ከገድላት አንደበት-ke gedilat andebet

ከገድላት አንደበት-ke gedilat andebet ከኢ/ኦ/ተዋሕዶ ቤ/ክ ገድላት ላይ የተገኙ የቅዱሳን አባቶቻችን እና የቅዱሳት እናቶቻችን ገድላቸው በየቀኑ ይነገርበታል!

"ንስሓ ሳይገባ እንዳይሞት"በኀጢአት ብንወድቅ እንኳን ቅዱሳን ለነፍሳችን ድኅነት ምን ያህል እንደሚተጉ ይኽ ታሪክ በእጅጉ ያስተምረናል። ንጉሥ ዓምደ ጽዮን በነገሠ ጊዜ እንደ አባቱ እግዚአብሔ...
12/12/2025

"ንስሓ ሳይገባ እንዳይሞት"

በኀጢአት ብንወድቅ እንኳን ቅዱሳን ለነፍሳችን ድኅነት ምን ያህል እንደሚተጉ ይኽ ታሪክ በእጅጉ ያስተምረናል። ንጉሥ ዓምደ ጽዮን በነገሠ ጊዜ እንደ አባቱ እግዚአብሔርን የሚወድ ሃይማኖቱ የቀና ነበር፡፡ ከዚኽም በኋላ ሰይጣን የዝሙትን ሥራ የሚያሠራው ሆነ፡፡ አንዲት የአባቱ ቅምጥ የነበረችውንም አመንዝራ ሴት አገባ፡፡ እርሷም ሰንበትን እስከሻረና ሃይማኖቱን እስከለመወጠ ድረስ ኀጢአትን አሠራችው፡፡ ስለዚህም የክቡር አባታችን የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ልጅ አባ ፊሊጶስ ንጉሡን አወገዘው፡፡ ንጉሡም አብያተ ክርስቲያናትን ዘጋቸው፡፡

በዚያም ወራት አባታችን ዜና ማርቆስ በደብረ ብሥራት ገዳም አልነበረም-በንጉሥ ዓምደ ጽዮን በአባቱ በይኩኖ አምላክ ዘመን ፈጽሞ ተሠውሮ ነበርና፡፡ ምክንያቱም ለንጉሥ ይኩኖ አምላክ የእኅቱ ልጅ ስለነበር ራስ ወይም ቢትወደድ አድርጎ በዓለም እንዳይሾመው ስለዚህ ከደብረ ብሥራት ሸሽቶ በምሁር ሀገር ወደሚገኝ የጎጎት ጫካ ውስጥ የይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት እንስከሚያልፍ ድረስ ተሠውሮ ኖረ፡፡

ንጉሥ ዓምደ ጽዮንም ሃይማኖቱን በካደ ጊዜ እስከ አርባ ዓመት በተሠወረበት ቦታ ኖረ፡፡ ልጆቹ ቅዱሳን መነኰሳትን ይጎበኛቸው ዘንድ በጣና ባሕር ወዳለች የደቅ ደሴት ሲሔድ በደመና ላይ ተጭኖ ነበር፣ ወደ ምሁር ሀገር ሲመለስም በአንበሶችና በነብሮች ጀርባ ላይ ሆኖ በሥውር ነበር፡፡ ንጉሥ ዓምደ ጽዮንም በነገሠ ጊዜ በ14ኛው ዓመት ጌታችን በሞት ሊወስደው ወደደ፡፡ ያንጊዜም ሰውን የምትወድ አምላክን የወለደች ክብርት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስለ ንጉሡ ልጇን መድኃኔዓለምን ማለደችው፡፡ ልጇ ያለ ንስሓ በቁጣው እንዳይቀሥፈው አባታችን ዜና ማርቆስ ይለምናት
ነበርና፡፡

አባታችንም በሚጸልይ ጊዜ እንዲህ ብሎ ለመናት፡- ‹ለሰው ዘር ሁሉ የምትራሪ አምላክን የወለድሽ በሁለት ወገን ድንግል የሆንሽ እመቤቴ ማርያም ሆይ! ባሪያሽ ዓምደ ጽዮን ከኃጢአቱ ተመልሶ ንስሓ ሳይገባ እንዳይሞት፤ የልጅሽ ጠላት ሰይጣን በዝሙት ሥራ ሳያስተው በፊት ወዳጅሽ ነበርና አስቢ፡፡ ልጅሽም ለጻድቃን ብቻ አልመጣምና ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ስለ ኃጢአተኞች ድኅነት ከአንቺ ከሥጋሽ ሥጋን ከነፍስሽ ነፍስን ነሥቶ ሰው ሆነ እንጂ፡፡ እርሱ ራሱ በቅዱስ ወንጌሉ ‹ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም ኃጥአንን ወደ ንስሓ ልጠራ መጥቻለሁ እንጂ› ብሏልና፡፡ እመቤቴ ሆይ! በልጅሽ ፊት ይህንን አሳስቢ፣ እርሱ እስከ ዘለዓለም ይቅርታ በማድረግ ምሕረቱ የበዛ መሐሪ ነው› እያለ ለመናት፡፡ በዚያም ወራት ክብርት እመቤታችን አባታችንን ዜና ማርቆስን ‹ወደ ዓምደ ጽዮን ሔደህ ንስሓ ግባ በለው› አለችው፡፡

የሕይወት እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ይህን ስለነገረችው አባታችን ዜና ማርቆስ ደስ አለው፡፡ እርሷ የምትራራ የሁላችን ተስፋ፣ የኃጥአን መዳኛቸው፣ ጻድቃንንም መልካም የሆነ ተጋድሏቸውን እስኪፈጽሙ ድረስ የምትረዳቸው ናትና፡፡ አባታችን አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም ‹‹እግዚአብሔር ሊምረው የወደደውን ሰው የማርያምን ፍቅር ያሳድርበታል›› ሲል የተናገረው ለዚህ ነው፡፡

ከዚኽም በኋላ አባታችን ዜና ማርቆስ ወደ ደብረ ብሥራት ገብቶ ከልጆቹ ጋር በ40 ዓመቱ ተገናኘ፡፡ እነርሱም ይህን ያህል ዘመን ሲጠፋባቸው ያረፈ መስሏቸው ነበርና አሁን
ባገኙት ጊዜ ተደንቀው ወዴት እንደነበር ሲጠይቁት አባታችንም ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው የሆነውን ነገራቸው፡፡ ከዚኽም በኋላ በትምህርትና በዕድሜ ከሌሎቹ
መነኰሳት ልጆቹ የሚበልጠውን ልጁን አባ እንድርያስን ወደ ንጉሥ ዓምደ ጽዮን ንስሓ እንዲገባ መልእክት ያደርስ ዘንድ ላከው፡፡ አባታችንም በገዳሙ ሆኖ ስለ ንጉሡ ሱባኤ ይዞ ስለነበር ንጉሡ ልቡናው ተመለሰለት፣ ያደረበት የዝሙት መንፈስም ለቆት ጠፋ፡፡ ንጉሡም የአባታችንን መልእክት ከሰማ በኋላ በተሰበረ ኅሊና ሆኖ ንስሓ ገባ፡፡ አባ እንድርያስንም ‹ኃጢአቴ ከሰው ሁሉ ኃጢአት የበዛ ነውና ከባድ ቀኖና ስጠኝ› አለው፡፡

ዳግመኛም ‹ለእኔ በማትገባኝ አመንዝራ ሴት ምክንያት የአባታችን የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ልጆች በግፍ እንድገድላቸውና ከመንበረ ክብራቸው እንዳሳድዳቸው ሰይጣን አስገድዶኛል፣ ስለዚህም የማትገባኝን አመንዝራ ሴት ስለማግባቴና ስለቅዱሳን ደም ፈጣሪዬ ተቆጥቶ ወደ ገሃነመ እሳት እንዳይጨምረኝ ከገጸ መዓቱ የተነሣ
እፈራለሁና› ብሎ መሪር እንባን አለቀሰ፡፡ አባታችን ዜና ማርቆስም በዚያች ሌሊት ስለእርሱ ከመስገድና ከመጸለይ
አላቋረጠም ነበር፡፡

ከዚኽም በኋላ ንጉሡ ከአባታችን ዜና ማርቆስ ረድእ ቀኖና ተቀብሎ በቀንም በሌሊትም በየሰዓቱ እልፍ እልፍ እየሰገደ በሌሊትም ከዙፋኑ ወደ መሬት ወርዶ እየሰገደ ያድራል። በቀንም በወርቅ ከተሠራ ልብሰ መንግሥቱ ሥር ከበግ ፀጉር የተሠራ ማቅ የሚለብስ ሆነ፡፡ ቀኖናም ከተቀበለ በኋላ የአባታችን ዜና ማርቆስ የጸሎቱ ኃይል ከአጋንንት ጦር እየረዳው በአንድ ዓመቱ ቀኖናውን ፈጽሞ በሰላም ዐረፈ፤ ወደ መንግሥተ ሰማያትም ገባ፡፡
(ገድለ አቡነ ዜና ማርቆስ ገጽ 248-254 )

የአቡነ ዜና ማርቆስ እመቤት አምላክን የወለደች ክብርት እመቤታችን እኛንም ታስምረን። ምንም እንኳን በከፋ ኀጢአት ብንወድቅ ለነፍሳችን ድኅነት የሚተጉ ቅዱሳን አባቶቻችንና ቅዱሳት እናቶቻችን የሰጠን ልዑል እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን!!!

የተስዓቱ ቅዱሳን ገድል ታትሞ ወጥቶ ለገዳሙ ዛሬ እንዲደርስ ተደርጓል። እንኳን ደስ አላችሁ!!! (የዘጠኙም ቅዱሳን የየራሳቸው ገድል ማለትም 9 የተለያየ ገድል ነው አንድላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ...
07/12/2025

የተስዓቱ ቅዱሳን ገድል ታትሞ ወጥቶ ለገዳሙ ዛሬ እንዲደርስ ተደርጓል። እንኳን ደስ አላችሁ!!!

