ብሕንሳ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

  • Home
  • Ethiopia
  • Hossana
  • ብሕንሳ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

ብሕንሳ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ሚዲያ EOTC Archdiocese of Hadiya and Silte በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት

ቅዱስ ሲኖዶስ በዛሬው አምስተኛ ቀን የጉባኤ ውሎ በአራት አጅንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳለፈ። ጉባኤው የቤተክርስቲያንን አንድነት የተመለከቱ አጀንዳዎችን ጨምሮ  የ2019 ዓ.ም የመን...
12/05/2026

ቅዱስ ሲኖዶስ በዛሬው አምስተኛ ቀን የጉባኤ ውሎ በአራት አጅንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳለፈ።
ጉባኤው የቤተክርስቲያንን አንድነት የተመለከቱ አጀንዳዎችን ጨምሮ የ2019 ዓ.ም የመንበረ ፓትርያርክ ዓመታዊ መደበኛ የበጀት ዕቅድን አጽድቋል ።

++++++++++++
ግንቦት 4 ቀን ​2018 ዓ.ም(ብሕንሳ ሚዲያ ሆሣዕና)
+++++++++++

የ፳፻፲፰ ዓ.ም ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በዛሬው አምስተኛ ቀን ስብሰባ በአራት አጅንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔዎችን ማሳለፉን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት በዕለታዊ መግለጫው አሳውቋል።
የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል (ረ/ፕ) ለ በሰጡት ማብራሪያ ቅዱስ ሲኖዶስ በቀዳሚነት የተመለከተው "ዋልድባ አብረንታት ገዳምን ይወቁ" በሚል ርዕስ የተዘጋጀውን መጽሐፍ አስመልክቶ በሊቃውንት ጉባኤ ተመርምሮ፣ ለቋሚ ሲኖዶስ ቀርቦ የነበረው መጽሐፍ ለምልአተ ጉባኤ እንዲቀርብ በተወሰነው መሠረት ቃለ ጉባኤውና የሊቃውንቱ ጥናት ለምልዓተ ጉባኤ በንባብ ተሰምቷል ብለዋል፡፡

በዚህም "ዋልድባ አብረንታት ገዳምን ይወቁ'' በሚል ርዕስ የተዘጋጀው መጽሐፍ በሊቃውንት ጉባኤ ተመርምሮ

ሀ· እመቤታችን ከሰማይ እንደወረደች አስመስሎ ኃይል አርያማዊት የሚሉ መናፍቃንን አስተምህሮ የሚያንጸባርቅ፤

ለ· የሰባቱ ምሥጢራት ቁጥር ማፋለስ

ሐ· ከመናንያን አባቶች የማይጠበቅ ትችትና ስድብ የበዛበት ርእሱን የለቀቀ ለብጥብጥና ክፍፍል የሚያነሳሳ በመሆኑ

መጽሐፉ እንዲወገዝ ሲል ያቀረበውን ሐሳብ ጉባኤው አድምጦ :-

1. ሊቃውንት ጉባኤ ጸሐፊውን አቅርቦ ያልጠየቀና መጽሐፉ የተጻፈው በገዳሙ ወይስ በማን ባለቤትነት መሆኑን ያልተብራራና ያልተገለጸ ስለሆነ በድጋሚ ወደ ሊቃውንት ጉባኤ እንዲላክና ጸሐፊውን ጠይቀው ውጤቱን ለቋሚ ሲኖዶስ እንዲያቀርቡ፤

