18/08/2026
የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተክርስቲያን መካነ ኢየሱስ ሪፈራል ማህበር ምዕመናን ሀዋሳ
==================================
ነሐሴ 6/2018 ዓ.ም የሪፈራል መካነ ኢየሱስ ማህበረ ምዕመናን ሀዋሳ
ርዕሰ ወደ ሰማያዊ ርስታችን በታላቅ ናፍቆትና በጽናት እንጓዝ! በሚል ርዕሰ የሪፈራል መካነ ኢየሱስ ማህበረ ምዕመናን ሀዋሳ
አገልጋይ ወንድም ዳዊት ኩሲያ በመዝ 84:1-7 ላይ ያለዉን የእግዚአብሔር ቃል መሰረት አድርጎ አስተምሯል ።
ወደ እግዚአብሔር ቤተመቅደስ/ወደጽዮን የሚደረግ ጉዞን በተመለከተ በዋሽንት የተዘመረ የቆሬ ልጆች መዝሙር ነው፡፡
መዝሙሩ የጽዮን ተጓዦች ለጉዞ ከመነሳታቸው በፊት በውስጣቸው ያለው ናፍቆት እና ከፍተኛ ገጉት፣ ጉዞ ከጀመሩ በኋላ በመንገዳቸው የሚያጋጥማቸው አስቸጋሪ ሁኔታ እና በመጨረሻ ወደ እግዚአብሔር ቤት ሲደርሱ የሚያገኙት ደስታ እና የነፍስ እርካታ ምን እንደሚመስል ይገልፃል፡፡
በጽዮን ወደሚገኘው ቤተመቅደስ ከሚወስዱ መንገዶች መካከል ዋነኛው እና አብዛኛው መንገደኞች የሚጠቀሙት "ባካ ሸለቆ" (ለቅሶ ሸለቆ) ተብሎ በሚጠራው ሥፍራ ውስጥ የሚያልፈውን መንገድ ነው፡፡
መንገዱ እጅግ አስቸጋሪ በሆነ መልክዓ ምድር የሚያልፍ በመሆኑ፣ ውሃ የሌለበት እና ደረቅ ቦታ በመሆኑ ከነበረው ከባድ ሁኔታ የተነሳ ተጓዦች የሚጓዙት በብዙ ፈተና እና ለቅሶ ነው፡፡
የዮሐንስ ወንጌል 3፡3፣ 1ኛ ጴጥ 1፡3-5፣ 1ኛ ጴጥ 2፡25
ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመስቀል ሞቶ እኛን አዳነን፡፡ እኛ በስሙ አምነን በመንፈስ ዳግመኛ የተወለድን የእግዚአብሔር ልጆች ነን፡፡
በክርስቶስ አምነን ለዳንን እና የእግዚአብሔር ልጆች የማይጠፋ ርስት/የዘላለም መኖሪያ በሰማይ ተይዞልናል/inheritance that doesn''t fade away, reserved in Heaven for you/.
ነፍሳችን ከነበረችበት የመቅበዝበዝ መንገድ ተመልሳ እና አዳኟን/እረኛዋን አውቃ ዕረፍትን አግኝታለች፡፡
አማኞች በክርስቶስ ሞት እና ትንሣኤ የተዘጋጀላቸውን የክብር ርስት ለመውረስ የተጠሩ እና ወደዚያ ክብር በጉዞ ላይ ያሉ ሰዎች ናቸው፡፡
መዝ 84፡6፣ መዝ 23፡ 1-6
እግዚአብሔር/እረኛችን ለምን በሸለቆ መንገድ ይመራናል?
1ኛ) ሊያስተምረን፤ ሊቀርፀን እና በመንፈሳዊ ሕይወታችን እንድንጠነክር ወዶ ነው፡፡
መዝ 84፡6፣ መዝ 119፡71፣ ኢዮብ 36፡22
ጌታ እግዚአብሔር ልጆቹን ለማስተማር እና በእምነታቸው ጠንካራ እንዲሆኑ ከመፈለግ ውጪ ሆን ብሎ ለመጣል ወይም ለማሳዘን ብሎ በሸለቆ መንገድ አይመራም ወይም አያስጨንቅም፡፡ የእርሱ ዓላማ ሳይገባን ቀርቶ ብናዝን እንኳ እንደገና ይራራልናል፡፡
2ኛ) በእርሱ እንድንታመን እና እንድንደገፍ
መዝ 84፡5
በሕይወት መንገድ ስንጓዝ ችግርን እና ስቃይን፣ ህመምን፣ መገፋትን እና መውደቅን ፈጽሞ እንዳናይ ሳይሆን በእነዚህ አስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ስናልፍ እግዚአብሔር ብቸኛ ረዳታችን እረኛችን እንደሆነ አውቀን ወደ እርሱ እንድንመለከትና በእርሱ እንድንታመን ፈቅዶ ነው።
3ኛ) ሊባርከን እና ወደ ደስታው ሊያስገባን ሲፈልግ
መዝ 84፡6፣ 2ኛ ነገ 3፡16-17
ሸለቆ የመከራ፣ የሃዘን እና የለቅሶ ቦታ ብቻ አይደለም፡፡ የበረከት ቦታ እንዲሁም ወደ ቀጣዩ የበረከት እና ክብር ስፍራ የምናልፍበት ቦታ ነው፡፡
ዮሴፍ በገዛ ወንደሞቹ ጉድጓድ ውስጥ ሲጣል እና በጳጥፌራ ሚስት በሃሰት ተከሶ ወህኒ ሲጣል ወደ ፌርዖን ቤተመንግስት መሄጃ መንገድ ሆኖለት ነበር፡፡ ዳንኤልም የተጣለበት ጉድጓድ መጥፊያው ሳይሆን ወደ ፋርስ እና ቂሮስ መንግስት ከፍታ ሥፍራ መውጫ መንገድ ሆኖለት ነበር፡፡
መንገዱን እንዴት እንጓዝ?
