጠቅልሎ ወደ ሰማያዊው ኢየሩሳሌም አሳረገላት።

"የቅዱሳኑ ሞት በእግዚአብሔር ፊት የከበረ ነው" (መዝ. 114፥15)።
ምሳሌ፦ አንድ ታላቅ ንጉሥ እናቱን ወደ መንግሥቱ ሲጠራት፣ ተራ መልእክተኛ ከመላክ ይልቅ ራሱ በክብር ሠረገላ ወጥቶ እንደሚቀበላት፣ ጌታም የእናቱን ነፍስ ለመቀበል ከልዕልናው ወረደ።

🙏🙏የሐዋርያት መሰብሰብና የሥጋዋ መነጠቅ
++++
ምስጢር፦
"ጠሊላነ ንግሥ ሶቤሃ ከደና" (የንግሥና ደመና ጋረዳት) የሚለው የቅኔው ክፍል፣ ሥጋዋ ከአይሁድ ክፋት ተሰውሮ በመለኮታዊ ጥበቃ መጠበቁን ያሳያል። ይህ መለኮታዊ መጋረጃ የእግዚአብሔርን ባለሟሎች ማንም ሊነካቸው እንደማይችል የሚያሳይ ምስጢር ነው።

ቅዱሳን ሐዋርያት በዓለም ዙሪያ ወንጌልን እየሰበኩ ሳለ፣ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በደመና ተጭነው በኢየሩሳሌም ተሰበሰቡ። ይህ መሰብሰባቸው ለስንብት ብቻ ሳይሆን፣ የእመቤታችንን ቅድስና ለመመስከርም ጭምር ነበር። ሥጋዋን በክብር ገንዘው ወደ ጌቴሴማኒ ሊቀብሯት ሲሄዱ፣ አይሁድ በምቀኝነት ተነሡ። ተውፋንያ የተባለው ሰው የአልጋዋን ቃሬዛ ሲይዝ እጆቹ ተቆርጠው ተንጠልጥለዋል፤ ይህ የቅድስናዋ ተሟጋች እግዚአብሔር መሆኑን ያሳያል። በኋላ ግን ተውፋንያ ተጸጽቶ በመማጸኑ ተፈውሷል። ይህን ሁሉ ግርግር ለማስቆምና ሥጋዋን ከክፉዎች ለመጠበቅ፣ መልአኩ ሥጋዋን ከዮሐንስ ጋር ነጥቆ በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር አኖረው።

"በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸልማ ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች" (መዝ. 44፥9)።

ምሳሌ፦
አንድ እጅግ ውድ የሆነ ዕንቁ በጠላቶች እጅ እንዳይወድቅ ባለቤቱ በጥንቃቄ በሳጥን ውስጥ ከድኖ (ሸፍኖ) እንደሚደብቀው፣ ጌታም የእናቱን ሥጋ በደመና ከድኖ ከምቀኞች እጅ ሰውሮታል።

🙏🙏የሱባኤው በረከትና የትንሣኤዋ ተስፋ
+++++
ምስጢር፦
የእመቤታችን ትንሣኤና ዕርገት ለእኛ የሕይወት ተስፋችን መገለጫ ነው። "ጊዜ ዕረፍታ" ስንል ለዘለዓለም የጠፋችበትን ሳይሆን፣ ሞትን ድል አድርጋ ዳግመኛ የተገለጠችበትን (አስተርእዮን) እናስባለን።
ሐዋርያት የሥጋዋ መነጠቅ ስላሳዘናቸው፣ "እንዴት በረከቷ ይለየናል?" ብለው ለ15 ቀናት በጾምና በጸሎት ሱባኤ ያዙ። ይህ ሱባኤ (ጾመ ፍልሰታ) የፍቅርና የጽናት ውጤት ነው። በሱባኤው መጨረሻም ሥጋዋን ተቀብለው ቀበሯት፤ ነገር ግን መቃብር አላስቀራትም። በሦስተኛው ቀን እንደ ልጇ ተነሥታ በክብር አረገች። ይህም ለእኛ ለክርስቲያኖች ታላቅ በረከት ነው፤ ምክንያቱም እመቤታችን በሰማይ ሆና የምታማልደን ሕያው እናት መሆኗን ያረጋግጥልናል። ዕረፍቷ "ሞተ" ሳይባል "አረፈች" መባሉ፣ ክርስቲያን ሁሉ በክብር እንደሚነሣ ተስፋ የሚሰጥበት ነው
"አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፣ አንተና የቅድስናህ ታቦት" (መዝ. 131፥8)።

