ዘባቤን ሚዲያ

21/05/2026

የጌታችን ንዑሳት በዓላት የሚባሉትም ዘጠኝ ሲሆኑ እነርሱም :- ስብከት ፣ ብርሃን ፣ ኖላዊ ፣ በዓለ ጌና ፣ ግዝረት ፣ ልደተ ስምዖን ፣ ቃና ዘገሊላ ፣ ደብረ ዘይትና መስቀል ናቸው ፡፡

21/05/2026

የጌታችን ዓበይት በዓላት ዘጠኝ ሲሆኑ እነሱም :- ጽንሰት ፣ ልደት ፣ ጥምቀት ፣ ደብረ ታቦር ፣ ሆሣዕና ፣ ስቅለት ፣ ትንሣኤ ፣ ዕርገትና ጰራቅሊጦስ ናቸው ፡፡

21/05/2026

ወደ ሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁት፥ እንዲሁ ይመጣል ። ሐዋ ፩፥፱-፲፩

ዘባቤን ሚዲያ:​​​​እንኳን ለጌታችን ለመድሃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የዕርገት በዓል በሰላም አደረሰን!!!‹‹በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ ለእግዚአብሔር ዘምሩ፡፡›› መዝ 67(6...
21/05/2026

ዘባቤን ሚዲያ:
​​​​እንኳን ለጌታችን ለመድሃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የዕርገት በዓል በሰላም አደረሰን!!!

‹‹በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ ለእግዚአብሔር ዘምሩ፡፡›› መዝ 67(68)፡33፡፡

‹‹ አምላክ በእልልታ፣ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ፡፡ ዘምሩ፣ ለአምላካችን ዘምሩ ፤ ዘምሩ ፣ ለንጉሣችን ዘምሩ፡፡ እግዚአብሔር ለምድር ሁሉ ንጉሥ ነውና ፤ በማስተዋል ዘምሩ፡፡ እግዚአብሔር በአሕዛብ ላይ ነገሠ ፤ እግዚአብሔር በቅድስናው ዙፋን ይቀመጣል፡፡ ›› መዝ 47፡5-8፡፡

‹‹ ነሆም አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፡፡ እስከ ቢታንያም አወጣቸው እጆቹንም አንሥቶ ባረካቸው፡፡ ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ ወደ ሰማይም ዐረገ፡፡ እነርሱም ሰገዱለትና በብዙ ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፣ ዘወትርም እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እየባረኩ በመቅደስ ኖሩ፡፡ ›› ሉቃ 23፡50-53፡፡

‹‹ #ዕርገት ›› የሚለው ቃል ዐረገ ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲሆን ‹‹ ከፍ ከፍ አለ ፣ ወደ ሰማይ ወጣ ›› ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በአንቀጸ ብርሃን ላይ ‹‹ በስምሽ በመለመን በመማጸን የሰው ልጆችን ጸሎት ያሳርጋሉ ›› እንዲል፡፡ እንዲሁም በእሁድ ውዳሴ ማርያም ላይ ‹‹ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ያሳረገ›› እንዳለ፡፡

በተጨማሪም በራእይ 8፡4 ላይ ‹‹የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳን ጸሎት ጋር በመልአኩ እጅ በእግዚአብሔር ፊት ወጣ›› በማለት ዐረገ የሚለውን ቃል በአማርኛ ‹‹ወጣ›› በማለት ይገልጸዋል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ ሞቶ ድኅነትን ከፈፀመ በኋላ በሦስተኛው ቀን የሞትን መውጊያ ሰብሮ ተነሣ፡፡ ከዚህ በኋላ በሞቱ ቀቢጸ ተስፋ ይዟቸው የነበረውን ሐዋርያትና አርድዕትን በተደጋጋሚ ትንሣኤዉን በመግለጥ ያጽናናቸው ነበር፡፡ ጌታችን ከሞት ከተነሣ ከኋላ ለአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ኪዳንንና ትምሕርተ ሕቡዓትን በዝርዝር አስተምሯቸዋል፡፡