2. የመጽሐፉ ሥርጭት በየትኛውም አህጉረ ስብከት እንዳይሠራጭ እንዲደረግ ፣

የገዳሙ አባቶች ቀደም ሲል በቋሚ ሲኖዶስ በተወሰነው መሠረት በሰላምና በፍቅር እስካሁን በቆዩበት ሁኔታ ውሳኔውን እንዲጠባበቁ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ በሁለተኛ የቤተ ክርስቲያን አንድነትን በተመለከተ በቀረበው አጀንዳ ላይ በተደረገው ውይይት በዚህ አጀንዳ ሥር የተመለከቱ ሁለት ንዑሳን ጉዳዮችን ምልዓተ ጉባኤው በቅደም ተከተል መወያየቱ ተገልጿል።
ጉባኤው በዚህ አጀንዳ ሥር የተመለከተው ቀዳሚው በትግራይ ክልል ስላለው ጉዳይ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት በቆጋ ኪዳነ ምሕረት የነበረውን ችግር የተመለከቱ ናቸው፡፡
እንደ መምህር ዳንኤል (ረ/ፕ) ማብራሪያ ምልዓተ ጉባኤው ይኽ ጉዳይ የቤተ ክርስያናችን አንድነትን የሚመለከት በመሆኑ በልዩ ትኩረት የሚከታተለውና የተፈጠሩት ችግሮች ሙሉ ለሙሉ እንዲፈቱ ከፍተኛ ጥረት ሲያደርግ መቆየቱ አሁንም እየተደረገ መሆኑ ለጉባኤው ተገልጧል።
ሁለተኛም ለዚሁ ጉዳይ ልዩ ትኩረት በማድረግ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የሚመራ፤ ብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁን ያካተተ፣ አንጋፋ አበው ሊቃነ ጳጳሳትን በአባልነት የያዘ፣ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም የተካተቱበት "የሀገራዊ ሰላምን የቤተ ክርስቲያን አንድነት" ኮሚቴ አቋቁሞ ጉዳዩን እየተከታተሉ መሆኑ፤ በተለይም ብፁዕ ዋና ጸሐፊውና ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ በምልዓተ ጉባኤው በተሰጣቸው ኃላፊነት በጉዳዩ የሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች ለጉባኤው ቀርቧል።
በተያያዘ ለዚሁ ጉዳይ ልዩ ትኩረት በማድረግ ምልዓተ ጉባኤው በየዓመቱ ባሉት መደበኛ ስብሰባዎች ሪፖርቶችን እንደሚሰማና፣ መግለጫም እንዲሚሰጥ ! ወደፊትም ይህ ተግባር እንዳማያቋርጥ ተገልጿል።
በዚሁ አጀንዳ የምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ቆጋ ኪዳነ ምሕረትን በተመለከተ ከአሁን በፊት የነበሩት የሀገረ ሰብከቱ ሊቀ ጳጳስን ጨምሮ አባቶች ሲጥሩ መቆታቸውንና አሁንም የክፍሉ ሊቀ ጳጳሰ የሆኑት ብፁዕ አቡነ ቶማስ በትኩረት እየሠሩበት መሆኑ ለምልዓተ ጉብኤው ተገልጧል፡፤

የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቶማስ፤ ለምልዓተ ጉባኤው ባቀረቡት መግለጫም፣ በአጀንዳው ጉዳይ ምልዓተ ጉባኤው ምንም የቤተ ክርስቲያን አንድነት ጉዳይ እንደ መሆኑና ተገቢን ክትትል ለማድረግ ለውይይት ቢያቀርበውም በርሳቸው በኩል ጉዳዩን እየተከታተሉት እንደሆነ፣ ሁለት ጊዜ በአካል ወደ ቦታው መሄዳቸውን ወደፊትም የሚደረስበትን ውጤት እንደሚገልፁ፣ ለጊዜው ግን በሂደት ላይ ስለሆነ ለወደፊቱ ጉዳዩ ፍጻሜ ሲያገኝ ቢያቀርቡ ምርጫቸው መሆኑን ለምልዓተ ጉባኤው ማሳወቃቸውን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል (ረ/ፕ) ለ በሰጡት ማብራሪያ ገልጸዋል ፡፡
ሌላው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተወያየበት አጀንዳ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት እየተከናወኑ ያሉ ልማታዊ ተግባራትን በተመለከተ ሲሆን ፡-

