የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር - ማህበረ ሩፋኤል

  • Home
  • Ethiopia
  • Motta
  • የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር - ማህበረ ሩፋኤል

የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር - ማህበረ ሩፋኤል CBE bank (1000260511118) Zemenu Adis & Shegaw Temesgen & Lingerew Ewunetie ይህ የጉልት ሩ?
(1)

23/11/2025

ጾመ ነቢያት (የገና ጾም)

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጌታችንን፣ የነቢያትንና የሐዋርያትን ቃል መሠረት በማድረግ በዐዋጅ ከደነገገቻቸው አጽዋማት አንዱ ጾመ ነቢያት፣ጾመ ልደት ተብሎ የሚጠራው ነው።

የዚህ ጾም መሠረት ነቢያት አስቀድመው ስለ ጌታ መወለድ ሱባኤ የቆጠሩበትን፣ ጾም የጾሙበትን በማሰብ የምንጾመው ታላቅ መታሰቢያ ነው።

ጾመ ነቢያት በየዓመቱ ከኅዳር ፲፭ ቀን ጀምሮ እስከ በዓለ ልደት ዋዜማ ድረስ የሚጾም፤ ከሰባቱ አጽዋማት መካከል አንደኛው ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም የእግዚአብሔርን ሰው መኾን ሲጠባበቁ የኖሩት የነቢያት ትንቢትና ጸሎት በጌታችን መወለድ ፍጻሜ ያገኘበት ወቅት በመኾኑ ‹‹ጾመ ነቢያት (የነቢያት ጾም)›› እየተባለ ይጠራል፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ዓለምን ለማዳን ሲል መወለዱን፣ ከእናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ጋር ወደ ግብጽ መሰደዱን፣ በባሕረ ዮርዳኖስ መጠመቁን፣ በትምህርቱ ብርሃንነት ጨለማውን ዓለም ማብራቱን፣ ለሰው ልጆች ድኅነት ሲል ልዩ ልዩ ዓይነት መከራ መቀበሉን፣ መሰቀሉን፣ መሞቱን፣ ከሙታን ተለይቶ መነሣቱን፣ ማረጉንና ዳግም ለፍርድ የሚመጣ መኾኑን፣ በአጠቃላይ የማዳን ሥራውን በየዘመናቱ የተነሡ ቅዱሳን ነቢያት በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝተው አስቀደመው በትንቢት ተናግረዋል፡፡

ለአዳም የተነገረው የድኅት ተስፋ ስለ ተፈጸመበትም ‹‹ጾመ አዳም (የአዳም ጾም)›› ይባላል፡፡ ስለ እግዚአብሔር ሰው መኾን በስፋት ትምህርተ ወንጌል የሚሰጥበት ወቅት በመኾኑም ‹‹ጾመ ስብከት (የስብከት ጾም)››፤ የጾሙ መጨረሻ (መፍቻ) በዓለ ልደት በመኾኑ ደግሞ ‹‹ጾመ ልደት (የልደት ጾም)›› በመባል ይታወቃል፡፡

በተመሳሳይ መልኩ ይህ ጾም ‹‹ጾመ ፊልጶስ (የፊልጶስ ጾም)›› ተብሎ ይጠራል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ፊልጶስ በአፍራቅያና አውራጃዋ ሁሉ እየተዘዋወረ በጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ወንጌልን በማስተማር፣ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን በማድረግ ብዙዎችን ወደ አሚነ እግዚአብሔር ሲመልስ ቆይቶ ትምህርቱን በማይቀበሉ የአፍራቅያ ሰዎች አማካይነት በሰማዕትነት ዐርፏል፡፡

ደቀ መዛሙርቱ ሥጋውን ሊቀብሩ ሲሉም ስለ ተሰወረባቸው የሐዋርያውን ሥጋ ይመልስላቸው ዘንድ ሱባኤ ይዘው፣ በጾም በጸሎት ተወስነው በለመኑት ጊዜ እግዚአብሔር ልመናቸውን ተቀብሎ በ፫ኛው ቀን መልሶላቸው ሥጋውን (አስከሬኑን) በክብር አሳርፈውታል፡፡ ደቀ መዛሙርቱ የሐዋርያውን ሥጋ ካገኙ በኋላ እስከ ጌታችን ልደት ድረስ ጾመዋል፡፡ ስለዚህም ጾመ ነቢያት ‹‹ጾመ ፊልጶስ›› እየተባለ ይጠራል፡፡

ከዚሁ ሁሉ ጋርም ወልደ አምላክ ክርስቶስን በግብረ መንፈስ ቅዱስ እንደምትፀንሰው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ካበሠራት በኋላ እመቤታችን ‹‹ሰማይና ምድር የማይወስኑትን አምላክ ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ?›› በማለት ጌታችንን ከመውለዷ አስቀድማ ጾማዋለችና ይህ ጾም ‹‹ጾመ ማርያም›› በመባልም ይታወቃል፡፡

በአጠቃላይ በዚህ በጾመ ነቢያት፣ ነቢያትም ሐዋርያትም፣ ቀደምት አባቶቻችንም ጾመው በረከት አግኝተውበታል፡፡ እኛ ምእመናንም የነቢያት፣ የሐዋርያት፣ የጻድቃንና የሰማዕታት አምላክ ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ሐዋርያት በረከት እንዲያሳትፈን በዚህ በጾመ ነቢያት ወቅት በጾም በጸሎት ተወስነን እግዚአብሔርን ልንማጸነው ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡-
ፍትሐ ነገሥት ንባቡና ትርጓሜው፣ አንቀጽ ፲፭፡፡
ጾምና ምጽዋት፣ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ፤ ገጽ ፵፯ -፶

ፔጁን ይቀላቀላሉን።

❤️Like ,Share ማድረግ አትርሱ

💚💜💙💚💜💙💚💜💙💛💚💛

👇👇👇👇👇👇👇👇👇👇👌
Join us
👉Telegram

https://telegram.me/Gult_Rufael

👉Facebook

https://www.facebook.com/Mahibere.Rufael

👉https://www.facebook.com/112771870182132

👉LinkedIn
https://www.linkedin.com/groups/12865549

👉ቤተሰብ ስለሆንን ከልብ እናመሰግናለን ።

የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር(ማህበረ ሩፋኤል) የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር(ማህበረ ሩፋኤል) አዲሱ ዓመት 𝟐𝟎𝟏𝟖 ዓ/ም እና የኢትዮጵያ ዘመን አቀማመር፣ ባሕረ ሐሳብ (አቡሻኽር)፣ የአጽዋማ...
11/09/2025

የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር(ማህበረ ሩፋኤል)
የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር(ማህበረ ሩፋኤል)

አዲሱ ዓመት 𝟐𝟎𝟏𝟖 ዓ/ም እና የኢትዮጵያ ዘመን አቀማመር፣ ባሕረ ሐሳብ (አቡሻኽር)፣ የአጽዋማትና በዓላት ሥሌት፣ የክፍላተ ዘመን (ወቅት) ፣ የወራትና ዕለታት ትርጓሜ በአጭሩ
የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር - ማህበረ ሩፋኤል

🌻 አዲሱ ዓመት 𝟐𝟎𝟏𝟖 ዓ/ም እና የኢትዮጵያ ዘመን አቀማመር፣ ባሕረ ሐሳብ (አቡሻኽር)፣ የአጽዋማትና በዓላት ሥሌት፣ የክፍላተ ዘመን (ወቅት) ፣ የወራትና ዕለታት ትርጓሜ በአጭሩ
▬▬▬▬▬ ▬▬ ▬▬▬▬▬

ወትባርክ አክሊለ ዓመተ ምሕረትከ
በቸርነትህ ዓመትን ታቀዳጃለህ፥
መዝሙር ፷፬ ÷፲፩

አቡሻኽር የተለያዩ የዘመን ቀመሮችን ያጠና ዘመን ቀማሪ የቁጥር ሰው (Mathematician) ነው። ሙሉ ስሙ አቡሻኽር ወልደ አቤል ሔሬም ሲሆን ዮሐንስ ፍቁርም ይሉታል። በ፲፱፻፷፪ በታተመው የአቡሻኽር መጽሐፍ ላይ የአቡሻኽርን ቁጥርና ሐሳብ የመረመሩ (የተነተኑ) ፱ ሊቃውንትን ይዘረዝራል። እነዚህም ሰዒድ ወልደ በጥሪቅ፣ ማኅቡብ መንበጋዊ፣ ስዒዳውያን አይሁድ፣ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቄርሎስ፣ ኤጲፋንዮስ፣ ዮሐንስ ዘደማስቆ፣ ማርቆስ ወልደ ቀምበር እና ጊዮርጊስ ወልደ አሚድ (ሃሚድም ይላሉ) ናቸው። አቡሻኽር መጽሐፉን የጻፈው እንደ ኢትዮጵያውያን አቆጣጠር በ ፲፩፻፵፱ ነው ይላሉ። አንዳንዶች እስከ ፲፩፻፺፫ ድረስ ከፍ ያደርጉታል።
መጽሐፉን የሀገራችን ሊቃውንት መርምረውታል፣ ሐተታ ጭረውበታል፣ አስተምረውታል። በዚህ ሂደትም ከሀገራችን የቁጥር መጻሕፍት ይመደባል።

አቤቱ አንተ ከጥንት ምድርን መሠረትክ ሰማያትም የጅህ ሥራ ናቸው፤ አነርሱ ያልፋሉ አንተ ግን ትኖራለህ፤ ሁላቸውም አንደ ልብስ ያረጃሉ አንደ መጎናጸፊያ ትለውጣቸዋለህ። አንተ ግን ያው አንተ ነህ፤ ዓመቶችህም ከቶ አያልፉም። መዝ ፻፩፤፪፬-፪፰

የሰው ልጅ ሐሳቡ፣ ንግግሩና ተግባሩ የሚከናወነው በጊዜ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ ዘመን ማለት በኅሊና ሲመረመር የጊዜና የዕድሜን መጠንና ልክ የሚወስን መሆኑን መጽሐፈአቡሻኸር ያስረዳል፡፡ ይህ ዘመን የሚባለው የጊዜ ዕድሜ በስያሜው አጠራር መሠረት ኃላፊ፣ የአሁንና የትንቢት (የወደፊት) ጊዜ ተብሎ በሦስት ክፍላተ ጊዜ ይመደባል፡፡
«ወፉካሬሁሰ ለዘመን በውስተ ልብ አርአያ ወሰን ውእቱ ለጊዜ ዕድሜ ወዝንቱሰ ጊዜ ዕድሜ ዘስሙ ዘመን ይትከፈል እመንገለ ስሙ ኅበ ሠለስቱ ክፍል ኀበ ዘኅለፈ ዘመነ ወኀበ ዘይመጽእ ወኀበ ዘሀሎሂ እንዲል]፡፡

ከጥንተ ፍጥረት እስከ ዳግም ምጽአት ድረስ ያለው ዘመን ሁሉ በእነዚህ ሦስት ጊዜያት ሲሠፈርና ሲቆጠር ይኖራል፡፡ ያለፈውንና የሚመጣውን ዘመን ቆጥሮና ሠፍሮ መረዳትና ማስረዳት እንደሚገባ ሲገልጽ ደግሞ፣ “ተሰአሉ ዘቀደሙ መዋዕለ ዘኮነ እምቅድሜክሙ እምአመ ፈጠሮሙ እግዚአብሔር ለእጓለ እመሕያው ዲበ ምድር እም አጽናፈ ሰማይ እስከ አጽናፈ ሰማይ ለእመ ኮነ ዝንቱ ነገር፤ እግዚአብሔር ሰውን በምድር ላይ ከፈጠረው ጀምሮ ከሰማይ ዳር እስከ ዳርቻዋ ድረስ ከቶ እንዲህ ያለ ታላቅ ነገር ወይም እንደ እርሱ ያለ ተሰምቶ እንደሆነ ከአንተ በፊት የነበረውን የቀድሞው ዘመን ጠይቅ” ተብሎ ተጽፏል ። ዘዳ.4÷32