መድኃኔዓለም ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣ ጀምሮ እስከ 40 ቀን ድረስ ሐዋርያትን ፣ አርድዕትን በጠቅላላው 120ውን ቤተሰብ ሲያጽናና ቆይቶ ለቅዱስ ጴጥሮስ የፕርትክና (ታላቅ አባት የመሆን) ሥልጣንን ከሰጠው በኋላ 120ውን ቤተሰብ ወደ ደብረ ዘይት ይዞአቸው ወጣ፡፡ በዚያም ሳሉ ‹‹ኃይልን እስክትለብሱ ድርስ በኢየሩሳሌም ጸንታችሁ ቆዩ›› የሚለውን ታላቁን የዕርገት መልእክት አስተላልፎ ከምድር ከፍ አለ፡፡

በመላእክት ምስጋና ‹‹በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ›› እንዲል ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ከዐይናቸዉም ተሰወረ፣ ሐዋርያትም ወደላይ አንጋጠው አንገታቸውን አቅንተው ይመለከቱ ነበር፡፡ ሐዋ 1፡2፡፡ በዚህ ጊዜ ሁለቱ ብርሃናውያን መላእክት እንዲህ ሲሉ ተናገሯቸው ‹‹የገሊላ ሰዎች ሆይ! ወደ ሰማይ እየተመለከታችሁ ለምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁ እንዲሁ ይመጣል፡፡››

ይህ ታላቅ የተስፋ ቃል የመላእክት ንግግር ከቅዱስ ዳዊት ትንቢት ጋር የተዛመደ ሲሆን የጌታችን ምጽአት በምሥራቅ በኩል እንደሚፈጸም ያሳያል፡፡ ሁለቱ መላእክት በንግግራቸው በዚህ ሲሄድ እንዳያችሁት በግርማ ደግሞ በዚህ ይመጣል ብለው ነበር፡፡ ቅዱስ ዳዊት ‹‹በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ ለእግዚአብሔር ዘምሩ ›› መዝ 67(68)፡33 በማለት ይናገራል፡፡ በመሆኑም ጌታችን ያረገው በምሥራቅ ነው ፤ ደግሞ ለፍርድ የሚመጣው በምሥራቅ ነው ማለት ነው፡፡

የጌታችን ዕርገት ምሳሌ እና ትንቢት አለው፡፡ ምሳሌው እንደምን ነው ቢሉ የቅዱስ ዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ ሦስት ቀን አድሮ በሦስተኛው ቀን መውጣቱ ለትንሣኤው ምሳሌ እንደሆነ ሁሉ እንዲሁ የቅዱስ ኤልያስ ዕርገትም ለጌታችን ዕርገት ምሳሌ ነው፡፡ ልዩነቱ ግን ቅዱስ ኤልያስ በመላእክት እርዳታ በፈቃደ እግዚአብሔር ያረገ ሲሆን ጌታችን ግን በፈቃዱ በራሱ ኃይል ዐርጓል፡፡

ትንቢቱም ቅዱስ ዳዊት ‹‹ ወደ ሰማይ ላረገው ለእግዚአብሔር ዘምሩ ›› መዝ 67(68)፡33 ብሎ የተናገረው ነው፡፡ በተጨማሪም ‹‹ወደ ላይ ዐረግህ ምርኮን ማረክህ ስጦታንም ለሰዎች ሰጠህ›› (መዝ 67፡18) የሚል እናገኛለን፡፡ በመጨረሻም የጌታችን ታላቁ የዕርገት መልእክት ‹‹ኃይልን እስክታገኙ በኢየሩሳሌም ጽኑ›› የሚለው ታላቅ መልእክት ነው፡፡

ጌታችን በኢሩሳሌም እንደተወለደ እንዳደገ እንዳስተማረ እንደተሰቀለ በቤተ ክርስቲያንም በቤተልሔም ሥጋው ደሙ የሚዘጋጅባት ቃሉ የሚነገርባት በቤተ መቅደስ ሥጋው የሚቆረስበት ደሙ የሚፈስባት ቦታ ናትና ኢየረሳሌም የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡ ስለሆነም ቅዱስን የእግዚአብሔር መንፈስ እንዲሁም ጸጋ ለማግኘት በቤተ ክርስቲያን መጽናት እንደሚገባ በአጭር ዐረፍተ ነገር ያስተማረው ታላቅ በዓል ነው፡፡

የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገቱን ከትንሣኤው አከታትሎ ወዲያውኑ አላደረገም ፣ ምክንያቱም ፈጽመው ክፋትን የተመሉ አይሁድና በኋላም የሚነሣ የረከሱ መናፍቃን ዕርገቱ ምትሐት ናት ብለው እንዳያስቡ ነው፡፡ ጌታችንም በረቀቀ ጥበቡ የደቀ መዛሙርቱን ተሸብሮ የነበረ ልቡናቸውን እያጽናና መነሣቱንም እያስረዳቸው ከትንሣኤው በኋላ አርባ ቀን ኖረ፡፡

ይህ የዕርገት በዓል ከጌታችን ዓበይት (ታላላቅ) በዓላት መካከል አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጌታችንን የዕርገት በዓል ሁለት ጊዜ ታከብራለች፡፡ ይኸውም በመጀመሪያ ጌታችን ያረገበትን ጥንተ በዓሉን ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የቀመር በዓል ነው፡፡

ዓመታዊ በዓላት ዓዋድያት (Movable Feasts) እና ዓዋድያት ያልሆኑ (Immovable Feasts) ተብለው በሁለት ሊከፈሉ ይችላሉ፡፡ ዓዋድያት (Movable Feasts) የሚባሉት በቅዱስ ዲሜጥሮስ ቀመር መሠረት መባጃ ሐመርን ተከትለው ወደፊት ወደኋላ በመመላለስ በየዓመቱ በተለያየ ቀንና ወር የሚውሉት ናቸው፡፡ እነዚህም እንደ ስቅለት፣ ሕመማት፣ ትንሣኤ፣ ደብረ ዘይት ፣ ሆሣዕና ፣ ዕርገትና ጰራቅሊጦስ የመሳሰሉት ናቸው፡፡

ዋድያት ያልሆኑ (Immovable Feasts) የሚባሉት ደግሞ ሁልጊዜም በወር ውስጥ በሚገኝ በታወቀ ቀን ብቻ በቋሚነት የሚውሉት ናቸው፡፡ እነዚህም እንደ ፅንሰት (ትስብእት) ፣ ልደት ፣ ጥምቀት ፣ ደብረ ታቦር ፣ ቃና ዘገሊላ ፣ ዘመን መለወጫ ፣ መስቀል ፣ 33ቱ የእመቤታችን በዓላት ፣ የመላእክት ፣ የሰማዕታትና የቅዱሳን በዓላት ናቸው፡፡

የጌታችን ዓበይትና ንዑሳት በዓላት፡- ለመጀመሪያ ጊዜ የጌታችንን በዓላት ማክበር የጀመሩት የከበሩ ሐዋርያት ናቸው፡፡ ሠለስቱ ምእት ደግሞ ከ325 ዓ.ም ጀምረው በዓላቱ በቀኖና በሕግ እንዲከበሩ አዘዋል፡፡ ለዚኽም በፍትሐ ነገሥቱ ላይ የተጻፈውን በማስረጃነት ማየት እንችላለን፡፡ ‹‹እግዚአብሔር የጠመመውን እያቀናላቸው፣ የጎደለውን እየሞላላቸው የጌታን በዓላት ማክበር እንዲገባ 318 ሊቃውንት በጉባኤ ኒቅያ በእግዚአብሔር አጋዥነት የጌታችንን በዓላት ያከብሩ ዘንድ፣ ተአምራቱን ይገልጹ ዘንድ፣ ምስጋናውንም ይናገሩ ዘንድ አዘዙ ተናገሩ›› እንዲል፡፡ (ፍትሐ ነገሥት ትርጓሜ፣ ገጽ 260)

የጌታችን ዓበይት በዓላት ዘጠኝ ናቸው፡፡ እነዚህም፡- ፅንሰት (ትስብእት)፣ ልደት፣ ጥምቀት፣ ደብረ ታቦር፣ ሆሣዕና፣ ስቅለት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገትና ጰራቅሊጦስ ናቸው፡፡

የጌታችን ንዑሳት በዓላት የሚባሉትም ዘጠኝ ሲሆኑ እነርሱም ስብከት ፣ ብርሃን ፣ ኖላዊ ፣ በዓለ ጌና ፣ ግዝረት፣ ልደተ ስምዖን ፣ ቃና ዘገሊላ ፣ ደብረ ዘይትና መስቀል ናቸው፡፡ የጌታችን የከበረ የዕረገቱ ረድኤት በረከት ይደርብን!

በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ላረገ አምላካችን ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስጋና ይሁን ከቸር አባቱ ከአብ ሕይወት ከሆነ ከመንፈስ ቅዱስም ጋራ ለዘለዓለሙ አሜን!

📜 ስንክሳር ዘወርሃ ግንቦት

#ሼር

የቻግኒ ብርሃነ ገነት በዓታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ የነበሩት አባታችን ቀሲስ ጌትነት ስሜነህ በድንገተኛ ህመም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል ። የአባታችን ሥርዓተ ቀብር ማኅበረ ካ...
20/05/2026

የቻግኒ ብርሃነ ገነት በዓታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ የነበሩት አባታችን ቀሲስ ጌትነት ስሜነህ በድንገተኛ ህመም ከዚህ ዓለም በሞት ተለይተዋል ።
የአባታችን ሥርዓተ ቀብር ማኅበረ ካህናት ፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ ዲያቆናትና ብዙኃን ምዕመናን ታጅቦ ፤ በማኅሌት ፣ በቅዳሴ ፣ በቅኔና በውዳሴ ታላቅ ሥርዓት ተፈጽሟል ።
​አምላክ ነፍሳቸውን በገነት ያኑርልን ፤ ለቤተሰቦቻቸው ፣ ለቻግኒ ምዕመናንና ለመላው የቤተክርስቲያኒቱ አገልጋዮች መጽናናትን ይስጥልን ።
​ነፍስ ይማር ! 🕊️

20/05/2026

ግንቦት 12 የእነዚህ ሁሉ በዓል ነው - የቅዱስ ሚካኤል የአቡነ ተክለ ሃይማኖት የቅድስት ክርስቶስ ሠምራ የዮሐንስ አፈ ወርቅ የነቢዩ ዳንኤልና እንባቆም ረድኤት በረከት ይደርብን በቅዱስ መስቀሉ ይጠብቀን ።

ለአስተዋይ ልብ !የዛሬው የያዕቆብ ወንድም ይሁዳ መልእክት ።​"ወዮላቸው በቃየን መንገድ ሒደዋልና፥ በበለዓምም የአመፅ ዋጋ ተቃጥለዋልና፥ በቆሬም መቃወም ጠፍተዋልና።" ይሁዳ 1፥11 ​ይህ የ...
20/05/2026

ለአስተዋይ ልብ !
የዛሬው የያዕቆብ ወንድም ይሁዳ መልእክት ።

​"ወዮላቸው በቃየን መንገድ ሒደዋልና፥ በበለዓምም የአመፅ ዋጋ ተቃጥለዋልና፥ በቆሬም መቃወም ጠፍተዋልና።"
ይሁዳ 1፥11

​ይህ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል በተለይ በዚህ ዘመን ስላሉ ሐሰተኞች አስተማሪዎችና መሪዎች በጥብቅ ያስጠነቅቀናል። ጥቅሱ ማንነታቸውን የምንለይበትን 3 አደገኛ መንገዶች በምሳሌነት ያሳየናል፦

​1. የቃየን መንገድ (የጥላቻ መንገድ) ፦ ከእውነተኛ ፍቅር የራቀ፣ በወንድም ላይ ጥላቻን፣ ቅናትንና መከፋፈልን የሚዘራ ሕይወት።

​2. የበለዓም መንገድ (የጥቅም መንገድ) ፦ ለገንዘብ፣ ለዝናና ለግል ጥቅም ሲሉ የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚያሳስቱና ለስህተት ራሳቸውን አሳልፈው የሰጡ መሪዎች።

​3. የቆሬ መንገድ (የዓመፅ መንገድ) ፦ በትዕቢት ተሞልቶ በእግዚአብሔር ሥልጣን፣ አደረጃጀትና መዋቅር ላይ ማመጽና ሥርዓት አልባ መሆን።

​ መደምደሚያ፦

መንፈሳዊ ሕይወታችንን እንፈትሽ! ከእነዚህ ከሦስቱ ጥፊዎች (ከጥላቻ፣ ከጥቅም ፍላጎትና ከዓመፅ) ራሳችንን እንጠብቅ።

​✍️ እግዚአብሔር ለአስተዋይነት ልብን ይስጠን !