ሀ. የቤተ ክርስቲያናችን ቀደምት ሠነዶች በዲጅታል ቴክኖሎጂ እንዲደራጁ መደረጉን በተመለከተ፣

ለ. ከ1970ዎቹ ዓ/ም ጀምሮ ታትመው ለአገልግሎት ያልዋሉ በመጋዝን ተከማችተው የቆዩ ግምታቸውን 133,477,990.00 (አንድ መቶ ሠላሳ ሦስት ሚሊየን አራት መቶ ሰባ ሰባት ሺህ ዘጠኝ መቶ ዘጠና) የሆነ በርካታ ልዩ ልዩ መጻሕፍትን በተመለከተ፣
16 ሚሊየን የሚሆኑ ለአራት አህጉረ ስብከት እስከ አሁን የተሸጡ መሆኑ
ሐ. ቤተ ክርስቲያናችን የኢንፎርሜሽን ኮምዩኒኬሽን ቴክኖሎጂ ተጠቃሚ እንድትሆን ማድረግን በተመለከተ፣

ብፁዕነታው የሥራዎቹን ዕቅድና የትኩረት አቅጣጫ በማብራራት የገለፁ ሲሆን ምልዓተ ጉባኤውም በከፍተኛ አድናቆት ተመልክቶታል

ምልዓተ ጉባኤውም የሥራው አመራር ሂደት ወደ ሁሉም አህጉረ ስብከት መሻገር እንደሚገባው ሥልጠና እንዲሰጥ ድጋፍ ማድረግ እንደሚያስፈለግ ለተግባራዊነቱም መተባባር እንደሚገባ ጉባኤው አጽንዖት እንደሰጠበት በመግለጫው ተወስቷል ።።

በመጨረሻም ጉባኤው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይቤተ ክህነት ጽ/ቤት ለ2019 ዓ·ም በጀት ዓመት ገቢና ወጪ ሒሳብ አስመልክቶ ከበጀትና ሒሳብ መምሪያ የተዘጋጀ ዓመታዊ መደበኛ የበጀት ዕቅድ 46 ገጽ የተመለከተ ሲሆን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ከበጀትና ሒሳብ መምሪያ የተዘጋጀውን ዓመታዊ የበጀት ዕቅድ በንባብ አዳምጦና ከጉባኤው በቀረቡት ጥያቄዎች የባለሙያዎችን ምላሽ ከሰማ በኋላ በጉዳዩ ላይ በስፋት ተነጋግሮ የሚከተለውን ውሳኔ አሳልፏል፡፡

በውሳኔውም መሠረት የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ያቀረበው የ2019 ዓ·ም በጀት ዓመት ከነመጠባበቂያው ብር7,101,018,660.16 (ሰባት ቢሊየን አንድ መቶ አንድ ሚሊየን አሥራ ስምንት ሺህ ስድስት መቶ ስልሳ ብር ከአሥራ ስድስት ሣንቲም) በበጀት ዓመቱ የበጀት አርዕስቱን ጠብቆ በሥራ ላይ እንዲውል የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መወሰኑን የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት የኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ መምህር ዳንኤል ሰይፈሚካኤል (ረ/ፕ) ለ በሰጡት ዕለታዊ ማብራሪያ አስታውቀዋል ።

EOTC TV

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ...
12/05/2026

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በሳዑዲ ዓረቢያ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው በአስጨናቂ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙ ወገኖችን በማስመልከት ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ መንግሥታት፣ ለዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋማት እና ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ አባታዊ መልእክት አስተላለፉ።

ግንቦት 4 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

ቅዱስነታቸው ያስተላለፉት አባታዊ መልእክት እንደሚከተለው ነው፦

መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

‹‹ተዘከሩ መቁሓነ ዘከመ ተሞቃሕክሙ ምስሌሆሙ ወእለ ተሣቀዩ ከመ ዘሀለውክሙ በሥጋክሙ፡-
ከእነርሱ ጋር አብራችኋቸው እንደታሰራችሁ ሆናችሁ እስረኞችን ዐስቡ፤ መከራ የጸናባቸውንም በሥጋችሁ ከእነርሱ ጋር እንዳላችሁ ሆናችሁ ዐስቡ››
(ዕብ. 13፡3)

