01/06/2025
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በቢሾፍቱና አካባቢው ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር የቃጅማ ደብረ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ወቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ቤቱ ክብረ በዓል ብፁዕ አባታችን አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳምና ሥራ አመራር መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ኃላፊ የቅዱስ ሲኖዶስ ቋሚ አባል እንዲሁም የኢትዮጵያ ሃይማኖቶች ተቋማት የሥራ አስፈጻሚ ቦርድ ሰብሳቢ : ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሶማሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት በታላቅ መንፈሣዊ ሥነ ሥርዓት ተከብሮ ዋለ።
መርሓ-ግብሩን የመሩት ክቡር የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሲሆኑ በቅደም ተከተል በተቀመጠው ሰዓት እና ደቂቃ መሠረት በሊቃውንት እና በሰንበት ትምህርት ዘማርያን ያሬዳዊ ዜማ እና ከተለያዩ ማኅበራት በተወጣጡ ወጣት ዘማርያን በኅብረት በአንድነት ዜማ
ምሥጋና ቀርቦአል።
በብፁዕ አባታችን መልካም ፈቃድ የህንጻ አሰሪ ኮሚቴ ሊቀ መንበር የሆኑህ አቶ መለሰ ግርማ ከመሠረት ጀምሮ እስከ ፍጻሜው የሒሳብ እና የሥራ አፈጻጸም ሪፖርት አቅረበዋል ። በተያያዘም የሕንፃ ቤተክርስቲያኑ ግንባታ ከተመሠረተ ጀምሮ የቃለ ዐዋዲውን ሕግ እና ሥርዓት ጠበቀው ለአሠሩ የወረዳው የአብያተ ክርስቲያናቱ ሰበካ ጉባኤ እና ህንጻ አሰሪ ኮሚቴ ለካህናት ለአረጋውያን አባቶች እና እናቶች እንዲሁም በእውቀታቸው በገንዘባቸውና በጉልበታቸው ለረዱና ለተባበሩ ድርጅቶች እና ግለሰቦች በብፁዓን አባቶች የሽልማትና የእወቅና ሰርተፍኬት ተበርክቶአል።
በብፁዕ አባታችንን አቡነ ጎርጎርዮስ ግብዣ ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሶማሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ "
ወይእዜኒ ኀረይክዎ ወቀደስክዎ ለዝንቱ ቤት ከመ ይሰመይ ስምየ እስከ ለዓለም ወህየኒ ይከውና አዕይንትየ ወልብየኒ በኵሉ መዋዕል። (ትርጉም ) አሁንም ስሜ ለዘላለም በዚያ ይኖር ዘንድ ይህን ቤት መርጫለሁ ቀድሻለሁም፤ ዓይኖቼና ልቤም ዘወትር በዚያ ይሆናሉ። 2ኛ ዜና 7፥16 በሚል መነሻ ቃል የራቀውን አቅርበው የቀረበውን አጉልተው ሰፊ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል።
በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ጎርጎዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት ያስተላለፉ ሲሆን ታሪክ ወደ ኃላ በማንሳት መሠረት ከተጣለበት ጊዜ አንስቶ የነበሩ ለሕንፃ ግንባታው ሥራ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ በመሥራት እራሳቸውን በማደራጀት ይህንን ህንጻ ቤተ መቅደስ ሠርታችሁ ለዚህ ቀን በመብቃታችሁ እንኳን ለዚህ ታሪካዊ እና የበረከት ቀን አደረሳችሁ በማለት በቃለ ምዕዳንና ጸሎት በዓሉ። ተጠናቋል።
በበዓሉ ላይም ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ ክቡር መልአከ ምሕረት ቆሞስ አባ ገብረ መድኅን ንጉሤ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ : የሀገረ ስብከቱ እና የወረዳው ቤተ ክህነት የክፍል ኃላፊዎች :የካቴድራል ገዳማት አድባራት አስተዳዳሪዎች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፣ ካህናት ፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ተገኝተዋል።