17/06/2020
ያዕቆብ ዋዩና የሲዳሚኛ መጽሐፍ ቅዱስ (Qullaawa Maxaafa)
ያዕቆብ ዋዩ ከዚህ በታች ፎቶግራፉ የሚታየው ሲሆን የተወለደው በሲዳማ ያናሴ/አርፌ አካባቢ ሲሆን ከልጅነቱ ጀምሮ ጌታን በማገልገልና ለትውልዱ መልካም አርአያ በመሆን የሚታወቅ ወንድም ነው፡፡ የትምህርት ዝግጅቱ ከዲፕሎማ ጀምሮ እስከ ሁለተኛ ዲግሪ ድረስ የሥነ-መለኮት ሥልጠና በኢትዮጵያ ቃለ ሕይወት ቤተ ክርስቲያን ዲላ አገልጋዮች ማሰልጠኛ፣ በአዲስ አበባ ኢቫንጀልካል ቲኦሎጂካል ኮሌጅ እና በኢትዮጵያ ድህረ-ምረቃ ሥነ-መለኮት ኮሌጅ ተከታትሏል፡፡ አብዘኛውን ጊዜ ወንጌልን በመስበክና በማስተማር አብያተ ክርስትያናትን የሚያገለግል ሲሆን አመርቂ በሚባል ሂኔታ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ሥራ ሠርቷል፤ ባሁኑ ጊዜ በአዲስ አባባ ወርድ ፎር ዘ ወርልድ በተባለ ድርጅት የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ሥራ አማካሪ ሆኖ በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡
ወንድማችን ያዕቆብ ዋዩ መጽሐፍ ቅዱስን (Qullaawa Maxaafa) በሲዳሚኛ ቋንቋ (Sidaama afoo) በመተርጎም ውጤታማ ከመሆኑም በላይ ለሲዳሚኛ ቋንቋ ዕድገት ያደረገው አስተዋኦ ትልቅ በመሆኑ በወንጌል አማኞች ብቻ ሳይሆን በመላው የሲዳማ ሕዝብና ልህቃን ዕውቅና ሊሰጠው የሚገባው ሰው ነው፡፡ በዚህ በሲዳሚኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ጊዜ እንደሥነ-መለኮት ምሁር የተለያዩ ጥንታዊ ቋንቋዎች (የእብራይስጥና የግሪክ ቅጂዎችን) በማጠንና በመተንተን መተርጎም ብቻ ሳይሆን ከሲዳማ ሕዝብ ባህልና ቋንቃ አውድ ጋር አዛምዶ በጽሑፍ ውስጥ እንዲቀመጥ ያደረገው ጥረት ቀላል አልነበረም፡፡ በመሆኑም ይህ ወንድም የቋንቋ ምሁር በተለይም የሲዳሚኛ ቋንቋ ሊቅ ቢባል ያንሰዋል እንጂ አይበዛበትም፡፡
ይህን የሲዳሚኛ መጽሐፍ ቅዱስ ኃላፊነት ወስዶ ያሳትመው የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማህበር እና ዳኒሽ ሚስዮን ሲሆን በማማከር እገዛ ያደረገው ኤስ አይ ኤል (Society of Linguistic Institute) የተባለ ድርጅት ነው፡፡ ለመተርጎም ሥራ በሲዳማ አካባቢ ያሉ ሦስት ቤተ ክርስቲያናት (ወንጌላዊት ቤተክርስቲያን መካነ ኢየሱስ ደቡብ ሲኖዶስ፣ የቃለ ሕይወት ቤተክርስቲያን መሃል ደቡብ ቀጣና እና የካቶሊክ) ቤተክርስቲያናት ተርጓሚዎችን እንዲመድቡና 50% የገንዘብ ድጋፍ እንዲያደርጉ ኃላፊነት የተሰጣቸው ሲሆን ሌሎቹ 5 (የሙሉ ወንጌል፣ የሕይወት ብርሃን፣ የገነት፣ የመሠረተ ክርስቶስ እና የአድቨንትስት) ቤተክርስቲያናት ሥራውን አይተው (Review) አስተያየት እንዲሰጡ ተደርጎ ሥራው እንደተጀመረ ወንድማችን ያዕቆብ ይናገራል፡፡
