12/05/2026
ቅዱስ ሲኖዶስ በዛሬው አምስተኛ ቀን የጉባኤ ውሎ በአራት አጅንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳለፈ።
ጉባኤው የቤተክርስቲያንን አንድነት የተመለከቱ አጀንዳዎችን ጨምሮ የ2019 ዓ.ም የመንበረ ፓትርያርክ ዓመታዊ መደበኛ የበጀት ዕቅድን አጽድቋል ።
++++++++++++
ግንቦት 4 ቀን 2018 ዓ.ም(ብሕንሳ ሚዲያ ሆሣዕና)
+++++++++++
የ፳፻፲፰ ዓ.ም ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በዛሬው አምስተኛ ቀን ስብሰባ በአራት አጅንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔዎችን ማሳለፉን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት በዕለታዊ መግለጫው አሳውቋል።
የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል (ረ/ፕ) ለ በሰጡት ማብራሪያ ቅዱስ ሲኖዶስ በቀዳሚነት የተመለከተው "ዋልድባ አብረንታት ገዳምን ይወቁ" በሚል ርዕስ የተዘጋጀውን መጽሐፍ አስመልክቶ በሊቃውንት ጉባኤ ተመርምሮ፣ ለቋሚ ሲኖዶስ ቀርቦ የነበረው መጽሐፍ ለምልአተ ጉባኤ እንዲቀርብ በተወሰነው መሠረት ቃለ ጉባኤውና የሊቃውንቱ ጥናት ለምልዓተ ጉባኤ በንባብ ተሰምቷል ብለዋል፡፡
በዚህም "ዋልድባ አብረንታት ገዳምን ይወቁ'' በሚል ርዕስ የተዘጋጀው መጽሐፍ በሊቃውንት ጉባኤ ተመርምሮ
ሀ· እመቤታችን ከሰማይ እንደወረደች አስመስሎ ኃይል አርያማዊት የሚሉ መናፍቃንን አስተምህሮ የሚያንጸባርቅ፤
ለ· የሰባቱ ምሥጢራት ቁጥር ማፋለስ
ሐ· ከመናንያን አባቶች የማይጠበቅ ትችትና ስድብ የበዛበት ርእሱን የለቀቀ ለብጥብጥና ክፍፍል የሚያነሳሳ በመሆኑ
መጽሐፉ እንዲወገዝ ሲል ያቀረበውን ሐሳብ ጉባኤው አድምጦ :-
1. ሊቃውንት ጉባኤ ጸሐፊውን አቅርቦ ያልጠየቀና መጽሐፉ የተጻፈው በገዳሙ ወይስ በማን ባለቤትነት መሆኑን ያልተብራራና ያልተገለጸ ስለሆነ በድጋሚ ወደ ሊቃውንት ጉባኤ እንዲላክና ጸሐፊውን ጠይቀው ውጤቱን ለቋሚ ሲኖዶስ እንዲያቀርቡ፤
2. የመጽሐፉ ሥርጭት በየትኛውም አህጉረ ስብከት እንዳይሠራጭ እንዲደረግ ፣
የገዳሙ አባቶች ቀደም ሲል በቋሚ ሲኖዶስ በተወሰነው መሠረት በሰላምና በፍቅር እስካሁን በቆዩበት ሁኔታ ውሳኔውን እንዲጠባበቁ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
ቅዱስ ሲኖዶስ በሁለተኛ የቤተ ክርስቲያን አንድነትን በተመለከተ በቀረበው አጀንዳ ላይ በተደረገው ውይይት በዚህ አጀንዳ ሥር የተመለከቱ ሁለት ንዑሳን ጉዳዮችን ምልዓተ ጉባኤው በቅደም ተከተል መወያየቱ ተገልጿል።
ጉባኤው በዚህ አጀንዳ ሥር የተመለከተው ቀዳሚው በትግራይ ክልል ስላለው ጉዳይ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት በቆጋ ኪዳነ ምሕረት የነበረውን ችግር የተመለከቱ ናቸው፡፡
እንደ መምህር ዳንኤል (ረ/ፕ) ማብራሪያ ምልዓተ ጉባኤው ይኽ ጉዳይ የቤተ ክርስያናችን አንድነትን የሚመለከት በመሆኑ በልዩ ትኩረት የሚከታተለውና የተፈጠሩት ችግሮች ሙሉ ለሙሉ እንዲፈቱ ከፍተኛ ጥረት ሲያደርግ መቆየቱ አሁንም እየተደረገ መሆኑ ለጉባኤው ተገልጧል።
ሁለተኛም ለዚሁ ጉዳይ ልዩ ትኩረት በማድረግ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የሚመራ፤ ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁን ያካተተ፣ አንጋፋ አበው ሊቃነ ጳጳሳትን በአባልነት የያዘ፣ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም የተካተቱበት "የሀገራዊ ሰላምን የቤተ ክርስቲያን አንድነት" ኮሚቴ አቋቁሞ ጉዳዩን እየተከታተሉ መሆኑ፤ በተለይም ብፁዕ ዋና ጸሐፊውና ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ በምልዓተ ጉባኤው በተሰጣቸው ኃላፊነት በጉዳዩ የሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች ለጉባኤው ቀርቧል።