ምሳሌ፦
የሰናፍጭ ቅንጣት መሬት ውስጥ ተቀብራ ትንሣኤዋን አሳይታ እንደምትበቅልና ለብዙዎች መጠለያ እንደምትሆን፣ እመቤታችንም በመቃብር ተቀብራ በልጇ ሥልጣን ተነሥታ ለዓለም ሁሉ የምልጃ መጠለያ ሆናለች።

🙏🙏ከበዓሉ የምናገኘው ሦስት ታላላቅ በረከቶች፦
+++++++
የቃል ኪዳን በረከት፦ መታሰቢያዋን ላደረገ ሁሉ ጌታ የሰጠው የምሕረት ቃል ኪዳን ተሳታፊ እንሆናለን።
የጽናት በረከት፦ እንደ ሐዋርያት በጾምና በጸሎት ከቆየን፣ የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራና የእመቤታችንን በረከት እንደምናገኝ እንማራለን።
የተስፋ በረከት፦ ሞት ፍጻሜ ሳይሆን የመንፈሳዊ ዕረፍት መጀመሪያ መሆኑን ተረድተን በቅድስና ለመኖር እንበረታታለን።

🙏🙏ይህንን የሐዋርያት መሰብሰብ ዘርዘር አድርገን እንመልከተው
++++++
የሐዋርያት መሰብሰብ፣ የአይሁድ ምቀኝነትና የሥጋዋ መነጠቅ
የሐዋርያት ተአምራዊ ስብስብና ሥርዓተ ግንዘት

ምስጢር፦
ሐዋርያት በደመና ተጭነው መምጣታቸው ቤተክርስቲያን በአንድነት (በጉባኤ) የምትገለጥባትና የእመቤታችን በረከት ለዓለም ሁሉ መሆኑን የሚያሳይ ምስጢር ነው።

እመቤታችን በምታርፍበት ጊዜ ሐዋርያት በዓለም ዙሪያ ወንጌልን ለማስተማር ተበትነው ነበር። ነገር ግን የእመቤታችንን ስንብትና በረከት እንዲሳተፉ መንፈስ ቅዱስ በደመና ጭኖ ከየአሉበት አምጥቶ በኢየሩሳሌም ሰበሰባቸው። ሐዋርያትም የእናታቸውን ዕረፍት አይተው እጅግ አዘኑ፤ ነገር ግን ጌታ በነገራቸው መሠረት ቅዱስ ሥጋዋን በታላቅ ክብርና በዝማሬ ገነዙት። ወደ ቀብሯ ቦታ ወደ ጌቴሴማኒ ይዘው ሲሄዱ፣ ምድር በዝማሬያቸውና በመላእክት ምስጋና ተሞልታ ነበር። ይህም እመቤታችን በሕይወቷም ሆነ በዕረፍቷ የቤተክርስቲያን አንድነት መሆኗን ያሳያል።

ምሳሌ፦
አንድ የእሳት ነበልባል ብዙ ችቦዎችን እንደሚያበራ፣ የእመቤታችን ዕረፍትም በዓለም ተበትነው የነበሩ ሐዋርያትን በአንድ ፍቅርና በአንድ ቦታ ሰብስቧቸዋል።

🙏🙏 የተውፋንያ ድፍረትና የመለኮታዊ ኃይል መገለጥ
+++++
ምስጢር፦
"ጠሊሳነ ንግሥ ሶቤሃ ከደና" (የንግሥና ደመና ጋረዳት) የሚለው ክፍል አይሁድ የእመቤታችንን ሥጋ ለማርከስ ቢፈልጉም መለኮታዊ ኃይል ግን ከለላ እንደሆናት የሚያሳይ ምስጢር ነው።