Teshale Humando

በ90 ዓመታቸው ዝቅ ብለው በዲቁና የሚቀድሱ ካህን🥰👌        ►መምሬ ብርሃኔ 🙏
19/05/2026

በ90 ዓመታቸው ዝቅ ብለው በዲቁና የሚቀድሱ ካህን🥰👌
►መምሬ ብርሃኔ 🙏

🔔 የክብር በዓል ጥሪ ማስታወቂያ 🔔​በመንፈሳዊ ዜማዋና ሥርዓቷ ዓለምን ያስደመመችው ቅድስት ቤተክርስቲያናችን ፣ የኢትዮጵያ የዜማና የሥነ-ጽሑፍ መሠረት የሆነውን የታላቁን የሊቁ የቅዱስ ያሬድ...
18/05/2026

🔔 የክብር በዓል ጥሪ ማስታወቂያ 🔔

​በመንፈሳዊ ዜማዋና ሥርዓቷ ዓለምን ያስደመመችው ቅድስት ቤተክርስቲያናችን ፣ የኢትዮጵያ የዜማና የሥነ-ጽሑፍ መሠረት የሆነውን የታላቁን የሊቁ የቅዱስ ያሬድን የመሰወሪያ እለት በየዓመቱ ግንቦት 11 በታላቅ ድምቀት ታከብራለች ።
​በመሆኑም በአሳሳ ከተማና በአካባቢው የምትገኙ ኦርቶዶክሳውያን ምዕመናንና ምዕመናት በሙሉ ፤ በአሶሳ ደብረ ሲና ቅዱስ ሚካኤል ካቴድራል በዕለቱ ተገኝታችሁ የሊቁን በረከት እንድትሳተፉ በቅዱስ ያሬድ ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን ።

​“የቅዱስ ያሬድ ረድኤትና በረከት ፤ የቅዱስ ሚካኤል ጥበቃና አማላጅነት አይለየን።”

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡፡ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫየእግዚአብሔር ሕዝብ ጉባኤ፣ የጌታችንና የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክ...
14/05/2026

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡፡

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

የእግዚአብሔር ሕዝብ ጉባኤ፣ የጌታችንና የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አካልና የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ የሆነችው ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ሲኖዶሳዊ በመሆኗ አበው ቅዱሳን በፍትሕ መንፈሳዊና በጉባኤ አድያም ዘአንጾኪያ “ወይኩን ሲኖዶስ ዘጳጳሳት ፪ተ ጊዜያተ በበዓመት - የጳጳሳት ጉባኤም በዓመት ሁለት ጊዜ ይሁን” ብለው በደነገጉት ቀኖና መሠረት፤ በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የሚመራው፣ የሐዋርያት መንበር ወራሽ የሆነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤውን በኅብረተ መንፈስ ቅዱስ ከሚያዝያ 28 እስከ ግንቦት 6 ቀን 2018 ዓ/ም ድረስ አካሄዷል፡፡

ምልዓተ ጉባኤው ስለ ሀገር ሰላም፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን አንድነት፤ ስለ ሰው ልጅ ሁሉ ደኅንነትና ክብር፣ በአጠቃላይ ወቅታዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ሰፊ ውይይቶችን በማድረግ ዘመኑን የዋጁ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡ ከውሳኔዎቹም መካከል፡-

የቤተ ክርስቲያናችንን አንድነት መጠበቅና ማስጠበቅ የቅዱስ ሲኖዶስ ተግባር በመሆኑ ጥንታዊትና ሐዋርያዊት የሆነችውን ቤተ ክርስቲያን በአንድነቷና በሉዓላዊነቷ እንደተረከብናት ለወደፊቱም ሉዓላዊ ክብሯ ተጠብቆ እንድትቀጥል በምልዓተ ጉባኤው የተሠየመው በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የሚመራው “የሀገራዊ ሰላምና የቤተ ክርስቲያን አንድነት” ኮሚቴ ሥራውን አጠናክሮ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

