24/12/2025
የኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል
ለሚመለከተው ሁሉ
ጉዳዩ - አስቸኳይ ማስተካከያ እንዲደረግ ስለመጠየቅ ይሆናል፡፡
የአማኑኤል ሕብረት ቤተ ክርስቲያን በካውንስሉ በህግ ተመዝግባ የምትንቀሳቀስና ላለፉት ረጅም አመታት መንፈሳዊና ሁለንተናዊ ተግባራትን በአገር ውስጥና በመላው አለም ስታከናውን የቆየች ቤተ እምነት መሆኗ ይታወቃል ።
ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደ ማንኛውም የሐይማኖት ተቋም ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ለስርዓተ አምልኮ ማስፈጸሚያ የሚሆን ቦታ በቂርቆስ ክፍለ ከተማ ወረዳ 02 እንድትረከብ በተወሰነላት መሰረት አስፈላጊውን ካሳ ከፍላ እያለ ቤቱን ማስረከብ የነበረበት የፌደራል ቤቶች ኮርፖሬሽን በልዩ ልዩ ምክንያት ተፈጻሚ ሳያደርግ ቆይቷል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ አስፈላጊውን ክፍያ አከናውና ላለችው የአማኑኤል ሕብረት ቤተክርስቲያን ማስረከብ ሲገባው ይባስ ብሎ ቦታውን ለእስልምና እምነት ተከታዮች መሰጠቱን በመስማታችን የተሰማን ቅሬታ ከፍተኛ ነው፡፡
ይህ አይነቱ አሰራር በኃይማኖት ተቋማት መካከል ሊያስከትል የሚችለው ግጭት ከግምት ውስጥ ያላስገባ በመሆኑ በአስቸኳይ እንዲታረም ስንጠይቅ በሐዘን ነው፡፡
የተወሰደው ኢ-ፍትሐዊ እርምጃ ሐይማኖትን ከሐይማኖት እንዲሁም በሕዝብ መካከል ከሚፈጥረው ግጭት ባሻገር የፍትህ ስርዓቱን አደጋ ላይ የሚጥል በመሆኑ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላትም ይህንን ተግባር እንድታስቆሙልን በአክብሮት እንጠይቃለን፡፡
ከኢትዮጵያ ወንጌል አማኞች አብያተ ክርስቲያናት ካውንስል ዋና ጽ/ቤት