የአዲሱን ዓመት 2018 ዓ/ም መባቻ፣ ወንጌላዊና ዘመኑን እንዴት በቀላሉ ማስላት ይቻላል ቢባል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የዘመን አቆጣጠርን ባሕረ- ሐሳብ ወይም አቡሻኽርን መሠረት በማድረግ እንደሚከተለው በቀላሉ ማስላት ይቻላል።
ከአዳም እስከ ክርስቶስ ያለው 5500 ዘመን ዓመተ ኩነኔ (ፍዳ) ሲሆን፣ ከክርስቶስ መወለድ እኛ እስካለንበት ያለው ዘመን ደግሞ ዓመተ ምሕረት ይባል። የኹለቱ ድምር ዓመተ ዓለም ይባላል።

ዓመተ ዓለም = ዓመተ ምሕረት ➕ ዓመተ ኩነኔ (ፍዳ)
= 2018 ➕ 5500
= 7518
ወንጌላዊ፦ በየ4 ዓመቱ አንድ ጊዜ የሚሾም ማለት ነው፡፡
ወንጌላዊ = ዓመተ ዓለም ➗ 4
= 7518 ➗ 4
= 1879 (ቀሪ 2️⃣ )
1879፦ መጠነ ራብዒት ይባላል፡፡ አንድ አራተኛ (1/4) ማለት ነው።
= 7518➖ ( 4 ✖1879)
= 7518➖ 7516
= 2
ቀሪው ‘1️⃣‘ ከሆነ ዘመኑ ዘመነ ማቴዎስ
ቀሪው ‘ 2️⃣ ‘ ከሆነ ዘመኑ ዘመነ ማርቆስ
ቀሪው ‘ 3️⃣ ‘ ከሆነ ዘመኑ ዘመነ ሉቃስ
ቀሪው ‘ 0️⃣ ‘ ከሆነ ዘመኑ ዘመነ ዮሐንስ ይሆናል።
ስለዚህ ቀሪው ‘2️⃣’ ስለሆነ የዘንድሮው ወንጌላዊ (2018) ማርቆስ ሲሆን ዘመኑ ዘመነ ማርቆስ ይባላል።
በሌላም በኩል ዓመተ ምሕረቱንም ለ4ቱ ወንጌላውያን ብናካፍለው የዘመኑን ወንጌላዊ ማወቅ እንችላለን።
2018 ➗ 4 = 504 (ቀሪ ‘2️⃣’ )
ቀሪው ‘2️⃣ ‘ በመሆነ ዘመኑ ዘመነ ማርቆስ እንደሆነም በዚህ ይታወቃል።

ዕለተ ቀመር፦ መስከረም አንድ የሚውልበት ቀን ነው፡፡
ዕለተ ቀመር = (ዓመተ ዓለም ➕ መጠነ ራብዒት) ➗ 7
= (7518➕ 1879) ➗ 7
= 9397 ➗ 7
= 1342 ቀሪ 3
ቀሪው ‘0️⃣ ‘ከሆነ ሰኞ
ቀሪው ‘1️⃣’ ከሆነ ማክሰኞ
ቀሪው ”2️⃣ ከሆነ ረቡዕ
ቀሪው ‘3️⃣ ‘ከሆነ ሐሙስ
ቀሪው ‘4️⃣’ከሆነ ዓርብ
ቀሪው ‘5️⃣ ‘ከሆነ ቅዳሜ
ቀሪው ‘6️⃣ ‘ከሆነ እሑድ መባቻ ይሆናል።

በመሆኑም ዘንድሮ ቀሪው ”3️⃣ ‘ ስለሆነ ዕለተ ቀመር ሐሙስ ይሆናል ወይም አዲሱ ዓመት 2018 ዓ/ም መባቻ መስከረም አንድ ቀን በዕለተ ሐሙስ ይውላል ማለት ነው።
ሥነ ፍጥረት የተጀመረባት እሑድ ጥንተ ዕለት፣ ዘመን አቆጣጠር የተጀመረባት ማክሰኞ ጥንተ ቀመር እንዲሁም ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት የተፈጠሩባት ዕለተ ረቡዕ ጥንተ ዮን (ዖን) ትባላለች።
ጥንታት ሦስት ናቸው። የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር የሚጀምረውም ከነዚህ ጥንታት ነው።
1· ጥንትነቱም ከፍጥረተ ዓለም፣
2· ከፍጥረተ ፀሐይ፣
3· ከፍጥረተ ጨረቃ እና ክዋክብት ነው።
ዓለም የተፈጠረበት ዕለተ እሑድ ጥንተ ዕለት ይባላል።
አዝርዕት ዕጽዋት እና አትክልት የተፈጠሩበት ዕለተ ሠሉስ ( ማክሰኞ) ደግሞ ጥንተ ቀመር ይባላል። ቁጥር የተጀመረበት እለት ስለሆነ ነው።
ፀሐይ ጨረቃ እና ክዋክብት የተፈጠሩበት ዕለተ ረቡዕም ጥንተ ዖን/ዮን/ በመባል ይታወቃል። ዖን ማለትም ብርሃን ማለት ነው። በመጽሐፍ “ዖን ይእቲ ስማ ለፀሐይ” እንዲል።

በተመሳሳይ ፤
መስከረም 1 በዋለበት ሚያዝያ 1 ይውላል
ጥቅምት 1 በዋለበት ግንቦት 1 ይውላል
ኀዳር 1 በዋለበት ሰኔ 1 ይውላል
ታኅሣሥ 1 በዋለበት ሐምሌ 1 ይውላል
ጥር 1 በዋለበት ነሐሴ 1 ይውላል።

የሥነ ፍጥረት መጀመሪያ ጥንተ ዕለት የሆነችው እሑድ አዲስ ዓመት በመጣ ቁጥር የዓመቱ መጀመሪያ (መባቻ ) ዕለት እንዳትሆን የምታደርጋት ጳጉሜን 5 ናት። ጳጕሜን 5 ዕለተ ምሪያ (ዕለተ መድኀኒት /ብርሃን /ልደት) ‹‹ምርያ›› ማለት ‹የተመረጠች ቀን› ማለት ሲሆን የምታዘዋውር ማለትም ነው፤ ይህች ዕለት ዓመቱ በዋለበት እንዳይውል የምታደርግ ናት፡፡ ለምሳሌ የዘንድሮው መስከረም 1 ቀን 2017 ዓ/ም ረቡዕ ውሎ መጪው መስከረም 1 ቀን 2018 ዓ/ም ሐሙስ እንዲውል የምታደርገው ጳጕሜን 5 ናት፡፡
ጳጕሜን 5 የምትውልበት ዕለት ሁልጊዜም ከቀጣዩ የገና (የልደት) በዓል ዕለት ጋር ተመሳሳይ ነው (በዓለ ልደት የሚውለውም ጳጕሜን 5 በዋለበት ቀን ነው)፡፡ የ2017 ዓ/ም ጳጉሜን 5 ረቡዕ ስለምትውል መጪው የገና (ልደት) በዓልም በተመሳሳይ በዕለተ ረቡዕ ታኅሣሥ 29 ቀን ይውላል ማለት ነው። በዚህም የጌታችንን የመድኀኔ ዓለም ክርስቶስ ልደቱን ስለምታሳውቅ (ስለምትመራ) ጳጕሜን 5 ዕለተ ምሪያ ከሚል ስያሜ በተጨማሪ ዕለተ መድኀኒት ዕለተ ልደት በመባል ትታወቃለች፡፡

ጳጕሜን 6 ስትሆን ደግሞ ዕለተ ሠግር (ሠግረ ዮሐንስ/ 6ኛ ጳጉሜን) (Leap year) ትሰኛለች። ዮሐንስ ተሻግሮ የሚውልባት ቀን ማለት ነው፡፡
በዐራት ዓመት አንድ ጊዜ ጳጕሜን 6 ቀን የምትኾነውም እነዚህ በየዓመቱ የተሰባሰቡ 15 ኬክሮሶች አንድ ላይ መጥተው በዐራት ዓመት አንድ ጊዜ አንድ ዕለት ስለሚኾኑ ነው፡፡ ጎርጎርዮሳውያኑ ይህቺን ሠግር በፌቡርዋሪ ወር ላይ ጨምረው ወሩን በየአራት ዓመቱ አንድ ጊዜ 29 ቀን ያደርጉታል፡፡
15ቱ ኬክሮስ በአራት ዓመት ተደምረው አንድ ዕለት መጡና በአራት ዓመት አንድ ጳጕሜን ስድስት ቀን እንድትኾን አድርገዋታል፡፡ የቀረችው 6 ካልዒትስ የት ትግባ? ከተባለ ካልዒት አንዲት ዕለት ትኾን ዘንድ 3600 ካልዒት ያስፈልጋሉ፡፡ ይህንን ያህል ካልዒት ለማግኘት 600 ዓመታት ያስፈልጉናል፡፡ ለዚህ ነው ጳጕሜን በየስድስት መቶ ዓመታት ሰባት የምትኾነው፡፡

በዘመነ ዮሐንስ ግን ስድስተኛዋ የጳጕሜን ቀን በዓለ ልደትን በአንድ ቀን ዝቅ ብሎ እንዲከበር ስለምታደርገው ልደትን ታኅሣሥ 28 ቀን እናከብራለን፡፡ ታድያ ምነው ጥምቀት፣ ግዝረትና ሌሎችም በዓላት አይለወጡም? ቢሉ ሊቃውንቱ የሚሰጡት ምላሽ ‹‹ትውልድ ሱባዔ እየቈጠረ በተስፋ የጠበቃት ዕለተ ልደትን ስለ ኾነ ነው፤ ሌሎቹ በዓላትም የመጡት በልደቱ ምክንያት ነው›› የሚል ነው፡፡
በጎርጎርዮሳውያንም ቢኾን በአራት ዓመት አንድ ጊዜ በዓለ ልደት ዝቅ ብሎ ይከበራል፡፡ የእነርሱ የማይታወቀው ጭማሪዋ ፌብርዋሪ ላይ ስለኾነች ነው፡፡ ያ ደግሞ አዲሱን ዓመት ካከበሩ በኋላ ስለሚመጣ ነው፡፡ የእኛ ግን የምትወድቀው ጳጕሜን መጨረሻ ላይ በመኾኗና ከአዲስ ዓመት በፊት ስለምትጨመር ቍጥሯ ጐልቶ ይታወቃል፡፡

የሀገረ እስክንድርያ 12ኛ ሊቀ ጳጳስ (ፓትርያርክ) በነበረው ቅዱስ ድሜጥሮስ የበዓላት እና አጽዋማት አቀማመር፦
1· ጾመ ነነዌ ፣ ዐቢይ ጾም ፣ ጾመ ሐዋርያት ከሰኞ፣
2· ደብረ ዘይት ፣ ሆሣዕና ፣ ትንሣኤ እና ጰራቅሊጦስ ከእሑድ፣
3· ርክበ ካህናት እና ጾመ ድኅነት ከረቡዕ፣
4· ዕርገት ከሐሙስ
5· ስቅለት ከዓርብ አይወጡም ።

