04/24/2025
ያሁኑ ይባስ!
ሰላም ለመልክእኪ እመልክአ ሐና ወኤልሳቤጥ::
ዘብዑድ ስኑ ወልምላሜሁ ፍሉጥ::
ማርያም ቅድስት ድንግልተ አፍኣ ወውስጥ::
ቤዛ ይኩነኒ ኪዳንኪ በገጸ ፈጣሪ ሥሉጥ::
አመ ወርኀ ነጊድ የሐልቅ ወይጸራዕ ሤጥ::
ነገረ አበዊነ!
የአባቶቻችን ጉዳይ ዝም ብለን ልናየው የሚገባ አይደለም::
ዝም ባልን ቁጥር የእነሱንም የቤተ ክርስቲያኒቱንም ውድቀት እያፋጥን እንደሆነ ይሰማኛል::
ጥቂቱ ለማስታወስ ያህል::
1/ ከቀኖና ውጭ ሁለት ሲኖዶስ ሲያቁዋቁም ዝም አልናቸው ከሐዋርያት ቀኖና ጋር ተቃራኒ የሆነ ሢመት ሲፈጽሙም ዝም አልናቸው እኛም በተለያየ መንገድ ተከፋፍለን አብረን ስናጠፋ ከረምን::
2/ እልሃቸው በረድ ሲልላቸው ታረቅን አሉ ስለተጣሰው ቀኖና ምንም ማብራሪያ ሳይሰጡ ተቀላቀሉ ዝም አልን::
3/ በየመንደሩ የከብረውን ሢመተ ክህነት ሲያዋርዱ ዓለም ዐቀፍ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያን የመንደር ሲያደርጉአት ዝም አልን:: ይሄ ጉዳይ እንደ ቀላል የምናልፈው መሆን የለበትም ለምሳሌ: የኦሮሚያ የትግራይ የቅባት ጳጳሳት ነን ባዮች በሀገራችን እንደ ልባቸው እየተንቀሳቀሱ እሱዋ ያልተነሳች ልታቁዋቁም መጣች እንዲሉ አበው በሌላቸው ክህነት ክህነት እንሰጣለን እያሉ በቤተ ክርስቲያን ላይ ሲቀልዱ ዝም አልን::
4/ አጥማቂ ነን የሚሉ መጥቁሎችን ባደባባይ እያሞገሱ ቤተ ክርስቲያንን የሲሞናውያን መቀለጃ ሲያደርጉአት ዝም አልን::
5/ በኛ ዝምታ ራሳቸውን እንደፈጣሪ ከቆጠሩት (አነ ፈጠርኩክሙ) ለማለት በዝግጅት ላይ ያሉት አባቶቻችን ምን ታመጣላችሁ በሚመስል መልኩ ትምህርተ ኑፋቄን በአደባባይ የቤተ ክርስቲኒቱ መሠረት የሆነው ነገረ ትስብእትንና ነገረ ማርያምን መናድ ጀመሩ:: በኛ ቤተ ክርስቲያን ካልገባን ከመምህራን ይጠየቃል ከመምህራን መልስ ካልተገኘም ሱባኤ ይያዝበታል እንጂ ብድግ ብሎ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት የተደረሱትን ከዚያም አልፎ የዘወትር ሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ የሆኑትን መጻሕፍት ብድግ ብሎ ትክክል አይደሉም ማለት ከስህተትም በላይ ስህተት ነው:: መረጋጋት ማንን ገደለ የሆነ ትምህርት ተምረዋል ማለት ጠቅላላ የቤተ ክርስቲያኒቱን ዕውቀት ጠንቅቀዋል ማለት አይደለም:: ይህን ሁሉ ያመጣው ግን የኛ ዝምታ ነው አንድ የቀረችን ሃይማኖታችን ናት ዝም ብለን አባቶች ያሉትን ነው የምንቀበል እያልን የመጨረሻ መጠጊያችን አፍርሰው መጠለያ እንዳያሳጡት በጊዜ እባካችሁ ተውን ልንላቸው ይገባል:: ይተው አንጅ! እመቤታችንማ ቤዛችን ናት ቅዱሳንማ ቤዛዎቻችን ናቸው ቤዛ ሲያሳጡን ለምን አንደነግጥም?
እጅግ የሚያሳዝነው የስቅለት ዕለት ሕዝበ ክርስቲያኑ ሁሉ በተመስጦ በሚውልበት ቀን መሆኑ ነው:: ለመሆኑ የስቅለት ቀን በአዳራሽ ጉባኤ የሚደረገው በምን ምክንያት ነው? በሀገራችን ስቅለት ብሔራዊ በዓል ስለሆነ ሥራ ዝግ ነው ያ ሁሉ ሕዝብ ቤተ ክርስቲያን መዋል ሲገባው እንዴት እዚያ ተገኘ? ይሄ ራሱ ሌላ ስህተት አይደለም ወይ?
ምንተ ንግበር ሊቃውንት ካህናት ዲያቆናት ምእመናን ወምእመናት! አሁንም ዝም እንበል?
መልሱን ለእናንተ እተዋለሁ!!