የእውነት ቃል መስካሪ

የእውነት ቃል መስካሪ We Preach and Teach the Gospel of Jesus Christ!
እውነትን ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል።

01/11/2024

ኢየሱስም እንዲህ አላቸው ፦ "እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደኔ ኑ ፤ እኔም አሳርፋችኀለሁ፡፡ ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ፤ ከእኔም ተማሩ፤ እኔም የዋህ ፥ በልቤም ትሑት ነኝና ለነፍሳችሁ ዕረፍትን ታገኛላችሁ፡፡ ቀንበሬ ልዝብ፣ ሸክሜም ቀሊል ነውና ፡፡"
ሄሎ ወዳጆቼ፦ እዚህ ጋር ኢየሱስ
እያለ ያለው "ማንም ሸክም የከበደ ቢኖር ወደኔ ይምጣና ይረፍ ፤ ልብ በለኝ ወገኔ ሸክም ከጫንቃህ ሳይወረድ ማረፍ የለም፡፡ ማንም የሒወትን ወይንም የነፍስን ሸክም ከኢየሱስ ውጭ በራሱ ሊያወርደው አይችልም፡፡ በራሱ የሞከረ ሲታገል ኖሮ ሳያርፍ ወደሲዖል ያመራል፡፡ ድምፁን ሰምቶ አምኖ ወደኢየሱስ የመጣ ግን እሱ ታደለ፤ ከመከራም ሥጋት ሁሉ ያርፋል፡፡ ወዳጄ ክርስትና ከማረፍ ነው እሚጀምረው፡፡ ከዚያም አርፈህ በጎልጎታ ላይ ተጨርሶ የቀለለውን ቀንበሩን ተሸክመህ የለዘበውን [የአማረውን] ሸክም ትቀዳጃለህ እንጂ አዲስን ፍልሚያ ሊያጋፍጥህ አይደለም ወደኔ ና ያለህ፡፡ ሲጠራህ እራሱን ተማምኖ መሆኑን ላፍታም አትዘንጋ! ከአመንክ ትከተለዋህ እርሱ በሰበረው ስብርባሪው፣ ባፈረሰውም ፍርስራሹ ላይ ቆመህ ድልን ትጎናፀፋለህ፡፡ አሁንም ላሹፍህ፦ እኔ የዋህ ነኝ ሲልህ አስተውል---- ይህን ዓለም ኢየሱስ የአንበረከከው ሲመቱት ባ ብሎ ሳይሆን ዝም የሚል በሸማቾቹም ፊት ሊታረድ ሲነዳ እያወቀ ዝም የሚል የእግዚአብሔር በግ ሆኖ እንጂ የሰማይ የምድር ንጉስ አንበሣው እኔ ነኝና ይታወቅልኝ ብሎ አግሥቶ አይደለም ፤ ፍቅሩን በተግባር ከውኖት እንጂ፡፡ ትሁት ነኝ ከኔም ተማር ሲልህ፦ የመናገር አባዜ ኖሮት ሳይሆን ኖሮ መናገርን ተናግሮ መኖርን ስላወቀበት ነው፡፡ እይ፦ እንደባሪያ እራሱን ዝቅ አድርጎ ጌታቸው የነበረ ኢየሱስ የደቀ መዛሙርቱን እግራቸውን ሲያጥብ፡፡ ንጉሳቸው -- እግራቸውን ፡፡ የሰማይ የምድር የሁሉ ፈጣሪ --- እግራቸውን፡፡ ወገኔ፦ ትልቅ መሆን፣ ገናና መሆን ፥ ማረፍ ፣ ዝና እንዲኖርህ ትፈልጋለህን?
እስቲ አስተውል! የቱስ ጀግና መሪ ነው እንኳ የመንግሥቱ (የግዛቱ) ሕዝብ ቀርቶ የአንድን ነፍስ ሸክም ወደኔ ና አሳርፍሃለሁ ብሎ ነፍስን የሚያሳርፍ ለዘለዓለምም የሚያድን፡፡ ኢየሱሳችን ግን ነፍሱን ለጠላቱ ቀድሶ አሳልፎ የሰጠ ፤ አልፎም ለዓለም ሁሉ ሕዝብ ሁሉ ወደኔ ኑ ነፍሳችሁ ከዘላለም ሞት ትድናለች ብሎ እየተጣራህ ነው፡፡ ሳይመሽ በቀን ወደሱ ሮጠህ አምልጥ፡፡ ዛሬም ያድናል ይታደግህማል!!! የትኛውም ሸክም የከበደህ ሁልህ ዕረፍትህን ወደሚሻ አባትህ ና!!! እሱ ከማንም በላይ ይወድሃል!!!
እንግዲያውስ፦
1) ከነ ሸክምክ ወደ ኢየሱስ ና!
2) ፈቃዱን ተሸከም
3) የውሃትነትን/ የዋህነትን ከሱ
ተለማመድ
4) ትህትናን ከእሱ ተማር፡፡
የሕይወት ጥያቄ ያለባችሁ ሁሉ
ጥያቄያችሁን በእግዚአብሔር ፊት አምጡት አባታችሁ ነውና የውስጣችሁን ይረዳችኀል ደግሞም ይረዳችኃል ፡፡
( የጣሩ ዋጋ የደሙ ፍሬ ነኝ ፦ አማኑኤል አበበ ፀሐይ)
ያሕዌ ሻሎም ሐብዚሁም!!!