ሰባተኛው ሀገራዊ ምርጫ ፍጹም ሰላማዊ ሆኖ በተረጋጋ መንገድ እንዲካሄድ፣ ለሀገር ሰላምና ለሕዝብ አንድነት በሚጠቅም ሁኔታ እንዲጠናቀቅ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምትጸልይ ሲሆን ምርጫው በሁሉም ወገን ለኢትዮጵውያን ዘላቂ ሰላምንና መረጋጋትን የሚያስገኝ ሆኖ እንዲፈጸም ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት ያሳስባል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የአርሲ ሀገረ ስብከትን በሊቀ ጵጵስና በቋሚነት እንዲመሩ፣ ሕዝቡን እንዲያጽናኑ እየደረሰ ያለውን ችግር ከቋሚ ሲኖዶስና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከሚመራው የሰላም ኮሚቴ ጋር በመሆን የሚመለከተውን የመንግሥት አካል በማነጋገር ዘላቂ መፍትሔ እንዲያፈላልጉ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ወስኗል፡፡

ከጥንት ጀምሮ “ቅዱስ ሲኖዶስ” በሚል ርእስ እየተዘጋጀ ይታተም የነበረው ታሪካዊ መጽሔት የቅዱስ ሲኖዶስ ቀኖናዊ ውሳኔዎችን በማካተት በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት አስፈጻሚነት ሕትመቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

የቤተ ክርስቲያናችንን ደንቦች መመሪያዎች መርምሮ ማጽደቅ የቅዱስ ሲኖዶስ ሉዓላዊ ሥልጣን በመሆኑ፡-

የስብከተ ወንጌል ሐዋርያዊ ተልእኮ ማስፈጸሚያ ደንብ በብፁዕ አቡነ ማርቆስ ሰብሳቢነት

የአንድነት ገዳማት ኅብረት መተዳደሪያ ደንብ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስና ብፁዕ አቡነ ማርቆስ ባሉበት በድጋሚ እንዲታይና ሌሎቹም ለውሳኔ የቀረቡ ደንቦች በሊቃውንትና በሕግ ባለሙያዎች ታርመው ለጥቅምት 2019 ዓ/ም ምልዓተ ጉባኤ እንዲቀርቡ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል

የቀድሞው የሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ “የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ”ና “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ” በሚሉ አርእስት አዘጋጅተው ያሳተሟቸው መጻሕፍትን የማሳተምና የማሰራጨት የባለቤትነት መብት ከሚያዝያ 29 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ለዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም እንዲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

ከተለያዩ አህጉረ ስብከት በቀረቡ ጥናቶችና የማጣራት ውጤቶች መሠረት፡-

የደቡብ ሱዳን ሀገረ ስብከት ከምሥራቅ አፍሪካ ሀገረ ስብከት ጋር ተደርቦ በብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ሊቀ ጳጳስ እንዲመራ፤
ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል ሊቀ ጳጳስ የጋምቤላንና የቤንሻንጉል ጉምዝ አህጉረ ስብከትን ብቻ እንዲመሩ፤
ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጰስ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከትን እንደያዙ እንዲቀጥሉ፤
ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም የቡኖ በደሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቄለም ወለጋ ሀገረ ስብከትን ደርበው በአባትነት እንዲመሩ፣
የኮንታ ዞን ሀገረ ስብከት እንዲሆን የቀረበው ጥያቄ የጸደቀ በመሆኑ ሀገረ ስብከቱ ራሱን ችሎ እንዲደራጅና በብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ሊቀ ጳጳስ እንዲመራ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤
የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የልማት ተግባራትን ምልዓተ ጉባኤው በከፍተኛ ደረጃ በማድነቅ፣ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመ/ፓ/ጠ/ቤ/ክ/ ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ሲቲ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ በአባታዊ አመራር የፈጸሙት አስደናቂ የሥራ አፈጻጸም በጉልህ የሚታይ ለውጥ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የሚጠቅም፣ ሉዓላዊ ክብሯን የሚያስጠበቅ፣ ለሁሉም አበው ምሳሌነት ያለው በመሆኑ ምልዓተ ጉባኤው እጅግ ከፍ ባለ ክብር አመስግኗል፡፡