በተጨማሪም ፦
ጾመ ነነዌ ከጥር 17 አትወርድም ከየካቲት 21 አትወጣም፣
ዐቢይ ጾም ከየካቲት 1 አይወርድም ከመጋቢት 5 አይወጣም፣
ደብረ ዘይት ከየካቲት 28 አይወርድም ከሚያዝያ 2 አይወጣም፤ ሆሣዕና ከመጋቢት 19 አይወርድም ከሚያዝያ 23 አይወጣም፣
በዓለ ስቅለት ከመጋቢት 24 አይወርድም ከሚያዝያ 28 አይወጣም፣ በዓለ ትንሣኤ ከመጋቢት 26 አይወርድም ከሚያዝያ 30 አይወጣም፣ ርክበ ካህናት ከሚያዝያ 20 አይወርድም ከግንቦት 24 አይወጣም፣ በዓለ ዕርገት ከግንቦት 5 አይወርድም ከሰኔ 9 አይወጣም፣
በዓለ ጰራቅሊጦስ ከግንቦት 15 አይወርድም ከሰኔ 19 አይወጣም፣ ጾመ ሐዋርያት ከግንቦት 16 አይወርድም ከሰኔ 20 አይወጣም፣
ጾመ ድኅነት ከግንቦት 18 አይወርድም ከሰኔ 22 አይወጣም።

የ2018 ዓ/ም የበዓላትና የአጽዋማትን መግቢያ ቀናትና ዕለታት ለማወቅ አስቀድሞ ከዚህ በታች የተዘረዘሩትን መረዳትና አቀማመራቸውን ( FORMULA) ማወቅ ያስፈልገናል።

1ኛ መደብ
2ኛ ወንበር
3ኛ አበቅቴ
4ኛ መጥቅዕ
5ኛ መባጃ ሐመር
6ኛ ተውሳክ

⭕ መደብ
መደብ = ዓመተ ዓለምን በ19 በመግደፍ እናገኛለን።

⭕ ወንበር
ወንበር ከመደብ አንድን ለዘመን በመተው ወንበርን እናገኛለን።

⭕ አበቅቴ
አበቅቴ፦ ማለት ተረፈ ዓመት/ዘመን ማለት ነው። አበቅቴ በአንድ ዕለት ውስጥ ያሉትን የሌሊቱንና የጨረቃን ኅድረት ከመዓልት(ቀን) ለይቶ ለማወቅ ያስችላል።

⭕ መጥቅዕ
መጥቅዕ ማለት ነጋሪት ወይም ደወል ማለት ነው፡፡ ነጋሪት ሲመታ፣ ደወል ሲደወል ሕዝብ ይሰበሰባል፤ መልእክትም ይተላለፋል፡፡ በዓላትና አጽዋማትም በመጥቅዕ ይሰበሰባሉ፤ መዋያቸውንም በዚህ ማወቅ ይቻላል፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከዕለታት ተውሳክ ጋር ተደምሮ መባጃ ሐመርን ያስገኛል፡፡

⭕ መባጃ ሐመር
መባጃ ሐመር መባጊያ ሐመር እየተባለም ይጠራል፡፡ መባጊያ ሐመር ሲሆን የበጋ መመላለሻ የሚል ትርጉም ይሰጣል፡፡ በሌላ በኩል መባጃ በራሱ ማቆያ፣ ማክረሚያ ተብሎ ይተረጎማል፡፡
ሐመር መርከብ፣ መጓጓዣ የሚለውን ትርጉም ያስገኛል፡፡ መባጃ ሐመር የመጥቅዕና የዕለታት ተውሳክ ድምር ሆኖ አጽዋማትና በዓላት የሚውሉበትን ቀን ያመለክታል፡፡ በሐመር የተመሰለውም አጽዋማትና በዓላት ወደ ላይና ወደታች የሚመላለሱበት ሥርዓት /መርከብ/ ስለሆነ ነው፡፡

ከሰባቱ አጽዋማት መካከል ዐራቱ በመባጃ ሐመር መሠረት በየዓመቱ እየተቀያየሩ ወይም ቀመር እየተሠራላቸው የሚወጡ ሲሆን፣ ሦስቱ ግን ያለ መባጃ ሐመር በየዓመቱ በተመሳሳይ ወቅት ይባጃሉ፡፡
በመባጃ ሐመር የሚባጁት አራት አጽዋማት ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ድኅነት፣ ጾመ ነነዌና ጾመ ሐዋርያት ሲሆኑ፣ ያለ ማባጃ ሐመር በየዓመቱ ቋሚ ጊዜ ይዘው የሚብቱት ሦስቱ አጽዋማት ደግሞ ጾመ ነቢያት፣ ጾመ ገሃድና ጾመ ማርያም /ፍልሰታ/ ናቸው፡፡

ጾመ ነቢያት ( የገና ጾም) በአራቱም ዘመናት ምን ጊዜም ኅዳር 15 እንዲጾም ተወስኗል፡፡
ጾመ ገሀድ የምትክ ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም ዓርብንና ሮብን የሚያሽር በዓል በዓርብና በሮብ ሲውል በትኩ በዋዜማው የሚጾም ጾም ነው፡፡ ለምሳሌ ጥምቀት ዓርብ ቢውል ሐሙስ ጾመ ገሀድ ይሆናል፡፡ ነገር ግን አበው ለጾም ማድላት አለብን በማለት ጾመ ገሀድ ምንጊዜም ጥምቀት በጾም ቀን ዋለም አልዋለም በዋዜማው እንዲጾም ወስነዋል፡፡
ጾመ ፍልሰታ ለማርያም፦ ሐዋርያት የእመቤታችንን ትንሣኤ ለማየት ይበቁ ዘንድ ሱባኤ ገብተው የጾሙት ጾም ሲሆን ምንጊዜም ነሐሴ 1 ቀን ገብቶ ከኹለት ሱባኤ በኋላ የእመቤታችን ዕርገት ይፈጸማል፡፡

⭕ ተውሳክ
ተውሳክ ማለት ለአንድ ጾም ወይም ለአንድ ዕለት የተሰጠ ልዩ ቁጥር (ኮድ) ማለት ነው፡፡ በዚህ ቁጥር መሠረትም አጽዋማትንና በዓላትን ማውጣት ይቻላል፡፡
የዕለታት ተውሳክ በቅዳሜ ይጀምራል።
የቀዳሚት ሰንበት 8 ፣ የእሑድ ሰንበት 7 ፣ የሰኞ 6፣ የማክሰኞ 5፣ የረቡዕ 4፣ የሐሙስ 3 ፣ የዓርብ 2 ናቸው ።

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ
መጥቅዕ = ያለፈው ዓመት መጥቅዕ + ጥንተ መጥቅዕ
(ጥንተ መጥቅዕ በየዓመቱ የማይቀያየር ቁጥር ሲሆን ይኸውም 19 ነው፡፡)

‹‹መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ፤ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ››
ይህም ማለት መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ ማለት በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውል ማለት ሲሆን፣ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ ማለቱ መጥቅዕ ባነሰ ጊዜ በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውለው ማለት ነው፡፡

መጥቅዕ በዛ የሚባለው ከ14 በላይ ሲሆን ነው፤ አነሰ የሚባለው ደግሞ ከ14 በታች ሲሆን ነው፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከ14 በላይ ከሆነ በዓለ መጥቅዕ በመስከረም ይውላል፤ መጥቅዕ ከ14 በታች ከሆነ ደግሞ በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት ይውላል፡፡
ይህ ሁል ጊዜም ቢሆን የሚያገለግል ሕግ ነው፡፡

ለምሳሌ የ2018ን መባጃ ሐመር ለማግኘት ፦

መባጃ ሐመርን ከመፈለጋችን በፊት ግን መጥቅዕን ማወቅ የግድ ነው፡፡ መጥቅዕን ለማወቅ ደግሞ የወንበርን ዓመታዊ ስሌት ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም፤

መደብ = ( ቅልክ + ድልክ ) ÷ 19
= ( 5500 + 2018) ÷ 19 = 7518 ÷ 19
= 395 ቀሪ 13
= 13

ወንበር = መደብ — 1
= 13 — 1 = 12
የ2018 ዓ/ም ወንበር 12 ነው ማለት ነው፡፡

ከዚህ በመነሣት መጥቅዕን ለማግኘት፤

መጥቅዕ = ወንበር (ጥንተ መጥቅዕ) ÷ 30
= 12 (19) ÷ 30 = 228 ÷ 30
= 7 ቀሪ 18
መጥቅዕ = 18

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ
የ2018 ዓ/ም መጥቅዕ = 18 ነው ብለናል ።
በዓለ መጥቅዕን ለማግኘት፤ መጥቅዕ ከ14 በላይ ስለሆነ መስከረም ላይ በዓለ መጥቅዕ ይውላል፡፡ ስለዚህ መስከረም 18 እሑድ በዓለ መጥቅዕ ሲሆን፤ ይህ በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ዕሑድ ተውሳኩ 7 ነው ማለት ነው፡፡

ስለዚህ፤
መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ = 18
በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት= እሑድ
የዕሑድ ተውሳክ = 7

መባጃ ሐመር = 18 + 7 = 2️⃣5️⃣

ስለዚህ የ2018 ዓ.ም መባጃ ሐመር 25 ስለሆነ በዚህ መሠረት የ2018 ዓ/ም በዓላትና አጽዋማት ማውጣት ይቻላል፡፡

የመባጃ ሐመር ዋነኛ አገልግሎት ከአጽዋማት ተውሳክ ጋር እየተደመረ በዓላትንና አጽዋማትን ማስገኘት ነው፡፡ ስለዚህ የአጽዋማትንና የበዓላትን ተውሳክ ማወቅ ይጠበቅብናል፡፡በመሆኑም መባጃ ሐመሩንና የበዓላትና የአጽዋማትን ተውሳክ በመጠቀም የ2018 ን የበዓላትና የአጽዋማትን መግቢያ እናገኛለን፡፡

⭕ ጾመ ነነዌ
ጾመ ነነዌ የራሱ የሆነ ተውሳክ የለውም፡፡ የሚወጣውም ያለ ተውሳክ በመባጃ ሐመር ብቻ ነው፡፡

ሀ. በዓለ መጥቅዕ በመስከረም በሚውልበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በጥር ይውላል፡፡
ለ. በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት በሚሆንበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡
ሐ. መጥቅዕ ከ፲፬(14) በላይ ሆኖ ከዕለት ተውሳክ ጋር ስንደምረው ከ፴(30) ከበለጠ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡

ከላይ የተዘረዘሩት ዐራት ነጥቦች መቼም ቢሆን የማይለወጡ ቋሚ ሕጎች ናቸው፡፡ በመሆኑም እነዚህን አራቱን በቃል አጥንቶ መያዝ ያስፈልጋል፡፡

ከላይ የተመለከትነውን የ2018 ዓ/ም ጾመ ነነዌ እናውጣ፡

መጥቅዕ 18 ሲሆን በዓለ መጥቅዕ መስከረም 18 እሑድ ነው፡፡ መባጃ ሐመሩ ደግሞ 2️⃣5️⃣ ነው፡፡ ከላይ በ “ሀ.” እንደተመለከተው በዓለ መጥቅዕ በመስከረም በሚውልበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በጥር ይውላል ብለናል፡፡
በተጨማሪም ጾመ ነነዌ ተውሳክ ስለሌላት በመባጃ ሐመር ብቻ ነው የምትወጣ ብለናል፡፡ ስለዚህ መባጃ ሐመሩ 2️⃣5️⃣ ስለሆነ ጥር 25 ቀን ጾመ ነነዌ ትገባለች ማለት ነው፡፡