20/04/2024

ኢየሱስ ክርስቶስ ሰላማችን ሆኖአል።

❤️ እርሱ ሰላማችን ነውና፤ ሁለቱን ያዋሐደ በአዋጅ የተነገሩትንም የትእዛዛትን ሕግ ሽሮ በመካከል ያለውን የጥል ግድግዳን በሥጋው ያፈረሰ፤ ይህም ከሁለታቸው አንድን አዲስን ሰው በራሱ ይፈጥር ዘንድ ሰላምንም ያደርግ ዘንድ፥ ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን በአንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋር ያስታርቅ ዘንድ ነው። መጥቶም ርቃችሁ ለነበራችሁ ለእናንተ ሰላምን፥ ቀርበው ለነበሩትም ሰላምን የምስራች ብሎ ሰበከ፤ በእርሱ ሥራ ሁላችን በአንድ መንፈስ ወደ አብ መግባት አለንና። ኤፌ.2፥14-17።

🙏“ሰላም ተገኝቶአል”፥ በበደላችንና በኃጢአታችንን ምክንያት ጠላቶቹ ሆነን ከእግዚአብሔር ሕይወት ርቀን ለነበርን፥ መጥመቁ ዮሐንስ፥ “እነሆ የዓለምን ኃጢአት ሁሉ የሚያሰወግድ የእግዚአብሔር በግ” ያለው የናዝሬቱ ኢየሱስ በመስቀል ላይ ክቡር ደሙን ባፈሰሰ ጊዜ ያ ክቡር ንጹሕ ደሙ አብ ደስ አሰኝቶታልና፤ አመጸኞችና ኃጢአተኞች፥ በደለኞችና ጠላቶቹ ለነበርን፥ ፍጹም፣ ሙሉ እና ነጻ የሆነ ይቅርታን አምጥቶልናልና፤ የኃጢአታችንን ሥርየት አገኘን። ያ ቅዱስ ደሙ፥ በእኛ ላይ የነበረውን የእግዚአብሔርን ቁጣ አብርዶታል። ይከስሰኝም የነበረ የዕዳ ጽሕፈትን ደመሰስልን። በዘላለማዊው መንፈስ፥ ሕሊናችንን አንጽቶ ከብዶብን ከነበረ ከበደለኝነትን ስሜት አሳረፈን። በአዲስም ልብ፥ አዲስ ፍጥረት አደረገን። የሕያው እግዚአብሔር ልጅ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ፥ የነፍሳችን ቤዛ ሆኖልናልና፤ ስለዚህም ሰላም አገኘን። እርሱ ሰላማችን ነውና።

“ሰላም በአደባባይ ታውጇል”፥ እውነትና ፍትህ ፍርድና ጽድቅ ከሚገኝበት ከብሩህ ሰማይ፥ ከርኅሩኁና በምሕረቱ ባለጠጋ ከሆነው ከክርስቶስ ኢየሱስ አምላክና አባት፥ በሚወደው በአንድያ ልጁ በኩል ለእኛ ያለውን የዘላለሙን ፍቅር በመግለጥ፥ እያየን መመልከት፥ እየሰማን ማስተዋል ተስኖን፥ እርስ በርስ ስንጣላና ስንጠላላ እንዲሁ በከንቱ እርሱንም ጠልተነው ለነበርን፥ ለኃጢአተኞቹ፥ ለሰው ልጆች ሁሉ፥ ከፍ ባለው ኮረብታ፥ በቀራንዮ ተራራ፥ ለገዳዮቹ፥ “የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው።” ብሎ፥ ለሰው ልጆች በሙሉ፥ በመስቀል ላይ ሰላሙን አወጀልን። ይህ፥ ለነፍሳችን፥ ምንኛ ድንቅ ነው! ምንኛ እረፍት! ተቅበዝባዧ ነፍሳችን፥ እረፍት የምታገኝበት ብቸኛው መልካም እረኛ፥ ነፍሱን ስለ እርሷ አኑሮአልና፥ ከእንግዲህ ወዲያ የምታርፈው እርሱን በመስማትና በማመን ብቻ ነው። ማረፊያዋ ጽኑዕና አስተማማኝ ነውና፥ ማንም ከእጁ አይነጥቃትምም።

