29/04/2026
ዑራኤል ማለት ትርጉሙ «የብርሃን ጌታ» «የአምላክ ብርሃን » ማለት ነው። ኢዮር፣ ራማ እና ኤረር የተባሉ ሦስት የመላእክት ከተሞች አሉ፡፡ እግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክትን ከፈጠራቸው በኋላ በነገድ 100 በአለቃ 10 አድርጎ በሦስቱ ሰማያት አስፍሯቸዋል፡፡ ኢዮርን በ4፣ ራማን በ3፣ ኤረርንም በ3 ከፍሎ ነው በዓሥሩ ከተማ ያሰፈራቸው፡፡
በዚህም መሠረት ኢዮርን ላይና ታች አድርጎ በ4 ከተማ ከፍሏታል፡፡ በእርሷ ያሉትን መላእክትን በ40 ነገድ 4 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያው ነገድ ‹‹አጋእዝት›› ይባላሉ፡፡ አለቃቸው ሣጥናኤል ነበር፤ እርሱም የመላእክትን ሁሉ ጸሎት ወደ እግዚአብሔር ያሳርግ ነበር፡፡ ከክብሩ ሲዋረድ ቅዱስ ሚካኤል በምትኩ ተሹሞበታል፡፡ ሁለተኛው ነገድ ‹‹ኪሩቤል›› ይባላሉ፡፡ እነርሱም መንበረ ሥላሴን ይሸከማሉ፡፡ የቀሳውስት አምሳል ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ሰብና ገጸ አንበሳ ናቸው፡፡ በሦስተኛው ከተማ በኢዮር ያሉት ሱራፌል ይባላሉ፡፡ የዲያቆናት አምሳል ናቸው፡፡ በትንቢተ ኢሳይያስ በምዕራፍ 6 ላይ የተገለጹትና ኢሳያስን ከለምጹ እንዲፈወስ ያደረጉት ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ላህምና ገጸ ንስር ናቸው፡፡
(በነገራችን ላይ ‹‹ከሩቤል›› ወይም ‹‹ሱራፌል›› የሚባሉ የግለሰብ መጠሪያ ስሞች ስህተት ናቸው፡፡ አንደኛ እነዚህ ስሞች የብዙ መላእክት መጠሪያን የሚወክሉ ናቸው፡፡ ለአንዱ ሲሆን ‹‹ኪሩብ፣ ሱራፊ›› ይባላል፡፡ ‹ኪሩቤል› ወይም ‹ሱራፌል› ማለት ግን የብዙ ቁጥራቸው መጠሪያ ነው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የቅዱሳን መላእክትን ስም እንዳለ በቁሙ ወስዶ ለግል መጠሪያ ስም ማዋል ተገቢ አይደለም፡፡ ‹‹ወለተ ሚካኤል፣ ክብፈ ገብርኤል….›› እየተባሉ ይሰየማሉ እንጂ ቀጥታ ‹ሚካኤል›፣ ‹ገብርኤል› እያሉ ሰዎችን መሰየም ስህተት ነው፡፡ 4ኛው ከተማ በኢዮር ያሉት ኃይላት ይባላሉ፡፡ የእሳት ሰይፍ ይዘው በሥሉስ ቅዱስ ፊት የሚቆሙ ናቸው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት የዛሉና የደከሙ ክርስቲያኖችን የሚያበረታቱ ናቸው፡፡ አለቃቸውም ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡)
ዳግመኛም እግዚአብሔር በራማ ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ‹‹አርባብ›› ይባላሉ፡፡ የሥላሴ እልፍኝ አስከልካዮች ናቸው፡፡ የእግዚአብሔርን መንበር በክንፎቻቸው ይሸፍናሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ ሁለተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት ‹‹መናብርት›› ይባላሉ፡፡ ለእግዚአብሔርን እጅግ ቅርብ የሆኑ ናቸው፡፡ የመብረቅ ጋሻቸውን የእሳት ጦራቸውን ይዘው የሥላሴ ጋሻ ጃግሬዎች ሆነው በተጠንቀቅ ይቆማሉ፡፡ የሰውን ችግር ለእግዚአብሔር ያቀርባሉ፡፡ መዝ 88፡6፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡
ሦስተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት ‹‹ሥልጣናት›› ይባላሉ፡፡ መላውን ፍጥረት ለመጠበቅ ሥልጣን የተሰጣቸውና የምጽአት ዕለት አዋጅ ነጋሪዎች ናቸው፡፡ ዳን 12፡1፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሱርያል ነው፡፡
ዳግመኛም እግዚአብሔር በኤረር ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ‹‹መኳንንት›› ይባላሉ፡፡ የሥላሴ የእሳት ባለ ቀስት ናቸው፡፡ የሰው ልጅ ልዩ ጠባቂዎች ናቸው፤ በተለይ በአደጋ ጊዜ ሎጥን እንዳዳኑት ፈጥነው ይደርሳሉ፡፡ በዕለተ ምጽዓት የሰውን ሁሉ ዐፅም ሰብስበው ለትንሣኤ ዘጉባኤ ያበቃሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሰዳካኤል ነው፡፡ ሁለተኛዎቹ ‹‹ሊቃናት›› ይባላሉ፡፡ የሥላሴ የእሳት ፈረሶች ናቸው፡፡ በእሳት ፈረስ ይመላለሳሉ፡፡ እነዚህም 24ቱ ካህናተ ሰማይ ሲሆኑ አለቃቸው ቅዱስ ሰላታኤል ነው፡፡
በኤረር ከተማ የሰፈሩት ሦስተኛዎቹ ‹‹መላእክት›› ይባላሉ፡፡ ፍጥረትን ሁሉ የሚጠብቁ ናቸው፡፡ አለቃቸው ቅዱስ አናንኤል ነው፡፡ በእነዚህ የማይጠበቅ ፍጥረት የለም፡፡ ከአዝርእት ጀምሮ ሁሉን ይጠብቃሉ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ ‹‹በእግዚአብሔር ፊት የሚቆሙ 7 መላእክትን አየሁ›› (ራዕ 8፡2) እንዳለ ሊቃነ መላእክት በቁጥር 7 ናቸው፡፡ እነርሱም፡- ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ገብርኤል፣ ቅዱስ ሩፋኤል፣ ቅዱስ ራጉኤል፣ ቅዱስ ዑራኤል፣ ቅዱስ ፋኑኤል እና ቅዱስ አፍኒን ናቸው፡፡
‹‹ዑራኤል›› የሚለው ስም ‹ዑር› እና ‹ኤል› ከሚሉ ሁለት ቃላት የተመሠረተ ስም ነው፡፡ ‹‹ዑራኤል›› ማለት ትርጉሙ ‹‹የብርሃን ጌታ፣ የአምላክ ብርሃን›› ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዑራኤል ከ7ቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሲሆን ከፍጥረተ ዓለም ጀምሮ በመብረቅና በነጎድጓድ ላይ የተሾመ መልአክ ነው፡፡ በመሆኑም መጽሐፈ ሄኖክ እንደሚገልጸው መባርቅት ለጥጋብና ለበረከት እንዲበርቁ ነጎድጓድም ለሰላም እንዲሆን ያሰማራል፡፡ ምሥጢረ ሰማይንና ሰማያዊውን ዕውቀት ሁሉ ለሄኖክ የገለጸለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ የፀሐይን፣ የጨረቃን፣ የከዋክብትንና የሰማይ ሠራዊትን ብርሃንን የሚመራው ይኸው ገናና መልአክ ነው፡፡ መጽሐፈ ሄኖክ 28፡13፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ ሆኖ በተሰቀለ ጊዜ ክቡር ደሙን በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ በብርሃነ መነሳንስ በዓለም ላይ የረጨው ይኸው ገናና መልአክ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ዕውቀት ተሠውሮበት ለነበረው ለኢትዮጵያዊው ሊቅ ለአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም በእመቤታችን ትእዛዝ ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ‹‹ዑራኤል የተባለ መልአክ ሊረዳኝ መጣ፡፡›› መጽሐፈ ዕዝራ 2፡1፡፡ አምላካችን እግዚአብሔር የሕይወትና የይቅርታ ዝናም በምድራችን ላይ ያዘንብ ዘንድ እንዲሁም የእርሻችንን አዝመራ በዝናም አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ ለምግብነት እንዲበቃ ከፈጣሪ ዘንድ ምሕረትን የሚለምን መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