⭕ ዐቢይ ጾም
የዐቢይ ጾምን ተውሳክ ለማግኘት ከጾመ ነነዌ ማግስት ጀምሮ እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት መቁጠር ነው፡፡ እኒህም ቀናት ፲፬(14) ናቸው፡፡ በመሆኑም የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ማለት ነው፡፡

የ2018 ዐቢይ ጾም መግቢያ = የ 2018 ዓ/ ም መባጃ ሐመር +
የዐቢይ ጾም ተውሳክ
መባጃ ሐመር = 2️⃣5️⃣
የዐቢይ ጾም ተውሳክ = ፲፬(14)
የዐቢይ ጾም መግቢያ = 25 + 14 = 39
39 — 30 = 9
ሰኞ የካቲት 9 ቀን የዐቢይ ጾም መግቢያ ነው ማለት ነው፡፡

⭕ ደብረ ዘይት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት ቆጥረን የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ብለናል፡፡ የደብረ ዘይትን ተውሳክ ለማግኘትም በተመሳሳይ መልኩ ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ደብረ ዘይት ያሉትን ቀናት ስንቆጥር ፵፩(41) ቀናትን እናገኛለን፡፡ ለ፴(30) ሲካፈል ቀሪ (፲፩)11ን እናገኛለን፡፡ ስለዚህ የደብረ ዘይት ተውሳክ ፲፩(11) ነው ማለት ነው፡፡
ደብረ ዘይት = የ2018 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የደብረ ዘይት ተውሳክ
= 2️⃣5️⃣ + 11 = 36
36 — 30 = 6
ከየካቲት ቀጥሎ ያለው ወር መጋቢት ስለሆነ መጋቢት 6 ቀን እሑድ ደብረ ዘይት ይሆናል ማለት ነው፡፡

⭕ ሆሣዕና
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ሆሣዕና ያሉት ቀናት ፷፪(62) ናቸው፡፡ እንደተለመደው ለ፴(30) ስናካፍለው ፪(2) ቀሪ እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የሆሣዕና ተውሳክ (፪)2 ነው ማለት ነው፡፡
ሆሣዕና = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የሆሣዕና ተውሳክ
= 2️⃣5️⃣ + 2 = 27
በ2018 ዓ.ም መጋቢት 27 ቀን እሑድ በዓለ ሆሣዕና ይሆናል ማለት ነው፡፡

⭕ ስቅለት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ስቅለት ያሉት ቀናት ሥልሳ ሰባት ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፯(7)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የስቅለት ተውሳክ ፯/7/ ነው ማለት ነው፡፡
ስቅለት = የ2018 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ
= 2️⃣5️⃣ + 7 = 32
30 — 2 = 2
በ2018 ዓ/ ም ዓርብ ሚያዝያ 2 ቀን በዐለ ስቅለት ይሆናል ማለት ነው፡፡

⭕ ትንሣኤ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ትንሣኤ ያሉት ቀናት ሥልሳ ዘጠኝ ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፱(9) እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የትንሣኤ ተውሳክ ፱ (9) ነው ማለት ነው፡፡

ትንሣኤ = የ2018 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የትንሣኤ ተውሳክ
= 2️⃣5️⃣ + 9 = 34
34—30 = 4
በ2018 ዓ/ ም እሑድ ሚያዝያ 4 ቀን በዐለ ትንሣኤ ይሆናል ማለት ነው፡፡

⭕ ርክበ ካህናት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ርክበ ካህናት ያሉት ቀናት ፺፫(93) ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለውቀሪ ፫(3)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የርክበ ካህናት ተውሳክ ፫(3) ነው ማለት ነው፡፡
ርክበ ካህናት = የ2018 መባጃ ሐመር + የርክበ ካህናት ተውሳክ
= 2️⃣5️⃣ + 3 = 28
በ2018 ዓ/ም ረቡዕ ሚያዚያ 28 ቀን ርክበ ካህናት ይሆናል ማለት ነው፡፡

⭕ ዕርገት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ በዓለ ዕርገት ያሉት ቀናት ፻፰(108) ናቸው፡፡ ፻፰(108)ን ለ፴(30) ስናካ ፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፲፰(18) ይቀራል፡፡ በመሆኑም የዕርገት ተውሳክ ፲፰(18) ነው ማለት ነው፡፡
ዕርገት = የ2018 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ
= 2️⃣5️⃣ + 18 = 43
43 — 30 = 13
በ2018 ዓ/ ም ሐሙስ ግንቦት 13 ቀን ዕርገት ይሆናል ማለት ነው፡፡

⭕ ጰራቅሊጦስ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጰራቅሊጦስ ያሉት ቀናት ፻፲፰(118)ናቸው፡፡ ፻፲፰(118)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ቀሪ ፳፰(28) ይሆናል፡፡
፳፰(28) የጰራቅሊጦስ ተውሳክ ይሆናል፡፡
ጰራቅሊጦስ = የ2018 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጰራቅሊጦስ ተውሳክ
= 2️⃣5️⃣ + 28 = 53
53 — 30 = 23
በ2018 ዓ.ም በዐለ ጰራቅሊጦስ ግንቦት 23 ቀን እሑድ ይሆናል ማለት ነው፡፡

⭕ ጾመ ሐዋርያት ( የሰኔ ጾም)
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ሐዋርያት ያሉት ቀናት ፻፲፱(119) ናቸው፡፡ ፻፲፱ (119)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፳፱ (29) ይቀራል፡፡
፳፱(29) የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ ነው ማለት ነው፡፡
ጾመ ሐዋርያት = የ2018 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ
= 2️⃣5️⃣ + 29 = 54
54 — 30 = 24
በ2018 ዓ.ም ሰኞ ግንቦት 24 ቀን የጾመ ሐዋርያት መግቢያ ይሆናል ማለት ነው፡፡

⭕ ጾመ ድኅነት ( ረቡዕ እና ዐርብ )
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ድኅነት ያሉት ቀናት ፻፳፩(121) ናቸው፡፡ ፻፳፩(121) ለ፴(30) ሲካፈል ፬(4) ጊዜ ደርሶ ፩(1) ይቀራል፡፡ የጾመ ድኅነት ተውሳክ ፩(1) ነው ማለት ነው።
ጾመ ድኅነት = የ2018 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ድኀነት ተውሳክ
= 2️⃣5️⃣ + 1 = 26
በ2018 ዓ/ም ግንቦት 26 ቀን የጾመ ድኅነት መግቢያ ዕለት ይሆናል ማለት ነው፡፡

በዚህም መሠረት በ2018 ዓ/ም መስቀል መስከረም 17 ቀን ቅዳሜ፣ ጾመ ነቢያት ( የገና ጾም) ኅዳር 15 ቀን ሰኞ፣ ጥምቀት ጥር 11 ቀን ሰኞ ፣ ጾመ ነነዌ ጥር 2️⃣5️⃣ ቀን ሰኞ፣ ዐቢይ ጾም የካቲት 9 ቀን ሰኞ፣ ደብረ ዘይት መጋቢት 6 ቀን እሑድ፣ ሆሣዕና መጋቢት 27 ቀን እሑድ፣ ስቅለት ሚያዚያ 2 ቀን ዐርብ፣ ትንሣኤ ሚያዚያ 4 ቀን እሑድ፣ ጰራቅሊጦስ ግንቦት 23 ቀን እሑድ፣ ዕርገት ግንቦት 13 ቀን ሐሙስ የሚውሉ ይሆናል።

በአጠቃላይ ግን የተፈለገውን ዓመት ( ያለፈውንም፣ ያኹንም የወደፊትንም) የተፈለገውን ዓመት የበዐላትና የአጽዋማት ተውሳክና መባጃ ሐመር ለማግኘት ወይም ለማወቅ የነነዌ ጾም መነሻ (የበዐላት ሁሉ መሠረት) ስለሆነ ጾሙ የሚጀምርበት ቀን በባህረ ሐሳብ ዘዴ መፈለግ ያስፈልገናል፡፡ የነነዌ ጾም የሚጀምርበትን ቀን ካገኘን ሌሎቹ በዐላትና አጽዋማት ከእሱ የሚርቁበት በተውሳካቸው ስለሆነ ተውሳካቸው እየተደመረበት የሚውሉበት ቀን ይገኛል፡፡ በዚህም መሠረት የበዐላቱና የአጽዋማቱ ተውሳካቸው እንደሚከተለው ይቀርባል፡፡

የበዐላቱና አጽዋማቱ ተውሳካቸው

ነነዌ ————————————– ( መባጃ ሐመር )
በአተ ጾም (ሁዳዴ የሚገባበት) ——— 14 (14)
ደብረ ዘይት ——————————— 11 (41)
ሆሣዕና ————————————- 2 (62)
ስቅለት ————————————- 7 (67)
ትንሣኤ ———————————— 9 (69)
ረክበ ካህናት —————————– 3 (93)
ዕርገት ———————————— 18 (108)
ጰራቅሊጦስ (ጴንጠቆስጤ) ————- 28 (118)
ጾመ ሐዋርያት (የሰኔ ጾም) ————— 29 (119)
ጾመ ድኅነት —————————— 1 (121)

የዕለታት ተውሳክ

ቅዳሜ ———————————– 8
እሑድ ———————————— 7
ሰኞ ———————————— 6
ማክሰኞ ———————————— 5
ረቡዕ ———————————— 4
ኀሙስ ———————————— 3
ዓርብ ———————————— 2

አዳም የተፈጠረው በዕለተ ዓርብ ነው። ከ40 ቀን በኋላም ወደ ገነት እግዚአብሔር አስገባው። አዳምም የእግዚአብሔርን ሕግ እየጠበቀ 7 ዓመት ከ1 ወር ከ17 ቀን በገነት ተቀመጧል። ከዚያ በኋላ አትብላ የተባለውን እጸ በለስ ስለበላ ተፈረደበት። አዳምም ንሥሓ በገባ ጊዜ እግዚአብሔር ከ5500 ዘመን በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ የሚል ተስፋ ሰጠው። የአዳም ልጆችም ይህን ይዘው ጌታ ሰውን ለማዳን የሚመጣበትን ጊዜ በፀሐይ በጨረቃ በከዋክብት እየቆጠሩ ይኖሩ ነበር። የዘመን ቁጥር የተጀመረበት ምክንያቱ ይህ ነው።

ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፤

ዓለም ከተፈጠረ በ5500 ዘመን በዘመነ ዮሐንስ መጋቢት 29 እሑድ ቀን በ 3:00 ሰዓት ተጸነሰ፤
ዓለም ከተፈጠረ በ5501 ዘመን ወይም በ1 ዓመተ ምሕረት በዘመነ ማቴዎስ ታኀሣሥ 29 ቀን ማክሰኞ ከሌሊቱ 10:00 ሰዓት ተወለደ።
በ5531 ዘመን ወይም በ31 ዓመተ ምሕረት ዘመነ ሉቃስ ጥር 10 ቀን ለ11 አጥቢያ ማክሰኞ ከሌሊቱ 10:00 ሰዓት ተጠመቀ።
በ5533 ዘመን ወይም በ33 ዓመተ ምሕረት ዘመነ ማቴዎስ ነሐሴ 13 እሑድ ቀን በቀትር ጊዜ ብርሃነ መለኮቱን ለሐዋርያት በደብረ ታቦር ገለጠ።
በ5534 ዘመን (በ34 ዓ.ም) በዘመነ ማርቆስ መጋቢት 22 ቀን እሑድ በአህያ ውርንጭላ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ (ሆሣዕና)።
በ5534 ዓ.ዓ (በ34 ዓ.ም) በዘመነ ማርቆስ መጋቢት 26 ቀን ሐሙስ በሠርክ ጌታችን መስዋዕተ ኦሪትን በመስዋዕተ ወንጌል የተካበት ነው።
በ5534 ዓ.ዓ (በ34 ዓ.ም) በዘመነ ማርቆስ መጋቢት 27 ቀን ቀትር በ6:00 ሰዓት ተሰቅሎ በ9:00 ሰዓት ነፍሱን ከሥጋው ለይቶ ሠርክ በ11:00 ሰዓት የተቀበረበት ነው።
በ5534 ዓ.ዓ ( በ34 ዓ.ም) በዘመነ ማርቆስ መጋቢት 29 ቀን እሑድ መንፈቀ ሌሊት ከሙታን ተለይቶ የተነሣበት ነው።
በ5534 ዓ.ዓ (በ34 ዓ.ም) በዘመነ ማርቆስ ግንቦት 8 ቀን በ 3:00 ሰዓት ያረገበት ነው።

ዓመታት፣ ወራት፣ ሳምንታት፣ ዕለታትና ሰዓታት የሚለኩት (የሚሠፈሩት፣ የሚቈጠሩት) በሰባቱ መሥፈሪያና በሰባቱ አዕዋዳት ነው፡፡
ሰባቱ መሥፈርታት የሚባሉትም፡- ሳድሲት፣ ኃምሲት፣ ራብዒት፣ ሣልሲት፣ ካልዒት፣ ኬክሮስ እና ዕለት ሲኾኑ ፤
ሰባቱ አዕዋዳት ደግሞ፡- ዐውደ ዕለት፣ ዐውደ ወርኅ፣ ዐውደ ዓመት፣ ዐውደ ፀሐይ፣ ዐውደ አበቅቴ፣ ዐውደ ማኅተም እና ዐውደ ቀመር ናቸው፡፡
አዕዋድ ዖደ ከሚል የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ዞረ ማለት ሲሆን፤ በየጊዜው እየዞረ የሚመጣ ማለት ነው።
ዓመተ ዓለም የሚሠፈርበት ሰባት አዕዋዳት ሲተነተኑ ፦

★ ዐውደ ዕለት –
ከእሑድ እስከ ቅዳሜ ያሉት ሰባቱ ዕለታት ሲኾኑ፤ አውራኅን (ወራትን) ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
★ ዐውደ ወርኅ – በፀሐይ ፴ (30) ዕለታት፣ በጨረቃ ፳፱ (29) ወይም ፴ (30) ዕለታት ናቸው፤ ዓመታትን ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
★ ዐውደ ዓመት –
በፀሐይ ቀን አቈጣጠር ፫፻፷፭ (365) ቀን ከ፲፭ (15) ኬክሮስ፤ በጨረቃ አቈጣጠር ፫፻፶፬ (354) ቀን ከ፳፪ (22) ኬክሮስ ነው፡፡
እነዚህ ሦስቱ በዕለት፤ አራቱ ደግሞ በዓመት ይቈጠራሉ፡፡
ዘመናትን ለማስገኘት በዚህ ሲመላለሱ ይኖራሉ፡፡
★ ዐውደ ፀሐይ –
፳፰ (28) ዓመት ነው፤ በዚህ ዕለትና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፡፡
★ ዐውደ አበቅቴ –
፲፱ (19) ዓመት ነው፤ በዚህ ፀሐይና ጨረቃ ይገናኙበታል፡፡
★ ዐውደ ማኅተም –
፸፮ (76) ዓመት ነው፤ በዚህ አበቅቴና ወንጌላዊ ይገናኙበታል፡፡
★ ዐውደ ቀመር –
፭፻፴፪ (532) ዓመት ነው፤ በዚህ ዕለትና ወንጌላዊ፣ አበቅቴም ይገናኙበታል፡፡
ዐውደ ቀመር ዘላለም የሚመላለስ ሲሆን፤ ከ5500 ዓ.ዓ. ጀምሮ 14 ጊዜ ተመላልሷል፡፡ ይኸውም፦ ( 5500 + 2017 ) / 532 = 14

የዘመናት (የጊዜያት) ክፍል እና መጠን
አንድ ዓመት በፀሐይ ፫፻፷፭ (365) ቀን ከ፲፭ (15) ኬክሮስ፤
አንድ ዓመት በጨረቃ ፫፻፶፬ (354) ቀን ከ፳፪ (22) ኬክሮስ ነው፡፡
አንድ ወር በፀሐይ ፴ (30) ዕለታት አሉት፤
አንድ ወር በጨረቃ ፳፱ (29) ወይም ፴ (30) ዕለታት አሉት፡፡
አንድ ዕለት ፳፬ (24) ሰዓት፤ አንድ ቀን ፲፪ (12) ሰዓት፤ አንድ ሰዓት ፷ (60) ደቂቃ ነው፡፡ አንድ ደቂቃ ፷ (60) ካልዒት፤ አንድ ካልዒት ፩ ( 1) ቅጽበት ነው፡፡
ኬክሮስ ማለት የክፍለ ዕለት ሳምንት (የዕለት ፩/፷ [ 1/60) ወይም ፩/፳፬ኛ (1/24) ሰዓት ] ነው፡፡ አንድ ዕለት ፳፬ (24) ሰዓት ወይም ፷ (60) ኬክሮስ ነው፡፡

ዓለም ከተፈጠረ ዘመን ከተቆጠረ ጀምሮ እስከ ዛሬ ያለው ዘመን በዓመተ ፀሐይ ሲቆጠር 7517 ዓመተ ዓለም ነው።

ዘመናት ሲቆጠሩ ዘመነ ማቴዎስ፣ ዘመነ ማርቆስ፣ ዘመነ ሉቃስ እና ዘመነ ዮሐንስ ናቸው። ሁልጊዜም ከዘመነ ሉቃስ ወደ ዘመነ ዮሐንስ ስንሸጋገር ጳጒሜን 6 ትሆናለች። ይህ እንዴት ሆነ?
3ቱ ዓመታት ( ዘመነ ዮሐንስ፣ ዘመነ ማቴዎስ፣ ዘመነ ማርቆስ) 365 ቀናት ከ6 ሰዓት ይይዛሉ። ስለዚህ የሦስቱ ዓመታት የ6 ሰዓታት ጥርቅም 18 ይሆናል። ዘመነ ሉቃስ ተገባዶ ወደ ዘመነ ዮሐንስ ስንሸጋገር 18+6=24 ሰዓት ( አንድ ቀን) ይሆናል። ስለዚህ በ4 ዓመቱ ጳጉሜን 6 ትሆናለች። በፈረንጆቹ leap year ይሉታል እሱም February ወር 29 ቀናትን ይይዛል ። በእኛ መጠነ ራብዒት ማለትም ዘመነ ዮሐንስ የሚውልበት ነው።
ቀደምት አባቶች ጳጒሜን 7 ቀናትን የምትይዝበት ዓመት እንዳለ ጽፈው አስቀምጠዋል። ይህም በ600 ዓመት አንዴ ይከሰታል። በቀን በ24 ሰዓታት ውስጥ ተጨማሪ 0.4 ሰከንድ አለ። ሪና መዐልትና ሪና ሌሊት የሚል ሌላም ስሌት አለ።
በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር አንድ ዓመት 365 ቀናት ከ15 ኬክሮስ ከ6 ካልዒት ወይንም 365 ቀናት ከ6 ሰዓት ከ2 ደቂቃ ከ24 ሰከንድ ነው። ስለዚህ 2 ደቂቃ ከ24 ሰከንድ ተጠራቅሞ ጳጒሜን 7 ያደርጓታል። ካልዒት ማለት 24 ሰከንድ ማለት ነው።
የ5 ዓመት 30 ካልዒት የ10 ዓመት 60 ካልዒት ነው።
60 ካልዒት ደግሞ 24 ሰከንድ ነው።
የ100 ዓመት 240 ሰከንድ ወይም 10 ኬክሮስ
የ200 ዓመት 20 ኬክሮስ፣
የ300 ዓመት 30 ኬክሮስ፣
የ400 ዓመት 40 ኬክሮስ፣
የ500 ዓመት 50 ኬክሮስ፣
የ600 ዓመት 60 ኬክሮስ።
60 ኬክሮስ 1440 ደቂቃ ወይም 24 ሰዓት ይሆናል።
ስለዚህ በ600 ዓመት አንድ ጊዜ ጳጒሜን 7 ይሆናል።

የጳጒሜን ወር ከዚህ ቀደም 7 ቀን የሆነችው በ1700 ዓ/ም ወይም በ7800 ዓመተ ዓለም ነበር። ቀጣዩ ከ 283 ዓመት በኋላ ወይም በ2300 ዓ/ም ላይ ይሆናል ፡፡

ኬክሮስ – ብርሃናት የሚመላለሱበት ከሰሜን እስከ ደቡብ የተዘረጋ የሐሳብ መስመር ነው።
ኬንትሮስ – ብርሃናት የሚመላለሱበት ከምሥራቅ እስከ ምዕራብ የተዘረጋ የሐሳብ መስመር ነው።

ባሕረ ሐሳብ ማለት ምን ማለት ነው?

ባሕረ ሐሳብ ማለት ቁጥር ያለው ዘመን ማለት ነው፡፡ በሌላ አገላለጽም የሐሳብ ባሕር ማለት ነው፡፡ በዓላት እና አጽዋማትን ለማውጣት የመደመር፣ የመቀነስ፣ የማባዛት ስሌትን ብቻ ሳይሆን ሐሳበ ፀሐይን፣ ሐሳበ ወርኅን፣ ሐሳበ ከዋክብትን ሐሳበ ዐበቅቴን ወዘተ አጠቃሎ የያዘ እንደ ባሕር የሰፋ በመሆኑ የሐሳብ ባሕር ተብሏል፡፡ የዘመን አቈጣጠር ማለት ስለማኅበራዊ ኑሮ ጠቄሜታና የሃይማኖት ተግባሮች ለማከናወን በሚያገለግል መልኩ ተፈጥሮአዊውን የወቅቶች ክፍፍል እርስ በርሳቸው የማመቻቸት ዘዴ ነው፡፡
ሐሳበ ዘመን የዘመን አቆጣጠር ማለት ሲሆን የሐሳበ ዘመን ትምህርት ባሕረ ሐሳብ ይባላል፡፡ ባሕረ ሐሳብ የሚለው ቃል ሐሰበ ቆጠረ ከሚለው ግስ የወጣ ዘመድ ዘር ነው፡፡ ስለዚህ ባሕረ ሐሳብ ማለት ቁጥር ያለው ዘመን ወይም ዓመተ ዓለም ማለት ነው፡፡ ባሕረ ሐሳብ
መባሉም የባሕር አዝዋሪቱ፣ መንገዱን፣ ጥልቀቱና ስፋቱ ረዥምና ሰፊ እንደሆነ የባሕረ ሐሳብ ትምህርትም መንገዱን ስፋቱ ልዩ ልዩ በሆነ የአጽዋማትና የሱባዔያት ምሥጢር የተሰናዳ ስለሆነ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር /የጊዜ ቀመር/ አንድ ዓመት በውስጡ ዐሥራ ሦስት ወራትን የያዘ ሆኖ በአራት ወቅቶች የተከፈለ ነው፡፡
አራቱ ክፍላተ ዘመን የሚባሉት፡-
✨ ክረምት ከሰኔ 26 ቀን – መስከረም 25 ቀን፣
✨ መፀው /መከር/ ከመስከረም 26 ቀን – ታኅሣሥ 25 ቀን፣
✨ በጋ / ሐጋይ/ ከታኅሣሥ 26 ቀን – መጋቢት 25 ቀን፣
✨ ጸደይ / በልግ/ ከመጋቢት 26 ቀን – ሰኔ 25 ቀን ናቸው፡፡