💍 ክርስቶስ በእጅ ወደ ተሠራች፥ የእውነተኛይቱ ምሳሌ ወደ ምትሆን ቅድስት አልገባምና፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ስለ እኛ አሁን ይታይ ዘንድ ወደ እርስዋ ወደ ሰማይ ገባ (ዕብ. 9፥24)፥ አሁን ከፍ ባለ ከፍታ፥ በአብ ግርማ ቀኝ በክብር፥ ከተቀመጠበት እና በራሱ ላይ የሚያንጸባርቅ የክብር አክሊል ከተደፋበት፥ ሰላም ታውጆልናልና፤ በብዙ መከራ ውስጥ በመታዘዝና በትዕግስት በማለፉ ዘሩንም በብርሃን የሚያይበት ነው። ሥራችንን ሠርቶልናልና ሰላምን ሰጠን። የአባቱን ልብ፥ አሳርፎአልና፥ የክብርን ዘውድ ተጫነው። ይህም፥ ወደ እግዚአብሔር እረፍት እንድንገባ ዘንድ በፊቱ ቅዱስና ነውር የሌለን ሆነን በእርሱ በኩል ልጆቹ አድርጎ በደስታ የተቀበለንበት ምልክት ነው። ይህም ሰላም፥ ልቡ ወድዶን በፍቅር ሲቀበለን፥ ለእኛ በመንፈሱ በውስጣችን ከሚፈሰው ፍቅር፥ የክብር ተስፋ ያለው ክርስቶስ፥ በእርሱ ባለን እምነት ሕይወቱን ደግሞ በእኔ ከመኖሩ የተነሣ፥ በሁኔታዎች የማይደፈርስ፥ እንደማያቋርጥ ጅረት የሆነ ዘላለማዊ ሰላም ነው።

07/01/2024

... a virgin shall bring forth a son, and thou shalt call his name JESUS: for he shall save his people from their sins. Mat.1:21.

