18/06/2020
[ፈጥኖ የሚረዳን የቅዱስ ሚካኤል ክብር በሊቁ በቅዱስ ያሬድ ድጓ]
✍ [በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ]
❖♥ የ99ኙ ነገደ መላእክት አለቃ ስለኾነው ስለ ቅዱስ ሚካኤል ክብር፣ ውበት፣ ምልጃ ማሕቶተ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ያሬድ በመጽሐፈ ድጓው እንዲኽ ይላል፡-
╬ “ክብረ ሚካኤል ናሁ ተዐውቀ
በትሕትናሁ ዐብየ ወልሕቀ
ዲበ አእላፍ ዘተሰምየ ሊቀ
ዘይትዐፀፍ መብረቀ ይተነብል ጽድቀ”
(የሚካኤል ክብረ እነሆ አኹን ታወቀ፤ በትሕናውም ፈጽሞ ላቀ ከፍ ከፍ አለ፤ በአእላፍ ነገደ መላእክት ላይ አለቃን የተባለ መብረቅን የሚጐናፀፍ ርሱ ጽድቅን ይለምናል) ይላል፡-
❖♥ የ99ኙ ነገደ መላእክት አለቃ ከመኾኑ ጋር ይልቁኑ ዮሐንስ በራእዩ በምዕ 8፡2 ላይ “በእግዚአብሔርም ፊት የሚቆሙትን ሰባቱን መላእክት አየሁ” ካላቸው፤ ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት በመዠመሪያ የሚጠቀሰው ቅዱስ ሚካኤል ነውና ሊቁ ያሬድ፡-
╬ ♥ “እስመ እምአፉሁ ይወጽዕ ነጐድጓድ
ሕብረ ክነፊሁ ያንበለብል ነድ
እምሊቃነ መላእክት የዐቢ በዐውድ
ሚካኤል ውእቱ መልአኩ ለወልድ”
(የወልድ አገልጋዩ ሚካኤል ነው፤ በዙሪያው ኹሉ ካሉት ከሊቃነ መላእክት ይበልጣል፤ የክንፉ መልክ ነባልባላዊ እሳትን ያቃጥላል፤ ከአንደበቱ ነጐድጓድ ይወጣልና) ይላል፨
╬ ♥“አዕበዮ ንጉሠ ስብሐት
ለሚካኤል ሊቀ መላእክት
ዘይስእል በእንተ ምሕረት
መልአከ ሥረዊሆሙ ለመላእክት”
(የምስጋና ባለቤት ክርስቶስ ለመላእክት ጭፍሮች አለቃቸው የኾነ ስለ ምሕረት የሚማልድ የመላእክት አለቃ ሚካኤልን ከፍ ከፍ አደረገው) በማለት ይጠቅሰዋል፡፡
❖♥ የስሙ ትርጓሜንም ስንመለከት ሚካኤል ማለት ቃሉ የዕብራይስጥ ሲኾን ሚ- ማለት “ማን”፤ ካ- “እንደ”፤ ኤል- “አምላክ” ማለት ነውና ሚካኤል ማለት “መኑ ከመ አምላክ” (ማን እንደ አምላክ) ማለት ነው፡፡
❖♥ የመልክአ ሚካኤል ደራሲም ይኽነን ይዞ
╬ “ሰላም ለዝክረ ስምከ ምስለ ስመ ልዑል ዘተሳተፈ
ወልደ ያሬድ ሄኖክ በከመ ጸሐፈ”
(የያሬድ ልጅ ሄኖክ እንደጻፈው ከልዑል ስም ጋር ለተባበረ ስም አጠራርኽ ሰላምታ ይገባል) ይለዋል፡፡
ቅዱስ ያሬድም፡-
╬ “መልአከ ፍሥሐ ሚካኤል ስሙ
ለመላእክት ውእቱ ሊቆሙ
መልአኮሙ ሥዩሞሙ
የሐውር ቅድሜሆሙ እንዘ ይመርሆሙ”
(ስሙ ሚካኤል የተባለ የደስታ መልአክ ለነገደ መላእክት አለቃቸው ነው፤ የተሾመላቸው አለቃቸው ርሱ እየመራቸው በፊት በፊታቸው ይኼዳል) ይላል
❖♥ በብሉይ ኪዳን ለአበው ነቢያት እየተገለጠ፤ ለሐዋርያትም በስብከት አገልግሎታቸው እየተራዳ፤ ለሰማዕታት፣ ለቅዱሳን አበው በተጋድሏቸው እየተገለጠላቸው አስደሳች መልኩን ያዩት ነበር።