(የዘጠኙም ቅዱሳን የየራሳቸው ገድል ማለትም 9 የተለያየ ገድል ነው አንድላይ ለመጀመሪያ ጊዜ የታተመው። ከነገረ ቅዱሳን አገልግሎታችን ውስጥ አንዱ ከዚኽ በፊት ያልታተሙ አዳዲስ ገድላትን ለገዳማት በማሳተም ሕዝበ ክርስቲያኑም በነፍስ በሥጋ እንዲጠቀም ለማድረግ የአቅማችንን ሞክረናል። አሁንም እግዚአብሔር ፈቅዶ ቅዱሳኑ በምልጃቸው ረድተውን የተስዓቱ ቅዱሳንን ገድል ብዛት 5ሺህ ኮፒ አሳትመን ለ9ኙም ገዳማት ለማስረከብ ዝግጅት ላይ ነን። ለአንዱ ገዳም (ለአቡነ ሊቃኖስ) ዛሬ ኅዳር 28 ቀን በዓመታዊ መታሰቢያ በዓላቸው ዕለት አስረክበናል። የተቀሩት ገዳማት ኅትመቱ ሲደርስ የሚወስዱ ይኾናል።)

የገጽ ብዛት= 1281 (በትልቁ በA4 መጠን፤ ልክ እንደ በስንክሳሩ መጠን ወይም በመልክዐ ጉባኤው መጠን ነው የተዘጋጀው)

ዋጋ= 2ሺህ 5 መቶ ብቻ (እኛ በወሰነው መሠረት።) ገድሉ "ቢያንስ 4 ሺህ እና 5 ሺህ ከዚያም በላይ ይሸጥ" የተባለ ቢኾንም ገድሉም በጣም ትልቅና በከፍተኛ ጥራት በክር ስፌት ጭምር የተዘጋጀ ስለኾነ በእኛ ውሳኔ መሠረት 2,500 (ኹለት ሺህ አምስት መቶ ብር ብቻ) በጣም በርካሽ እንዲሸጥ ስናደርግ ወደፊት ገዳማቱን በዐሥራትም ጭምር እንዲደገፉ ለማድረግ አስበን ነው እንጂ ከገድሉ ግዝፈትና ጥራት አንጻር ቢያንስ ከ5 ሺህ በታች የሚሸጥ መጽሐፍ አይደለም።

አ.አ ላይ ገድሉ የሚገኝበትን ቦታ ወደፊት (ከ5 ቀን በኋላ) የምናሳውቅ ይኾናል። (እስከዚያ መጠበቅ የማይችል አክሱም አካባቢ ካለው ከአቡነ ሊቃኖስ ገዳም ማስመጣት ይችላል።)

በዚኽች ዕለት ኅዳር 28 ቀን በዓመታዊ በዓላቸው ታስበው በሚውሉት በአቡነ ሊቃኖስ ገዳም ውስጥ ጌታችን ልክ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ዓይነት መንገድ በሀገራችን በሚገኘው በዚህ ገዳም ላይም ነሐሴ 13 ቀን ብርሃነ መለኮቱን ገልጦበታል። የተገለጠውም እንደነ ሄኖክና ኤልያስ በሞት ፋንታ የለተሰወሩት ለአቡነ ሊቃኖስ ነው። አቡነ ሊቃኖስ ከዘጠኙ ቅዱሳን ውስጥ አቡነ ሊቃኖስ ለየት የሚሉበት ነገር ቢኖር ዓሥሩም የእጆቻቸውና የእግሮቻቸው ጣቶች እንደፋና ያበሩ ነበር፡፡ ይህንንም ገድለ አቡነ አረጋዊ ‹‹ቆመው ጸሎት በሚጸልዩበት ጊዜ ዓሥሩ የእጆቻቸው ጣቶችና ዓሥሩ የእግሮቻቸው ጣቶች እንደፋና የሚያበሩበትና እንደመብረቅ የሚብለጨልጩበት ጊዜ አለ›› በማለት ይገልጸዋል፡፡ በሥዕላቸውም ላይ ይህንኑ ለማሳየት አባቶቻችን የራሳቸውን ጥበብ ተጠቅመዋል፡፡ የአቡነ ሊቃኖስ ገዳማቸው በደብረ ቁናጽል አክሱም ከአባ ጰንጠሌዎን ገዳም አቅራቢያ ይገኛል፡፡ ጻድቁ ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን ያደረጉ ነበር፡፡ መላእክትም ዘወትር ባለመለየት ይጎበኙዋቸው ነበር፡፡ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስም ዘወትር እየተገለጠላቸው ይባርካቸውና ቃልኪዳን ይሰጣቸው ነበር፡፡

አቡነ ሊቃኖስ በጸሎታቸው አጋንንትን አውጥተዋል፣ ድውያንን ፈውሰዋል፣ ዕውራንን አብርተዋል፣ ሙታንን አንሥተዋል፡፡ ከተስዓቱ ቅዱሳን ውስጥ አራቱ ሞትን ሳያዩ ተሠውረዋል፡፡ አቡነ አረጋዊ ጥቅምት 14 ቀን ተሰወሩ፡፡ አቡ ገሪማ ሰኔ 17 ቀን፣ አቡነ አፍጼ ግንቦት 29 ቀን፣ አቡነ ሊቃኖስ ህዳር 28 ቀን ተሠወሩ፡፡

ጌታችን ነሐሴ 13 ቀን ልክ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን በገለጠበት ዓይነት መንገድ በዚህ በፎቶው ላይ በሚታየው በአቡነ ሊቃኖስ ገዳም ላይም ብርሃነ መለኮቱን ገልጦበታል።

አቡነ ሊቃኖስ እንደ ሙሴ ከደረቅ ጭንጫ ላይ ውሃ በተአምራት በማፍለቅ ይታወቃሉ። አቡነ ገሪማ፣ አቡነ ጰንጠሌዎኖንና አቡነ ሊቃኖስ ሦስቱም የተሰጣቸው ጸጋ የተለያየ ነበር፡፡ አቡነ ገሪማ ለሠርክ መሥዋዕት የሚሆነውን ስንዴ በተአምራት ዕለቱን ዘርተው ዕለቱን አጭደው ነዶውን ዛፍ ላይ አውጥተው በሬዎቹንም ከዛፍ ላይ አውጥተው አበራይተው ዘሩን ከመሬት አጠራቅመው ዕለቱን ለቅዱስ ሥጋ ወደሙ መፈተቻ ያዘጋጁ እንደነበር ገድላቸው ይናገራል፡፡ አቡነ ጰንጠሌዎን ደግሞ በጠዋት ወይራ ተክለው ዕለቱን ግንዱን ፈልጠው ለማዕጠንት ፍሕም አገልግሎት ይጠቀሙበት ነበር፡፡ አቡነ ሊቃኖስ ደግሞ በደረቅ ጭንጫ ላይ ውሃ በተአምራት አፍልቀው ለቅዳሴ ማይ ጸሎት ይጠቀሙበት ነበር፡፡ ዓለምን በእጃቸው እፍኝ የያዙ እነኚህ እጅግ የከበሩ ታላላቅ ቅዱሳን ከሚያደርጉት ተአምር ውስጥ ለአንዳቸው የተሰጠው ለሌላኛው አልተሰጣቸውም ነበር፡፡ የሦስቱም የተአምራት ውጤት የሆኑት ስንዴ፣ የማዕጠንት ፍሕምና ማይ/ውሃ ደግሞ የግድ ለቅዳሴው አገልግሎት አስፈላጊ ናቸው፡፡

ሦስቱም ቅዱሳን የሚገኙበት ገዳማቸው የተለያየና የተራራቀ ቢሆንም አቡነ ገሪማ በተአምራት ዕለቱን ዘርተው ያጨዱትን የስንዴ ነዶና ራሳቸውን በሬዎቹንም ከዛፍ ላይ አውጥተው አበራይተው ያመረቱትን ስንዴ ለአቡነ ጰንጠሌዎንና ለአቡነ ሊቃኖስ በነፋስ አውታር ጭነው ይልኩላቸዋል! አቡነ ሊቃኖስም እንደ መሴ ከጭንጫ ላይ ያፈለቁትን ውሃ በወንፊት አድርገው ለአቡነ ገሪማና ለአቡነ ጰንጠሌዎን ይልኩላቸዋል፡፡ አቡነ ጰንጠሌዎንም ዕለቱን ተክለው ዕለቱን ለሠርክ መሥዋዕት ያደረሱትን የወይራ የማዕጠንት ፍሕም በሻሽ አድርገው ለአቡነ ሊቃኖስና ለአቡነ ገሪማ ይልኩላቸዋል፡፡

የዳግማዊው ሙሴ የአቡነ ሊቃኖስ ረድኤት በረከታቸው ይደረርብን በጸሎታቸው ይማረን!

