26/05/2026
የአማራ ክልል የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የኢድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መግለጫ
ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች በሙሉ፤ የአማራ ክልል የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ለ1447ኛው አመተ ሂጅራ የኢድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል እንኳን በሰላም፣ በጤና እና በሕይወት አደረሳችሁ እያለ ልባዊ ምኞቱን ይገልጻል።
የኢድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል ታላቁ የነቢዩ ኢብራሂም እና የልጃቸው ኢስማኢል ለፈጣሪያቸው ያሳዩትን ፍጹም ታዛዥነት፣ ታማኝነት እና የላቀ የራስን ሂወት አሳልፎ የመስጠት እሴት የምናስብበት ታላቅ ዕለት ነው። ይህ በዓል ፈጣሪን በመፍራትና በትሕትና የሚገኝን መለኮታዊ እፎይታ የሚያበስር ሲሆን፣ ምዕመናን የበዓሉን መሥዋዕትነት (ኡድሂያ) ለቤተሰብ፣ ለዘመድ እና ይልቁንም ለተቸገሩ ወገኖች በችሮታ (ሃይማኖቱ በሚያዘው መሰረት) በማካፈል በተግባር የሚገልጹት የወንድማማችነት መገለጫ ነው።
የክልላችን የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የዕለቱን መንፈሳዊ ትርጉም መሠረት በማድረግ የሚከተሉትን የሰላም ጥሪዎች ያስተላልፋል፦
ነቢዩ ኢብራሂም ውድ ልጃቸውን ለመሠዋት የወሰኑት ቁርጠኝነትና ታዛዥነት፤ ዛሬ ለእኛ ለሰው ልጆች ትልቅ ትምህርት አለው። እኛም ለክልላችንና ለሃገራችን ሰላም ስንል የራሳችንን ፍላጎት፣ ቁጣና ጥላቻ ገትተን ለሰላም ቅድሚያ ለመስጠት ልባችንን ልናዘጋጅ ይገባል። እውነተኛ ሰላም የሚገኘው እንደ በዓሉ አስተምህሮ መሰረት፦ በትሕትና፣ በይቅርታና ለሕዝብ ደህንነት ሲባል ራስን ዝቅ በማድረግ እንደሆነ ይታመናል።
በዓሉ የሚታሰብበት የመሥዋዕትነት ሥነ-ሥርዓት ፍቅርን፣ አንድነትን እና ዕርቅን የሚሰብክ ነው። ይህንን የበዓል በረከት ለተጎዱትና ለተቸገሩት ወገኖቻችን ስናካፍል፣ ልባችንንም ለሕዝባችን አንድነትና ለዘላቂ ሰላም ክፍት ማድረግ ይጠበቅብናል። ሰላም የሁሉም ነገር መሠረት እንደመሆኑ መጠን፣ በዓሉ የተጣሉ የሚታረቁበትና የተቀያየሙ ይቅር የሚባባሉበት እንዲሆን ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።
በክልላችን በተለያዩ ምክንያቶች የተፈናቀሉ፣ የተቸገሩና አቅመ-ደካማ ወገኖቻችንን በዚህ ቅዱስ ዕለት በመጠየቅና ካለን ላይ በማካፈል የበዓሉን እውነተኛ መንፈስ በተግባር ማሳየት ይኖርብናል። ለዘመናት የዘለቀውን የሃይማኖቶች መከባበር፣ መተሳሰብ እና የቆየውን የጋራ አብሮነትና መልካም እሴቶቻችንን ይበልጥ በማጠናከር ለትውልድ ማስተላለፍ የሁላችንም የጋራ ኃላፊነት ነው።
በድጋሚ ለተከበራችሁ የእስልምና እምነት ተከታዮች በሙሉ፣ ይህ ታላቅ በዓል የሰላም፣ የፍቅር፣ የይቅርታና የብልጽግና እንዲሆንላችሁ በአማራ ክልል የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ስም መልካም ምኞታችንን እንገልጻለን።
ኢድ ሙባረክ! መልካም የኢድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል!
የአማራ ክልል የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ
ባሕር ዳር፣ ኢትዮጵያ
ግንቦት 13/ 2018