ሐዋርያት ሥጋዋን ይዘው ሲሄዱ አይሁድ በምቀኝነት ተነሡ። "ቀድሞ ልጇ ተነሣ እያሉ ዓለምን አወኩ፣ አሁን ደግሞ እሷም ተነሣች ሊሉ ነው" በማለት ሥጋዋን ለማቃጠል ወሰኑ። ከእነርሱም መካከል ተውፋንያ የተባለው አይሁዳዊ በድፍረት ሮጦ የአልጋዋን ቃሬዛ በሁለት እጆቹ ያዘ። በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ በእሳት ሰይፍ ሁለት እጆቹን ቆረጣቸው፤ እጆቹም ከአልጋው ላይ ተንጠልጥለው ቀሩ። ይህ ክስተት የእመቤታችንን ቅድስና የሚጋፋ ሁሉ ፍርድ እንደሚጠብቀው ያሳያል። ይሁን እንጂ ተውፋንያ በሠራው ጥፋት ተጸጽቶ በመማጸኑና ሐዋርያትም በመጸለያቸው፣ እጆቹ ተመልሰው ድነውለታል። ይህም የእመቤታችን ምሕረት ለጠላቶቿም ጭምር መሆኑን ያስተምረናል።

"ኃጥአን ሰይፋቸውን መዘዙ... ሰይፋቸው ወደ ልባቸው ይገባል" (መዝ. 36፥14-15)።

የሥጋዋ መነጠቅና ወደ ገነት መወሰድ
++++++
ምስጢር፦
የእመቤታችን ሥጋ ከሐዋርያት ተለይቶ መወሰዱ፣ ቅዱስ ሥጋዋ ምድራዊ የአይሁድ የተንኮልና የርኩሰት ሥራቸው እንዳይነካውና በክብር ተጠብቆ ለትንሣኤ እንዲዘጋጅ የተደረገ መለኮታዊ ጥበቃ ነው።

🙏🙏 አይሁድ ሁለተኛ ክፉ ነገር እንዳያደርጉ፣ የእግዚአብሔር መልአክ የእመቤታችንን ሥጋ ከሐዋርያው ዮሐንስ ጋር ነጥቆ ወሰዳቸው። ሐዋርያት በዐይናቸው እያዩ በደመና ተሰውራ ወደ ገነት ተወሰደች። በዚያም በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር እንድትቆይ ተደረገ። "ከደና" (ጋረዳት/ሸፈናት) የሚለው ቃል እዚህ ላይ ጎልቶ ይታያል፤ ጌታ እናቱን ከክፉዎች ዐይንና እጅ ሰወራት። ሐዋርያው ዮሐንስም የእመቤታችንን ሥጋ በገነት ሲያይ መቆየቱ፣ ለሌሎቹ ሐዋርያት በኋላ ለሚደረገው ሱባኤ መሠረት ሆኗቸዋል።

ምሳሌ፦
አንድ ብልህ አባት ውድ ሀብቱን ሌቦች ሊዘርፉት ሲመጡ፣ ሀብቱን ነጥቆ ማንም በማያውቀው አስተማማኝ ቦታ እንደሚያስቀምጠው፣ ጌታም እናቱን ከአይሁድ ተንኮል ነጥቆ በገነት አኖራት።

🙏🙏የሐዋርያት ሱባኤ፣ ትንሣኤዋና ሰማያዊ ዕርገቷ
+++++++
የሐዋርያት ሐዘንና የሱባኤው መጀመር

ምስጢር፦
ሐዋርያት የእመቤታችንን ሥጋ ለማግኘት ሱባኤ መያዛቸው፣ በረከትንና መለኮታዊ ምስጢርን ለማግኘት ጾምና ጸሎት አስፈላጊ መሆናቸውን የሚያሳይ ምስጢር ነው።

የእመቤታችን ሥጋ በመላእክት ተነጥቆ ወደ ገነት መወሰዱ ሐዋርያትን እጅግ አሳዘናቸው። "እንዴት የእናታችን በረከት ይለየናል?" በማለት በሐዘን ተከዙ። በዚህም ምክንያት ሐዋርያት የሥጋዋን መገኘት ተስፋ በማድረግ ሱባኤ (የጾምና የጸሎት ጊዜ) ያዙ። ይህም ዛሬ በቤተክርስቲያናችን የምንጾመው "ጾመ ፍልሰታ" መሠረት ነው። ሐዋርያት በአንድ ልብ ሆነው መጾማቸው፣ እግዚአብሔር ለጸሎትና ለጽናት የሚሰጠውን ታላቅ ዋጋ ያሳያል። ዮሐንስ ወንጌላዊ ሥጋዋ በገነት መኖሩን ለሐዋርያት ቢነግራቸውም፣ እነርሱ ግን በዐይናቸው አይተው በክብር ለመቅበርና በረከቷን ለመካፈል ባላቸው ጉጉት ሱባኤውን ቀጠሉበት።