❖♥ ይኽነን የቅዱስ ሚካኤልን ውበት ቅዱስ ያሬድ እንዲኽ ይገልጠዋል፡-
╬ “መልአከ ፍሥሐ ዘዐጽፉ መብረቅ
ሐመልማለ ወርቅ ሚካኤል ሊቅ”
(መጐናጸፊያው መብረቅ የኾነ የደስታ መልአክ፤ አለቃ ሚካኤል የወርቅ ዐመልማሎ ነው)
❖♥ የመልክአ ሚካኤል ደራሲም ይኽነን ውበቱን ሲገልጠው፡-
╬ “ሰላም ለአክናፊከ እለ በሰማያት ያንበለብሉ
ከመ ሠርቀ ፀሓይ ሥነ ጸዳሉ”
(የጸዳሉ ውበት እንደ ፀሓይ አወጣጥ የኾነ በሰማያት ለሚያንበለብሉ ክንፎችኽ ሰላምታ ይገባል) ይለዋል፡፡
❖♥ ቅዱስ ያሬድ ደግሞ፡-
╬ “ውእቱ ሊቆሙ ወመልአኮሙ ሚካኤል ስሙ
ዐይኑ ዘርግብ ልብሱ ዘመብረቅ
ሐመልማለ ወርቅ”
(ዐይኑ የርግብ (እንደ ርግብ የዋህ፣ ጽሩይ) የኾነ ልብሱ የመብረቅ መጐናጸፊያ የኾነለት የወርቅ ዐመልማሎ ስሙ ሚካኤል የተባለ ርሱ የመላእክት አለቃቸው መሪያቸው ነው) ይላል፡፡
❖♥ የቅዱስ ሚካኤል ተራዳኢነትና አማላጅነት ቅዱስ ያሬድ እንዲኽ ይገልጠዋል፡-
╬ በ፲ወ፬ቱ ትንብልናከ ዐቢይ ልዕልናከ
በመንክር ትሕትናከ
አስተምህር ለነ ሰአልናከ”
(በዐሥራ አራቱ ልመናኽ ምልጃኽ፤ በታላቅ ልዕልናኽ በሚያስደንቅም ትሕትናኽ ሚካኤል ትለምንልን ዘንድ ማለድንኽ)
╬ “ዘወሀበ ትንቢተ ለኤልዳድ ወሙዳድ
አመ ምጽአቱ ይምሐረነ ወልድ
ሰአል ለነ ሚካኤል መንፈሳዊ ነገድ
ከመ ንክሃል አምስጦ እምሲኦል ሞገድ”
(ለኤልዳድና ለሙዳድ የትንቢትን ጸጋ የሰጠ የሚኾን ወልድ በሚመጣ ጊዜ ይምረን ዘንድ ከረቂቅ ነገድ ወገን የኾንኸው ሚካኤል ከሲኦል እሳታዊ ሞገድ ማምለጥ እንችል ዘንድ ለእኛ ለምንልን) ይላል፡፡
╬ “ከናፍሪሁ ነድ ዘእሳት አልባሲሁ ዘመብረቅ ሚካኤል ሊቀ መላእክት ውእቱ ይዕቀብክሙ ነግሀ ወሠርከ ሌሊተ ወመዐልተ”
(ከናፍሮቹ የእሳት ልብሶቹ የመብረቅ የኾነ የመላእክት አለቃ ሚካኤል በተራኢነቱ በጠዋትም፤ በሠርክም፤ በቀንም በሌሊትም ይጠብቃችኊ) አለ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ፨
❤ ቅዱሳን መላእክት ሰው የጸለየውን ጸሎት ያቀረበውን መሥዋዕት ቅድመ እግዚአብሔር በማድረስ የእግዚአብሔርን ምሕረት ወደ ሰው በማምጣት ሰውን ከአምላካቸው ጋር በማማለድ ጸንተው ያሉ እንደኾኑ በብዙ ሥፍራ ላይ ተዘርዝሯል፡-
✍️ ለምሳሌ ያኽል ዘፍ 48፥15፤ ዘጸ 23፥20፤ መሳ 6፥11፤ ኢዮ 33፥23፤ መዝ 33፥7፤ 88፥6፤ 90፥11፤ 1ነገ 19፥5፤ 2ነገ 6፥15፤ ዳን 3፥17፤ 4፥13፤ 8፥15-19፤ ዘካ 1፥12፤ ማቴ 18፥10፤ ሉቃ 1፥19፤ 13፥6-9፤ 15፥7፤ ዮሐ 20፥11፤ የሐዋ 12፥6፤ ዕብ 1፥14፤ ራእ 8፥3-4ን ይመልከቱ)፡፡
❤ የቅዱስ ሚካኤል በረከት ይደርብን።
[በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ] [በድጋሚ የተለጠፈ]