ማሳሰቢያ፦ ገድሉ አ.አ ላይ መሸጥ ከጀመረ በነጋዴዎች እጅ ገብቶ በኋላ ላይ በጣም በተጋነነ ዋጋ እንዳትገዙ ከአሁኑ ዝግጅት አድርጋችሁ ተጠባበቁና ልክ መሸጥ ሲጀምር ከምናሳውቃችሁ የተለመዱ ቦታዎች እንድትወስዱ ይኹን።

የእናታችን የቅድስት ወለተ ጴጥሮስ ቅዱስ ዐፅሟ የሚገኝበት ሬማ መድኀኔዓለም ገዳም!ረድኤት በረከቷ ይደርብንና በዚኽች ዕለት ይኽን ታላቅ ተኣምር አደረገች፦ ቅድስት ወለተ ጴጥሮስ ካረፈች በኋላ...
26/11/2025

የእናታችን የቅድስት ወለተ ጴጥሮስ ቅዱስ ዐፅሟ የሚገኝበት ሬማ መድኀኔዓለም ገዳም!
ረድኤት በረከቷ ይደርብንና በዚኽች ዕለት ይኽን ታላቅ ተኣምር አደረገች፦ ቅድስት ወለተ ጴጥሮስ ካረፈች በኋላ የዕረፍቷ የመታሰቢያ በዓሏ በደረሰ ጊዜ ከደስያትና ከአድባራት ከገዳማት ከየአገሩ ስፍር ቁጥር የሌለው ሕዝብ ተሰበሰበ፡፡

ከእነርሱም መካከል መምህራንና መነኮሳት፣ ቀሳውስት ዲያቆናት ከነማዕጠንታቸው ነበሩ፡፡ ከእነርሱም መካከል የዕለት ጉርስ የሌላቸው ብዙ ነዳያን፣ ዐይነ ሥውራንና አንካሶች ነበሩ፡፡

የቅድስት ወለተ ጴጥሮስ ገድሏና ተአምራቷ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ ተሰምቷልና ለበዓሏ የመጣውን ሕዝብ የገዳሙ መነኮሳት በየማዕረጋቸው አስቀምጠዋቸው ለዝክሯ
የተዘጋጀውን ብዙ መብልና መጠጥን በልተውና ጠጥተው እስኪያስተርፉ ድረስ ሰጧቸው፡፡ ነገር ግን ከዚያ በፊት
ዝክሯን ሲያዘጋጁ በመነኮሳቱ ዘንድ ታላላቅ ተአምራት ተደረገ፡፡ ይኸውም ለመታሰቢያ ከሚጋገር እንጀራ የተረፈ አንድ እንጀራ ብቻ የሚሆን ሊጥ በትልቅ ጋን ውስጥ ነበር፡፡ ያም አንድ እንጀራ ብቻ የሚሆነው ሊጥ በትልቁ ጋን ውስጥ ሳለ ሊጡ በተአምራት ወደላይ እየፈላ እስኪፈስ ድረስ ሞልቶ እየፈሰሰ ተገኘ፡፡ መነኮሳቱም ወደሌላ ዕቃ እየገለበጡ በሚቀዱ ጊዜ ሊጡ አልጎድል ብሎ ነበር፤ በየቀኑም እየጨመረና እየበዛ ሞልቶ ይገኝ ነበር፡፡ ይህንንም ምሥጢር የሚያውቁ መነኮሳይያት እኅቶች ለማንም አልተናገሩም ነበር-ከእናታችን ከቅድስት ወለተ ጴጥሮስ የተአምራቷ ኃይል የተነሣ እጅግ ያደንቃሉ እንጂ፤ ነገር ግን አንዲት ለመናገር የምትቸኩል እኅት ሊጡ በተአምራት እንደሚፈላ ጮኻ ተናገረች፡፡ ያንጊዜም ሊጡ ወዲያውኑ መፍላቱን አቆመ፡፡ እንጀራ ጋጋሪዋም ከሊጡ በምትቀዳ ጊዜ እያደር እየጎደለ ሔደ፡፡

እንዲሁም በተመሳሳይ ሁኔታ በገዳሙ ውስጥ ጥቂት ዱቄት ነበረች፣ ያችም ዱቄት በብዙ ዕንቅብ እየወሰዱ ሌላ ቦታ እስኪያስቀምጡ ድረስ በተአምራት እጅ በረከተ፡፡ ነቢዩ ኤልያስ በሰራጵታ ዱቄቱን አበርክቶ መበለቲቱን እንደመገባት (1ኛ ነገ 17፡7-17) እንደዚሁ ሁሉ የቅድስት ወለተ ጴጥሮስ የዕረፍቷ መታሰቢያ ይደረግበት ዘንድ የተዘጋጀው ዱቄት በተአምር በርክቶ ተገኘ፡፡ በዚህም ጊዜ ሌላኛዋ አንዲት እኅት ይህንን ተአምር አይታ ጮኻ በተናገረች ጊዜ ዱቄቱ መብዛቱ ቆመ፡፡ለመናገር የሚቸኩል ሰው የእግዚአብሔርን በረከት ያሳጣል፡፡ ሐዋርያው ‹‹ሰው ሁሉ ለመስማት ፈጠነ ለመናገር የዘገየ ይሁን›› እንዳለ ዳግመኛም አረጋዊ መንፈሳዊ ‹‹ለመናገር የሚቸኩል ሰውን ፈጣሪው ይርቀዋል›› አለ፡፡ እንደገናም በእናታችን የዕረፍቷ መታሰቢያ ወቅት ጥቂት ዕንጨት በርክታ ብዙ ሆና ከማታ እስከ ጠዋት ድረስ ብዙ እንጀራ ጋገረች፡፡ ሌላም በእንጀራው በወጡ በጠላው ላይ የተደረገው ተአምር ተነግሮ አይዘለቅም-የተአምራቷን ብዛት እግዚአብሔር ያውቃል እንጂ በሰው ዘንድ ተቆጥሮ አያልቅም፡፡››

(ገድለ ቅድስት ወለተ ጴጥሮስ ገጽ 107-108)

የእናታችን የቅድስት ወለተ ጴጥሮስ ረድኤት በረከቷ ይደርብን፣ በጸሎቷ ይማረን።
✞ ✞ ✞

(የቅዱሳን ገድላቸውን ተአምራታቸውን በየቀኑ በቴሌግራም ቻናል በኩልም ይከታተሉ።)

https://t.me/kegedilatandebet2721

‹‹ክብርህ ከመላእክት ኹሉ ክብር ከፍ ያለ የምሕረት መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ሆይ! መሬትና ውኃ ለአልተቀላቀለበት ከነፋስና እሳት ብቻ ለተፈጠረው መልአካዊ ገጽታህ ሰላም እላለሁ፤ ከላይ ከሰማይ ...
21/11/2025

‹‹ክብርህ ከመላእክት ኹሉ ክብር ከፍ ያለ የምሕረት መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ሆይ! መሬትና ውኃ ለአልተቀላቀለበት ከነፋስና እሳት ብቻ ለተፈጠረው መልአካዊ ገጽታህ ሰላም እላለሁ፤ ከላይ ከሰማይ ተልከህ በምትመጣበት ጊዜ በሲኦል የሚኖሩ ግዞተኞች ኹሉ ‹ቅዱስ ሚካኤል ሆይ! መጣኽልን ደረስኽልን› እያሉ ደስታቸውን ይገልጣሉ፡፡›› (መልክዐ ቅዱስ ሚካኤል)

በመላው ዓለም የምትኙ ኦርቶዶክሳውን እና ኦርቶዶክሳውያት ኹላችሁ እንኳን ለሊቀ መላእክት ለቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ በዓል አደረሳችሁ አደረሰን! ለሀገራችን ሰላም ለሕዝባችን ፍቅር አንድነትን ያድለን!

ዱራታዎስና ቅዱስ ሚካኤል! የእግዚአብሔር ወዳጅ የሆነ ስሙ ዱራታዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፡፡ የሚስቱም ስም ቴዎብስታ ነው፡፡ እነርሱም ሁልጊዜ ያለማቋረጥ የዚህን የከበረ መልአክ የቅዱስ ሚካኤልን የበዓሉን መታሰቢያ ያደርጉ ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ በሀገር ውስጥ ችግር በሆነ ጊዜ ገንዘባቸው አለቀ፡፡ ለቅዱስ ሚካኤልም ለበዓሉ መታሰቢያ የሚያደርጉትን እስኪያጡ ድረስ ቸገራቸው፡፡ ዱራታዎስም ሸጦ ለመልአኩ በዓል መታሰቢያ ያደርገው ዘንድ የእርሱንና የሚስቱን ልብስ ይዞ ወጥቶ ሄደ፡፡
የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም በታላቅ መኮንን አምሳል ለዱራታዎስ ተገለጠለትና ወደ ባለጸጎች ሄዶ በእርሱ ዋስትና በአንድ ዲናር አንድ በግ እንዲወስድ፣ ሁለተኛም ወደ ባለ ስንዴ ዘንድ ሄዶ በእርሱ ዋስትና ስንዴን እንዲወስድ ዳግመኛም ወደ ዓሣ አጥማጅ ዘንድ ሄዶ አንድ ዓሣ እንዲወስድ ነገር ግን ወደቤቱ ሳይርስ የዓሣውን ሆድ እንዳይቀድ አዘዘው፡፡ ዱራታዎስም እንደታዘዘው አደረገ፡፡ ወደቤቱም በተመለሰ ጊዜ ቤቱ ሁሉ በበረከት ተመልቶ አገኘው፡፡ እርሱም እጅግ ተደስቶ የዚህን የክበር መልአክ የመታሰቢያውን በዓል አደረገ፡፡ ጦም አዳሪዎችንና ድኆችን ጠርቶ አጠገባቸው፡፡
ከዚህም በኋላ ለዱራታዎስና ለሚስቱ ቅዱስ ሚካኤል ሁለተኛ ተገለጠላቸው፡፡ ዱራታዎስንም የዓሣውን ሆድ እንድሰነጥቅ አዘው፡፡ በሰነጠቀውም ጊዜ 300 የወርቅ ዲናር በዓሣው ሆድ ውስጥ ተገኘ፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ዱራታዎስንና ሚስቱን ቴዎብስታን እንዲህ አላቸው፡- ‹‹ከዚህ ዲናር ወስዳችሁ ለባለ በጉ፣ ለባለ ዓሣውና ለባለ ስንዴው ዕዳችሁን ክፈሉ፡፡ የቀረውም ለፍላጎታችሁ ይሁናችሁ እግዚአብሔር አስቧችኋልና በጎ ሥራችሁን፣ መሥዋዕታችሁንና ምጽዋታችሁን አስቦ በዚህ ዓለም አሳመረላችሁ፣ በኋለኛውም መንግሥተ ሰማያትን አጀጋጀላችሁ›› አላቸው፡፡
እነርሱም ይህን ነገር ሲሰሙ ደነገጡ፡፡ የከበረ ገናናው መልአክም ‹‹ከመከራችሁ ሁሉ ያዳንኳችሁ የመላእክት አለቃ እኔ ሚካኤል ነኝ፣ መሥዋዕታችሁንና ምጽዋታችሁን ወደ እግዚአብሔር ፊት ያሳረግሁ እኔ ነኝ፡፡ አሁንም በዚህ ዓለም ከበጎ ነገር እንድታጡ አላደርጋችሁም›› አላቸው፡፡ ይህንንም ከነገራቸው በኋላ ወደ ሰማያት ወጣ፡፡ እነርሱም በፍርሃትና በክብር ሰገዱለት፡፡››
የመላእክት አለቃ ቅዱስ የሚካኤል ጥበቃው አይለየን! ከበዓሉ በረከት ይክፈለን!

