29/11/2025
ህዳር 21
+++ ጽዮን ማርያም+++
"ጽዮን" ማለት "ጸወን - አምባ - መጠጊያ" ማለት ነው። አንድም በምሥጢሩ "ማሕደረ አምላክ" ማለት ነው። ጽዮን የሚለው ስም በቁሙ ለቅዱስ ዳዊት ተራራ : ለኪዳኑ ደግሞ ጽላት ሆኖ ሲያገለግል ትንቢታዊ ምሥጢሩ ግን ለድንግል ማርያም፣ ለቤተ ክርስቲያንና ለዘላለማዊት ርስት ያገለግላል።
እግዚአብሔር ከዘመነ አበው በኋላ በጊዜው ለእስራኤላውያን ክብር፣ ሞገስ፣ አምባ የምትሆናቸውን ታቦተ ጽዮንን በቅዱስ ሙሴ አማካኝነት ሰጥቷቸዋል። (ዘጸ. ፴፩፥፲፰)
ከዚያም ለአምስት መቶ ዓመታት ከእነርሱ ጋር በመሆኗ በፈጣሪና በእነርሱ መካከል ድልድይ ሆና ኖራለች።
ከዚያም ባለቤቱ መድኃኔዓለም ሲፈቅድ በዘመነ ሳባ በቀዳማዊ ምኒልክ (እብነ መለክ - እብነ ሐኪም) አማካኝነት ወደ ኢትዮጵያ መጥታለች። እነሆ በሃገራችን የሦስት ሺህ ዓመት ቆይታዋን ልትደፍን የቀራት ጥቂት ዓመታት ብቻ ናቸው። ጌታ እንደ ፈቀደ ቅዱስ መስቀሉንና ታቦተ ጽዮንን ይዘን ይሔው በቸርነቱ እንኖራለን።
በነገራችን ላይ በዚህ ዘመን ታቦተ ጽዮንን ለመውሰድና ለመስረቅ የሚፈልጉ ብዙ ቀሳጢዎች እንዳሉ እናውቃለን። ነገር ግን አያስጨምቀንም። ምክንያቱም የመጣችውም የምትጠበቀውም በፈቃደ እግዚአብሔር ነውና እንጸልያለን እንጂ አንጨነቅም። በተለያየ ወሬም ራሳችንን ውጥረት ውስጥ አንከትም። ባለቤቱ እንድትሔድ ከፈቀደ ደግሞ ማንም ጉልበተኛ አያስቀራትም።
ታቦተ ጽዮን ብዙ ጊዜ "ጽላተ ኪዳን፣ ታቦተ ሕጉ" እየተባለች ትጠራለች። "ጽሌ" ማለት "ሰሌዳ" እንደ ማለት ሲሆን "ጽላት" ደግሞ በብዙ ቁጥር ነው። "ኪዳን" ደግሞ በፈጣሪና በሰው ልጆች መካከል ያለ "ውል - ስምምነት" ነው።
"ታቦት" ማለት "ማሕደር - ማደሪያ" እንደ ማለት ነው። ሕጉ የተጻፈባቸውን ሰሌዳ "ጽላት" ስንላቸው የጽላቱ ማደሪያ ደግሞ "ታቦት" ይባላል። ጽላት (ታቦትን) ያመጣ ፈጣሪ ነው። በሐዲስ ኪዳንም ምሥጢርና ሐተታ ቢኖረውም ሁለት ቦታ ላይ ስለ ታቦት ተጠቅሶ እናገኘዋለን። (፪ቆሮ. ፮፥፲፮ ፣ ራእይ. ፲፩፥፲፱)
++ ኅዳር 21 የምናከብርበት ዋናው ዓለማ ++
፩ኛ. ታቦተ ጽዮን (ጽላተ ኪዳን)- ለሊቀ ነቢያት ቅዱስ ሙሴ መሰጠቷን እናስባለን። ይህ ሲሆንም ቅዱስ ሙሴ አርባ መዓልት አርባ ሌሊት ጾሞ እንደ ተቀበለ እያሰብን ማለት ነው።
(ዘጸ. ፴፩፥፲፰ ፣ ዘዳ. ፱፥፲፱)
፪ኛ. በሊቀ ካህኑ ኤሊ ዘመን ታቦተ ጽዮን በታሪኳ ለመጀመሪያ ጊዜ በአሕዛብ (ኢሎፍላውያን) እጅ ተማርካለች። ነገር ግን ዳጐን የሚባለውን የአህዛብ ፃኦት የሰባበረችበትን ቀን እናስታውሳለን ።
(፩ሳሙ. ፭፥፩)
፫ኛ. በዘመነ ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት በአሚናዳብ ሠረገላ ሁና ከአቢዳራ ቤት ስትመጣ ቅዱሱ ንጉሥ በታላቅ ሐሴት በፊቷ ዘመረ፤ አገለገለ። ምድራዊ ክብሩን እስኪረሳ ድረስ ለታቦተ አምላክ ተቀኘላት። በዚህም ምክንያት ሚስቱ ሜልኮል ንቃው ማኅጸኗ ተዘግቷል እስክትሞትም ደረስ አልወለደችም ነበር እንዲል።
