21/05/2026
ዘባቤን ሚዲያ:
እንኳን ለጌታችን ለመድሃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የዕርገት በዓል በሰላም አደረሰን!!!
‹‹በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ ለእግዚአብሔር ዘምሩ፡፡›› መዝ 67(68)፡33፡፡
‹‹ አምላክ በእልልታ፣ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ፡፡ ዘምሩ፣ ለአምላካችን ዘምሩ ፤ ዘምሩ ፣ ለንጉሣችን ዘምሩ፡፡ እግዚአብሔር ለምድር ሁሉ ንጉሥ ነውና ፤ በማስተዋል ዘምሩ፡፡ እግዚአብሔር በአሕዛብ ላይ ነገሠ ፤ እግዚአብሔር በቅድስናው ዙፋን ይቀመጣል፡፡ ›› መዝ 47፡5-8፡፡
‹‹ ነሆም አባቴ የሰጠውን ተስፋ እኔ እልክላችኋለሁ ፤ እናንተ ግን ከላይ ኃይል እስክትለብሱ ድረስ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆዩ፡፡ እስከ ቢታንያም አወጣቸው እጆቹንም አንሥቶ ባረካቸው፡፡ ሲባርካቸውም ከእነርሱ ተለየ ወደ ሰማይም ዐረገ፡፡ እነርሱም ሰገዱለትና በብዙ ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ፣ ዘወትርም እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እየባረኩ በመቅደስ ኖሩ፡፡ ›› ሉቃ 23፡50-53፡፡
‹‹ #ዕርገት ›› የሚለው ቃል ዐረገ ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲሆን ‹‹ ከፍ ከፍ አለ ፣ ወደ ሰማይ ወጣ ›› ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በአንቀጸ ብርሃን ላይ ‹‹ በስምሽ በመለመን በመማጸን የሰው ልጆችን ጸሎት ያሳርጋሉ ›› እንዲል፡፡ እንዲሁም በእሁድ ውዳሴ ማርያም ላይ ‹‹ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ያሳረገ›› እንዳለ፡፡
በተጨማሪም በራእይ 8፡4 ላይ ‹‹የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳን ጸሎት ጋር በመልአኩ እጅ በእግዚአብሔር ፊት ወጣ›› በማለት ዐረገ የሚለውን ቃል በአማርኛ ‹‹ወጣ›› በማለት ይገልጸዋል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ዓርብ ሞቶ ድኅነትን ከፈፀመ በኋላ በሦስተኛው ቀን የሞትን መውጊያ ሰብሮ ተነሣ፡፡ ከዚህ በኋላ በሞቱ ቀቢጸ ተስፋ ይዟቸው የነበረውን ሐዋርያትና አርድዕትን በተደጋጋሚ ትንሣኤዉን በመግለጥ ያጽናናቸው ነበር፡፡ ጌታችን ከሞት ከተነሣ ከኋላ ለአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ኪዳንንና ትምሕርተ ሕቡዓትን በዝርዝር አስተምሯቸዋል፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጎ ከተነሣ ጀምሮ እስከ 40 ቀን ድረስ ሐዋርያትን ፣ አርድዕትን በጠቅላላው 120ውን ቤተሰብ ሲያጽናና ቆይቶ ለቅዱስ ጴጥሮስ የፕርትክና (ታላቅ አባት የመሆን) ሥልጣንን ከሰጠው በኋላ 120ውን ቤተሰብ ወደ ደብረ ዘይት ይዞአቸው ወጣ፡፡ በዚያም ሳሉ ‹‹ኃይልን እስክትለብሱ ድርስ በኢየሩሳሌም ጸንታችሁ ቆዩ›› የሚለውን ታላቁን የዕርገት መልእክት አስተላልፎ ከምድር ከፍ አለ፡፡