በዚህም መሠረት በብፁዕ ጠቅላይ ዋና ሥራ አስኪያጁ አባታዊ መሪነት እየተከናወኑ ያሉት ተግባራት ማለትም፡-

የቤተ ክርስቲያንን ቀደምት ሠነዶች በዲጂታል ቴክኖሎጅ እንዲደራጁ የተደረገበት ሥልት ተጠናክሮ እንዲቀጥል፤

ከ1970 ዓ/ም ጀምሮ በመጋዝን ተከማችተው የቆዩ በርካታ ልዩ ልዩ መጻሕፍትን የማሠራጨት ሂደት በተጀመረው መንገድ እንዲጠናቀቅ፤

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የኢንፎርሜሽንና ኮምኒኬሽን ተጠቃሚ እንድትሆን የተጀመረው ዘመኑን የዋጀ ቴክኖሎጂ በሁሉም የቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር በየደረጃው ተጠናክሮ ተግባራዊ እንዲሆን፤

በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥር የተጀመሩ የሕንፃ ግንባታዎችና አጠቃላይ የልማት ሥራዎች በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ ሁሉም አህጉረ ስብከትና ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን አስተዋጽኦና ትብብር እንዲያደርጉ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት ያሳስባል፡፡

በሰሜን አሜሪካ የሰሜን ካሊፎርኒያ፣ ኔቫዳና አሪዞና ሀገረ ስብከት ኆኅተ ሰማይ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስና ቅድስት አርሴማ ገዳም የመንፈሳዊ ኮሌጅ፣ የአብነት ት/ቤት ሥርዓተ ትምህርት የቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖና፣ ታሪክና ትውፊት በጠበቀ መልኩ ተጠናክሮ መዋቅራዊ ተጠሪነቱም በአግባቡ ተጠብቆ ሥራ ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ያቀረበውን የ2019 ዓ/ም በጀት በማጽደቅ በተገቢው መንገድ ሥራ ላይ እንዲውል ምልዓተ ጉባኤው ወስኗል፡፡

በመጨረሻም ቅዱስ ሲኖዶስ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በተነጋገረባቸው ጉዳዮች በትኩረት የተወያየው የቤተ ክርስቲያናችንን ሁለንተናዊ ዕድገትና ተቋማዊ ሕልውና ስለማስጠበቅ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ሀገራችንን ጨምሮ በመላው ዓለም እየታየ ያለው ግጭትና የሰላም መታጣት በእጅጉ አሳስቦታል፡፡

በመሆኑም ስለ ዓለምና ስለ ሀገራችን ሰላም፣ ስለ ሰው ልጆች ደኅንነት፣ በየቦታው በሃማኖታቸው ምክንያት መከራ የሚደርስባቸውን በየቦታው የሚገኙና ግጭት ባለባቸው ቦታዎች ያሉ ኦርቶዶክሳውያንን በማሰብ በመጪው የ2018 ዓ/ም ጾመ ሐዋርያት በመላው ዓለም ባሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት፣ አድባራትና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ጸሎተ ምሕላ እንዲደርስ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በመላው ዓለም፣ በደቡብ አፍሪካና በሳውዲ ዐረቢያ የሚኖሩ ዜጎቻችን ሰብዓዊ መብት እንዲከበር፣ የርኅራኄ ምሕረትና ፍትሕ እንዲያገኙ የሚመለከታቸው አካላት ተገቢውን ክትትል እንዲያደርጉ ቅዱስ ሲኖዶስ ሐዋርያዊ ጥሪውን በማቅረብ ለሰባት ቀናት ሲያካሂድ የሰነበተውን ቀኖናዊ ጉባኤ ዛሬ ግንቦት 6 ቀን 2018 ዓ.ም. በጸሎት አጠናቋል፡፡

“እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ”

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም
ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት
አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ

ግንቦት 6 ቀን 2018 ዓ/ም

Address

Asosa

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ዘባቤን ሚዲያ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Place Of Worship

Send a message to ዘባቤን ሚዲያ:

Share