ጥቅምት 28-ጸሎቱና በረከቱ ከኹላችን ጋር ለዘለዓለሙ ይኹንና አባታችን ማር ይምዓታ የአደረገው ተኣምር ይኽ ነው፡- የአባታችን አባ ጉባ ቤተ ክርስቲያን አቅራቢያ በኾነች በምድር ርኁባን አንዲ...
07/11/2025

ጥቅምት 28-ጸሎቱና በረከቱ ከኹላችን ጋር ለዘለዓለሙ ይኹንና አባታችን ማር ይምዓታ የአደረገው ተኣምር ይኽ ነው፡- የአባታችን አባ ጉባ ቤተ ክርስቲያን አቅራቢያ በኾነች በምድር ርኁባን አንዲት ሴት ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን የዚኽች ሴት የወርቅና የብር ጌጦቿ፤ የከበሩ የልብሶቿም ጌጣ ጌጦች ገንዘቧ ኹሉ ተሰረቀ፡፡

ይኽችም ሴት ወደ አባታችን አባ ጉባ ቤተ ክርስቲያን ሔዳ ወደ ውስጥ ገብታ በመሪር ልቅሶና በተቃጠለ ልብ አለቀሰች፡፡ ‹‹ቅዱሳን አባቶቼ አባ ይምዓታና አባ ጉባ ሆይ! በዚኽች ሌሊት ገንዘቤን ኹሉ ሰረቁኝ፡፡ ከምለብሰው ልብስ ስንኳን አላስቀሩልኝም፡፡ አባቶቼ ቅዱስ ማር ይምዓታና የአባ ጉባ ሥዕል ሆይ! ለምኑልኝ፡፡ የሰረቁኝ እሊያ ሌቦች ይራሩልኝ ዘንድ እለምናችኋለሁ፤ እማልዳችኋላሁ›› አለች፡፡ የአባታችን አባ ጉባ ደብር ካህናትም ‹‹የገንዘብሽን ሌባ ያጋልጡልሻልና አትደንግጭ›› አሏት፡፡

በዚያች ሌሊትም ኹለቱ ቅዱሳን ያ ሌባ ተኝቶ ሳለ ወደዚያ ሌባ ቤት ደረሱ፡፡ በታላቅ ጽኑ መቅሠፍትም ይገርፉት ጀመር፡፡ ያም ሌባ ከግርፋቱ ብዛት የተነሣ ጮኸ፡፡ ጎረቤቶቹም ጩኸቱን ሰምተው ‹‹ምን ኾንህ›› አሉት፡፡ እርሱም ‹‹እገሊት የምትባል ሴትን ንብረት ስለ ሰረቅኹ እነሆ ኹለቱ ቅዱሳን አባ ይምዓታና አባ ጉባ ይገርፉኛል፤ ‹ለምን ሰረቅኽ?› እያሉ ይደበድቡኛል›› አላቸው፡፡ ‹‹ጌቶቼ ሆይ! ይቅር ይለኝ ዘንድ ለምኑልኝ፡፡ የዚያችን ሴት ንብረትም ከሸሸግኹበት አውጥቼ እመልስላታለኹ›› እያለ ይጮኻል፤ ይጨነቃል፡፡ እነሆ እነዚኽ ቅዱሳን አባ ይምዓታና አባ ጉባ ይደበድቡኛል›› አለ፡፡ እሊያስ ቅዱሳን በዚኽ አሉ፤ ነገር ግን ቅዱሳንን አያይዋቸውም፤ በዚያ በሌባው ጀርባ ላይ የዱላውን ሰንበርና የግርፋቱን ምልክት ብቻ ያያሉ እንጂ፡፡

እንደዚኽ በግርፋት እየተገረፈ ሦስት ቀናት ተቀመጠ፡፡ በቀንና በሌትም ጮኸ፡፡ ነገር ግን መነሣት አይችልም ነበር፡፡ በሦስተኛው ቀን ቅዱሳን አባ ማር ይምዓታና አባ ጉባ ተገለጡለትና ‹‹እስኪ ዐይኖችህን አንሣና ወደ እኛ ተመልክት›› አሉት፡፡ ያን ጊዜም ቅዱሳን ማር ይምዓታና አባ ጉባ በቀይና በሐመልሚል ፈረሶቻቸውን ላይ ተጭነው ከቤተ መቅደሳቸው ሲወጡ ተገለጡለት፡፡ ፈታቸውም እንደ ፀሐይ ይበራልና በላያቸው ከአለው ብርሃን የተነሣ ይጠይቃቸው ዘንድ አልቻለም፡፡ ያን ጊዜም የዚያችን ሴት ንብረት የሰረቀ ያ ሌባ በኹለቱ ቅዱሳን በአባ ይምዓታና በአባ ጉባ የጸሎታቸው ኀይል የሰረቃትን ንብረት ኹሉ ወስዶ ሰጣት፡፡
የአባታችን ማር ይምዓታና የአባ ጉባ ጸሎታቸውና በረከታቸው ከኹላችን የማኅበር ልጆች ጋር ይኹን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

(በቅርቡ ከሚታተመው ከተስዓቱ ቅዱሳን ገድል ላይ የተወሰደ)

ከባሕር ወለል በላይ በ2300 ሜትር ከፍታ ላይ የሚገኘው እጅግ አስገራሚው የአቡነ ይምዓታ ፍልፍል ዋሻ ቤተ መቅደስ!
ጥቅምት 28 ቀን በዓመታዊ የዕረፍታቸው በዓል ታስበው የሚውሉት አቡነ ይምዓታ ይህንን ተራራ በተአምራት በፈረስ እንደወጡት ገድላቸውን ጠቅሰው የገዳሙ አባቶች ይናገራሉ፡፡ ከአገልጋዮቻቸው አንደኛው ለፈረሱ ራት ሳር ሳይሰጠው በውሸት "ለፈረሱ ሳር ሰጥቼዋለሁ" ብሎ አቡነ ይምዓታን ይዋሻቸዋል፡፡ እርሳቸውም የተሰወረውን ሁሉ ያውቁ ነበርና "...ውሻ እንጂ የሰው ልጅ በሐሰት አይጮህም" ብለው ሐሰትን ስለመናገሩ ገሠጹት፣ ወዲያውም በተአምራት ከአንገቱ በላይ የውሻ መልክ ያለው ሆነ፡፡

የአቡነ ይምዓታ ፍልፍል ዋሻ ቤተ መቅደስ ትግራይ ገርዓልታ ልዩ ስሙ ‹‹ጎሕ›› ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ይገኛል፡፡ ቤተ መቅደሱ ሰማይን እንደ ምሰሶ ደግፈው የያዙ የሚመስሉ በጣም ረጃጅም ተራሮች መካከል በአንደኛው ጭፍ ላይ ይገኛል፡፡ ቤተ መቅደሱ ከባሕር ወለል በላይ በ2300 ሜትር ከፍታ ላይ የሚገኝ ሲሆን ቤተ መቅደሱ ያለበት የተራራው ርዝመት ብቻውን 300 ሜትር ነው፡፡ ቤተ መቅደሱ በር ላይ ለመድረስ በጭንቅና በፍርሃት ሆኖ ተራራውን እንደዝንጀሮ በእጅ እየቧጠጡ መውጣት ይጠይቃል፡፡ እርሱም ቢሆን በገዳሙ አባቶች እገዛና ድጋፍ ነው፡፡
ቤተ መቅደሱ እጅግ የሚደንቀው በተፈጥሮአዊ አቀማመጡ ብቻ አይደለም ውስጡ ያሉት የግድግዳ ላይ ሥዕሎችም በ6ኛው መ/ክ/ዘመን የተሣሉ እጅግ ድንቅና ጥንታዊ ናቸው፡፡

ስለዚሁ የአቡነ ይምዓታ እጅግ አስደናቂ ቤተ መቅደስ ገድለ አቡነ አረጋዊ ‹‹በሞት በዐረፉ ጊዜ የሥጋቸው ሥርዓተ ግንዘት በመላእክት እጅ ነው የተከናወነው፡፡ ይልቁንም ቁመቱና ርዝመቱ ከታላላቅ ገደል እጅግ በጣም የሚበልጥ የድንጋይ ዓምድ ከወንዝ ማዶ ዘንበል ብሎ መጥቶ ሥጋቸውን በክብር ተቀብሎ በተራራው ጫፍ ላይ እስከዛሬም ድረስ ፈጽሞ ሳይነቃነቅና ሳይናወፅ ቀጥ ብሎ ቆሞ ይገኛል›› በማለት ይገልጻል፡፡

ከተስዓቱ ቅዱሳን አንዱ የሆኑትና የሥጋቸው ሥርዓተ ግንዘት በመላእክት እጅ የተከናወነላቸው የአቡነ ይምዓታ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!
✞ ✞ ✞

(ለ3ኛ ጊዜ በተከፈተው አዲስ ቻናል በኩልም በጽሑፍና በድምፅ ይከታተሉ።)
https://t.me/kegedilatandebet27217

"ልጄን ከሞት እንደምታስነሣው አምናለሁ"በዐፄ ናዖድ ዘመነ መንግሥት ለአንዲት ሴት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ልጇን ከሞት በማስነሣት ያደረጉላት ድንቅ ተአምር ይህ ነው፦ ሴቲቱም ልጇ ከሞተና ...
15/10/2025

"ልጄን ከሞት እንደምታስነሣው አምናለሁ"

በዐፄ ናዖድ ዘመነ መንግሥት ለአንዲት ሴት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ልጇን ከሞት በማስነሣት ያደረጉላት ድንቅ ተአምር ይህ ነው፦ ሴቲቱም ልጇ ከሞተና ነፍሱ ከሥጋው ከተለየች በኃላ እናቲቱ በአባታችን ጸሎት በማመን የአባታችንን ማኅበር ወደሚጠጡበት የሕፃኑን በድን ወሰደችው።