በመላእክት ምስጋና ‹‹በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ›› እንዲል ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ከዐይናቸዉም ተሰወረ፣ ሐዋርያትም ወደላይ አንጋጠው አንገታቸውን አቅንተው ይመለከቱ ነበር፡፡ ሐዋ 1፡2፡፡ በዚህ ጊዜ ሁለቱ ብርሃናውያን መላእክት እንዲህ ሲሉ ተናገሯቸው ‹‹የገሊላ ሰዎች ሆይ! ወደ ሰማይ እየተመለከታችሁ ለምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁ እንዲሁ ይመጣል፡፡››
ይህ ታላቅ የተስፋ ቃል የመላእክት ንግግር ከቅዱስ ዳዊት ትንቢት ጋር የተዛመደ ሲሆን የጌታችን ምጽአት በምሥራቅ በኩል እንደሚፈጸም ያሳያል፡፡ ሁለቱ መላእክት በንግግራቸው በዚህ ሲሄድ እንዳያችሁት በግርማ ደግሞ በዚህ ይመጣል ብለው ነበር፡፡ ቅዱስ ዳዊት ‹‹በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ ለእግዚአብሔር ዘምሩ ›› መዝ 67(68)፡33 በማለት ይናገራል፡፡ በመሆኑም ጌታችን ያረገው በምሥራቅ ነው ፤ ደግሞ ለፍርድ የሚመጣው በምሥራቅ ነው ማለት ነው፡፡
የጌታችን ዕርገት ምሳሌ እና ትንቢት አለው፡፡ ምሳሌው እንደምን ነው ቢሉ የቅዱስ ዮናስ በዓሣ አንበሪ ሆድ ሦስት ቀን አድሮ በሦስተኛው ቀን መውጣቱ ለትንሣኤው ምሳሌ እንደሆነ ሁሉ እንዲሁ የቅዱስ ኤልያስ ዕርገትም ለጌታችን ዕርገት ምሳሌ ነው፡፡ ልዩነቱ ግን ቅዱስ ኤልያስ በመላእክት እርዳታ በፈቃደ እግዚአብሔር ያረገ ሲሆን ጌታችን ግን በፈቃዱ በራሱ ኃይል ዐርጓል፡፡
ትንቢቱም ቅዱስ ዳዊት ‹‹ ወደ ሰማይ ላረገው ለእግዚአብሔር ዘምሩ ›› መዝ 67(68)፡33 ብሎ የተናገረው ነው፡፡ በተጨማሪም ‹‹ወደ ላይ ዐረግህ ምርኮን ማረክህ ስጦታንም ለሰዎች ሰጠህ›› (መዝ 67፡18) የሚል እናገኛለን፡፡ በመጨረሻም የጌታችን ታላቁ የዕርገት መልእክት ‹‹ኃይልን እስክታገኙ በኢየሩሳሌም ጽኑ›› የሚለው ታላቅ መልእክት ነው፡፡
ጌታችን በኢሩሳሌም እንደተወለደ እንዳደገ እንዳስተማረ እንደተሰቀለ በቤተ ክርስቲያንም በቤተልሔም ሥጋው ደሙ የሚዘጋጅባት ቃሉ የሚነገርባት በቤተ መቅደስ ሥጋው የሚቆረስበት ደሙ የሚፈስባት ቦታ ናትና ኢየረሳሌም የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡ ስለሆነም ቅዱስን የእግዚአብሔር መንፈስ እንዲሁም ጸጋ ለማግኘት በቤተ ክርስቲያን መጽናት እንደሚገባ በአጭር ዐረፍተ ነገር ያስተማረው ታላቅ በዓል ነው፡፡
የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገቱን ከትንሣኤው አከታትሎ ወዲያውኑ አላደረገም ፣ ምክንያቱም ፈጽመው ክፋትን የተመሉ አይሁድና በኋላም የሚነሣ የረከሱ መናፍቃን ዕርገቱ ምትሐት ናት ብለው እንዳያስቡ ነው፡፡ ጌታችንም በረቀቀ ጥበቡ የደቀ መዛሙርቱን ተሸብሮ የነበረ ልቡናቸውን እያጽናና መነሣቱንም እያስረዳቸው ከትንሣኤው በኋላ አርባ ቀን ኖረ፡፡
