24/03/2023
የገጠሩ ውብ ባህላችን የኔታ ገብረ መድኅን በጥቂቱ እንደዘረዘሩት
አንድ ወጣት ለአቅመ አዳም ሲደርስ እናትና አባት “ልጃችን ደረሰ ምን እናድርግ” ብለው ያስባሉ፣ ይወያያሉ። “ማንን እንዳረው” ብለው መፈለግ ይጀምራሉ። ጠባዩአን፣ ትህትናዋን፣ መልካም ምግባሯን አይተው ይመርጣሉ።
ከወገን መርጠው ሽማግልና ይልካሉ። “እንግዳ ይመጣልና ከቤት ሰው አይጥፋ” የሚል መረጃ ለሴት ወገን ቤተሰቦች ይደርሳል።
👉🏽እናትና አባት የአብና የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ናቸው። የሚታጭለት የወልድ ምሳሌ ነው። የምትሆነውን ሴት መፈለግ ደግሞ “ዐየ፣ መረመረም፣ እንደ አንቺ ያለ አላገኘም” እንዳለ መጽሐፍ። የምትታጨዋ የድንግል ምሳሌ ናት።
👉🏽የሚያጩት ሽማግሌዎች የቅዱስ ገብርኤል፣ “እንግዳ ይመጣልና ከቤት አትጥፉ” የሚለው መረጃ የነቢያት ትንቢት ምሳሌ ናቸው።
ሽማግሌዎች የሴት ቤት ደርሰው በውጭ ይቆማሉ። ግቡ ሲባሉ “አንገባም፣ መጀመሪያ ጉዳያችንን አድምጡን” ይላሉ። 👉🏽ቅዱስ ገብርኤል ለእመቤታችን ደርሶ ያለ ሰላምታና ማብራሪያ “ትወልጃለሽ” እንዳላላት።
“ልጃችሁን ለልጃችን” ብለው ሙያውን፣ ጠባዩን ያስረዳሉ። የትውልድ ሀረጉን እንከ ሰባት ቤት ይጠይቋቸዋል፣ ሽማግሌዎቹም ይመልሳሉ። 👉🏽ቅዱስ ገብርኤል ለእመቤታችን “የአብ ልጁ፣ ከዳዊት ዙፋን የሚወለድ፣ በዳዊት ዙፋን መንግሥቱ የምትጸና፣ … ” እያለ እንዳስረዳት።
ወላጆች መጀመሪያ “አይሆንም” ይላሉ። 👉🏽እመቤታችን “ይህ እንዴት ይሆንልኛል፣ ወንድ አላውቅምና” ብላ እንደጠየቀች።
ከተወያዩ በኋላ የሠርግ ቀነ ቀጠሮ ይሰጣል። 👉🏽አምላካችን ከአዳም ጋር ለ5500 ዘመን የያዘው ቀነ ቀጠሮ ምሳሌ!
ሙሽራው ሚዜ ይዞ ይመጣል፤ ሙሽሪት ሚዜዎቿን ይዛ ለብቻ ወደተሠራላቸው ጫጉላ ይመጣሉ። 👉🏽እመቤታችን አምላክን የወለደችው በቤቷ ሳይሆን በውጭ በበረት የመሆኑ ምሳሌ። 👉🏽የሙሽራው ሚዜዎች የመላእክት፣ የሙሽሪት ሚዜዎች የእረኞች ምሳሌ ናቸው።
የወንድና የሴት ሚዜዎች አይተዋወቁም። ሙሽሮቻቸውን ያጅባሉ። 👉🏽መላእክትና እረኞች ያለቅድሚያ ትውውቅ በኅብረት እንደዘመሩ።
👉🏽 “ጸጋን የተመላሽ ሆይ” የተባለች የምልዕተ ጸጋ ድንግል ማርያም ምሳሌ ናትና ሙሽሪት ተሸፋፍና ዐይኗን ብቻ ያየዋል።
ሙሽሪትና ሙሽራውን በጫጉላ ባሉበት ወቅት ለማየት ሳንቲም እየከፈሉ ያዩአቸዋል። 👉🏽ሰብአ ሰገል ጌታን ለማየት ወርቅ፣ ዕጣን፣ ከርቤ የማምጣታቸው ምሳሌ።
ለሙሽራው ስም ያወጡለታል። 👉🏽አምላካችን በሥጋ ተገልጦ ወደ ዓለም ሲመጣ ክርስቶስ፣ ኢየሱስ፣ አማኑኤል፣ መድኃኔ ዓለም፣ … እየተባለ እንደተጠራ!
ይህ ሁሉ የሚከናወነው በሙሽሪት መኖሪያ ነው። 👉🏽መጀመሪያ ሙሽራው መጥቶ በሙሽሪት ቤት ወደተዘጋጀው ጫጉላ መግባቱ መጀመሪያ አምላካችን ወደ ድንግል መጣ እንጂ እመቤታችን ወደ ሰማይ ያለመሄዷ ምሳሌ። መለኮት ወደ ትስብእት መጣ እንጂ ትስብእት ወደ መለኮት ያለመሄዱ ምሳሌ።
ሙሽራው ሙሽሪትን ይዞ ሲሄድ እናቶች ጥላ ይዘው “እንዳላይሽ ደመናው ዞሯል በላይሽ” እያሉ ይዘምራሉ። 👉🏽በደመና መንፈስ ቅዱስ የተዋጀች፣ በፍጹም ምሥጢር የተመሠጠረች እመቤታችን በዚህ ዓለም በሴቶች ጠባይ አለመኖሯን የመግለጥ ምሳሌ።
የሙሽራ አሳዳሪ የሚባለው ለሙሽራው የተዘጋጀውን የበግ ሽልማት ይዞ ጥሩንባውን እየነፋ ከሙሽራው ፊት ፊት ይሄዳል። 👉🏽የመጥምቀ መለኮት ዮሐንስ ምሳሌ።
ቤት ሲደርሱ፣ ይዞ የመጣውን በግ ራሱ ሙሽራው አርዶ አወራርዶ ለሚዜዎቹ ያበላል። 👉🏽ራሱ መሥዋዕት፣ ራሱ ካህን፣ ራሱ ተቀባይ የሆነ የአምላካችን ምሳሌ።
አቤት! ውብ! እጹብ!
በምሕረት አቤሴሎም የተዘጋጀ