በዚያ የማኅበር ቤትም ጋን ተቀምጦ አገኘች። ጋኑንም አስተካክላ በምድር ላይ አቆመችውና "አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ በጸሎትህ ተማጽኛለሁ፣ ማኅበርህ በሚሠራበት በዚህ ጋን ልጄን ከሞት እንደምታስነሣው አምናለሁ..." ብላ ከጸለየች በኃላ በእምነት ሆና የልጇን በድን ከጋኑ ውስጥ ጨመረችው። ልጁም ያንጊዜ ወዲያውኑ ከሞት ተነሥቶ ከጋኑ ውስጥ እንዳለ ጮኸ። እናቱም አውጥታ ጡቷን ሰጠችውና ጠባ። አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እኛንም በሕይወተ ሥጋ ያለነውን ከኅሊና ሞት ያስነሡን፣ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!
✞ ✞ ✞

በረከታቸው ይደርብንና ዳግመኛም አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ያደረጉት ተአምር ይህ ነው፡- በአንዲት አገር ውስጥ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ዝክር የምታዘክር አንዲት ሴት ነበረች፡፡ ዝክራቸውንም እንድትዘክር አንድ ጻድቅ አባት ነግረዋታልና፡፡ ከዕለታትም በአንደኛው ቀን የአገሩ ልጆች በአንድ ትልቅ ገደል ሥር ተሰብስበው እየተጫወቱ ትልቁ ገደል በላያቸው ላይ ወደቀባቸውና ሁሉም ልጆች ወዲያው ሞቱ፡፡ አንድ ስንኳ የተረፈ የለም፡፡

የእነዚያም ልጆች ወላጆቻቸውና ዘመዶቻቸው ታላቅ ልቅሶን አለቀሱላቸው፡፡ ይህም የሆነው በመጋቢት ሦስት ቀን ነው፡፡ ልጆቹም ከሞቱ በኋላ ሦስት ሰዓት በሆነ ጊዜ የዚያች የአባታችንን ዝክር የምታዘክረው ሴት ልጅ ከሞተ በኋላ ተነሣ፣ ከተቀበረበትም ወጣ፡፡ ፀሐይም ከመጥለቋ አስቀድሞ ወደ ቤቱ ሄዶ ከእናቱ ዘንድ ደረሰ፡፡ እናቱም ስታየው በደስታ ጮኸች፡፡ የሀገሪቱም ሰዎች ሁሉ ተሰብስበው ወደ እርሷ መጡና ሞቶና ተቀብሮ የነበረውን የሴቲቱን ልጅ አሁን በሕይወት ሲያገኙት እጅግ አደነቁ፡፡ ልጁንም ‹‹ከሞት እንዴት ተነሣህ?›› አሉት፡፡ ልጁም እንዲህ አላቸው፡- ‹‹የሞትነውን ልጆች ሁላችንንም የእሳት ነበልባል የሚመስሉ መላእክት ወደ ሰማይ ወሰዱን፡፡ ከዚያም በኋላ በመንገድ ከአንድ ትልቅ ሰው ጋር ተገናኘን፣ የራስ ጠጉሩ እንደበረዶ ነጭ ነው፣ እንደተፈተለም ነጭ ሐር ነው፡፡ እንደ መብረቅ ያለ ልብሱንም ባየን ጊዜ ልጆች ሁላችን ደንግጠን ወደቅን፡፡ እርሱንም የሚከተሉት እንደ ሰማይ ከዋክብት ነበሩ፡፡ ከልጆቹም ሁሉ እኔን ለይቶ ብቻዬን እጄን ያዘኝ፡፡ መላእክትንም ‹ይህንን መታሰቢያዬን የምታደርግልኝ የዚያችን ሴት ልጅ ለምን አመጣችሁት? አሁንም እኔ ወደ እናቱ መልሼ እወስደዋለሁ› አላቸው፡፡ ያንጊዜ በገደል ተቀብሬ ወደነበርኩበት ወደ በድኔ መለሰኝ፤ በሥላሴም በመስቀል ምልክት ሦስት ጊዜ ባረከ፤ ገደሊቱም ቀጥ ብላ ቆመች፤ በድናችንንም ተቀጥቅጦ እንደ አመድ ሆኖ አገኘነው፡፡ ያን ጊዜም እጄን ይዞ አስነሣኝና ‹አንቺ ነፍስ ወደ ሥጋሽ ተመለሺ ብሏል እግዚአብሔር› አለ፡፡ ያንጊዜም ነፍሴ ወደሥጋዬ ተመለሰች፤ እንደቀድሞውም ሆንኩ፡፡ ገደሊቱንም ‹በሦስተኛው ቀን እስክመለስ ድረስ ተደፊ› አላት፤ ገደሊቱም ወደ መሬት ተደፋች፡፡ ያንጊዜም ‹ሂድ ወደ እናትህ ተመለስና እናትህን ‹እነሆ ልጅሽን ላኩልሽ እንዲሁም ነፍስሽን በሰማይ አድናታለሁ ብለህ ንገራት› አለኝ፡፡ ከዚህም በኋላ ከሩቅ ጠራኝና ‹እናትህ ስሙ ማነው ብላ ብትጠይቅህ ያ የታመንሽበት ገብረ መንፈስ ቅዱስ ነው› ብለህ ንገራት› ብሎኝ ከእኔ ተሰወረ፡፡ እኔም ወደ እናንተ መጣሁ›› አላቸው፡፡ ከዚያ የነበሩና የልጁንም ምስክርነት የሰሙና አባታችን ልጁን ከሞት እንዳስነሡት ያዩ የሀገሩ ሰዎች ሁሉ በመደነቅ ‹‹የአባታችንን መታሰቢያ ለማድረግ ነፍሳችንንም ሥጋችንንም ሥዕለት አድርገን ለመስጠት ወስነናል፡፡ ገንዘባችንን ከብቶቻችንን ሁሉ ሰጥተናል›› እያሉ ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡

በሦስተኛውም ቀን መንፈቀ ሌሊት በሆነ ጊዜ ማለትም በዕረፍታቸው ዕለት መጋቢት 5 ቀን በሆነ ጊዜ የሀገሪቱ ሰዎች ወንዶችም ሴቶችም ቀሳውስት ዲያቆናት ሁሉ ተሰብስበው ዕጣን መብራት ይዘው ወደ ቤተ ክርስቲያን ገቡ፡፡ ያን ጊዜም ገደል ተጭኗቸው ሞተው የነበሩ እነዚያ ልጆች ሁሉም በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጸሎት ከሞት ተነሥተው በእጃቸው መብራት ይዘው ‹‹ይህ አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሙታንን ከመቃብር የሚያስነሣ ተአምረኛ ነው፤ እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ላይ የሚደነቅ ነው›› እያሉ በመዘመር ከመቅደስ ወጡ፡፡ እንዲህም እያሉ ከእናቶቻቸውና ከአባቶቻቸው ከዘመዶቻቸውም ጋር ተገነኙ፡፡ በደስታና በእልልታም ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡

የአባታችን የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ልመናቸው በተዋሕዶ ልጆች በሁላችን ላይ ይደረግልን በረከታቸው ይደርብን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡
+ + +

በረከታቸው ይደርብንና አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ያደረጉት ተአምር ይህ ነው፡- አንድ ኃጢአተኛ ሰው ነበር፡፡ ብዙ ሥራይ የሚያድርግ ጣዖታትን በማማለክ፣ ምስልን በመሥራት በማመንዘር ብዙ ኃጢአት ይሠራ ነበር፡፡፡ አንድ ቀንም የአቡነ ገብረ መንፈስን ገድል የሚናገር መጽሐፍ ወዳለበት በመጋቢት 5 ቀን ሔደ፡፡ ገድሉን ኪዳኑን የሚናገር መጽሐፍ ሲነበብ ጌታችን የጻድን መታሰቢያ ለሚያደርጉ ሁሉ የሰጠውን የምሕረት ኪዳን እንደሰጠው ሰማ፡፡
ከዚህም በኋላ ያ ሰው ‹‹…ከእንግዲህስ ወዲህ የጻድቁን የአቡነ ገብረ መንፈስን መታሰቢያ አደርጋለሁ፣ በጸሎቱም እታመናለሁ›› ብሎ አሰበ፡፡ እንደዚሁ የአቡነ ገብረ መንፈስን የገድሉን መጽሐፍ ሰምቶ ከዚያ ወጥቶ ሲሔድ በመንገድ ያሸመቁ ወንበዴዎች አግኝቶ ጽኑ ድብደባ ደበደቡት፤ ልብሱንም ገፈው ወሰዱበት፡፡ ሰውነቱም ተጎድቶ በደም ተነክሮ ወደቤቱ ገባ፡፡ በዚያች ቀንም ሞተ፡፡ መላእክትም መጥተው ነፍሱን ለፍርድ በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት አቆሟት፡፡ ያንጊዜም አቡነ ገብረ መንፈስ መንቶ ከእግዚአብሔር ፊት ቆመና ‹‹..አቤቱ ይህችን ነፍስ ማርልኝ፣ ለእኔ ባደረገችው ቸርነትና በሰጠኸኝ ቃልኪዳን አምናለችና…›› እያለ ጽኑ ምልጃን አቀረበ፡፡ በዚህም ጊዜ ጌታችን ‹‹ስለአገልጋዬ ስለማይበል ቃሌም ኃጢአቷን ይቅር ብያታለሁ፣ ወደመሐይምናን አንድነት ውሰዷት›› አለ፡፡ ወዲያውም ጌታችን ቅዱስ ሚካኤልን ወደ ዘላለም ሕይወት እንዲወስዳት ባዘዘው ጊዜ አቡነ ገብረ መንፈስ ደስ አለው፡፡ ፊቱም እንደፀሐይ በራ፡፡
+ + +
ዳግመኛም አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ያደረጉት ተአምር ይህ ነው፡- ዝሙትን የምትወድ፣ ሰንበትን የምትሽር፣ በሐሰት የምትምል አንዲት ሴት ነበረች፡፡ እግዚአብሔር በእርሷ ተቆጥቶ እባብ አዘዘባት፡፡ ልትፀፀዳ በሜዳ ተቀምጣ ሣለ እባብ መጥቶ ወደሆዷ ገባ፤ እሷንም ቤት አድርጎ ኖረ፡፡ የበላችውን ይበላል፣ የጠጣችውንም ይጠጣ ነበር፡፡ ካልበላች ካልጠጣች ደግሞ አንጀቷን ይበላል፣ ደሟንም ይጠጣል፡፡ እርሷም ከስታ የዕንጨት ቅርፊት መሰለች፡፡ በሆዷም እያደገ ስለሔደ ከሁዷ እስከ አንገቷ ሞላ፡፡ ከባሏም ጋር በምትነጋገርበት ጊዜ ያ እባብ በሆዷ ውስጥ እየቀና ያውካት ነበር፡፡