ይህ የዕርገት በዓል ከጌታችን ዓበይት (ታላላቅ) በዓላት መካከል አንዱና ዋነኛው ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የጌታችንን የዕርገት በዓል ሁለት ጊዜ ታከብራለች፡፡ ይኸውም በመጀመሪያ ጌታችን ያረገበትን ጥንተ በዓሉን ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የቀመር በዓል ነው፡፡
ዓመታዊ በዓላት ዓዋድያት (Movable Feasts) እና ዓዋድያት ያልሆኑ (Immovable Feasts) ተብለው በሁለት ሊከፈሉ ይችላሉ፡፡ ዓዋድያት (Movable Feasts) የሚባሉት በቅዱስ ዲሜጥሮስ ቀመር መሠረት መባጃ ሐመርን ተከትለው ወደፊት ወደኋላ በመመላለስ በየዓመቱ በተለያየ ቀንና ወር የሚውሉት ናቸው፡፡ እነዚህም እንደ ስቅለት፣ ሕመማት፣ ትንሣኤ፣ ደብረ ዘይት ፣ ሆሣዕና ፣ ዕርገትና ጰራቅሊጦስ የመሳሰሉት ናቸው፡፡
ዋድያት ያልሆኑ (Immovable Feasts) የሚባሉት ደግሞ ሁልጊዜም በወር ውስጥ በሚገኝ በታወቀ ቀን ብቻ በቋሚነት የሚውሉት ናቸው፡፡ እነዚህም እንደ ፅንሰት (ትስብእት) ፣ ልደት ፣ ጥምቀት ፣ ደብረ ታቦር ፣ ቃና ዘገሊላ ፣ ዘመን መለወጫ ፣ መስቀል ፣ 33ቱ የእመቤታችን በዓላት ፣ የመላእክት ፣ የሰማዕታትና የቅዱሳን በዓላት ናቸው፡፡
የጌታችን ዓበይትና ንዑሳት በዓላት፡- ለመጀመሪያ ጊዜ የጌታችንን በዓላት ማክበር የጀመሩት የከበሩ ሐዋርያት ናቸው፡፡ ሠለስቱ ምእት ደግሞ ከ325 ዓ.ም ጀምረው በዓላቱ በቀኖና በሕግ እንዲከበሩ አዘዋል፡፡ ለዚኽም በፍትሐ ነገሥቱ ላይ የተጻፈውን በማስረጃነት ማየት እንችላለን፡፡ ‹‹እግዚአብሔር የጠመመውን እያቀናላቸው፣ የጎደለውን እየሞላላቸው የጌታን በዓላት ማክበር እንዲገባ 318 ሊቃውንት በጉባኤ ኒቅያ በእግዚአብሔር አጋዥነት የጌታችንን በዓላት ያከብሩ ዘንድ፣ ተአምራቱን ይገልጹ ዘንድ፣ ምስጋናውንም ይናገሩ ዘንድ አዘዙ ተናገሩ›› እንዲል፡፡ (ፍትሐ ነገሥት ትርጓሜ፣ ገጽ 260)
የጌታችን ዓበይት በዓላት ዘጠኝ ናቸው፡፡ እነዚህም፡- ፅንሰት (ትስብእት)፣ ልደት፣ ጥምቀት፣ ደብረ ታቦር፣ ሆሣዕና፣ ስቅለት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገትና ጰራቅሊጦስ ናቸው፡፡
የጌታችን ንዑሳት በዓላት የሚባሉትም ዘጠኝ ሲሆኑ እነርሱም ስብከት ፣ ብርሃን ፣ ኖላዊ ፣ በዓለ ጌና ፣ ግዝረት፣ ልደተ ስምዖን ፣ ቃና ዘገሊላ ፣ ደብረ ዘይትና መስቀል ናቸው፡፡ የጌታችን የከበረ የዕረገቱ ረድኤት በረከት ይደርብን!
በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ላረገ አምላካችን ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስጋና ይሁን ከቸር አባቱ ከአብ ሕይወት ከሆነ ከመንፈስ ቅዱስም ጋራ ለዘለዓለሙ አሜን!
📜 ስንክሳር ዘወርሃ ግንቦት
#ሼር