ምሳሌ፦
የጠፋውን ውድ ሀብት ለማግኘት በብርቱ እንደሚፈለግ ሁሉ፣ ሐዋርያትም የእመቤታችንን ቅዱስ ሥጋ ለማግኘት በጾም ፍለጋ አደረጉ።

የሥጋዋ መገኘትና ሥርዓተ ቀብሯ
+++++
ምስጢር፦
የእመቤታችን ሥጋ ለሐዋርያት መሰጠቱ፣ ቤተክርስቲያን ለሥጋዊውም ሆነ ለመንፈሳዊው በረከት ያላትን ባለቤትነት የሚያረጋግጥ ምስጢር ነው።

ሰፋ ያለ ማብራሪያ፦
ሐዋርያት በጾምና በጸሎት ከቆዩ በኋላ፣ እግዚአብሔር ልመናቸውን ሰምቶ የእመቤታችንን ሥጋ በነሐሴ 14 ቀን ሰጣቸው። ሐዋርያትም በታላቅ ዝማሬና ምስጋና ሥጋዋን ይዘው በጌቴሴማኒ ቀበሯት። ይህ የቀብር ሥነ-ሥርዓት ምድራዊ ሞትን ሳይሆን፣ እንደ ዘር መሬት ውስጥ ገብታ ለታላቅ ትንሣኤ መዘጋጀቷን የሚያሳይ ነበር። "ጊዜ ዕረፍታ" ስንል ይህንን የክብር ዕረፍት ጭምር ነው። በዚያን ጊዜ ሐዋርያው ቶማስ በሀገረ ስብከቱ (በሕንድ) ስለነበረ በቀብሯ ላይ አልተገኘም ነበር፤ ይህም ለትንሣኤዋ ምስክርነት ሌላ መለኮታዊ ምክንያት ሆነ።
ማጣቀሻ፦ "አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፣ አንተና የቅድስናህ ታቦት" (መዝ. 131፥8)።

ትንሣኤዋ፣ ዕርገቷና የቶማስ ምስክርነት
++++
ምስጢር፦ የእመቤታችን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ ለሰው ልጅ ሁሉ የትንሣኤያችን በኩራትና ሞትን ድል የማድረግ ተስፋችን ነው። "ጠሊሳነ ንግሥ ሶቤሃ ከደና" እንዲል፣ በክብር ደመና ተጭና ወደ ሰማይ አርጋለች።

እመቤታችን በመቃብር ለዘለዓለም አልቀረችም። እንደ ልጇ በሦስተኛው ቀን በነሐሴ 16 ቀን ተነሣች። ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ በደመና ተጭኖ ከሕንድ ሲመጣ፣ እመቤታችን ስታርግ በሰማይ አገኛት። "ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፣ ዛሬም ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ልቅርን?" ብሎ በሐዘን ሲማጸናት፣ እመቤታችንም ለምስክርነት እንዲሆነው ሰበኗን (የተገነዘችበትን ጨርቅ) ሰጥታው አረገች። ቶማስ ለሐዋርያት ይህንን የምስራች በነገራቸው ጊዜ፣ እነርሱም ትንሣኤዋን ለማየት በድጋሚ ጾመው ነሐሴ 16 ቀን ትንሣኤዋን ለማየት በቅተዋል። ይህ ዕርገት እመቤታችን ዛሬም በሰማይ ሆና ለዓለም የምታማልድ ሕያው እናት መሆኗን ያሳያል።

ምሳሌ፦
ፀሐይ ለጥቂት ጊዜ በደመና ተከልላ ቆይታ ድንገት በታላቅ ብርሃን እንደምትወጣ፣ እመቤታችንም በመቃብር ለጥቂት ጊዜ ቆይታ በታላቅ ብርሃን ተነሥታ አርጋለች።

ይህ "አስተርእዮ ማርያም" የተባለው የእመቤታችን የዕረፍት በዓል፣ እግዚአብሔር ለሰው ልጅ የሰጠውን ክብር የምናይበት ነው። ከዕረፍቷ እስከ ትንሣኤዋ ያለው ታሪክ የሚያስተምረን፦
ሞት ለክርስቲያን ዕረፍት እንጂ ፍጻሜ አለመሆኑን፣
በጾምና በጸሎት (እንደ ሐዋርያት) የሰማይን በረከት ማግኘት እንደሚቻል፣
እመቤታችን በሰማያዊ ክብሯ ሆና ዛሬም እንደምትባርከንና እንደምታማልደን ነው።