ይህ የሲዳሚኛ መጽሐፍ ቅዱስ ትርጉም ሥራ የፈጀው ጊዜ 16 ዓመት (ከህዳር 1991-2007 ዓ.ም) ሲሆን በእነዚህ ሁሉ ጊዜያት የአንበሳውን ድርሻ ወስዶ በመሥራትና እስከ መጨረሻ ጸንቶና ብዙ ተግዳሮቶችን አልፎ ሥራውን ከዳር ያደረሰው ወንድማችን ያዕቆብ ዋዩ ነበር፡፡ በመጀመሪያ ከእርሱ ጋር የነበሩት የሁለቱ ቤተ ክርስቲያናት ተወካዮች አንዱ በጡረታ እና ሌላው በራሱ ምክንያት ሲያቋርጡ በእነርሱ ምትክ የተመደቡትን ሥራውን ማላመድ ለወንድማችን ያዕቆብ ተጨማሪ ሸክም ከመሆኑም በተጨማሪ ከዋና ቅጂዎች የተተረጎመውን በኮምፒዩተር የመጻፍ ኃላፊነትም የእርሱ የእርሱ ብቻ ነበር፡፡
በእነዚህ ሁሉ ዓመታት ያዕቆብን ካጋጠሙት ተግዳሮቶች መካከል አንዱና ዋናው ቤተክርስቲያኑ በገባችው ቃል መሠረት 50% የገንዘብ ድጋፍ ለ11/2 ብቻ ያውም እየተንጠባጠበ ካደረገች በኋላ መቋረጡ ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ ያዕቆብ ካቋረጠ ሥራው እንደማይቀጥል ስለገባቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ማህበርና ዳኒሽ ሚስዮን ለሚቀጥሉት ለ141/2 ድጋፍ በማድረግ ቀጥሎ እንዲያጠናቅቅ አድርገዋል፡፡ የገንዘቡ መቋረጥ ብቻ ሳይሆን በዚያን ጊዜ የነበሩት የቤተክርስቲያን መሪዎች “ይኸን ሁሉ ጊዜ ለምን ታጠፋለህ? ለቀህ ወደ ቤተክርስቲያን አገልግሎት ብትሄድ ይሻልሃል” እያሉ ሞራል የሚነካ ንግግር ሲናገሩት እርሱ ግን እየሠራ ያለውን ሥራ ጠንቅቆ ስለሚያውቅ ጥርሱን ነክሶ ከዳር ሊያደርስ የቻለ የጠራውን ጌታና ቤተክርስቲያኑን ያላሳፈረ ቆራጥ አገልጋይ ነው፡፡
ወንድማችን ያዕቆብ ይህንና የመሳሰሉትን ተግዳሮቶች አልፎ የሲዳሚኛ መጽሐፍ ቅዱስ (Qullaawa Maxaafa) በ2007 ዓ.ም ተጠናቅቆ በህዳር 2008 ዓ.ም እንዲመረቅ አድርጓል፡፡ ባሁኑ ጊዜ አዲስ ኪዳን በሲዳሚኛ መቅረጸ-ድምጽ (Sidama Bible Audio Recording) በአሜሪካ (Faith Comes by Hearing) በሚባል ድርጅት ተዘጋጅቶ እንዲመጣ የተላከ ሲሆን በሂደቱ በኮሮና በሽታ ተፅዕኖ ምክንያት የዘገየ ቢሆንም እንኳ ተጠናቅቆ እንደሚመጣ በመጠባበቅ ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም ሥራ ላይ ወንድማችን ያዕቆብ 1 ወር ሙሉ አስተባባሪ ሆኖ፣ ከዚህ ቀደም አብረውት ይሠሩ የነበሩትን አቶ ቀጸላ ቃንቁራ ከመካነ ኢየሱስ እና አቶ ተፈራ ጃና ከካቶሊክ ቤተክርስቲያን በማሳተፍ ሥራው በጥራትና በቅልጥፍና እንዲሠራ ከማድረጉም በላይ እርሱ በአራቱ ወንጌላትና በራዕይ ላይ የኢየሱስ ገጸ-ባሕሪይ ሆኖ በመቀረጽና ሌሎችንም ቀልጣፋ አንባቢያን በመመልመል ትልቅ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ይህን ፕሮግራም ሲያካሂዱ የነበሩት የድርጅቱ ተወካዮች ኬንያውያን ሲሆኑ ሥራው ከታሰበው ጊዜ በላይ በፍጥነት በመጠናቀቁ ተደስተው “እስካሁን በሌሎች ሀገሮች ከተሠሩት ሁሉ በጥራትም ሆነ በጊዜ ፍጥነት ተወዳዳሪ የለውም” በማለት አድናቆታቸውን ገልጸውለተጋል፡፡