እውነተኛ እምነትም ሆነ ጤናማ አመለካከት የሚመዘነው መከራ ስለሚቀበሉ ሰዎች ሰምቶና አይቶ በዝምታ ባለማለፍ፤ ይልቁንም በእነርሱ ሕመም ውስጥ ራስን በማስገባት በሚሰማው ጥልቅ ኀዘን እና በሚደረገው ድጋፍ ነው፡፡ ይልቁንም በዚች ዓለም የምንኖር ለችግርና ለመከራ ቅርብ እንደመሆናችን የታሰሩትን መጎብኘት፣ የተገፉትን ማጽናናት፣ በስደት ምድር ላይ ሆነው በሞት ፍርድ የሚጨነቁትን ወገኖች ስቃይም እንደራሳችን ስቃይ በመቁጠር ስለእነርሱ ድምፅ መሆንና ማዘን ስንችል በሰማያዊው መንግሥት የማይጠፋ የጽድቅ ዋጋን እናከማቻለን፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን!

እረኛ በበረት ውስጥ ያለችው አንዲት በግ ስትጠፋ ወይም ለአደጋ ስትጋለጥ ዝም ብሎ እንደማያይ ሁሉ፣ በሳዑዲ ዓረቢያ ምድር በሞት ጥላ ሥር ሆነው ‹‹የፍትሕ ያለህ›› እያሉ የሚጮኹ፤ በጭንቀት ቀናትን የሚቆጥሩና ድምፅ የሌላቸው ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን የተሻለ ኑሮ እናገኛለን ብለው በተሰደዱበት ሀገር ሕይወታቸው በጅምላ ሊቀጠፍ እንደሆነ መረጃውን ከልዩ ልዩ መገናኛ ብዙኃን የተገነዘብን በመሆኑ የዲፕሎማሲ ግንኙነት ጠቀሜታው የሰው ልጆችን ሕይወት ለመጠበቅ ነውና የኢትዮጵያ መንግሥት በከፍተኛ ደረጃ ከሚገኙ ከሳዑዲ ባለሥልጣናት ጋር በመነጋገር በግፍ የተፈረደባቸው ልጆቻችን የሞት ፍርድ እንዲነሳላቸውና ወደ ሀገራቸው የሚመለሱበት መንገድ ይመቻች ዘንድ የተጀመሩ ሥራዎች ልዩ ትኩረት እንዲሰጥባቸው፤ ወገኖቻችንም በቋንቋ እጥረትና በሕግ አማካሪ እጦት ለሞት እንዳይዳረጉ ከአደራ ጭምር እናሳስባለን ፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ለሰው ልጅ የሰጠው ታላቅ ስጦታ ሕይወት ነው፤ "አትግደል" የሚለው ሕግም በማንኛውም ምድርና ቋንቋ የሚሠራ ሲሆን ፍርድ ያለ ምሕረት ከሆነ አምላካዊ ቁጣን ይጋብዛልና የሳዑዲ ባለሥልጣናት የሁለቱን ሀገራት የቆየ ታሪክና ወዳጅነት አስበው፣ በሞት ፍርድ ጥላ ሥር ላሉት ወገኖቻችን ምሕረትን እንዲያደርጉ፣ ቅጣቱንም ወደ እስራት እንዲቀይሩ በአባታዊ ርኅራኄ እንጠይቃለን ፡፡

ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችም በማያውቁት ቋንቋ እንዲሁም ባልተረዱት የሕግ ሂደት ሞት የተፈረደባቸውን ወገኖች ስቃይ ተመልክተው የፍትሕ መዛባትን እንዲቃወሙና የንጹሐንን ነፍስ እንዲታደጉ ጥሪያችንን እናቀርባለን።