🙏 ከበዓሉ የምናገኛቸው አራት ታላላቅ በረከቶች🙏
++++++++
** የሞት ፍርሃትን የማሸነፍ በረከት
ማብራሪያ፦ የአስተርእዮ በዓል ሞትን "ዕረፍት" ብሎ ይጠራዋል። እመቤታችን በክብር ማረፏ፣ ሞት ወደ ክርስቶስ መሄጃ ድልድይ እንጂ ጥፋት አለመሆኑን ያረጋግጥልናል። ይህ በዓል በነፍሳችን ላይ ያለውን የሞት ጥላ ያስወግዳል።

ምሳሌ፦
አንድ ተማሪ ፈተናውን ጨርሶ ውጤቱን ለመቀበል ወደ መድረክ እንደሚጠራ፣ ቅዱሳንም የዚህን ዓለም ፈተና ጨርሰው ለክብር እንደሚጠሩ ያሳየናል።

🙏🙏የአማላጅነት ቃል ኪዳን በረከት
++++++++
ማብራሪያ፦
ጌታችን ለእናቱ "ስምሽን የጠራውን፣ መታሰቢያሽን ያደረገውን እምርልሻለሁ" የሚል ቃል ኪዳን ሰጥቷታል። በዓሉን ስናከብር ከዚህ መለኮታዊ ቃል ኪዳን በረከትን እንካፈላለን፤ ከኃጢአት ሸክምም የምንረግፍበትን ዕድል እናገኛለን።

ምሳሌ፦
የአንድ ታላቅ ባለሥልጣን እናት የምታቀርበው ልመና በልጇ ዘንድ ተቀባይነት እንዳለው ሁሉ፣ የድንግል ማርያም ልመናም በእግዚአብሔር ዘንድ እጅግ ፈጣንና ተሰሚ ነው።

🙏🙏የመንፈሳዊ ጽናትና የትዕግሥት በረከት🙏🙏
+++++++
ማብራሪያ፦
እመቤታችን በሕይወቷ ብዙ መከራን አሳልፋለች፤ በዕረፍቷ ግን ታላቅ ክብርን አገኘች። ይህ በዓል በችግር ውስጥ ያሉ ምእመናን በትዕግሥት ከጸኑ መጨረሻቸው ክብር መሆኑን የምስራች ይነግራቸዋል።
ምሳሌ፦ አንድ ገበሬ በዝናብና በፀሐይ ተገርፎ ዘርን ቢዘራ፣ በመከር ወቅት በደስታ እህሉን እንደሚሰበስብ፤ እኛም በምድር ብንጋደል በሰማይ የዕረፍትን መከር እናጭዳለን።

🙏🙏 የቅድስናና የንጽሕና በረከት
+++++
ማብራሪያ፦
የእመቤታችን ሥጋ መቃብር አላስቀረውም፤ ምክንያቱም ሥጋዋ ንጹሕና የተቀደሰ ነበር። ይህ በዓል እኛም ሥጋችንን ከኃጢአት ብንጠብቅ የትንሣኤ ክብር ተካፋዮች እንደምንሆን ተስፋ ይሰጠናል።
ምሳሌ፦ ንጹሕ ልብስ የለበሰ ሰው ወደ ንጉሥ ግብዣ እንደሚገባ፣ በቅድስና የኖረ ሥጋም ወደ ሰማያዊው ግብዣ ለመግባት ባለሟልነት አለው።

🙏🙏 እኛ ማድረግ ያለብን ዐበይት ነጥቦች
++++++
በጸሎትና በሱባኤ መጽናት (የሐዋርያት ፈለግ)

ማብራሪያ፦
ሐዋርያት የእመቤታችንን በረከት ያገኙት በጾምና በጸሎት ተወስነው ነው። እኛም በሕይወታችን መከራ ሲገጥመን ወይም በረከትን ስንፈልግ፣ እንደ ሐዋርያት ወደ እግዚአብሔር በሱባኤ መቅረብ አለብን።
ምሳሌ፦ በር እስካልተንኳኳ ድረስ እንደማይከፈት ሁሉ፣ እኛም በጸሎት የሰማይን ደጅ ሳናንኳኳ መለኮታዊ ምስጢር አይገለጥልንም።