ከክረምት በስተቀር እያንዳንዱ ወቅት በውስጡ ዘጠና ዘጠና ቀናት ይዟል፡፡ ክረምት ግን ለብቻው 95 ቀናትን የያዘ ነው፡፡

ዐራቱ ክፍላተ ዘመን
የቅዱስ ያሬድ ድርሰቶች ጊዜ፣ ወር፣ ዘመን አላቸው፡፡ አንድን ዓመት በዐራት ክፍለ ዘመን በመክፈል ድርሰቱን ውሱን አድርጎታል፡፡ ዘመኑም እንዲሁ በድርሰቱ የተወሰነ ሆኗል፡፡ እነዚህም ዘመናት ዘመነ መፀው፣ ዘመነ ሐጋይ፣ ዘመነ ጸደይ፣ ዘመነ ክረምት በመባል ይታወቃሉ፡፡

2.1. ዘመነ መፀው

መፀው በሌላ አነጋገር ጥቢ ይባላል፡፡ እንደ ሌሊት ከብዶ የሚታየው ክረምት አልፎ መስከረም ከጠባ በኋላ በ4ኛው ሳምንት ስለሚጀምር ነው ጥቢ የሚባል ተጨማሪ ስያሜ የተሰጠው፡፡
ዘመነ መፀው ከመስከረም 26 እስከ ታኅሣሥ 25 ድረስ ያለው ጊዜ ነው፡፡ የዕለቱ ቁጥርም 90 ይሆናል፡፡ ከዘመነ ክረምት ቀጥሎ በመሆኑ ዘመነ ክረምትን በማስቀደም ጽጌንና መፀውን በማስተባበር ቅዱስ ያሬድ የሚከተለውን ብሏል፡፡ “ግሩም በሆነው ኃይልህ እንመካ ዘንድ አንተ ዘመናትን ሠራህ ክረምትን ለዝናባት መፀውን ለአበቦች
ሰጠህ” ድጓ ዘጽጌ ኩፋሌ 2 ኢዮ.2÷23 ኤር.5፥24/

መፀው መሬት በክረምት የተሰጣትን ዘር አበርክታ፣ አብዝታ ለፍሬ የምታደርስበት የምርት ወቅት ነው፤ መፀው በአብዛኛው የአዝመራ መሰብሰቢያ ጊዜው ነው፡፡ በዚህ ክፍለ ዘመን በዋናነት ሦስት ወራት ያገኛሉ፤ እነርሱም ጥቅምት፣ ኅዳርና ታኅሣሥ ናቸው፡፡ ይህ ወቅት
በኢትዮጵያ ምድር አበቦች በየሜዳው በየሸንተረሩና በየተራራው ፈክተው የሚታዩበት አዝርእት የሚያሸቱበትና ለፍሬ የሚበቁበትን ወራት ይዞ ይገኛል፡፡

2.2. ዘመነ ሐጋይ /በጋ/

ዘመነ ሐጋይ ይህ የበጋ ወቅት ነው፡፡ “ሐጋይ”…. በጋ ሆነ ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ነው፡፡ ይህም ከታኅሣሥ 26 እስከ መጋቢት 25 ቀን ያለውን ጊዜ ያጠቃልላል፡፡ ሐጋይ በጋ የጥርን፣ የየካቲትንና የመጋቢትን ወር ይይዛል፡፡
ዘመነ ሐጋይ የቃሉ ትርጓሜ ዘመነ ፀሐይ ማለት ሲሆን ሥርወ ቃሉም ኃገየ … ከሚለው ግእዝ የተገኘ ነው፡፡ ከዐራቱ ክፍላተ ዘመን አንዱ እጅ ወይም አንድ አራተኛው ሐጋይ ይባላል፡፡ የሐጋይ ፍቺ በጋ እንደሆነ ሁሉ እንዲሁም መፀውም ጸደይም በእርሱ ስም በጋ ይባላሉ፡፡
“ዘጠኝ ወር በጋ” እንዲሉ፣ አንዳንድ ጊዜም መጽሐፍት በሁለት ከፍለው ይናገራሉ፡፡ “ክረምትና በጋን አንተ ሠራህ” ፤ “በበጋም በክረምትም እንዲህ ይሆናል” / መዝ.75፥17፣ ዘካ.14፥10፣ ዘፍ.10፥22/ እንዲል
ኃጋይ ማለት መገኛ መክረሚያ በጋ፣ ፀደይ፣ ደረቅ ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በመፀው ያሸተውና ያፈራው መኸር የሚታጨድበት፣ የሚሰበሰብበትና በየማሳው ከተከመረ በኋላ የሚበራይበት፣ በጎተራ የሚከተትበት በመሆኑ “የካቲት” የሚለውን ወር ይዞ እናገኘዋለን፡፡ የግብርናው ኅብረተሰብ እህሉን በጎተራው ከትቶ ለተወሰነ ጊዜ
የሚያርፍበት በመሆኑ የዓመት በዓላት እንደ ልደት፣ ጥምቀት ያሉት፣ ዘመነ መርዓዊ የሚባለው የጋብቻ ዘመን በዚህ ወቅት የተካተቱ ናቸው፡፡

2.3. ዘመነ ጸደይ /በልግ/

ዘመነ ጸደይ ማለት የቃሉ ትርጉም ዘመነ በልግ (የበልግ ዘመን) ማለት ነው፡፡ ጸደይ በበጋና በክረምት መካከል የሚገኝ በውስጡ የሚያዝያን፣ የግንቦትንና የሰኔ ወራትን የያዘ ክፍለ ዘመን ነው፡፡ በመሆኑም ጸደይ የሌሎች ወቅቶችን ባሕርያት አሳምሮ የያዘ ነው፡፡ ምክንያቱም በአንድ በኩል የበልግ አዝመራ የሚታጨድበት የሚወቃበትና የሚዘራበት ሲሆን፤ በሌላ በኩል ደግሞ ለክረምት የሚዘራ ማሳ የሚታረስበት /ለዘር ዝግጁ የሚሆንበትን ጊዜ ነው፡፡ በአብዛኛው ግን ዘመነ በልግ ነው፡፡
ቅዱስ ያሬድ በድጓው “ይሁብ ዝናመ ተወን” የበልግ ዝናምን ይሰጣል እንዳለው የበልግ ወቅት ነው፡፡ ይህም ወቅት በልግ አብቃይ በሆነው የሀገራችን ክፍል የበልግ አዝመራ የሚዘራበት፣ በልግ አብቃይ ባልሆነው ክፍል ደግሞ መሬት ለክረምቱ የዙር ጊዜ የሚያዘጋጅበት ነው፡፡
“አንድ ሰኔ የነቀለውን ሁለት ሰኔ አይተካውም” እንደሚባለው የግብርናው ኅብረተሰብ ቀጣይ የግብርና ሥራውን በትጋት የሚሠራበት ወቅት ነው፡፡

2.4. ዘመነ ክረምት

ዘመነ ክረምት ማለት ዘመነ ውሃ ማለት ነውና በዚህ ዘመን ውኃ ይሰለጥናል፡፡ ውሃ አፈርን ያጥባል፣ እሳትን ያጠፋል፣ ቢሆንም በብሩህነቱ ከእሳት፣ በቀዝቃዛነቱ ከነፋስ፣ በእርጥብነቱ ከመሬት ጋር ተስማምቶ ይኖራል፡፡
ክረምት በውስጡ አራት ወራትን /ሐምሌ፣ ነሐሴ፣ ጳጒሜንና መስከረም/ የያዘ ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ “ያረሁ ክረምተ በበዓመት፣ ይሰምዑ ቃሎ ደመናት፣ በየዓመቱ ክረምትን ያገባል፤ ደመናትም ቃሉን ይሰሙታል” ሲል በድጓው እንደነገረን የዘመናት ጌታ ልዑል እግዚአብሔር በየዓመቱ አዙሮ የሚያመጣልን ወቅት ነው፡፡ ደመናትም
ለቃሉ ትእዛዝ ተገዢዎች በመሆን ዝናመ ምሕረቱን ጠለ በረከቱን የሚያወርዱበት ጊዜ ነው፡፡ ከሰኔ 26 እስከ መስከረም 25 ድረስ ያለውን ጊዜ ይይዛል፡፡

ዓመተ ወንጌላውያን
የሦስቱ ወንጌላውያን ማለትም የዮሐንስ፣ የማቴዎስና፣ የማርቆስ ዘመናት እያንዳንዳቸው ከመስከረም 1 ጀምሮ እስከ ጳጉሜን 5 ድረስ 365 ቀን ከስድስት ሰዓት ነው፡፡ ዘመነ ሉቃስ ግን ከመስከረም 1 እስከ ጳጉሜን 6 ቀን በመሆኑ 366 ቀናት ይኖሩታል፡፡

ወራት
በግእዝ ቋንቋ “ወርኅ” የምንለው ቃል በአማርኛ ወር እንለዋለን ይህም ወደ ብዙ ቁጥር ሲለወጥ ወራት ይሆናል፡፡ በኢትዮጵያ ዘመን አቈጣጠር እያንዳንዳቸው 30 ቀናት ያሏቸው 12 ወራት፣ 5 ወይም በየዐራት ዓመት 6 ቀናት የሆነች ጳጉሜን ያሉ ሲሆን በአውሮፓውያን
አቈጣጠር ግን የየወሩ የቀናት ቁጥር ለየት ይላል፡፡

የወራቱ ስም የግእዝ መገኛው እና አማርኛው አቻ ትርጉም

1 የወሩ ስም – መስከረም
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – መሴ እና ከረም
ትርጉም – መሴ-አለፈ ፣ መሸ ፤ ከረም-ክረምት፤ ክረምት አለፈ ፣ ክረምቱ መሸ
2 የወሩ ስም – ጥቅምት
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – ጠቀመ
ትርጉም – ሠራ፤ ጠቃሚ ጊዜ
3 የወሩ ስም – ኅዳር
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – ኀደረ
ትርጉም – አደረ-ሰው በወርኃ ኅዳር አዝመራ ማሳ ውስጥ ለጥበቃ ማደሩን ይገልፃል
4 የወሩ ስም – ታኅሣሥ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – ኀሠሠ
ትርጉም – መረመረ — ፈለገ— በመኸር ወቅት የሰብል ምርመራን ያመለክታል ፤ ሰብዐ ሰገል በታኅሣሥ ወር የተወለደውን ጌታችንን ማሰሳቸውን ፣ መፈለጋቸውንም ያመለክታል።
5 የወሩ ስም – ጥር
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – ነጠረ ፣ አጥረየ፣ ጠየረ
ትርጉም – ነጠረ – ጠረረ- ብልጭ አለ፤ ነጻ፤ የፀሐይን ግለት ወቅት ያሳያል ፤ አጥረየ – ገዛ (ከብቱም ምርቱም የሚሸጥበት የሚገዛበት ወቅት)
6 የወሩ ስም – የካቲት
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – ከተተ ፣ ከቲት
ትርጉም – መክተቻ (እኅልን ወደ ጎተራ)
7 የወሩ ስም – መጋቢት
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – መገበ
ትርጉም – በቁሙ የሚመግብ (በጎተራ የተከተተው የሚበላበት)
8 የወሩ ስም – ሚያዝያ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – መሐዘ
ትርጉም – ጎለመሰ ጎበዘ ሚስት ፈለገ (ወርኀ ሰርግ መሆኑን ሲያጠይቅ)
9 የወሩ ስም – ግንቦት
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – ገነበ
ትርጉም – ገነባ፤ ሠራ፤ ቆፈረ፤ ሰረሰረ (ለእርሻ የመሬቱን መዘጋጀት ያሳያል)
10 የወሩ ስም – ሰኔ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – ሰነየ
ትርጉም – አማረ (አዝርዕቱ)
11 የወሩ ስም – ሐምሌ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – ሐመለ
ትርጉም – ለመለመ ፣ ሐመልማል ሆነ ፣ ለቀመ (ለጎመን)
12 የወሩ ስም – ነሐሴ
የግእዝ ሥርወ ቃሉ – አናሕስየ፣ ነሐሰ ሠራ
ትርጉም – አቀለለ፤ ተወ (የክረምቱን እያደር መቅለል ያሳያል)
13 የወሩ ስም – ጳጉሜን
ሥርወ ቃሉ – ኤጳጉሚኖስ (ግሪክ)
ትርጉም – ተጨማሪ ማለት ነው፡፡