በመጨረሻም፣ ማንኛውም በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ሰው ሕይወቱ ሊጠፋ አይገባምና ኦርቶዶክሳውያን ልጆቻችን የክርስትናችን አንዱ መገለጫ የአንደኛው ወገን ሕመምን በጋራ መካፈል እንደሆነ ተረድታችሁ ወደ ፈጣሪያችን በጸሎት እንድትማጸኑ፤ መላው ኢትዮጵያውያንም ለመፍትሔው የበኩላችሁን ጥረት እንድታደርጉ ስንል አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን።

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!!
አሜን።

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ግንቦት 4 ቀን 2018 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
© የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት

6 ነፍሳት ተጠምቀው የቅድስት ሥላሴን ልጅነት አገኙ+++++++++++++ግንቦት 03 ቀን 2018 ዓ/ም(ብሕንሳ ሚዲያ ሆሣዕና) ++++++++++++በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ጊቤ ወረዳ ቤተ...
11/05/2026

6 ነፍሳት ተጠምቀው የቅድስት ሥላሴን ልጅነት አገኙ

+++++++++++++
ግንቦት 03 ቀን 2018 ዓ/ም(ብሕንሳ ሚዲያ ሆሣዕና)
++++++++++++

በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ጊቤ ወረዳ ቤተክህነት በኤሬራሞ ብርሃናተ-ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተክርስቲያን ለወራት ትምህርት ሃይማኖት ሲከታተሉ የቆዩ 6 አዳዲስ ኢ_አማንያን አዲስ ቤተክርስቲያን ተተክሎ በተመረቀበት ዕለት ግንቦት 02 ቀን 2018 ዓ/ም ተጠምቀው የቅድስት ሥላሴን ልጅነት አግኝተው ወደ ኦርቶዶክሳዊት መቅደስ ገብተዋል።

በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት በጊቤ ወረዳ ቤተክህነት አዲስ ቤተክርስቲያን ለመስራት የመሠረት ድንጋይ ተጣለ!+++++++++++++++ግንቦት 03 ቀን 2018 ዓ/ም(ብሕንሳ ሚዲያ/ሆሳዕና)+++...
11/05/2026

በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት በጊቤ ወረዳ ቤተክህነት አዲስ ቤተክርስቲያን ለመስራት የመሠረት ድንጋይ ተጣለ!

+++++++++++++++
ግንቦት 03 ቀን 2018 ዓ/ም(ብሕንሳ ሚዲያ/ሆሳዕና)
++++++++++++++++

በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት በጊቤ ወረዳ ቤተክህነት ገነተዋጌሻ አዲስ ለምሰራው ኢየሱስ ቤተክርስቲያን የመሠረት ድንጋይ በብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ የሀዲያና ስልጤ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አባታዊ መመሪያ የሀገረ ስብከታችን ዋና ሥራ አስኪያጅ ክቡር መልአከ ሕይወት ቀሲስ ንጉሴ ባወቀ በተገኙበት ቆሞስ አባ ገብረ ማርያም ባርከው ግንቦት 01 ቀን 2018 ዓ/ም የመሠረት ድንጋይ አኑረዋል።

ክብር መልአከ ሕይወት ቀሲስ ንጉሤ ባወቀ በመልእክታቸው "ዛሬ በታላቅ ደስታና መንፈሳዊ ሐሴት የተሰበሰብነው የዚህን የቅድስት ቤተክርስቲያን የመሠረት ድንጋይ ለማኖር ነው ለዚህ ታላቅና ለተቀደሰ ዓላማ የተመረጡ ይህንን መሬት የሰጡ አቶ ሜግሶ ካቤን ቅድስት ቤተክርስቲያን ተመሰግናቸዋለች" ያሉ ሲሆን በቆሞስ አባ ገብረ ማርያም የተመራው የመሠረት ድንጋይ የማኖር ጸሎት መርሐግብር ተጠናቋል ።