አንድ ቀንም ባሏ ጎሽ ጠጥቶ ሰክሮ እርሷን አነጋገራት፤ እርሷም እምቢ አለችው፡፡ ‹‹ቀድሞ በኃጢአቴ ምክንያት ለዚህ ከይሲ ዳርጎኛልና አሁንስ እንደገና አልበድልም›› ብላ እምቢ አለችው፡፡ እርሱ ግን በግድ ደረሰባት፡፡ እባቡም አባለዘሩን ነከሰውና ባሏ ወዲያው ሞተ፡፡ እርሷም በዚህ ሁኔታ እስከ ሦስት ዓመት ቆየች፡፡
ከዕለታትም አንድ ቀን አንድ ጻድቅ ሰው ከሩቅ አገር ወደ እርሷ መጥቶ ሣለ እባቡን በሴቷ ሆድ ውስጥ አድጎ አየው፡፡ እርሷም እግዚአብሔርን እንደተፈታተነችና ለዚህ ክፉ ከይሲ አሳልፎ እንደሰጣት ነገረችው፡፡ ኃጢአቷንም አምና ንስሓ ገብታ እንዲጸልይላት ለመነችው፡፡ ያም ጻድቅ ሰው ‹‹…ስዕለት ተሣይ፣ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስንም ዝክር አዘክሪ፣ ገንዘብሽንም ለእርሱ ስጪው›› አላት፡፡ እርሷም ‹‹እሺ ከእንግዲህ ወዲህ ለእርሱ ሰጥቻለሁ›› አለችው፡፡ ጻድቁም ሰው ከእርሷ ዘንድ ሔደ፡፡ ያችም ሴት የአባታችን የአቡነ ገብረ መንፈስ ዝክር እስከሚደረግበት ቀን ድረስ ቆይታ ከፈጣሪው ምሕረትን ተስፋ አድርጋ በመጋቢት 5 ቀን የአባታችንን መታሰቢያ አደረገች፡፡ ለካህናት፣ ለምእመናን፣ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ግብዣ አድረገች፡፡ ለቤተ ክርስቲያንም ብዙ ዕጣን፣ መብራት፣ ሰጠች፡፡
በዚያችም ሌሊት አቡነ ገብረ መንፈስ ያች ሴት ወዳለችበት መጣ፡፡ እርሷም አልተኛችም ተቀምጣ ነበር፡፡ ቤተሰቦቿም ያዳምጡ ነበር፡፡ አባታችንም በቤቷ በር ላይ ቆሞ እባቡን ‹‹…አንተ እባብ ከዚህች ሴት ሆድ ውስጥ ውጣ፣ ወደ ሥፍራህ ሒድ፣ እግዚአብሔርም እንዳዘዘህ አፈርን ብላ›› አለው፡፡ ያንጊዜም ሴቲቱን በመስቀል ምልክት ባረካት፡፡ ያም እባብ ቀድሞ በባበት መንገድ ወጥቶ በምድር መላ፡፡ አባታችንም ሔደ፡፡ እርሷም ቤተሰቦቿን ጠራችና እባቡን ገደሉት፡፡ ርዝመቱ 5 ክንድ ሆነ፡፡ የአገሩም ሰዎች በማድነቅ የአቡነ ገብረ መንፈስን መታሰቢያ አደረጉ፡፡ ያችም ሴት ሌላ ባል አገባችና 7 ልጆችን ወለደች፡፡ እስክትሞትም ድረስ የጻድቁን የአቡነ ገብረ መንፈስን መታሰቢያ እያደረገች ኖረች፡፡

ጻድቁ በባሕር ውስጥ 100 ዓመት ተዘቅዝቀው ለጸለዩላት ለቅድስት ኢትዮጵያ ቃል ኪዳናቸውን አሳስበው የዐሥራት ሀገራቸውን ይጠብቁልን!!!

(ምንጭ፦ አለቃ አያሌው ታምሩ የተረጎሙት ገድለ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ዘአኅተሞ ተስፋ ገብረ ሥላሴ፣ 1992 ዓ.ም)

(ሥዕሉ፦ በገበታ ላይ የተሣለ እጅግ ጥንታዊ የጻድቁ ሥዕል-በቢሮአችን የሚገኝ!)

ምድሪቱን ባርከው ወተት ያፈለቁት ጻድቅ!አባታችን በርተሎሜዎስ የጎንደር አውራጃ ምድረ እንፍራንዝን ተሻግሮ ምጽራሓ በሚሏት ደሴት ውስጥ አደረ፡፡ በዚያም የአባ አኖርዮስን ልጅ ቅዱስ አባ ጌርሎ...
14/10/2025

ምድሪቱን ባርከው ወተት ያፈለቁት ጻድቅ!
አባታችን በርተሎሜዎስ የጎንደር አውራጃ ምድረ እንፍራንዝን ተሻግሮ ምጽራሓ በሚሏት ደሴት ውስጥ አደረ፡፡ በዚያም የአባ አኖርዮስን ልጅ ቅዱስ አባ ጌርሎስን አገኘው፡፡ ከእርሱ ጋራም ብዙዎች ቀናትን ኖረ፡፡ ብዙዎች ተአምራት ተገለጡለት፡፡ አንዱ ተአምርም አባ ያፍቅረነ እግዚእና አባ በርተሎሜዎስ በአንድነት ቆመው ሳለ መንፈሳዊ አባታችን ጻድቅ በርተሎሜዎስ በቆመበት በኩል ከምድር ወተት መነጨ፡፡ አባ ያፍቅረነ እግዚእ በቆመበት ሥፍራም ውኃ መነጨ፡፡ አባታችን አባ በርተሎሜዎስም ውዳሴ ከንቱ እንዳይሆንበት ‹‹ሰይጣን ወተትን ከምድር በማመንጨት ለማሳት እንደዚኽ ይፈታተነኝን!›› ብሎ እያሰበ ስለዚኽ ነገር እጅግ አዘነ፡፡ አባ ያፍቅረነ እግዚእም በመንፈስ ቅዱስ ዐውቆ ‹‹ይኼ በእግዚአብሔር ፈቃድ እንጂ ከሰይጣን ስላልኾነ ስለምን ታዝናለህ? እግዚአብሔር እኮ በመንግሥተ ሰማያት ታላቅ አድርጎ መርጦሃል›› አለው፡፡

አባታችን አባ በርተሎሜዎስ በከንቱ ምስጋና በሰው ዘንድ ተወድሶ እንዳይኾንበት ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ተጋድሎውን ለማንም ቢኾን ሊገልጥ አልወደደም ነበር፡፡ ይህም ይታወቅ ዘንድ ጌታችን ቃልኪዳን ሲሰጣቸው ‹‹አንተ ከወንድሞች መካከል ለአንዱም ስንኳ ገድልህን ሳትነግር በምሥጢር ሠውረህ ነበር፤ እኔ ግን የገድልህን ክብር በዓለም ዳርቻዎች ኹሉ ገልጬ በዐሥራ አምስቱ አህጉራተ ገነት በአምስቱ አህጉራተ መንግሥተ ሰማያትም እሾምሃለሁ፡፡›› ዘመኑም ወደ ቅድስት ደብረ ዘመዳ ከገባ መቶ ዘጠና ዓመት ከዘጠኝ ወራት ኖረ፡፡

ንዑድ ክቡር አባታችን አባ በርተሎሜዎስ ታቦቷን ወደ ዋሻው ቤተ መቅደስ ውስጥ በአገባበት ጊዜ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአደረገችለት ተኣምር ይኽ ነው፡- መቆሚያውን በዋሻው በር እጅግ በደረቀች ዐለት ላይ አደረገ፡፡ በአንዲት ዕለትም ቆሞ ሳለ ጣዕሙ ወተት የሆነ ነጭ ውኃን ከእግሩ በታች አፈለቀችለት፡፡ ወንድሞቼ ሆይ! እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለወዳጆቿ የምታደርገው ዕፁብ ድንቅ ነው! ለዚኽ ተኣምርም አንክሮና ምስጋና ይገባዋል፡፡ ንዑድ ክቡር አባታችን አባ በርተሎሜዎስም ጣዕሙም እንደ ወተት የኾነ ነጭ ውኃ በአየ ጊዜ ይኽን ተኣምር አደነቀ፡፡

ጻድቅ አባታችን አባ በርተሎሜዎስም ይኽንን አይቶ ለእመቤቱ ለድንግል ማርያም ‹‹ቀድሞ ለሌሎች ቅዱሳን ያልተደረገን ለእኔ ከአደረግሽልኝስ እለምንሻለሁ፤ እሺ በይኝና ከእግሬ በታች ያመነጨሽውን ይኽንን መልኩን ለውጠሸ ጣዕሙም በልክ እንዲኾን አድርጊልኝ፡፡ ይኽ ዛሬ የመነጨ ውኃማ ለዘወትር ከኾነ የሀገሩ ሰዎችና መኳንንቱ ለራሳቸው መሻት ይቀሟቸዋል እንጂ ለልጆቼ ገዳማውያን አይጠቅማቸውምና ጣዕሙ በልክ ይኹን፡፡ ለገዳማውያን ልጆቼ ተስፋ ይኾናቸው ዘንድ ግን ሀብተ ረድኤትሽ አይለየን›› ብሎ ለመናት፡፡