(፩ዜና. ፲፭፥፳፭)
ሊቃውንትም ይህን ሲያመሰጥሩ "ቅድስትድንግል ማርያምን በትንቢት መነጽር ተመልክተው እንዲህ ብለዋል፦
"ሰላም ለኪ ማርያም እምነ
ዘሰመይናኪ ጸወነ
ሶበ እምርሑቅ ርእየ ዘጽላሎትኪ ስነ
ለቢሶ ዳዊት ልብሰ ክብር ዘየኀይድ ዓይነ
ቅድመ ታቦተ ሕግ ኃለየ ወዓዲ ዘፈነ እንዲል ።
፬ኛ. በቅዱስ ሰሎሞን(መፍቀሬ ጥበብ) ዘመንም ግሩም የሆነ ቤተ መቅደስ ተሰርቶላት ስትገባ ታላቅ ሐሴት ሆኖ ነበር። እግዚአብሔርም በደመና ወርዶ ንጉሱን አነጋግሮ ነበር (፪ኛ ዜና ፭፥፩ ፩ኛ ነገ ፰*፩)።
፭ኛ. በዚያ ዘመን ንጉስ ሚኒሊክ (ዕብነ ሐኪም) ታቦተ ፅዮንን ይዞ ገብቷል።
፮ኛ. በዘመነ አፄ ባዜን (፬ኛው ክ.ዘ.መ) አማናዊት ጽዮን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ አክሱም ፅዮን በስደት መጥታ ገብታለች። በዚህም ጊዜ ሁለቱ ጺዮኖች (ታቦተ ፅዮን እና ፅዮን ማርያም) ሲገናኙ አክሱም ከክብራቸው የተነሳ በብርሃን አሸብርቃለች።
፯ኛ. በ፬ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በአብርሃ ወአፅብሓ ዘመን አስራ ሁለት መቅደስ ያሏትን ቤተ መቅደስ ለእመብርሃን ሰርተዋል: በጌታችንም ተቀድሷል።
፰ኛ. በአረመኔዋና የቤተ ክርስቲያን ቀንደኛ አውዳሚ በሆመችው በዮዲት ጉዲት ቤተ መቅደሷ ስትፈርስ ወደ ዝዋይ ትሰደድ ነበር በኋላም ቤተ መቅደሷ ሲሰራ ተመልሳ እንደመጠችም በኅዳር ፳፩ ቀን ትከበር ነበር።
እንግዲህ ኅዳር 21 ቀን እነዚህን ምክንያቶች እያሰብን በደማቅ ሁኔታ እናከብራለን።
እንግዲህ ከፍጡራን በላይ ከፈጣሪ በታች የሆነች እናታችንን ስናስብ "ቅድስት" ማለታችን እንደሌሎች ቅዱስን በእኩል ደረጃ እያሰብን ሳይሆን ትርጉሙ ይለያል፣ የእርሷም ቅድስና ልዬ ነውና፦ ቅድስተ ቅዱሳን : ንፅሕተ ንፁሓን: ብርክት እምብሩካን: ኅሪት እምኅሩያን እያልን እንጠራታለን።
ወዳጄ! "ስለ ፅዮን ዝም አንልም" እንዲል ዳዊት በመዝሙሩ እኛ የምንጮኸው ለዝና አልያም ደግሞ መናፍቃንን ለማናደድ የሚመስላቸው ፀረ ተዋህዶ የሆኑ ተዋስያንና ጥገኞች፣ ባህላቸውን እንኳ የማያውቁ ነገር ግን እኛን እየታከኩ ልደት በለው ትንሳኤ ያከብሩና ዞረው ደግሞ እኛን ለመተቸት ይመጣሉ። ክብርና ምስጋና ለመድኃኔዓለም ይሁንና ከአስርቱ ትዕዛዛት አንዱ "እናት እና አባትህን አክብር" ብሎ ትዕዛዝ የሰጠ አምላክ አሁን ደግሞ የነገራት ሁሉ በኩር የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ ንፅሕተ ንፁሓን: ቅድስት: ንዑድ ክብርት የሆነች እናቱን አክብሮ እንድናከብራት "ለፅዮን የማይገዛ ትውልድ ይጠፋል " ብሎ ለማያከብሯት በማስጠንቀቅም ለእኛ ለምናከብራት ደግሞ እነሆ ትውልድ ሁሉ በፊትሽ ይማልላሉ (ሰአሊለነ ቅድስት እያሉ ይጮሃሉ) ብሎ በግልፅ አስቀምጦልናል።
አሜን ማርያም ሆይ! ትውልድ ሁሉ ብፅዕት ይሉሻል!!!
፨፨እንኳን ለዓመቱ ህዳር ፅዮን በሰላም አደረሳቹህ መልካም በዓል ይሁንላቹህ የዓመት ሰው ይበለን!!!