06/09/2025
ዘመኑን መቀደስ
ክፍል አንድ
(በመምህር የኔታ ገብረ መድኅን እንየው )
✍️ያለ ዘመን በባሕርዩ ጸንቶ ይኖር የነበር፤አሁንም ያለ፤ ለዘለዓለሙም የሚኖር እግዚአብሔር ብቻ ነው።
ሌሎች ፍጡራን ግን የጊዜ መነሻና መዳረሻ አላቸው።ለሕያዋን ፍጡራንም መኖሪያቸው እግዚአብሔር ነው።
✍️ፍጡራን እኛ የምንመላለስበት የአሁን ጊዜ ግን በዘለዓለማዊነት መካከል ጣልቃ የገባ ስፍረ ዘመን ነው።ከዚህ ጊዜያዊ ዘመን በኋላ የማይለካ ዘለዓለማዊነትን እንወርስ ዘንድ ተስፋ እናደርጋለን።
በዚህ አሁናዊ ስፍረ ዘመንም ዕድሜያችን እና ሥራችን ሲለካበት ይኖራል። በቀኝም ሆነ በግራ የምንቆመው በዚህ ጊዜ ባስመዘገብነው ውጤት ነው።ነጻ ፈቃዳችንን በነጻነት ጊዜ ተጠቅመን ስንሠራ ወይ ለፍትሀ እግዚአብሔር ወይም ለምሕረተ እግዚአብሔር የተገባን እንሆናለን።
✍️ያለፈው ዓመት ከተሰጠን ከዕድሜያችን አንዱ ዓመት ሲሆን የሚመጣውም ዓመትም ከቀሪ ዕድሜያችን አንዱ ዓመት ነው።ስለዚህ ዕድሜን ማበላሸት ራስን ከመብላት ይቆጠራል ጊዜን በግድየለሽነት መግደል ራስን ከማጥፋት ይቆጠራል።
እያንዳንዷ ሰከንድ፣ሰዓት፣ቀን ፣ዕለት፣ዓመት..የምትውለው ከዕድሜያችን እየተቀነሰች ስለሆነ የትኛውም ጊዜ ድኅነታችንን የምንፈጽምበት የተወደደ ጸጋ ነው።"በተወደደ ሰዓት ሰማሁህ በመዳንም ቀንረዳሁህ ይላልና እንሆ የተወደደው ሰዓት አሁን
ነው፤እንሆ የመዳን ቀን አሁን ነው።"፪.ቆሮ.፮፥፪ እንዳል።
✍️በዚህች ፈጣን ጊዜ፦ትናንትን ተቀባይ፤ዛሬን ጠባቂ፤ነገን ለተተኪው ትውልድ አቀባይ የሆኑ ክርስቲያኖች ጊዜያቸውን በአግባብ ተጠቅመው በሁለገብ ኦርቶዶክሳዊት ዕይታና በነባራዊ ሁነት ላይ በቂ ግንዛቤ ኑሯቸው ባለቸው የክህሎት አቅም ሁሉ ዕድሜያቸውን ሳያባክኑ በጊዜው ሁሉ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊነት ማስቀጠል ግዴታ አለባቸው።
✍️ሰው ከእግዚአብሔር ጋራ፣ሰው ከሰው ጋራ፣ሰው ከሥነ ፍጥረታት ጋራ ያለው መስተጋብር የሚወሰነው በፈጣሪና በፍጡር መካከል ያለውን ግንኙነት በጊዜው ሁሉ መጠበቅ ሲቻል ነው።
✍️ከተግባር ሁሉ ትልቁ ስኬት ተፈጥሮን እና መዳረሻዋን መረዳት ነው።መረዳት የሌለው ሕይወት ግን ጽኑዕ ሸክም ነው፡፡ኦርቶዶክሳዊ ደግሞ ምሉዕነት ነው።ክርስቲያናዊ መረዳት ፍጡራዊ ድንበር የለውም።ድንበሩ ወሰኑ ህላዌ እግዚአብሔር ነው።
✍️ከአቅም ሁሉ ከተግባር ሁሉ የሚበልጠው የአስተሳስብ ብልጫ ነው።በዚህ ዘመን ያለን አማኞች ዋናው ክፍተታችን የአስተሳስብ ጉድለት ነው።የወሬ ክምችት ዕውቀት አይሆንምና በኦርቶዶክሳዊ አስተሳስብ ቅኝት ውስጥ ጊዜውን መዋጀት እንዳለብን ጊዜው ራሱ ግድ ይለናል።"ዘመኑን ዋጁ።"ኤፌ.፭፥፲፮እን.
✍️ዘመኑን ዋጁ ማለት ዘመኑን ምሰሉ ማለት አይደለም።
ዘመኑን መቀደስ ቻሉ ዘመኑን አስከትሉት እንጂ ዘመን የወለደውን ንጉሥ የወደደውን እያላችሁ አትከተሉ ማለቱ ነው።
ሃይማኖት፣ቀኖና፣ትውፊት እንደ አባቶቻችን አሠራር ግን እንደ ዘመናችን ሲሆን ዘመኑን መዋጀት ይባላል።
✍️በሥሁት እሳቤ እየተመሩ ዘመኑን ከመከተል በርቱዕ እሳቤ እየተቃኙ ዘመኑን ማስከተል እጅግ ይበልጣል።
✍️ከላይ እንዳየነው ጊዜ ማለት ራሱ በሂደታዊ ድኅነት ውስጥ ያለ ሰው ነው። (ጧት፣ቀን፣ማታ፣ሌሊት- ህፃንነት፣ወጣትነት፣ጉልምስና፣ ሽምግልና፣ ሞት ወጣኒነት፣ማዕከላዊነት፣ፍጹምነት፣) ስለዚህ ጊዜን ማባከን ጸረ ራስነት ነው።ወይም ነገረ ድኅነትን ማማሰን ነው።
✍️ጊዜ ከቅጽበት ቢጀምርም ምልዓቱ ሂደታዊነት ነው።ምሥጢረ ድኅነትም ከቅጽበት ቢጀምርም አፈጻጽሙ ሂደታዊነት ነው።"የራሳችሁን መዳን ፈጽሙ"ፊል.፪፥፲፪ እን.