ሊቁ አባ ጊዮርጊስም በመልአኩ አማላጂነት እጅግ ብዙ ድርሰቶችን የደረሱት መልአኩ ጽዋ ሕይወትን ካጠጣቸው በኋላ ነው፡፡ በመጀመሪያም አባ ጊዮርጊስ የተወለዱት በቅዱስ ዑራኤል አብሳሪነት ነው፡፡ በቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ የተመሠረቱ አብዛኞቹ ቅዱሳት ገዳማት በቅዱስ ዑራኤል መሪነት ነው፡፡ ድርሳኑ ላይ የማይጠቅሳቸው የሀገራችን የከበሩ ቅዱሳት ገዳማትና ቅዱሳን ነገሥታት የሉም፡፡
የብርሃን እናቱ ድንግል ወላዲተ አምላክን ከልጇ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ስትሰደድ መንገድ እየመራ ወደ ግብጽ እና ወደ አገራችን ኢትዮጵያ ያመጣቸው ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ እመቤታችንን ከተወደደ ልጇ ጋር በደመና ጭኖ መላ ኢትዮጵያን ካስጎበኛት በኋላ ቅድስት አገራችንን ለእመቤታችን የዓሥራት አገር እንድትሆን ያደረገው መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል በዓመት 3 ዓበይት በዓላት አሉት፡፡ ጥር 22 በዓለ ሲመቱ ነው፡፡ መጋቢት 27 የጌታችንን ክቡር የሆነ ወርቀ ደሙን ለዓለም የረጨበት ነው፡፡ ሐምሌ 22 ቀን ቅዳሴ ቤቱ የሚከበርበትና ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል የዕውቀትን ጽዋ ያጠጣበት ዕለት ነው፡፡
የሊቀ መላእክት የቅዱስ ዑራኤል ጥበቃው አይለየን! በጸሎቱ ይማረን
እና
፡-
ቅዱስ ዑራኤል ለነቢዩ ዕዝራ ጽዋዓ ልቡና ያጠጣዉ ጥበብና ማስተዋልን የሰጠዉ የጠፉትን ቅዱሳት መጻህፍትን በቃሉ አጥንቶ እንደገና እንዲጽፋቸዉ የረዳዉ መልአክ ነዉ
( ) ቅዱስ ዑራኤል ቅድስት ማርያም ልጅዋን ህጻኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ይዛ ለስደት በተነሳች ጊዜ ከምድረ እስራኤል ወደግብጽ ከዚያም ወደ ቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያ እየመራ ያመጣት መልአክ ነው።
( )
ለዕዝራ ሱቱኤል፤ ለቅዱስ ያሬድ፤ ለአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እና ለሌሎችም ቅዱሳን ጽዋ ልቦና አጠጥቷቸዋል፡፡ ወደ ሔኖክም እየመጣ የተሰወሩትን ምስጢር እና ያያቸውን ራእዮች ይተረጉምለት ነበር፡፡ በድርሳኑ እንደ ተገለጸው በረዳትነቱ በአማላጅነቱ ብዙ ደጋጎችን ረድቷል፡፡
የክርስቶስንም ደም በብርሃን ጽዋዕ ተቀብሎ የኢትያጵያን ምድር የረጨ ሲኾን ሥላሴን በቅዳሴ በውዳሴ ከሚያመሰግኑና ለሰው ልጆች ለምሕረት ለብሥራት ከሚላኩ መላእክት አንዱ ነው፡፡
ያደረገው ተአምር ይህ ነው። ዘወትር ሌት ከቀን የሚጮህ ጋኔን የሚጥለው በሲዶና አገር የሚኖር አንድ ሰው ነበር፡፡ በዚችው አገር ውስጥ የይቅርታ የምሕረት መላአክ የሆነ የመላእክት አለቃ በቅዱስ ዑራኤል ስም የተሠራች ቤተ ክርስቲያን ነበረች፡፡
