31/05/2026
ርደተ መንፈስ ቅዱስ ወይንም የመንፈስ ቅዱስ መውረድ በብሉይ ኪዳን በትንቢት የተነገረና በሐዲስ ኪዳን የተፈጸመ ነው፡፡ ነቢዩ ኢዮኤል ስለ መንፈስ ቅዱስ ወደዚህ ዓለም መውረድ፣ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋና ሀብትነት ዓለም እንደሚታነጽና ሃይማኖት እንደሚጸና እንዲህ ሲል ተናግሯል፤ ‹‹ከዚህም በኋላ እንዲህ ይሆናል፤ መንፈሴን በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ አፈሳለሁ፡፡›› (ኢዩ. ፪፥፳፰)
👉በሉቃስ ወንጌል እንደተጻፈው ደግሞ ጌታችን ኢየሱስ ድኅነተ ዓለምን ፈጽሞ ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በ፵ኛው ቀን ወደ ሰማየ ሰማያት በሚያርግበት ጊዜ ደቀ መዛሙርቱን ይዞ ወደ ቢታንያ ከወጣ በኋላ በተስፋ እንዲጠብቁና ከሰማይ የሚወርደውን መንፈስ ቅዱስ እስከሚጎናጸፉ ድረስ የእግዚአብሔርን ትእዛዛ እንዲጠበቁ እንዲህ ሲል አዘዛቸው፤ ‹‹እነሆ፥ እኔ የአባቴን ተስፋ ለእናንተ እልካለሁ፤ እናንተ ግን ከአርያም ኃይልን እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ተቀመጡ፡፡›› ከዚህም መመሪያ በመነሣት አባቶቻችን የአምላካቸውን ትእዛዝ አክባሪዎችና ጠባቂዎች በመሆናቸው ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሰው በቤተ መቅደስ እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ቆዩ፡፡ (ሉቃ. ፳፬፥፵፱)
👉ከዚህም በኋላ ዓለምን ዞረው በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በሁሉም ቋንቋ ተናገሩ፤ አስተማሩም፡፡ ‹‹ኀምሳው ቀንም በተፈጸመ ጊዜ ሁሉም በአንድነት በአንድ ቦታ ተሰብስበው ነበር፡፡ ድንገትም እንደ ዐውሎ ነፋስ ድምፅ ያለ ከሰማይ ድምፅ መጣ፤ የነበሩትንም ቤት ሞላው፡፡ እንደ እሳት የተከፋፈሉ የእሳት ላንቃዎችም ታዩአቸው፤ በሁሉም ላይ ተቀመጡባቸው፡፡ ሁሉም መንፈስ ቅዱስን ተሞሉ፤ ይናገሩ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እንደ አደላቸው መጠንም እየራሳቸው በሀገር ሁሉ ቋንቋ ይናገሩ ጀመር›› እንዲል፤ (ሐዋ. ፪፥፩-፬)
👉ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም ስለ ወረደው መንፈስ ቅዱስ አምስት መሠረታዊ ትርጓሜ እንዳሉት ያስተምራሉ፡፡ እነርሱም፤
፩ኛ. መንፈስ ቅዱስ ናዛዚ ነው፤ ትርጓሜውም አረጋጊ ወይንም የሚያረጋጋ ማለት ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያልተረጋጉትን ያረጋጋልና፤ ወንጌል ሲሰበክ የእግዚአብሔር ቃል በመሆኑ ሰዎችን ወይንም ምእመናን የሚያረጋጋ ኃይል ነው፡፡
፪ኛ. መንፈስ ቅዱስ መጽንዒ ወይም የሚያጸና ነው፤ በተለያዩ ዘመናት የተነሡ ነቢያት፣ ቅዱሳን አባቶችና ሐዋርያት እንዲሁም ጻድቃን ሰማዕታትም ሰይፉና ስለቱን የታገሡት፣ መከራና ሥቃዩን የቻሉትና መስቀሉን የተሸከሙት አጽናኒው መንፈስ ቅዱስ በውስጣቸው ስላደረባቸው ነው፡፡
፫ኛ. መንፈስ ቅዱስ መንጽሒ ወይም የሚያነፃ ነው፤ የሰዎችን ኃጢአት የሚያስወግድ፣ ከእድፋችን የሚያነጻ፣ ሰውነትን ለእግዚአብሔር ማደሪያ የሚያዘጋጅ ነው፡፡
፬ኛ. መንፈስ ቅዱስ ከሳቲ ወይም ምሥጢር የሚገልጽ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን ነቢዩ ሙሴና ዕዝራን ስንመለከት እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በየዘመናቱና በየደረጃው ምሥጢራትን እየገለጸላቸው መጻሕፍትን ጽፈዋል፡፡
፭ኛ. መንፈስ ቅዱስ መስተፍስሒ ወይም የሚያስደስት ነው፤ ያዘኑ ሰዎችን ከኀዘን ያወጣል፤ ኀዘናቸውንም ወደ ደስታ ይቀይራል፤ ሐዋርያት በተዘጋ ቤት ተቀምጠው ያዝኑ ነበር፤ ጌታችን ወደ ሰማይ ባረገ ሰዓት ግን አጽናንቷቸዋል፡፡ ‹‹እስከ ዓለም ፍጻሜ በዘመኑ ሁሉ ከእናንተ ጋር እኖራለሁ›› እንዲል፤ ምክንያቱም የማይለይ የመንፈስ ቅዱስን ኃይል ሰጥቷቸዋልና ለዘለዓለም ከእነርሱ ጋር ይኖራል፡፡ (ማቴ. ፳፰፥፳)
እንኳን አደረሳችሁ!
ቤተሰብ እንሁን ለሌሎችም እናጋራ
🔎ዩቱዩብ ቻናል፦https://youtube.com/channel/UCez7ZZH--fX056XMW64P2CA
🔎 ፌስቡክ ገጽ፦ https://www.facebook.com/Nairobi-Meserete-Haimanot-Sunday...
🔎 ቴሌግራም ቻናል፦ https://t.me/MesreteHaimanot27