09/06/2024
ክርስቶስ በስጋው ፍጡር ማለት ምን ማለት ነው?
/ክፍል አንድ/
የተዋህዶን ትርጉም በደንብ ለተረዳ ኦርቶዶክሳዊ ይህ አገላለጽ ሊጸንበት አይችልም፡፡ ተዋህዶ ማለት ሁለት አካላት አንድ አካል፣ ሁለት ባሕርያት አንድ ባሕርይ የሆኑበት ታላቅ ምስጢር ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ስንል፣ ፍጹም ሰው፣ ፍጹም አምላክ፣ ስግው ቃል፣ክሁለት አካል አንድ አካል፣ ከሁለት ባህርይ አንድ ባህርይ የሆነ ማለት ነው፡፡
በተዋህዶ ስጋ የራሱን ገንዘብ ሳይለቅ (በተአቅቦ)፣ የመለኮትን ገንዘብ ገንዘቡ አደረገ፡፡ መለኮትም የራሱን ገንዘብ ሳይለቅ (በተአቅቦ)፣ የስጋን ገንዘብ ገንዘቡ አደረገ፡፡ በመሆኑም ስግው ቃል ኢየሱስ ክርስቶስ፣ አንድ አካል፣ አንድ ባሕርይ ያለው፣ ፍጹም ሰው፣ ፍጹም አምላክ ነው ብለን እናምናለን፡፡ ሲራብ፣ ሲጠማ፣ ሲደክም፣ ሲተኛ፣ ሲታመም፣ ሲሞት ብናየው፣ አንዲህ የሆነው ማነው ቢሉን አምላካችን ጌታቸን ኢየሱስ ክርስቶስ እንላለን፡፡ በደረቅ ግንባር አይንን ሲፈጥር፣ ውሃን ወደ ወይን ጠጅ ሲቀይር፣ ድውያንን ሲፈውስ፣ ሽባን ሲተረትር፣ ሙት ሲያስነሳ፣ ሞትን ድል አድርጎ ሲነሳ፣ ሲያርግ ያየነው እርሱ ማነው ቢለው ቢጠይቁን አሁንም ደግመን፣ ስግው ቃል፣ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ብለን እንመልሳለን፡፡
ንስጥሮስ ይህንኑ ጥያቄ ቢጠየቅ፣ እንዲህ ይመልሳል፡፡ የተራበው፣ የተጠማው፣ የታመመው፣ የሞተው ስጋው ነው፡፡ ድውያንን የፈወሰው፣ ሙታንን ያስነሳው፣ ሞትን ድል ያደረገው ደገሞ መለኮት ነው ይላል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስን ሁለት ማነነት ያለው፣ ሁለት ፈቃድ ያለው፣ ሁለት እኔ ባይ አካል ያለው ያደርግና፣ ይህን ያደረገው ስጋው ነው፡፡ ይህን ያደረገው መለኮቱ ነው በማለት ክርስቶስን ከሁለት ይክፍለዋል፡፡
ይህ ንስጥሮሳዊ ኑፋቄ፣ ከ1500 ዓመታት በኋላ ወንድማችንን አክሊል በሚያደርገው የlive ውይይት፣ ኢየሱስ በስጋው መለኮቱን ያመልከዋል? በማለት ጥያቄ ሲቀርብለት ሰምተናል፡፡ ለጊዜው ጥያቄስ መልስ ባይሰጠውም፣ ጠያቂው በማወቅም ይሁን ባለማወቅ፣ ክርስቶስን ስጋው እና መለኮቱ በማለት ክፍሎ ሲናገር ስምተነዋል፡፡ እንዲህ ያለ እምነትና ጥያቄ ንስጥሮሳዊነት ነው፡፡
ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና! የታመመው፣ የሞተው፣ ሞትን ድል አድርጎ የተነሳው፣ ያረገውም አንዱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ‹‹አትፍራ ፊተኛውና መጨረሻው ሕያውም እኔ ነኝ ሞቼም ነበርኩ እነሆም ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ሕያው ነኝ፣ የሞትና የሲኦል መክፈቻ አለኝ›› (ራዕ 1፡18) ያለው እርሱ አንዱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡
ክርስቶስ በስጋው ፍጡር፣ ማለትና ስጋው ፍጡር ነው ማለት አንድ ነውን?
በፍጹም አንድ አይደለም፡፡ ስጋው ብለን ስንጠራ በተዋህዶ የከበረውን የስግው ቃልን (ኢየሱስ ክርስቶስን) ስጋ ማለታችን ነው፡፡ ይህም ስጋ በተዋህዶ ከብሯልና፣ ከተዋህዶ በኋላ ከመለኮት ነጥለን ስጋው ፍጡር ነው አንልም፡፡ ለመለኮትም እንዲሁ ነው፡፡ ከተዋሆዶ በኋላ መለኮትን ከስጋ ነጥለን፣ ብቻውን ፈጣሪ ነው አንልም፡፡ ክርስቶስ በስጋ ፍጡር ማለት ስህተት የለበትም፡፡
ክርስቶስ በስጋ ፍጡር ስንልስ ምን ማለታችን ነው?
ፊደላት ታላቅ ትርጉም እንዳላቸው የምንረዳው አዚህ ጋር ነው፡፡ ክርስቶስ በስጋ ስንል፣ "በ" ፊደል ተዋህዶን የምታመለክት አያያዥ ቃል ናት፡፡ ክርስቶስ በስጋ ስንል፣ መለኮት በስጋ ማለታችን ነው፡፡ በዚህም መለኮት በተዋሃደው ስጋ ምክኒያት ገንዘብ ያደረገውን የስጋን ገንዘብ እንጠራበታለን፡፡
ፍጡርነት የስጋ ገንዘብ ነው፡፡ ኢፍጡርነት የመለኮት ገንዘብ ነው፡፡ ተዋህዶ፣ እኒህ ሁለት ባህርያት አንድ ባህርይ ሆኑ ብሎ ማመን ነው፡፡ ይህም ማለት፣ ስጋ ፍጡርነቱን ሳይለቅ (በተአቅቦ) ፈጣሪ ሆነ፡፡ መለኮትም፣ ኢፍጡርነቱን (ፈጣሪነቱን) ሳይለቅ (በተአቅቦ)፣ ፍጡር ሆነ ብሎ ማመን ነው፡፡ ፍጡር ሆነ ሲባል፣ ሰው ሆነ ከማለት ጋር አንድ ነው፡፡ ሌላ የተለይ ትርጉም ወይም ማብራሪያ የለውም፡፡ ፍጡር ሆነ ሲባል፣ በተዋህዶ ማለት ነው፡፡ ውላጤን እያሰቡ፣ ወይም አርዮሳዊ ክህደትን እያሰቡ፣ ወይም ኢአማንያን የሚያነሱትን ኑፋቄ እያሰቡ፣ ይህንን የቀና ኦርቶዶክሳዊ እምነትና ትምህርት በሌላ መተርጎም ተገቢ አይደለም፡፡
ይቆየን!
/ይቀጥላል…../