በዕለቱም መጋቤ ጥበብ ቀሲስ ወርቁ ተክሌ የሀገረ ስብከቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ፣ሊቀ ትጉሃን መ/ር ትግስቱ ሀንደጎ የሀገረ ስብከቱ ዋና ፀሐፊ፣ፀሐፌ ትእዛዝ መ/ር ሞላ ዓለሙ የሀገረ ስብከቱ ስብከተ-ወንጌል ክፍል ሃላፊ ፣መጋቤ መንክራት ቀሲስ አድማሱ የኋላሸት የጊቤ ወረዳ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የወረዳ ሥራ አስኪያጆች፣መምህራን ቤተክርስቲያን፣ተጋባዥ እንግዶች፣በረካታ ምዕመናንና ምዕመናት ተገኝተዋል።

በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት በጊቤ ወረዳ ቤተክህነት የኤሬራሞ ብርሃናተ-ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተክርስቲያን ተመረቀ!++++++++++++++ግንቦት 2 ቀን 2018 ዓ/ም(ብሕንሳ ሚዲያ...
10/05/2026

በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት በጊቤ ወረዳ ቤተክህነት የኤሬራሞ ብርሃናተ-ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተክርስቲያን ተመረቀ!

++++++++++++++
ግንቦት 2 ቀን 2018 ዓ/ም(ብሕንሳ ሚዲያ ሆሣዕና)
+++++++++++++

በኢትዮጵያ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ጊቤ ወረዳ ቤተክህነት የኤሬራሞ ብርሃናተ-ዓለም ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተክርስቲያን በብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ የሀዲያና ስልጤ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አባታዊ መመሪያ ሰጪነት የሀገረ ስብከታችን ዋና ሥራ አስኪያጅ ክቡር መልአከ ሕይወት ቀሲስ ንጉሴ ባወቀ በተገኙበት በቆሞስ አባ ገብረ ማርያም የባርኮት እና የምርቃት መርሃግብር ተከናወነ።

የቤተመቅደስ ግንባታ የሰንበት ትምህርት ቤት አዳራሽ፣የቤተልሔም ግንባታ፣አጥር፣የካህናት ማረፊያ እና ሽንት ቤትን ጨምሮ ሁለት ዓመት የፈጃ ሲሆን ከ4,183,990ብር በላይ ወጪ የተደረገበት ሲሆን አብዛኛው ወጪውን መቀመጫውን ደቡብ አፍሪካ ፕሮቶሪያ ያደረገው ማኅበረ ሐዋርያት ሲሸፍን መሬቱን ደግም ሙሉ በሙሉ በነፃ አቶ ቀጭኔ ኤርጋንዶ ከእነ ቤተሰቦቻቸው ጋር በመሆን ሰጥተዋል።

በመጨረሻም ክብር መልአከ ሕይወት ቀሲስ ንጉሤ ባወቀ የብፁዕ አቡነ ሕርያቆስን የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት ያስተላልፉ ሲሆን ለደብሩ እና ትጉህ አገልገሎቶች በብፁዕ አባታችን የተሰጠው የስም ስያሜ ደብደቤ ያሰሙ ሲሆን አጭር ትምህርተ ወንጌል በማስተማር የመርግብሩ ፍጻሜ ሆኗል።

በዕለቱም መጋቤ ጥበብ ቀሲስ ወርቁ ተክሌ የሀገረ ስብከቱ ምክትል ሥራ አስኪያጅ ፣ሊቀ ትጉሃን መ/ር ትግስቱ ሀንደጎ የሀገረ ስብከቱ ዋና ፀሐፊ፣ፀሐፌ ትዕዛዝ መ/ር ሞላ ዓለሙ የሀገረ ስብከቱ ስብከተ-ወንጌል ክፍል ሃላፊ ፣መጋቤ መንክራት ቀሲስ አድማሱ የኋላሸት የግቤ ወረዳ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣የወረዳ ቤተክህነት ሥራ አስኪያጆች፣መምህራን ቤተክርስቲያን፣ተጋባዥ እንግዶች፣በርካታ ምእመናንና ምዕመናት ተገኝተዋል።

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በቃሊቲ አካባቢ ለበጎ አድራጎት ሥራ ከ23 ዓመት በፊት ያስገነቡትን Gተ1  የመኖሪያ ሕንጻ  ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማኅበር  በስጦታ አበረከቱ።...
10/05/2026