በተያያዘ ለዚሁ ጉዳይ ልዩ ትኩረት በማድረግ ምልዓተ ጉባኤው በየዓመቱ ባሉት መደበኛ ስብሰባዎች ሪፖርቶችን እንደሚሰማና፣ መግለጫም እንዲሚሰጥ ! ወደፊትም ይህ ተግባር እንዳማያቋርጥ ተገልጿል።
በዚሁ አጀንዳ የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ቆጋ ኪዳነ ምሕረትን በተመለከተ ከአሁን በፊት የነበሩት የሀገረ ሰብከቱ ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ አባቶች ሲጥሩ መቆታቸውንና አሁንም የክፍሉ ሊቀ ጳጳሰ የሆኑት ብፁዕ አቡነ ቶማስ በትኩረት እየሠሩበት መሆኑ ለምልዓተ ጉብኤው ተገልጧል፡፤
የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቶማስ፤ ለምልዓተ ጉባኤው ባቀረቡት መግለጫም፣ በአጀንዳው ጉዳይ ምልዓተ ጉባኤው ምንም የቤተ ክርስቲያን አንድነት ጉዳይ እንደ መሆኑና ተገቢን ክትትል ለማድረግ ለውይይት ቢያቀርበውም በርሳቸው በኩል ጉዳዩን እየተከታተሉት እንደሆነ፣ ሁለት ጊዜ በአካል ወደ ቦታው መሄዳቸውን ወደፊትም የሚደረስበትን ውጤት እንደሚገልፁ፣ ለጊዜው ግን በሂደት ላይ ስለሆነ ለወደፊቱ ጉዳዩ ፍጻሜ ሲያገኝ ቢያቀርቡ ምርጫቸው መሆኑን ለምልዓተ ጉባኤው ማሳወቃቸውን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል (ረ/ፕ) ለ በሰጡት ማብራሪያ ገልጸዋል ፡፡
ሌላው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተወያየበት አጀንዳ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት እየተከናወኑ ያሉ ልማታዊ ተግባራትን በተመለከተ ሲሆን ፡-
ሀ. የቤተ ክርስቲያናችን ቀደምት ሠነዶች በዲጅታል ቴክኖሎጂ እንዲደራጁ መደረጉን በተመለከተ፣
ለ. ከ1970ዎቹ ዓ/ም ጀምሮ ታትመው ለአገልግሎት ያልዋሉ በመጋዝን ተከማችተው የቆዩ ግምታቸውን 133,477,990.00 (አንድ መቶ ሠላሳ ሦስት ሚሊየን አራት መቶ ሰባ ሰባት ሺህ ዘጠኝ መቶ ዘጠና) የሆነ በርካታ ልዩ ልዩ መጻሕፍትን በተመለከተ፣
16 ሚሊየን የሚሆኑ ለአራት አህጉረ ስብከት እስከ አሁን የተሸጡ መሆኑ
ሐ. ቤተ ክርስቲያናችን የኢንፎርሜሽን ኮምዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ እንድትሆን ማድረግን በተመለከተ፣
ብፁዕነታው የሥራዎቹን ዕቅድና የትኩረት አቅጣጫ በማብራራት የገለፁ ሲሆን ምልዓተ ጉባኤውም በከፍተኛ አድናቆት ተመልክቶታል
ምልዓተ ጉባኤውም የሥራው አመራር ሂደት ወደ ሁሉም አህጉረ ስብከት መሻገር እንደሚገባው ሥልጠና እንዲሰጥ ድጋፍ ማድረግ እንደሚያስፈለግ ለተግባራዊነቱም መተባባር እንደሚገባ ጉባኤው አጽንዖት እንደሰጠበት በመግለጫው ተወስቷል ።።
በመጨረሻም ጉባኤው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይቤተ ክህነት ጽ/ቤት ለ2019 ዓ·ም በጀት ዓመት ገቢና ወጪ ሒሳብ አስመልክቶ ከበጀትና ሒሳብ መምሪያ የተዘጋጀ ዓመታዊ መደበኛ የበጀት ዕቅድ 46 ገጽ የተመለከተ ሲሆን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ከበጀትና ሒሳብ መምሪያ የተዘጋጀውን ዓመታዊ የበጀት ዕቅድ በንባብ አዳምጦና ከጉባኤው በቀረቡት ጥያቄዎች የባለሙያዎችን ምላሽ ከሰማ በኋላ በጉዳዩ ላይ በስፋት ተነጋግሮ የሚከተለውን ውሳኔ አሳልፏል፡፡
በውሳኔውም መሠረት የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ያቀረበው የ2019 ዓ·ም በጀት ዓመት ከነመጠባበቂያው ብር7,101,018,660.16 (ሰባት ቢሊየን አንድ መቶ አንድ ሚሊየን አሥራ ስምንት ሺህ ስድስት መቶ ስልሳ ብር ከአሥራ ስድስት ሣንቲም) በበጀት ዓመቱ የበጀት አርዕስቱን ጠብቆ በሥራ ላይ እንዲውል የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መወሰኑን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል (ረ/ፕ) ለ በሰጡት ዕለታዊ ማብራሪያ አስታውቀዋል ።
EOTC TV