15/02/2026
የሉርድ ማርያም ዓመታዊ ክብረ-በዓል በድምቀት ተከበረ።
በኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተክርስትያን በሶዶ አገረ ስብከት በዱቦ ሉርድ ማርያም ቁምስና የሉርድ ማርያም ዓመታዊ ክብረ-በዓል የካቲት 08/2018 ዓ.ም. በድምቀት ተከበረ።
በዕለቱም የሶዶ አገረ ስብከት ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ደጀኔ የክብረ በዓሉን መሥዋዕተ ቅዳሴ መርተዋል።
በበዓሉ የሀዋሳ አገረ ስብከት ጳጳስ ብፁዕ አቡነ መርሀክርስቶስ በመሥዋዕተ ቅዳሴው የተገኙ ሲሆን ካህናት ፣ ገዳማውያን ፣ መነኮሳት ፣ ወጣት መዘምራን እና ከተለያዩ አገረስበከት የመጡ ምዕምናን ተገኝተዋል።
ብጹዕ አቡነ ደጀኔ “የሉርድ ማርያም በዓል የእግዚአብሔር ስም ከፍ የሚልበት እና በእርሷ አማካኝነት ቸርነቱ የሚታይበት ታላቅ በዓል ነው። ይህ ስፍራም ከእግዚአብሔር ጋር በጸሎት የምንገናኝበት ስፍራ ነው። እናታችን ሉርድ ማርያም ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉንም አዲስ እንደሚያደርግ በመተማመን በመከራም ውስጥ ሆነን በጽናት እንድናገለግለው ትጋብዘናለች። የእርሷ ክብረ በዓል ያለፈውን ጊዜ ብቻ አስታውሰን የምንተወው ሳይሆን ሁሌም በልባችን የምናሰላስለው ጥሪ ነው። የእግዚአብሔር ጥሪ በሰዎች መስፈርት የሚለካ ሳይሆን በትህትና እና በመታዘዝ የሚገኝ ነው።” በማለት የዕለቱን ቃለ እግዚአብሔር አሰምተዋል።
በበዓሉም በተለያዩ ቋንቋዎች ስለቤተክርስትያናችን፣ ስለ ሰላም፣ ስለ ሕሙማን፣ ስለ ወጣቶች፣ እና ስለ ሀገር መሪዎች እንዲሁም በተለያዩ ሐሳቦች ላይ የምልጃ ጸሎት ተደርጓል።
የሉርድ ማርያም ክብረ-በዓል ከዋዜማው ጀምሮ በአስተምህሮ ፣ በጸሎት ፣ በዑደት ፣ በዝማሬ የተከበረ ሲሆን በዓሉን ለየት የሚያደርገው የእመቤታችን የሉርድ ማርያም ዋሻ ለመንፈሳዊ ነጋድያን ይሆን ዘንድ በብጹዕ አቡነ ደጀኔ መመረቁ ነው።
ክብረ-በዓሉ በጸሎት ፣ በዝማሬ ፣ በዑደት እና በቡራኬ ተጠናቋል።
ምንጭ : ሰላም ካቶሊክ ቲቪ Pax Catholic TV