ይህ ሰው የመላእክት አለቃ በሆነ በቅዱስ ዑራኤል በዓል ጥር 22 ቀን ካህናት በማኅሌት ጊዜ በፍቅርና በሰላም ሲዘምሩና ሲያሸበሽቡ ሳለ ከዚችው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ገባ፡፡ ያን ጊዜ በዉስጧ ቀይ ሰው መልኩ ከደም ግባቱ ጋር እጅግ ያማረ ከሰው ሁሉ ይልቅ የሚበልጥ በመካከላቸው ቁሞ ከእያንዳንዱ ፊት የሚወርደው ላብ በመሐረም ሲጠርግ አየ፡፡ ያን ጊዜ ከእግሩ በታች ተንፈራገጠ ጋኔኑም ጥቁር ከላዩ የእንጨት ቅርፊትን የመሰለ ሁኖ ወጣ፡፡
ጋኔኑም እሱን ትቶ ሸሸ ዑራኤልም ሽሽቱን አይቶ ፈጥነህ ወደኔ ና ቢለው ፈርቶ ሽሽቱን ቀጠለ ያን ጊዜ አንገቱን አንቆ በያዘው በትር መስቀል ስለደበደበው ጩኾ አለቀሰ፡፡
መልአኩም ሁለተኛ ታሠቃየው ዘንድ ወደዚህ ሰው ትመለሳለህን? ቢለው ከእንግዲህስ ወዲህ ወደሱ ብመለስ የአምላክህ መለኮታዊ ሰይፍ ከሁለት ይከፋፍለኝ ሲል በፊቱ ማለና እንዲሄድ ለቀቀው፡፡ ያም ሰው ያየውንና የሰማውን ሁሉ ለሰዎች ተናገረ፡፡ ያዩና የሰሙ ሰዎች ሁሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑ የቅዱስ ዑራኤልንም ተአምራት አደነቁ፡፡
ለእግዚአብሔርና ለእናቱ ለድንግል ማርያም ምሥጋና ይሁን ለኛም ምሕረትና ይቅርታ ይደረግልን፡፡
የመላእክት አለቃ የሆነ የቅዱስ ዑራኤል ረድኤቱ እና ልመናው ከመላው ህዝበ ክርስቲያኑ ጋር ይሁን፡፡ አሜን።
የበዓሉ መታሰቢያ ኅዳር 21 ለእዝራ ሱቱኤል ጽዋ ልቦና ያጠጣበት፡፡ ቀን በዓለ ሢመቱ። ቀን ከፈጣሪው ቃል ኪዳን የተቀበለበት፡፡
ዑራኤል ድንግል ማርያም በአካለ ሥጋ እያለች ወደ ሰማይ አሳርጓታል፡፡
ዑራኤል እመብርሃን በስደቷ ጊዜ ወደ ኢትዮጵያ መርቶ አምጥቷታል፡፡
ዑራኤል ሆይ ይህች የበዓለ ሢመት ዕለት የተመረጠች እለት ናት፡፡ ከድንግል እረፍት በኃላ ቃል ኪዳን የተቀበልክባት ቀን ናት፡፡
ዑራኤል ሆይ በምእመን መስቀል ላይ የተሾምክ ታማኝ አገልጋይ ካሕን ነህና አሳሳች ከሚሆን ከሰይጣን አገዛዝ ነፃ አውጥተህ ማኅበራዊ አንድነታችንን ለሁል ጊዜ ጠብቅ የሃይማኖት ጥመኞችንም ታጠጣ ዘንድ የእጅህን ጽዋ ላክልን፡፡
ዑራኤል ሆይ ለነበልባላዊ አካለ ቆምህና ለእሳታዊ ሥነ መልክእህ ሰላም እላለሁ፡፡ ዑራኤል ሆይ ለዕዝራ ሱቱኤል ምሥጢር የሚገልጽ ትንቢትን የሚያናግር ጽዋ ልቡናን ለመጋት እንደ ተቻኮልክ ሁሉ በውስጥ በአፍአ የከበርክ መልአክ ነህና የአንደበቴን ምስጋና ለመቀበል ፈቃደኛ በመሆን ከኅዘኔ ታረጋጋኝ ዘንድ በሩጫ በችኮላ ፈጥነህ ወደኔ ና፡፡
ከመዓርና ከወተት ይልቅ ለሚጥመው ሰም አጠራርህ ሰላም እላለሁ፡፡
ዑራኤል ሆይ ክፍልህ በደመ ወልደ እግዚአብሔር የተነከረ የታለለ ነውና ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ትሆን ዘንድ ግሩም የሚሆን እግዚአብሔር ሥልጣን በክብር ከፍ ከፍ አደረገህ፡፡
ዑራኤል ሆይ ችግረኞችን ለሚመለከቱ ዓይኖችህና የቅዱሳን ጸሎት ሰምተው ወደ እግዚአብሔር ለሚያቀርቡ አዕዛኖችህ ሰላም እላለሁ፡፡
ዑራኤል ሆይ ቀይሓን እሳታውያን ለሆኑ ጉንጮችህና ከዚያ ዓለም ሽቶ ልዩ መዓዛ ላላቸው አእናፎችህም ሰላም እላለሁ፡፡
Follow 👉👉 ኦርቶዶክስ ተዋህዶ Orthodox Tewahdo