ከዚህ ሁሉ የ16 ዓመታት የያዕቆብ ብዙ ድካምና ልፋት በኋላ ተጠናቅቆ ከ6-7 ሚሊየን ለሚሆነው ሕዝብ አገልግሎት እንዲሰጥ የቀረበው የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂ ቁጥር 3,000 /ሦስት ሺህ/ ብቻ መሆኑ ደስታው ሙሉ እንዳይሆን ከማድረጉ በተጨማሪ በምረቃው ዝግጅት ላይ ታሳትፎ እንዳይኖረው ተደርጎ በሥነ-ሥርዓቱ ላይ እንደማንኛውም ተጋባዥ እንግዳ ሆኖ እንዲገኝ ጥቂት ቀናት ሲቀሩ ተነግሮት ስሜቱን ዋጥ አድርጎ ፕሮግራሙን በመሳተፍ አለፈ፡፡
ከምንም በላይ ያዕቆብን ብቻ ሳይሆን የዚህን አካባቢ ሕዝበ-ክርስቲያንና አገልጋዮች ልብ እጅግ ያሳዘነውና ያስከፋው ክስተት በመጽሐፍ ቅዱሱ ዳግም ህትመትና ሥርጭቱ ላይ የታየው ቅጥፈትና ተንኮል የተሞላ ድርጊት ነው፡፡ ይኸውም የሲዳሚኛ መጽሐፍ ቅዱስ ፍላጎት በማህበረሰቡ በተለይም በወጣቱ ዘንድ እጅግ በጣም ከፍተኛ ስለነበር በብዙ ጉትጎታና ግፍት ለዳግም ህትመት በቅቶ ወደ 16,000 /አሥራ ስድስት ሺህ/ ቅጂ መጥቷል የተባለው የውኃ ሽታ ሆኖ መቅረቱ ነበር፡፡ ዳግም ታትሞ የመምጣቱ ወሬ የደረሳቸው ሰዎች የት እንደሚያገኙ ስላልገባቸው በተደጋጋሚ ያዕቆብ ጋር እየደወሉ ይጠይቃሉ፡፡ እርሱም የዚህን አካባቢ አስተባባሪዎች ሲጠይቅ በቂ መረጃ ማግኘት አልቻለም ነበር፡፡ ነገር ግን ከላይ ተገለጸው የአዲስ ኪዳን መቅረጸ-ድምጽ ለመሥራት የሲዳሚኛ መጽሐፍ ቅዱስ ሲፈለግ በዲላ ከተማ እንደሚገኝ ተነግሯቸው ከዚያ አስመጥተው እንደተጠቀሙ ተሰማ፡፡ የባሰ አታምጣ በሉኝና የሚፈልጉ ሰዎች ከዚያ ሄደው ለመግዛት አስተባባሪውን በስልክ በሚጠይቁበት ጊዜ አልቋል ይባላል፡፡ 16,000 /አሥራ ስድስት ሺህ/ እንዴት ሆኖ፣ ማንስ ገዝቶት፣ ከመቼውስ አለቀ የሚለው ጥያቄ የሁላችንም ይሆናል፡፡
በመጨረሻም የወንድማችን የያዕቆብ ልፋትና ጥረት ሕዝቡ የእግዚአብሔር ቃል በራሱ ቋንቋና አውድ አግኝቶ እርሱን ደስ የሚያሰኝ ሕይወት እንዲኖርና በሁለንተናዊ ማንነቱ እንዲለወጥ በመመኘት እንደሆነ እንረዳለን፡፡ በተጨማሪም ይህ የሲዳሚኛ መጽሐፍ ቅዱስ በሕዝቡ ቋንቋ ተተርጉሞ እንዲዳረስ በሚያደርግበት ጊዜ ለቋንቋው ዕድገትና ለሥነ-ጽሑፉ ያደረገው አስተዋፅኦ ቀላል የሚባል ስላይደለ በአካባቢው ሕዝብ፣ ምሁራንና መንግስት ዕውቅና ሊሰጠው ይገባል የሚል አስተያየት አለን፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ይህ በወንድማችን ያዕቆብ ልፋትና ጥረት እውን የሆነው የሲዳሚኛ መጽሐፍ ቅዱስ (Qullaawa Maxaafa) የሕዝብ ሀብትና ንብረት ስለሆነ በሥርጭቱ ላይ የሚታየው ችግርና ቅጥፈት የተሞላበት አካሄድ ተገቢ ክትትልና እርምት ተደርጎ ለሕዝቡ ተዳረሽ እንዲደረግ በአጽንኦት ያሳሰብን ላሁኑ በዚሁ ላይ እናበቃለን፡፡