እመቤታችን ወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያምም ልመናውን ኹሉ የምትቀበል ናትና ወተትነቱን ወደ ውኃ ለወጠችው፡፡ የእመቤታችን የወላዲተ አምላክ የቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎቷና በረከቷ፤ የጻድቁ አባታችን የአባ በርተሎሜዎስም ቃል ኪዳን ኹላችንን ከድንገተኛ ሞት ያድነን፤ ሀገራችንን ሰላም ያድርጉልን።
✞ ✞ ✞

"ገድለ አቡነ በርተሎሜዎስ ወገድለ አቡነ ዮሐንስ ምስለ ተኣምረ ማርያም ዘደብረ ዘመዳ" ገድል እንደ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ አሳትመን ለገዳሙ አስረክበናል። ገድሉ የኹለቱን ቅዱሳን ገድል በአንድ ላይ አጠቃሎ የያዘ ሲሆን በይዘቱ እጅግ የተለየ ነው። በሌላ ቦታ የትም የማትገኝ በደብረ ዘመዳ ገዳም ብቻ የምትገኝ ተኣምረ ማርያምን ያካተተ ሲሆን 30 አዳዲስ ተኣምራትን አካቷል። ገድሉን ለማግኘት የገዳሙን ተወካይ ያናግሩ። +251911671794 (አባ ያሬድ)

(የበፊቶቹ ኹለቱም የቴሌግራም ቻናሎች በተለያየ ጊዜ ስለተጠለፉ ለ3ኛ ጊዜ በተከፈተው አዲስ ቻናል በኩልም በጽሑፍና በድምፅ ይከታተሉ።)

1. ቴሌግራም ቻናል
https://t.me/kegedilatandebet27217

በሀገራችን ኢትዮጵያ ለቅድስት አርሴማ ጽላት የተቀረጸላትና ቤተ መቅደስ የታነጸላት እርሷ ገና በእናቷ ማኅፀን ሳትፀነስ በመንፈስ ቅዱስ ታውቆ መሆኑ በእጅጉ ይደንቃል! ገና በእናቷ ማኅፀን ሳት...
09/10/2025

በሀገራችን ኢትዮጵያ ለቅድስት አርሴማ ጽላት የተቀረጸላትና ቤተ መቅደስ የታነጸላት እርሷ ገና በእናቷ ማኅፀን ሳትፀነስ በመንፈስ ቅዱስ ታውቆ መሆኑ በእጅጉ ይደንቃል! ገና በእናቷ ማኅፀን ሳትፀነስ የቅድስት አርሴማን ጽላት ያሠሩላትና ቤተ መቅደስ ያነጹላት በግብፅ 40 ዘመን ነግው ሳለ ንግሥናቸውን ትተው ወደ ኢትዮጵያ መተው 16 ፍልፍል ቤተ መቅደሶችን የሠሩት የድባጋው አቡነ ሙሴ ናቸው፡፡ ይህም ሰማዕቷ እንደ ነቢዩ ኤርሚያስ አስቀድማ የተመረጠች መሆኑን ያሳያል፡፡

አርመን ኤችሚዚን የሚገኘውና ቅድስት አርሴማ በመጀመሪያ የተቀበረችበት መካነ መቃብሯ የነበረበት ቦታ። ቅድስት አርሴማ (Saint Hripsime) በ290 ዓ.ም በአርመን በሰማዕትነት ካረፈች በኋላ ይኽ የመጀመሪያው ቤተ ክርስቲያን በስሟ የተሠራውም አርመን ኤችሚዚን ውስጥ በ395 ዓም ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ባወቀና በፈቀደ የቅድስት አርሴማ የከበረ ዐፅሟ በሀገራችን በግሸን ደብረ ከርቤ እንደሚገኝ አባቶች ይናገራሉ፣ መጽሐፈ ጤፉትም ላይ ተጽፏል። ግሸን ማርያም ላይ በክብር ተቀምጦ ከሚገኘው ከጌታችን ቅዱስ መስቀል በተጨማሪ የበርካታ ቅዱሳን ዐፅሞችም ይገኛሉ፤ ከእነዚኽም ውስጥ፡- የእመቤታችን እናት የቅድስት ሐና ዐፅም፣ የሐዋርያው የቅዱስ በርተሎሜዎስ ዐፅም፣ የቅዱስ ጊዮርጊስ ዘልዳ ዐፅም፣ የቅዱስ ገላውዴዎስ ዐፅም፣ የሊቃነ ጳጳሳቱ የሳዊሮስና የዲዮስቆሮስ ዐፅም፣ ሔሮድስ በቤተልሔም ያስፈጃቸው ሕፃናት ዐፅም፣ የጌታችን ወንድም የቅዱስ ያዕቆብ ዐፅም፣ የቀዳሜ ሰማዕት የቅዱስ እስጢፋኖስ ዐፅም፣ የሐዋርያው የቅዱስ በርናባስ ዐፅም፣ የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ ራስ፣ የሰማዕቷ የቅድስት አርሴማ ዐፅም እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡

ከቅዱስ መስቀሉ በተጨማሪ ጌታችን በዕለተ ዐርብ በራሱ ላይ የደፋው አክሊለ ሶክ፣ ለብሶት የነበረው ቀይ ልብስ፣ ከሮም የመጣው ከለሜዳው፣ ሐሞት የጠጣበት ሰፍነግ (ጽዋ) ፣ የታሠረበት ገመድና የተገረፈበት ጅራፍ፣ ቅዱስ ዮሐንስ የሣለው ኩርዓተ ርእሱ ሥዕል በግሸን ይገኛሉ። ይኽንንም የጌታችን ቅዱስ መስቀል ወደ ሀገራችን ቅድስት ኢትዮጵያ እንዴት እንደመጣ በዝርዝር የምታስረዳው ‹‹መጽሐፈ ጤፉት›› ላይ በገጽ 60፣ 127፣ 137 እና 141 ላይ በግልጽ ተጽፎ እናገኘዋለን። ቅድስት ሀገራችን ኢትዮጵያ የእግዚአብሔር የምሥጢር ሀገር ናት የሚባለው በብዙ ምክንያት ነው።

በኢትዮጵያና በመላው ዓለም ብዙ አብያተ ክርስቲያናት በስሟ እየታነጹ ከክርስቶስ አምላኳ በተቀበለችው አማናዊ ቃል ኪዳንም ብዙ ሕሙማን እየተፈወሱ በረከቷን እያገኘን እንገኛለን፡፡ ታቦቷ በኢትዮጵያ በብዛት፤ በደቡብ አፍሪካ በረስተንበርግ፤ በዱባይ እና በአውሮፓ ስኮትላንድ ግላስኮ፤ በሰሜን አሜሪካ ቨርጂንያ መካነ ሰማዕት የቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ይገኛል።

ቅድስት አርሴማን መሰገኗት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቀደምት ሊቃውንት ውስጥ ሊቁ አርከ ሥሉስ እና አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ የሚጠቀሱ ሲኾኑ፦

ሊቁ አርከ ሥሉስም ይኽነን የቅድስት አርሴማ ተጋድሎ ሲመሰክር፡-

“በጾታ ኅሩያን ዕደው እንዘ ተኀብሪ ጾታ፤
እንበለ ትፍርሂ ምንተ ብልኀተ ኲያንው ወሰይፍ ልሳነ መንታ፤
ዘፈጸምኪ ስምዐ በእንተ ኢየሱስ ንጉሠ ኤፍራታ፤
ሰላም ለኪ አርሴማ ምስለ እምኪ አጋታ፤
ወለደናግል ሰላም ምስሌኪ ዘሞታ።”

(በተመረጡ ወንዶች ወገንነት ተባብረሽ ኹለት አፍ ያለው ሰይፍንና የጦሮችን ስለትን ምንም ሳትፈሪ የኤፍራታ ንጉሥ ስለሚኾን ስለ ኢየሱስ ምስክርነት የፈጸምሽ አርሴማ ከእናትሽ ከአጋታ ጋር ሰላምታ ለአንቺ ይገባል፤ ካንቺ ጋር የሞቱ ለኾኑ ደናግል ሰላምታ ይገባል) በማለት በኅብረት አመስግኗቸዋል፡፡

ታላቁ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም በተአምኆ ቅዱሳን ታላቅ መጽሐፉ ላይ፦
“ሰላም ለአርሴማ ቅድስት ከመ በቀልት ዘይመስል ቆማ፤
ወዘከለላ ዘመንፈስ ግርማ፤
ዘፈጸመት ገድላ በጻማ፤
ወበመንግሥተ ሰማይ ዐቢይ ስማ።”፡

(ገድሏን በሥቃይ የፈጸመች፤ የመንፈስ ግርማ የጋረዳትና ቊመቷ እንደ ዘንባባ የሚመስል ለምትኾን ለቅድስት አርሴማ ሰላምታ ይገባል፤ በመንግሥተ ሰማይም ስሟ ታላቅ ነው) በማለት ያወድሳታል።

እንኳን ለእናታችን ለሰማዕቷ ለቅድስት አርሴማ ዓመታዊ የዕረፍቷ በዓል በሰላም አደረሰን፣ አደረሳችሁ!!!