1ኛ) በታላቅ ጉጉት እና ናፍቆት
መዝ 84፡ 1-2፣ መዝ 42፡1-3፣ ኢዮብ 19፡ 25-27
በእግዚአብሔር መገኛ ቦታ መሆን እጅግ ያጓጓል፡፡
ይህች ምድር መኖሪያችን አይደለችም፡፡ እኛ እንግዶች/«የሰው አገር ሰው»/ ነን፡፡ እውነተኛው ሰማያዊ አገራችን ሁልጊዜ ሊናፍቀን ይገባል፡፡
የምንጠብቃት አዲስቱ ኢየሩሣሌም አልኖርንባትም፡፡ ነገር ግን በእምነት አይተናታል፡፡ (ራዕይ ምዕ 21 እና 22) በእምነት ስለምናውቃት ዘወትር ትናፍቀናለች፡፡
ዕብ 13፡14፣ ፊልጵ 3፡20፣ 2ኛ ጴጥ 3፡8፣ ያዕ 4፡14
ምድር ላይ የምንኖረው ጊዜ በጣም ጥቂት ነው፡፡ እንግዶች ስለሆንን ዘላለማዊ ቤታችን ይናፍቀናል፡፡
እንግድነት ካልተሰማን እና የዓለም ሰዎች አኗኗር እና አካባቢያቸውን ለምደን ምቾት ከሰጠን ራሳችንን መጠየቅ አለብን፡፡ ከየትኛው አገር ነኝ?
2ኛ) ሁልጊዜ በማሰብ
መዝ 84፡5፣ ቆላ 3፤2
በልቡ ወደ ጽዮን የሚወስደውን መንገድ የሚያስብ ሰው የተባረከና የተመሰገነ ነው።
ዘወትር ሊያሳስበን የሚገባው የማይሞላው የዚህ ምድር ኑሮ፣ ቁሳዊ ፍላጎቶች እና የጊዜያዊ ደስታ ማግኛ መንገዶች ሳይሆኑ የሰማዩ መንግስት ሊሆን ይገባል፡፡
3ኛ) እስከመጨረሻው በጽናት
መዝ 84፡ 7፣ ምሳሌ 4፡18፣ ዳንኤል 12፥13. ዕብ 10:38-39፣ ራዕ 21፡7
ክርስቲና ወደፊት የመሄድ/የመጓዝ ሕይወት ነው፡፡ ጉዞው ከቆመ ወይም ወደኋላ ከሆነ አደጋ አለው! ጉዞውን ከሌሎች ጉዞዎች ለየት የሚያደርገው ወደፊት በተራመድን ቁጥር እየደከምን ሳይሆን ሃይልን እያገኘን መሄዳችን ነው፡፡
አማኝ እረኛውን ተከትሎ እስከመጨረሻው ይጓዛል፡፡ በሸለቆ ርዝመትና ጥልቀት አይፈራም፤ እረኛውን ተጠራጥሮ ወደኋላ አይመለስም፡፡ ካፈገፈገ/ወደኋላው ከተመለሰ ከሚጠፉት አንዱ ይሆናል፡፡
በመጨረሻ
መዝ 84፡7፣ ራዕ 21፡4
በጉዞአችን መጨረሻ የምንገባባት ቅድስቲቱ ከተማ፣ በአዲሲቱ አየሩሳሌም በመንገዳችን የገጠመን ስቃይ፣ ሃዘን፣ መከራ፣ ለቅሶ እና የሞት ፍርሃት ሁሉ ዳግም የማናይባት፣ ሁሉም ዓይነት እንባችን ከሁሉም ፊት ዳግም ላይታይ ለመጨረሻ ጊዜ የሚታበስበት ርስታችን ነች፡፡
ወደፊት የሚያራምደን የእርሱ ሃይል ነው፡፡ የመንገዱ ርዝመትና አስቸጋሪነት ቢያስለቅሰንም ቢያደክመንም ወደ ዕረፍት የሚያደርሰን በቂ ሃይል እና ፀጋ አለው፡፡ የእርሱን ሃይል በድካማችን እየገለፀ ብርታቱን እየጨመረልን ወደፊት ያስኬደናል፡፡
የምንጓዘው ወደ ዘላለም ዕረፍት፣ ደስታ እና ክብር ነው፡፡
👉ሁልጊዜ አዳዲስና ትምህርታዊ, አስተማሪና ቁምነገር ያለውን መንፈሳዊ መረጃዎችን ለማግኘት ይህንን ( Page Like Follow share ) እያደረጋችሁ ተከታተሉን !!
የማህበር ምዕመናን ዲጂታል የወንጌል አገልግሎት ዘርፍ
👇
ተጨማሪ መረጃ ለማግኘት ከታች ያለው Page Follow በማድረግ ቤተሰብ ይሁኑ
https://tr.ee/VcHXkRfRGI
Facebook
https://www.facebook.com/share/1BX2xBEgrx/
YouTube
https://www.youtube.com/
Telegram
https://t.me/EECMYR70