13/04/2023

_________________________________________________________________________________ አምነን እንድንበትና እንኖርበት ዘንድ የተገለጠው የእግዚአብሔር ፍቅር (1ኛ ዮሐ. 3፥1) ______________________________________________________________________
እንድን ዘንድ የእውነትን ፍቅር አምነን መቀበል አለብን (2ኛ ተሰ. 2፥10)። ይህም እግዚአብሔር በመስቀል ላይ በውድ ልጁ በኩል የገለጠልን ፍቅር ነው። ቀራንዮ ተራራ ላይ ከሠራው ሥራ ተለይቶ የእግዚአብሔር ፍቅር በኃጢአቱ ለወደቀ ሰው ትርጉም የለውም። ቀራንዮ ላይ የተሠራውም ሥራ ቅዱስና ቅን ከሆነው ከእግዚአብሔር ቁጣ ጋር ካልተገናኘ ትርጉም የለውም። ኢየሱስ ሰላምንና የሕይወትን ትርጉም ሊሰጠን ብቻ አልሞተም። በማይታዘዙት ልጆች ላይ አሁን ከሚገለጠው እና ሊመጣ ካለው ከእግዚአብሔር ቁጣም ደግሞ እንጂ።
እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ የመዓዛ ሽታ የሚሆንን መባንና መሥዋዕት አድርጎ ራሱን ስለኛ አሳልፎ በመስጠቱ አብን አርክቶታልና። ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እኛም ፍቅሩን አይተናል። ከታላቅ ፍቅሩም የተነሣ በሕይወት እንድንኖር፥ ድምጹን እንድንሰማ ዘንድ ሙት መንፈሳችንን ቀሰቀሰው፥ መጽሐፍ እንዲህ እንደሚል፥ “በክርስቶስ ፊት የእግዚአብሔርን የክብሩን እውቀት ብርሃን እንዲሰጥ በልባችን ውስጥ የበራ። በጨለማ ብርሃን ይብራ ያለ እግዚአብሔር ነውና (2 ቆሮ. 4፥6)።” አብ በርቶልን ስለሳበን እንጂ እኛ ለእርሱ ካለን ፍቅር ወደ ኢየሱስ አልመጣንም። እርሱ ስቦን እንጂ። ወደ ዓለም የመጣውን በእግዚአብሔር አንድያ ልጅ በኩል የተገለጠውን የእውነትን ፍቅር ለተቀበሉትና በልጁ አምነው የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ሥልጣን ስለሰጣቸው መጽሐፍ እንዲህ ይላል፥ “... እነርሱ ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም (ዮሐ. 1፥13)።” የተወለድነው፥ ከእግዚአብሔር ቁጣ ያመለጥነው እርሱ ራርቶልን፥ ስለማረንና በጨለማችን በርቶ ወደ ራሱ ስለሳበን እንጂ አንዳች ከእኛ የሆነው የለም።ያደረገልንን የማዳኑን ድንቅ ሥራውን አይተን እንድንረዳ ዘንድ በመንፈሱ በርቶልን የልባችንን ድንዳኔ አስወግዶልን በእሺታ መንፈስ ደግፎን አብ ወደ ራሱ ስቦናል።
ስለዚህም በልጁ አምነንም ደግሞ በልጁ ደም የኃጢአታችንና የበደላችንን ሥርየት አግኝተዋል። እግዚአብሔር በልጁ ደም ይቅር ብሎናል። ይህም የነፍሳችን ቤዛ ነው። ይህ ብቻ አይደለም፥ ደግሞ በእርሱ እንድንኖር፥ እርሱም በእኛ እንዲኖር ዘንድ በመንፈሱ አትሞናልና። ሕያው መንፈሱ የርስታችን መያዣ ነውና በላይ በሰማይ ያለውን በታች በምድር በእኛ የአብን ፈቃድ እንድንኖር ዘንድ ለእግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እስኪዋጅ ድረስ በእኛ የሚሠራው እርሱ ነው።
ጸጋውን በጥበብና በአዕምሮ አብዝቶልን የእግዚአብሔርን የፈቃዱን እውቀት ምሥጢር አስታውቆናልና ደግሞም ጌታችንና መድኃኒታችንን እርሱን ደስ የሚያሰኘው ነገር ምን እንዲሆን መርምረን እርሱ እንደተመላለሰ፥ እርሱን በመምሰል በቅድስና ሕይወት እንድንመላለስ የሚያስችለን መንፈሱ ነው። ይህም የሰጠን የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ (ኤፌ.1፥ 8፣9፣13፤ 5፥1፣10)።
በውስጥ ሰዋችን እየጠነከርን እርሱን እንድንመስል ዘንድ እርሱንና በቀራንዮ አናት ላይ ልጁን ስለኛ እንዲሰጥ ያደረገውን የእግዚአብሔርን ፍቅር፥ ክርስቶስ ኢየሱስንና እርሱን ከሙታን ያስነሣውን የትንሣኤውን ኃይል እንድንረዳ ለሚያስችለን ለእግዚአብሔር መንፈስ ክብር ይሁንለት።
በመስቀል ላይ የተሠራልን ሥራ፥ የክርስቶስ ግርፋት፥ ሕመሙ፥ ስቅለቱ፥ ሞቱ፥ መቀበሩ እና ትንሣኤው ሁሉ በዓመት አንድ ጊዜ የምናከብረው ክብረ ፋሲካ በዓል ሳይሆን፥ የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን እንድንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደ ሰጠን የምናይበትና እንዲሁም በመሆናችን የጸጋው ክብር የሚመሰገንበት፥ ዳሩ ግን ዓለም ይህን እንድታውቀው ዘንድ አትረዳውም (1ኛ ዮሐ. 3፥1፤ ዮሐ. 1፥10)።
ለእኛ ግን በመንፈሱ በልባችን የእግዚአብሔርን ፍቅር ስለፈሰሰ፥ ፋሲካው ከቅዱሳን ጋር የማይጠፋውን ርስት እንድንካፈል ያበቃንን አብን ዘወትር እያመሰገንን እምነታችን በእርሱ እየተጨመረ እርሱን በመምሰል በእግዚአብሔር እውቀት እያደግን፥ ዘላለም በላይኛው ሀገራችን ከእርሱ ጋር እንድንኖር ዘንድ ለእኛ ይገለጥልን ያለውን የእግዚአብሔርን ልጅ፥ ማራናታ ጌታ ሆይ ቶሎ ና። ሌሎችም ከእኛ ጋር እንዲሉ ማንም የተጠማ ወደዚህ ይምጣ፥ የሕይወት ውኃ ምንጭን በነጻ ይጠጣ፥ እያልን የተባረከውን ተስፋችንን የምንጠብቅበት ነው። ስላደረገልን ነገር ሁሉ እግዚአብሔር ይመስገን።

በእውነትህ ቀድሳቸው፤ ቃልህ እውነት ነው። ዮሐ. 17፥17።
19/04/2022

በእውነትህ ቀድሳቸው፤ ቃልህ እውነት ነው። ዮሐ. 17፥17።

Address

Wolkite
EMMANUELABEBE

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when የእውነት ቃል መስካሪ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Place Of Worship

Send a message to የእውነት ቃል መስካሪ:

Share