የዓመቱ ወራት ሥፍረ ሰዓት

መስከረም .. የቀኑ ርዝመት …12 … የሌሊቱ ርዝመት ….12
ጥቅምት …. የቀኑ ርዝመት …11 … የሌሊቱ ርዝመት ….13
ህዳር …….. የቀኑ ርዝመት …10 … የሌሊቱ ርዝመት ….14
ታህሣሥ … የቀኑ ርዝመት …09 … የሌሊቱ ርዝመት ….15
ጥር ……… የቀኑ ርዝመት …10 ….የሌሊቱ ርዝመት… 14
የካቲት ……. የቀኑ ርዝመት …11 … የሌሊቱ ርዝመት… 13
መጋቢት……. የቀኑ ርዝመት… 12 … የሌሊቱ ርዝመት… 12
ሚያዝያ……. የቀኑ ርዝመት… 13 … የሌሊቱ ርዝመት ….11
ግንቦት …… የቀኑ ርዝመት …14 … የሌሊቱ ርዝመት …10
ሰኔ …….. የቀኑ ርዝመት …15 … የሌሊቱ ርዝመት ….09
ሐምሌ …. የቀኑ ርዝመት …14 … የሌሊቱ ርዝመት …10
ነሐሴ …… የቀኑ ርዝመት …13 … የሌሊቱ ርዝመት ….11
5.ሳምንት

ሳምንት “ሰመነ” ስምንት አደረገ ከሚለው ከግእዝ ቃል የተገኘ ነው፡፡ በሕገ ዑደት መሠረት ዕለት ከተነሣበት ማለትም ከእሑድ እስከ እሑድ ያለው ጊዜ ሳምንት ተብሎ ይጠራል፡፡ በዚህ ሳምንት ውስጥ ያሉት ቀናት እያንዳንዳቸው 24 ሰዓት ያላቸው ናቸው፡፡

እሑድ ማለት “አሐደ” አንድ አደረገ ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ
ስለሆነ ትርጉሙ አንድ ማለት ነው፡፡
ሰኞ ሁለተኛ ፣ ማክሰኞ /ማግስት/ ሦስተኛ፣ ረቡዕ አራተኛ፣ ሐሙስ
አምስተኛ፣ ዓርብ ስድስተኛ ፣ቅዳሜ ሰባተኛ ቀን ነው፡፡
እግዚአብሔር አምላክ ዓለምን በስድስት ቀናት /ከእሑድ – ዐርብ/ ፈጥሮ ያረፈባትና ሰዎችም እንዲያርፉበት ያዘዛት ሰባተኛዋ ቀን በግዕዝ ቀዳሚት ሰንበት ተብላ ትጠራለች፡፡

የዕለታት ስያሜ
እሑድ ፡ አሐደ ከሚለው ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም አንድ አደረገ /የመጀመሪያ ሆነ/ ማለት ነው፡፡
በዚህ ቀን ፍጥረታት መፈጠር ስለጀመሩ እሑድ ተብሏል፡፡
ሠኑይ /ሰኞ/፡ ሠነየ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም ሁለት አደረገ ማለት ነው፡፡ ለሥነ ፍጥረት ሁለተኛ ስለሆነ ሰኑይ/ ሰኞ/ ተብሏል፡፡ አንድም ሠናይ (ያማረ) ማለት ነው።
ሠሉስ/ማክሰኞ/ ፡ ሠለሰ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ሦስት አደረገ ማለት ነው፡፡ ማክሰኞ የሚለው የሰኞ ማግስት ማለት ነው፡፡
ረቡዕ ፡ረብዐ /አራት አደረገ/ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ለሥነ ፍጥረት አራተኛ ቀን ማለት ነው፡፡
ሐሙስ፡ ሐመሰ /አምስት አደረገ/ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ለሥነ ፍጥረት አምስተኛ ቀን ማለት ነው፡፡
ዓርብ ፡ ዓረበ ከሚል ግስ የተገኘ ሲሆን ተካተተ ማለት ነው፡፡ ፍጥረታት እሑድ መፈጠር ጀምረው አርብ ስለተካተቱ /ተፈጥረው ስለተፈፀሙ/ አርብ ተብሏል፡፡
ቅዳሜ፡ ቀዳሚት ማለት ሲሆን ሰንበተ ክርስቲያን ከሆነችው ከዕለተ እሑድ ቀድማ ስለምተገኝ ቀዳሚት ሰንበት /ቅዳሜ/ ተብላለች፡፡
«ወይእዜኒ በጽሃ ጊዜሁ ለነቂህ እምነዋም ኀለፈት ሌሊት ወመጽአት መዓልት ወንግድፍ እምላእሌነ ምግባረ ጽልመት ወንልበስ ወልታ ብርሃን ከመናንሰሉ በምግባረ ጽድቅ።
ከእንቅልፍ የምትነሱበት ሰዓት አሁን እንደ ደረሰ ዘመኑን እወቁ ካመንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን ዛሬ ወደ እኛ ቀርቧል፤ ሌሊት አልፏል፤ ቀኑ ቀርቧል፤ እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃን ጋሻ ጦር እንልበስ፤ በቀን እንደምንሆን በአግባቡ እንመላለስ። በዘፈንና በስካር በዝሙትና በመዳራት አይሁን፤ በክርክር እና በቅናት አይሁን»
ሮሜ ፩፫፥፩፩

«የአክለክሙ መዋእል ዘሃለፈ ፥ ያለፈው ዘመን ይበቃችኋል» እንደተባለ
(፩ኛ ጴጥሮስ ፬ ፥ ፫- ፬ ) በኃጢአት፣ በርኩሰት፣ በጠብ፣ በክርክር፣ በቁጣ፣ በቂም በቀል፣ በስካር ያለፈው ይብቃ። መጭውን ዓመት የሰላም፣ የጤና፣ የንስሐ ያድርግልን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር ዘሃሎ በአርያም
ወለወላዲቱ ድንግል ማርያም
ወለመስቀሉ ክቡር ዕፀ ፍቅር ወሰላም

አሜን ‼

መ ል ካ ም አ ዲ ስ ዓ መ ት
🌼 🌸 🌻 🌹 🏵 🌼 🌸 🌻 🌹 🏵 🌼

ፔጁን ይቀላቀላሉን።

❤️Like ,Share ማድረግ አትርሱ

💚💜💙💚💜💙💚💜💙💛💚💛

👇👇👇👇👇👇👇👇👇👇👌
Join us
👉Telegram

https://telegram.me/Gult_Rufael

👉Facebook

https://www.facebook.com/Mahibere.Rufael

👉https://www.facebook.com/112771870182132

👉LinkedIn
https://www.linkedin.com/groups/12865549

👉ቤተሰብ ስለሆንን ከልብ እናመሰግናለን ።

ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር።(መዝ68÷31)ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች ወይስ ታደርሳለች?🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር - ማህበረ ሩፋ...
11/01/2025

ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር።(መዝ68÷31)

ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች ወይስ ታደርሳለች?
🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏🙏
የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር - ማህበረ ሩፋኤል

ኢትዮጵያ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብዙ ቦታዎች ላይ የተጠቀሰች ሀገር ስትሆን በነቢየ እግዚአብሔር ክቡር ዳዊት በመዝሙር 67፡31 ላይ “መልእክተኞች ከግብፅ ይምጡ፤ ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” ተብሎ የተቀመጠው ግን በብዙዎች ዘንድ በሰፊው የሚታወቅ ነው፡፡ ይህ የመዝሙር ክፍል በግዕዙ “ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር” የሚል ሲሆን በግዕዙና በአማርኛው ትርጉም መካከል ልዩነቶች እንዳሉ አንዳንድ ሊቃውንት ያስረዳሉ፡፡

ቀደምት አበው እንዳስተማሩትና የግእዝ ቋንቋ ሊቃውንትም እንደሚያስረዱት “በጽሐ” የሚለው የግእዝ ቃል ቀጥታ የአማርኛ ትርጉሙ “ደረሰ” ማለት ነው፡፡ በዚህም መሠረት “ታበጽሕ” የሚለው ቃል “ታደርሳለች” የሚለውን ትርጉም ይይዛል ማለት ነው፡፡ በግዕዙ “ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር” የሚለውም ወደ አማርኛ ሲተረጎም “ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ታደርሳለች” የሚል ይሆናል፡፡

በሌላ በኩል “ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” የሚለው የአማርኛው ትርጉም ወደ ግዕዙ ቢመለስ ደግሞ “ኢትዮጵያ ትሰፍሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር” የሚል ይሆናል፡፡ በግዕዝ “ሰፍሐ” ማለት በአማርኛ “ዘረጋ” ማለት ነውና፡፡ “ትሰፍሕ” ማለት ደግሞ “ትዘረጋለች” ማለት ይሆናል፡፡ ይህም “…ይሰፍሑ ክነፊሆሙ…” ማለት “ክንፋቸውን ይዘረጋሉ” ማለት እንደሆነው ያለ ነው፡፡ስለዚህ “ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር” የሚለው “ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” ከሚለው ይልቅ “ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ታደርሳለች” የሚለው የአማርኛው ትርጉም የበለጠ ይስማማዋል፡፡

ይህንን ልዩነት መተንተን ያስፈለገበት ዋነኛው ምክንያት “ታደርሳለች” እና “ትዘረጋለች” በሚሉት ቃላት መካከል ልዩነት ስላለና ልዩነቱም ከመጻሕፍት ምሥጢራት ጋር የሚያያዝ ስለሆነ ነው፡፡ እጅን መዘርጋት ማንም ሊዘረጋ ይችላል፡፡ለመቀበል ወይም ለመስጠት እጅን መዘርጋት አስፈላጊ ቢሆንም እጁን የዘረጋ ሁሉ ግን አይቀበልም ወይም አይሰጥም፡፡ ዘርግቶም ሊቀበልም ላይቀበልም ይችላልና፡፡ ዘርግቶ ሊሰጥም ላይሰጥም ይችላልና፡፡ እጁን የሚያደርስ ግን ወይ ይሰጣል ወይም ይቀበላል፤ አለበለዚያም ሰጥቶ ይቀበላል ወይም ተቀብሎም ይሰጣል፡፡ በጸሎት ጊዜ እጃችንን የምንዘረጋው በእምነት ሆነን ቸርና ለጋስ የሆነው አምላካችን የሚሰጠንን መልስና በረከት ለመቀበል መዘጋጀታችንን የሚያሳይ መሆኑን ነባቤ መለኮት የኑሲስ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ አስተምሯል፡፡