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በቃሊቲ አካባቢ ለበጎ አድራጎት ሥራ ከ23 ዓመት በፊት ያስገነቡትን Gተ1 የመኖሪያ ሕንጻ ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማኅበር በስጦታ አበረከቱ።

+++++++++++
ግንቦት 2 ቀን 2018 ዓ.ም(ብሕንሳ ሚዲያ ሆሣዕና)
+++++++++++

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል የዋሽንግተን እና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት የስጦታ መርሐ ግብር ላይ ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፣የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተገኝተዋል።

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ለበጎ አድራጎተት እንዲውል የሕንጻ ቁጥሩ 982 የሆነውንና በግል ገንዘባቸው በ544 ካሬ ሜትር ቦታ ያረፈ ሕንጻ በመገንባት ለዚሁ ዓላማ እንዲውል አድርገዋል።

ሕንጻው ያረፈበት ቦታ 240 ካሬ ሜትር ሲሆን በግንባታ ወቅት የወጣበት ወጪ ከ3ሚሊዮን በላይ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ባለው የገበያ ዋጋ ከ120 ሚሊዮን በላይ ይገመታል።ሕንጻው ከተገነባ 23 ዓመታትን ማስቆጠሩ ተገልጿል።

በመርሐ ግብሩ አቶ አምሓ ይልማ ባቀረቡት መልእክት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ሕንጻውን በገነቡበት ወቅት ያስተላለፉትን በሕግ ፊት የሚጸና ተብሎ የተመዘገበውን የኑዛዜ ሰነድ በጽሑፍ አቅርበውታል።
ቤቱን ለመቄዶንያ አረጋውያንና አእምሮ መርጃ ማዕከል ለማስተላለፍ ከቤተ ሰብ ጭምር ኮሚቴ (ቦርድ) ተቋቁሟል ተብሏል።
በመቀጠልም በስጦታ አድራጊ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤልና በስጦታ ተቀባይ መቄዶንያ የውል ስምምነት ሰነድ እና ካርታ ርክክብ ተፈጽሟል።

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በስጦታ መርሐ ግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልእክት እግዚአብሔር የሰጠኝን ቤት ለእግዚአብሔር አስረክቤያለሁ ብለዋል። ብፁዕነታቸው ጨምረው እንደገለጹት 19 ዓመት የቤቱ ኪራይ ለበጎ አገልግሎት ውሏል ብለዋል።
መስጠት የማይፈልጉ ኃይሎች የእኔን ስጦታ ሲተቹ ሰምቻለሁ።

ይህ ግን አግባብነት የለውም ብለዋል። ብፁዕነታቸው እኔ የሚቆጠር ንብረት የለኝም ያሉ ሲሆን በመጨረሻም ካርታውንና የቤቱን ቁልፍ የመቄዶንያ መሥራች ብኒያም በለጠ ተረክበው የምስጋና መልእክት አስተላልፈዋል።
ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል 18 ዓመታቸው ስለመነኮሱ እግዚአብሔር የመቄዶንያ መሥራች ብንያም በለጠ የጠራቸው አባት መሆናቸውን እናምናለን። ስጦታቸውን የሚያጣጥሉ ኃይሎች መፈጠራቸው አሳዝኖናል ብለዋል።
ቀድሞም የቤት ኪራዩን ሜቄዶንያ ሲጠቀምበት የቆየ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን ቤቱ ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል 58ኛ መቄዶንያ ቅርንጫፍ እንዲባል ጠይቀዋል።

በመቄዶንያ ታሪክ ትልቁ ስጦታ ይህ ነው በማለት የመቄዶንያ መሥራቹ ብኒያም በለጠ ተናግረዋል።
በመቀጠልም የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች ስለስጦታው አርአያነት ያለው ነው በማለት አድናቆታቸውን ገልጸዋል።
የመቄዶንያ አረጋውያንና አእምሮ ሕሙማን ማዕከል ተረጅዎችም ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ አባታዊ ትምህርት የሰጡ ሲሆን ብፁዕነታቸው በሰጡት ትምህርት የትንሣኤው በኩር የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኔ ተማሩ በማለት ያስተማረውን ትምህርት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በተግባር አውለውታል ብለዋል።

