17/07/2026
ሐምሌ ፯ የቅድስት ሥላሴ በዓል ነው፤የአብ ጸጋ፥የወልድ ቸርነት፥የመንፈስ ቅዱስ ፍቅር አንድነት ይደርብን ይደርባችሁ ።
ይህ ዕለት:-በመለኮት አንድ በስም፣በአካል፣በግብር ሦስት የሆኑ ቅድስት ሥላሴ በአንድነት በሦስትነት ለአብርሃምና ለሣራ የተገለጡበት፥በአብርሃም ድንኳን በእንግድነት የተስተናገዱበትና ሣራ ካረጀች ካፈጀች በኋላ ይሥሐቅን እንደምትወልድ የተናገሩበት ዕለት ነው።ዘፍ:፲፰፥፩።
ሥላሴ በሴት አንቀጽ “ቅድስት” የተባሉበት ምክንያት:-፩ኛ:-እናት በወለደችው ልጅ ላይ እናት መሆኗ እንደማይጠረጠር ሁሉ ሥላሴም የሚታየውንና የማይታየውን ዓለም መፍጠራቸው ፈጽሞ ስለማይጠረጠር ነው፤ሮሜ: ፩፥፳። ፪ኛ:-የልጅ መወለዱ ከእናት እንደ ሆነ ሁሉ እኛም በጥምቀት ከሥላሴ በመወለዳችን ነው፤ዮሐ:፫፥፭። ፫ኛ:-እናት ፈጭታ፥ጋግራ ቤተሰቧን እንደምትመግብ ሁሉ ሥላሴም በእናት አምሳል ዓለሙን ስለሚመግቡ ነው፤ ፬ኛ:-የእናት አንጀት በተፈጥሮ ርኅሩኅ እንደሆነ ሁሉ ሥላሴም በባህርያቸው ለፈጠሩት ፍጥረት እንደ እናት አንጀት ርኅሩኅ በመሆናቸው ነው።ኢሳ:፵፱፥፲፭።ከዚህም ጋር “ቅድስት” ለአንዲት ሴት የሚሰጥ ስያሜ በመሆኑ ቃሉ ለሥላሴ መቀጸሉ አንድነታቸውን ሲያስረዳልን “ሥላሴ” የሚለው ደግሞ ሦስትነታቸውን የሚያስረዳልን በመሆኑ ነው፥ትርጉሙ ሦስትነት ማለት ነውና።