🙏🙏 ለቅዱሳን መካነ መቃብርና ንዋያተ ቅድሳት ክብር መስጠት
+++++++
ማብራሪያ፦
ተውፋንያ ቅዱሱን ቃሬዛ በድፍረት በመንካቱ ተቀጥቷል። ይህ የሚያስተምረን ቤተክርስቲያንን፣ ንዋያተ ቅድሳትንና ቅዱሳንን በሥርዓትና በክብር መያዝ እንዳለብን ነው። ድፍረት በረከትን ያርቃል።

ምሳሌ፦
የሚነድ እሳትን በባዶ እጅ የጨበጠ እንደሚቃጠል፣ ቅዱሳን ነገሮችንም ያለ ፍርሃተ እግዚአብሔር በድፍረት መያዝ በመንፈሳዊ ሕይወት ላይ ጉዳት ያመጣል።

🙏🙏 በፍቅርና በአንድነት መኖር
++±+
ማብራሪያ፦
ሐዋርያት ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች መጥተው በአንድ ልብ ተሰብስበው እናታቸውን አክብረዋል። እኛም በቤተክርስቲያን ውስጥ በዘር፣ በቋንቋና በልዩነት ሳንከፋፈል በፍቅር መኖር ይገባናል። የእመቤታችን በረከት የሚገኘው በአንድነት ባለበት ቦታ ነው።

ምሳሌ፦
የአንድ ሰው ጣቶች ተለያይተው ምንም ዓይነት ከባድ ነገር ማንሳት እንደማይችሉ፣ በአንድነት ሲጨበጡ ግን ኃይል እንደሚኖራቸው ሁሉ፤ ክርስቲያኖችም በአንድነት ሲቆሙ በረከታቸው ይጸናል።

ማጠቃለያ መልእክት፦
==============
አስተርእዮ ማርያም የክብር በዓል ነው። በዚህ ዕለት እመቤታችንን ስናስብ፣ ዕረፍቷን በረከታችን፣ ትንሣኤዋን ተስፋችን፣ አማላጅነቷን ደግሞ መመኪያችን አድርገን በቅድስና ልንመላለስ ይገባል።
"የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም በረከትና ምልጃ ከሁላችን ጋር ይሁን።"

🙏 “ለግሪክ ሰዎችና ላልተማሩም፥ ለጥበበኞችና ለማያስተውሉም ዕዳ አለብኝ፤”
በወንጌል አላፍርምና፤
አስቀድሞ ለአይሁዳዊ ደግሞም
ለግሪክ ሰው፥ ለሚያምኑ ሁሉ
የእግዚአብሔር ኃይል ለማዳን ነውና።
ጻድቅ በእምነት ይኖራል ተብሎ እንደ ተጻፈ የእግዚአብሔር ጽድቅ ከእምነት ወደ እምነት በእርሱ ይገለጣልና። ሮሜ 1÷14

እግዚአብሔር ሆይ የሚሳንህ ነገር የለምና የራቀውን አቅርበህ የረቀቀውን አጉልተህ እየሰማነው ካለነው መርዶና ሰቀቀን ዕረፍተ ሥጋንና ዕረፍተ ነፍስን አትንሣን

ጸልዩ በእንተ ሰላም
ስለ ሰላም እንጸልይ
ስለ ሀገራችን እንጸልይ
ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንጸልይ
በጭንቅ በመከራ ስላሉት እንጸልይ
በረሀብ በስደት ስላሉት እንጸልይ
በጽኑ ሕመም ተይዘው ስለሚሰቃዩት እንጸልይ
ስለ ሃይማኖት መሪዎች አባቶቻችን እንጸልይ
ስለ ሀገር መሪዎች እንጸልይ
የሰላም የምህረት የቸርነት ባለቤት እግዚአብሔር ሰላሙን ምህረቱን ቸርነቱን አይንሳን

አባ አትናቴዎስ ወልደ ጎርጎርዮስ
ዘዝዋይ ገዳም
ጥር 20/5/2018 ✍️
⛪️⛪️⛪️⛪️⛪️⛪️⛪️

Address

8102 Midcrown Drive
San Antonio, TX
78239

Opening Hours

4am - 10pm

Telephone

+12109200871

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Debre Edom St. Mary Ethiopian Orthodox Tewahedo Church posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Place Of Worship

Send a message to Debre Edom St. Mary Ethiopian Orthodox Tewahedo Church:

Share

Category