ይህቺ ቅድስት ሀገረ እግዚአብሔር ኢትዮጵያ ግን ‹‹ታበጽሕ›› (ታደርሳለች) ተብሎ ነው የተነገረላት፡፡ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲወለድ ከሰብአ ሰገል አንዱ በመሆን ሥጦታን ለተወለደው አምላክ በማቅረብ በእውነት እጆቿን (ስጦታን ይዛ) ወደ እግዚአብሔር አድርሳለች፡፡ ይህም ከአምላኳ በነቢያት በኩል ለርሷ የተሰጠና የተነገረላት ትንቢት ነው (መዝ 67:31)፡፡ መዝሙረኛው ዳዊት ይህንን “በፊቱም ኢትዮጵያ ይሰግዳሉ … የተርሴስና የደሴቶች ነገሥታት ስጦታን ያመጣሉ፤ የሳባና የዓረብ ነገሥታትም እጅ መንሻን ያቀርባሉ፤ የምድር ነገሥታት ሁሉ ይሰግዱለታል” ብሎ ገልጾታል፡፡ (መዝ. 71፡9-10)

ለተወለደው አምላክ በቤተልሔም ተገኝተው አምሐ ካቀረቡት ሦስት ነገስታት (ሰብአ ሰገል) መካከል አንዱ የሆነው ንጉሥ በዲዳስፋ (አንዳንድ ጸሐፊያን ባልዛር ወይም ባዜን ይሉታል) የኢትዮጵያ ንጉሥ እንደነበር የታሪክ ሊቃውንት ያስተምራሉ፡፡መልኩም ጥቁር እንደነበርና ከርቤን (አንዳንድ ጸሐፊያን ወርቅን ይላሉ) በአምላኩ በክርስቶስ ፊት እንዳቀረበ ይገልፃሉ፡፡ ዛሬም ድረስ ምዕራባውያን በሚሠሩት የልደት የፊልም፣ተውኔትና በሚሥሏቸው የሰብአሰገል ሥዕሎች ላይ አንዱን (ኢትዮጵያዊውን)ጥቁር አድርገው ይስሉታል፡፡ ይህም አምሐ ካቀረቡት ሦስት ነገስታት መካከል አንዱ ኢትዮጵያዊ እንደነበር ምዕራባውያን ሊቃውንትም ያውቁ እንደነበር ይጠቁማል፡፡ ኢትዮጵያ ክርስቶስን ያወቀችውና መባ በማቅረብ ልደቱን ያከበረችው ከተወለደበት ጊዜ ጀምሮ ስለሆነ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቀዳማዊት ቤተ ክርስቲያን መባሉዋ ትክክል ነው፡፡ ብሉይ ኪዳንን በንግስተ ሳባ አማካኝነት የተቀበለች ኢትዮጵያ ተስፋ ልደቱን፣ የነቢያትን ሱባኤ የምታምንና የምትጠብቅ ስለነበረች ጌታ በተወለደ ጊዜ ከሰብአ ሰገል አንዱ የሆነው ኢትዮጵያዊ ንጉስና ሰራዊቱ ወደ ቤተልሔም የሄዱት የተቆጠረው ሱባኤ መፈጸሙን ተረድተው እንደነበር ሊቃውንት ያስረዳሉ፡፡

ለኢትዮጵያ ነገስታት ስጦታን መስጠት የተለመደ ነገር ነበር፡፡ ንግስተ ሳባ ስጦታን የክርስቶስ ምሳሌ ለነበረው ለእስራኤል ንጉሥ ለሰሎሞን አበርክታለች፡፡ይህም “ለንጉሡም መቶ ሀያ መክሊት ወርቅ እጅግም ብዙ ሽቱ የከበረም ዕንቍ ሰጠችው፤ የሳባ ንግሥት ለንጉሡ ለሰሎሞን እንደ ሰጠችው ያለ የሽቱ ብዛት ከዚያ ወዲያ አልመጣም ነበር” (1ኛ ነገ 10: 10) ተብሎ ተጽፏል፡፡ የአዲስ ኪዳን መጀመሪያ ላይ የነገሠውና ከሰብአ ሰገል አንዱ የሆነው የኢትዮጵያ ንጉሥ ባልዛር (ባዜን) ደግሞ ለሰማያዊው ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስ ከርቤን አበርክቷል፡፡

ወደ እግዚብሔር የተዘረጉት፣ እንዲሁም የደረሱት የኢትዮጵያ እጆች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ልጅዋ በስደት ሳሉ ተቀብለው አስተናግደዋቸዋል፡፡ በዚህም ብዙ በረከት አግኝተዋል፡፡ ሀገሪቱም ለቅድስት ድንግል ማርያም አስራት ተደርጋ ተሰጥታለች፡፡ ይህም ዛሬም ለእርስዋ ልዩ ፍቅር ያለው ሕዝበ ክርስቲያን እንዲኖር መሠረት ሆኗል፡፡

ወደ እግዚአብሔር ተዘርግተው ወደ እርሱም የደረሱት የኢትዮጵያ እጆች ክርስትናንም ተቀብለው ተመልሰዋል፡፡ በሐዋርያት ሥራ 8፡26 ላይ እንደተገለጸው የንግሥት ህንደኬ ጃንደረባ የነበረው ባኮስ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዶ ሲመለስ በሐዋርያው ፊሊጶስ ተጠምቆ ክርስትናን ይዞ ወደ ኢትዮጵያ ተመልሷል፡፡ በቅዱስ ፍሬምናጦስ በኩል ወደ እስክንድርያ የተዘረጋው ከዚያም የደረሰው የኢትዮጵያ እጅ ምስጢረ ክህነትን ይዞ ተመልሷል፡፡በአፄ ዳዊት ዘመንም የተዘረጉት የኢትዮጵያ እጆች ግማደ መስቀሉን ይዘው ተመልሰዋል፡፡ ክቡር ዳዊት በመዝሙሩ “መልእክተኞች ከግብፅ ይምጡ፤ ኢትዮጵያ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” እንዳለ ኢትዮጵያ ሐዋርያዊ የክህነት ውርስን ከግብፅ መልእክተኞች፣ በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ መንበር ከተሾሙ ሊቃነ ጳጳሳት ተቀብላ፣ በሐዋርያዊ አስተምህሮም ተባብራ (አንድ ሆና) ስለኖረች፣ ስለምትኖር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሐዋርያዊ ውርስ ተገለጠ፣ ልበ አምላክ የተባለ የንጉስ ዳዊት ትንቢትም ተፈጸመ፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ክቡር ዳዊት በመዝሙሩ “ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” ያለውን ሊቃውንት ሲያብራሩት ኢትዮጵያ (የመጽሐፍ ቅዱሷ) እጆቿን ወደ እግዚአብሔር የምትዘረጋው አንድም ጸሎትን፣ ምሥጋናን፣ ስጦታን፣ መስዋዕትን ለማድረስ ሲሆን ሁለትኛም በዚሁ ፈንታ ጸጋን፣ ምህረትን፣ ቸርነትንና በረከትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ለመቀበል ነው። ይህ አማናዊ ቃል መንፈሳዊ ትንቢት እንጂ “ሀገራዊ መፈክር” አይደለም። እጅን መዘርጋትም ቢሆን በትህትና የሚፈጸም አገልግሎት እንጂ በየአደባባዩ “ምንም አንሆንም” እያሉ ለመታበይ የሚውል መፈክር አይደለም። በየመዝሙሩም ይህንን ቃል ስንጠቀም የእግዚአብሔርን ቸርነት በማሰብ እንጂ “አንድ ጊዜ እጇን ትዘረጋለች ተብሎ ተጽፏልና ማንም አይነካንም” ብሎ በመመካት ሊሆን አይገባም። ይልቁንም በትህትና ልብ ስንጸልይ የምናስበውና ተስፋ የምናደርገው የትንቢት ቃል እንጂ በጸሎት ሳንተጋ እንደዚያ ስለተባለ ብቻ የሚፈጸምልን አድርገን መታበይ የለብንም።

ቃሉንም ከመንፈሳዊ አውድ ውጭ መውሰድ አይገባም። ኢትዮጵያ እጆቿን የምትዘረጋው ከመከራና ከፈተና ለመጠበቅ ቢሆንም “የዓለም ገዥ (ልዕለ ኃያል) ሀገር ለመሆን ነው” ብሎ ማሰብ ግን መንፈሳዊነት የጎደለው አካሄድ ነው። ከኢኮኖሚ አንጻርም ቢታይ እግዚአብሔር ለሚለምኑት ሁሉ በረከትን የሚሰጥ ቢሆንም ኢትዮጵያን ብቻ በበረከት አትረፍርፎ ሌላውን ዓለም የሚነፍግ አይደለም። በመንፈሳዊውም በየአደባባዩ “እጆቿን ትዘረጋለች” ስላልን ብቻ “የዓለም ብርሃን ትሆናለች” ማለት አይደለም። እውነተኛውን የክርስቶስ ወንጌል ለዓለም የሚሰብኩ ሐዋርያት ሲኖሯት ነው የዓለም ብርሃን የምትሆነው። ዛሬ ግን እንኳን ለዓለም ቀርቶ ሀገር ውስጥ ላሉት የተለያየ ቋንቋ ለሚናገሩ ወገኖች እንኳን ወንጌል በበቂ ሁኔታ አልተሰበከም፣ ብዙ የተሰበከለትም የገዛ ወንድሙን ከመበደል አልታቀበም።

የቅዱሳት መጻሕፍትን ንባብና ትርጉም እንዲሁም ታሪክን ለራሳቸው ዓላማ የሚበርዙ ልዩ ልዩ መናፍቃን፣ ፖለቲከኞችና ሌሎች ግለሰቦች የክቡር ዳዊትን ትንቢት ያለአውዱ እየጠቀሱ አንዳንዶችን ግራ ሊያጋቡ ቢሞክሩም ከላይ በተጠቀሱት ታሪካዊና፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማስረጃወች የንጉስ ዳዊት ትንቢት ለሀገራችን ለኢትዮጵያ ብሎም ለኢትዮጵያ ምልክት ለኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን የተነገሩ መሆናቸውን እንረዳለን፡፡ ዛሬም በጸሎትና በምስጋና የሚዘረጉት የኢትዮጵያ እጆች ወደ እግዚአብሔር ደርሰው ረድኤትን፣ በረከትንና ድኀነትን የዘላለም ሕይወትን ለሕዝቦቿ ይዘው ይመለሳሉ፡፡ ሰማያዊ ጸጋ በምድራዊ ምቾትና ባለጸግነት የሚመዘን አይደለምና፡፡
ፔጁን ይቀላቀላሉን።

❤️Like ,Share ማድረግ አትርሱ

💚💜💙💚💜💙💚💜💙💛💚💛

👇👇👇👇👇👇👇👇👇👇👌
Join us
👉Telegram

https://telegram.me/Gult_Rufael

👉Facebook

https://www.facebook.com/Mahibere.Rufael

👉https://www.facebook.com/112771870182132

👉LinkedIn
https://www.linkedin.com/groups/12865549

👉ቤተሰብ ስለሆንን ከልብ እናመሰግናለን ።

Address

Motta

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር - ማህበረ ሩፋኤል posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Place Of Worship

Send a message to የጉልት ሩፋኤል ልጆች ማህበር - ማህበረ ሩፋኤል:

Share