ብፁዕነታቸው ራሳቸውን በመስጠት ትልቁን መሰናከል አልፈዋል ብለዋል። ዛሬ ያጣነው የሚሠራ እንጂ የሚያወራ አይደለም ሲሉ መልዕታቸውን አጠቃለዋል።
በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ኤልያስ የኖርዲክ ሀገራት እና የግሪክ አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ የመጨረሻ ትምህርትና ጸሎት መርሐ ግብሩ ተጠናቋል።

© EOTC TV

10/05/2026

ቀጥታ ስርጭት ከኤሬራሞ ቅዱስ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተክርስቲያን

10/05/2026

ቀጥታ ስርጭት ከኤሬራሞ ቅዱስ ጵጥሮስ ወጳውሎስ ቤተክርስቲያን

ዓመታዊው የግንቦት ልደታ  ክብረ በዓል በሆሣዕና ደብረ ኢዮር ቅዱስ ራጉኤል ወልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን በድምቀት ተከበረ። +++++++++++++ግንቦት 1 ቀን 2018 ዓ.ም (ብሕንሳ ሚዲ...
09/05/2026

ዓመታዊው የግንቦት ልደታ ክብረ በዓል በሆሣዕና ደብረ ኢዮር ቅዱስ ራጉኤል ወልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን በድምቀት ተከበረ።

+++++++++++++
ግንቦት 1 ቀን 2018 ዓ.ም (ብሕንሳ ሚዲያ ሆሳዕና)

+++++++++++++

‹‹ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ
አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ››

‹‹ድንግል ሆይ በኃጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለም፤
በሕግ በሆነ ሩካቤ ከሐናና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ››
አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም

ዓመታዊው የግንቦት ልደታ ክብረ በዓል በሀዲያ እና ስልጤ ሀገረ ስብከት በሆሣዕና ደብረ ኢዮር ቅዱስ ራጉኤል ወልደታ ለማርያም ቤተክርስቲያን የሀገረስብከቱ ዋና ስራአስኪያጅ ክቡር መልአከ ሕይወት ቀሲስ ንጉሤ ባወቀ በተገኙበት በድምቀት ተከብሯል።

በክብረ በዓሉ ላይ ክቡር መልአከ ሕይወት ቀሲስ ንጉሤ ባወቀ የሀዲያና ስልጤ ሀገረስብከት ዋና ስራአስኪያጅ ፣ሊቀ ትጉሃን ትዕግስቱ ሃንዳጎ የሀገረስብከቱ ዋና ጸሐፊ፣የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ምእመናንና ምእመናት በተገኙበት በድምቀት ተከብሯል።

09/05/2026



በሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ጊቤ ወረዳ ቤተክህነት የኤሬራሞ አዲስ የተተከለው የቅዱስ ጴጥሮስ ወዻውሎስ ህንፃ ቤተ መቅደስ በብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ የሀዲያ እና ስልጤ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ መልካም ፈቃድ መልአከ ሕይወት ቀሲስ ንጉሤ ባወቀ የሀገረ ስብከቱ ዋና ስራአስኪያጅ፣የሀገረ ስብከቱ ልዑካን፣የወረዳ ቤተክህነት ሊቃነ ካህናት፣ተጋባዥ እንግዶች፤ አባቶች ካህናት፣ መምህራን፣ ዘማሪያን እንዲሁም በርካታ ምዕመናን በተገኙበት በታላቅ ድምቀት እየተመረቀ ይገኛል ።
++++++++++++++++++++++++++
ግንቦት 01 ቀን 2018ዓም (ብሕንሳ ሚዲያ/ሆሣዕና)

Address

Hossana

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ብሕንሳ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ሚዲያ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Place Of Worship

Send a message to ብሕንሳ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ሚዲያ:

Share