በክሕደቱ ምክንያት ንስጥሮስን የቀሰፈው መልአክ-ቅዱስ ዮናኤል!የረከሰና ተጣራጣሪ ስሙ ንስጥሮስ የተባለውን ከሓዲ ንጹሕና ኅቱም በኾነ ድንግልናዋ ላይ እና በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤል ብሥራት ያ...
07/10/2025

በክሕደቱ ምክንያት ንስጥሮስን የቀሰፈው መልአክ-ቅዱስ ዮናኤል!
የረከሰና ተጣራጣሪ ስሙ ንስጥሮስ የተባለውን ከሓዲ ንጹሕና ኅቱም በኾነ ድንግልናዋ ላይ እና በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤል ብሥራት ያለ ወንድ በኅቱም ድንግልና ጸንሳ በኅቱም ድንግልና በወለደች በልጇ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ በመሳደቡ በእውነት አምላክን የወለደች እመቤታችን ድንግል ማርያም በመላእክት አለቃ በቅዱስ ዮናኤል እጅ እንደቀሰፈችው ተነገረ፡፡ የንስጥሮስ ክሕደቱ ፈጽሞ በበዛ ጊዜ ከበታቹ ያሉ ካህናት ከክሕደቱና ከስሕተቱ እንዲመለስ ይቈጡትና የታዘቡት ነበር፡፡ ሰይጣን በሽንገላ ምክሩ አስቶታልና እርሱ ግን ምንም አልተመለሰም፡፡

በአምላካችን በእግዚአብሔር ፈቃድም ከእግዚአብሔርና ከእመቤታችን ማርያም ዘንድ ተልኮ ይኽ የመላእክት አለቃ ዮናኤል መልአክ የቊጣ ሰይፍን በመያዝ ንስጥሮስን ገሠፀው፡፡ ያን ጊዜም ንስጥሮስ ከአልጋው ተነሣና ከምድር ላይ ወድቆ፤ አንገቱ ከጀርባው ተጣበቀ፤ ፊቱ ወደ ኋላ፤ ጆሮዎቹም ወደ ፊት፤ ራሱም ወደታች፤ እግሮቹም ወደላይ ኾኑ፡፡ ልሳኑም አንድ ክንድ ያህል ተጎለጎለ፤ ልቡም ጠፋ፡፡ የዐይኑ ብርሃንም ተሠወረና የወይን ስካር እንዳሰከረው ኾነ፡፡ ያን ጊዜም ይኽ ንስጥሮስ በክፉ አሟሟት ሞተና መላእክት ተቀብለው ወደ ሲኦል ጥልቅ ውስጥ ወረወሩት፡፡

ይኽ ኹሉ የኾነው በእውነት አምላክን በወለደች በኹለት ወገን ድንግል በኾነች በእመቤታችን ማርያም ድንግልና ላይ ስለተሳደበና የመላእክት አለቃ ይኽ መልአክ ቅዱስ ዮናኤል በቊጣ ሰይፉ ስለቀሰፈው ነው፡፡ በሰው ላይ የተሳደበ ኹሉ ኀጢአቱ ይሰረይለታል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ላይና አምላክን በወለደች በኹለት ወገን ድንግል በኾነች በእመቤታችን ድንግል ማርያም በንጽሕናዋና በድንግልናዋ ላይ የተሳደበ ግን በዚኽ ዓለምም ኾነ በሚመጣውም ዓለም ኀጢአቱ አይሰረይለትም፡፡

የመልአኩ የቅዱስ ዮናኤል ምልጃና ልመና ኹላችን የጥምቀት ልጆችን ከሁከትና ከክሕደት ዘመን ያድነን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

✝️ ይኽ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ዮናኤል ከከመላእክት አለቃ ከጓደኛው ከቅዱስ ፋኑኤል ጋር ከሰማይ የተገኘ ኅብስትንና ከሰማይ የተቀዳ ጽዋን ለክብርት እመቤታችን የመገባት ነው፡፡

✝️ ይኽ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ዮናኤል ቅዱሳንን ከዋሊ በረሓ በአንበሳ ከሚጫነው ከብፁዕ አባ ሳሙኤል የቅድስናው ቦታ ከኾነች አብረንታት ከዋልድባ ገዳም የመጡ ቅዱሳን ከብዙ የሕግ ታቦታት ጋር የእመቤታችን የድንግል ማርያምን ታቦት ይዘው ወደ ጐረጐር ገዳም እስከ ደረሱ ድረስ የመራቸው ነው፡፡
✝️ ይኽ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ዮናኤል ለሐዋርያው ፊልጶስ ተገልጦለት ከኢየሩሳሌም ወደ ጋዛ በሚወስደው በበረሓው መንገድ በቀትር ጊዜ ‹‹ተነሥተህ ሒድ›› ብሎ ፊልጶስን ወደ ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ የላከው ነው፡፡
✝️ ይኽ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ዮናኤል በብርሃን ክንፎቹ ፈጽሞ እየበረረ የተሳለ ጦርንና ሰይፍን በመያዝ በዋሻዎችና በዛፎች፤ በምድር ጉድጓድ ውስጥም ለሚኖሩ ቅዱሳን ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልኮ ምግባቸውን የሚያመጣላቸው ነው፡፡
✝️ አምላካችን ኖኅን ከጥፋት ውኃ የጠበቀው በመላእክት አለቃ በቅዱስ ዮናኤል እጅ ነው፡፡
✝️ ከጌራራ ምድር ንጉሥ ከአቤሜሌክ እጅ አብርሃምንም ያዳነው እርሱ ነው፡፡
✝️ ይሥሐቅንም ከተሳለ ሰይፍ (ካራ) ያዳነው እርሱ ነው፡፡ ያዕቆብንም ከወንድሙ ከዔሳው ያዳነው እርሱ ነው፡፡
✝️ በኮቦር ወንዝ ሳለ ለነቢዩ ሕዝቅኤል ተገልጦለት ምሥጢራትን የነገረው ይኽ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ዮናኤል ነው፡፡
✝️ የጻድቅ አቤልን ነፍስ ወደ ሰማይ ያሳረገው የመላእክት አለቃ ቅዱስ ዮናኤል መልአክ ነው፡ ወደ ጌታ ዙፋን አደረሰውና የገነት ደጃፍ ከሚጠብቅ ከሱራፌል ጋር በገነት እግር ሥር አስቀመጠው፡፡
✝️ ከዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት አንዱ የኾነ፤ ምሕረትን የሚለምንና የሚማልድ ክቡርና ኀያል የኾነ የመላእክት አለቃ የመልአኩ የቅዱስ ዮናኤል ስለ ቀናች ኃይማኖት ከነገሥታትና ከመኳንንት ዘንድ የተሰደዱትንና የተንከራተቱትን፤ በክፉዎች አጋንንት ማሰሪያ የታሰሩትንና በክፉ አገዛዝ የተያዙትን፤ በሰንሰለት የታሰሩትንና ኀላፊና ጠፊ የኾነች ይኽችን ዓለም በመናቅ ከአባታቸው ቤት የወጡትንም የሚረዳቸው እርሱ ነው፡፡
✝️ የቂሣርያ ሀገር ሰው ለኾነ ኢጣልቄ ለሚሏት የሰጲራ ሕዝብ የመቶ አለቃ ለኾነ ስሙ ቆርኔሌዎስ ለተባለ ሰው በዘጠኝ ሰዓት ከመላእክት አለቃ ከቅዱስ ሚካኤል ጋር ቅዱሳንን የሚረዳ ይኽ የእግዚአብሔር መልአክ ዮናኤል ተገለጠለትና ወደ እርሱ ገብቶ ‹‹ቆርኔሌዎስ ሆይ! ሰላም ለአንተ ይኹን! የእግዚአብሔር ሰላም ከአንተ ጋር ይኑር፤ እነሆ ጸሎትህና ምጽዋትህ በጐ ሥራህም ወደ ፈጣሪህ ፊት ዐርጓል፤ በጐ ሥራህን አስቧልና›› ብሎ አበሠረው፡፡

በድጋሚ የመልአኩ የቅዱስ ዮናኤል ምልጃና ልመና ኹላችን የጥምቀት ልጆችን ከሁከትና ከክሕደት ዘመን ያድነን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

(ከነገረ ቅዱሳን አገልግሎታችን ውስጥ አንዱ ከዚኽ በፊት ያልታተሙ አዳዲስ ገድላትንና ድርሳናትን ለገዳማት በማሳተም ሕዝበ ክርስቲያኑም በነፍስ በሥጋ እንዲጠቀም ለማድረግ የአቅማችንን ሞክረናል። (በቅርቡም እጅግ ግዙፍ በኾኑ ታላላቅ ሥራዎች ይጠብቁን!) ለአሁኑ እግዚአብሔር ፈቅዶ፦
1ኛ. በ33ቱ በዓላቶቿ የሚነበብ "መንገለ ጽዮን" የተሰኘ ድንቅ የእመቤታችንን ድርሳን ከጽንሰቷ እስከ ዕርገቷ ድረስ ያለውን የሚያወሳ፤
2ኛ. የሊቀ መላእክት የቅዱስ ዮናኤልን ድርሳን፤
3ኛ. የስድስቱን የጎረጎር ማርያምን ቅዱሳን ገድል (ከዚኽ በፊት የታተመ ቢኾንም ብዙ እርማትና ማሻሻያ ተደርጎበት) እነዚኽን ሦስቱን ድርሳናትና ገድል አንድላይ ብዛት 3ሺህ ኮፒ አሳትመን ለገዳሙ ስናስረክብ እጅግ ደስታ ይሰማናል።

የገጽ ብዛት= 771 (በትልቁ በB5 መጠን)
ዋጋ= 2ሺህ (ገዳሙ በወሰነው መሠረት)

ገድሉ የሚገኝበት ቦታ፦
1ኛ. ቋንቋዬነሽ ሥላሴ ኮሌጁ 5ኛ ፎቅ ቋንቋዬነሽ ስቱድዮ (ተወካይ፦ ሰብለ ወንጌል 0924035131)

2ኛ. ቃሊቲ አካባቢ ቼራሊያ ንግድ ባንክ ያለበት ሕንፃ 3ኛ ፎቅ ግዕዝ ቲዩብ ስቱድዮ
(ተወካይ፦ አቤሌክ 0910122219)

3ኛ. አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ መጻሕፍት መሸጫ መደብር 6 ኪሎ ቅዱስ ማርቆስ ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ ቁ.11 (ነገር ግን ለጻድቁ በዓለ ጽንሰት ወደ ገዳማቸው ስለሔዱ ከእዚህ መውሰድ የምትችሉት ከጥቅምት 5 በኋላ ነው።)

4ኛ. ፒያሳ ገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ክርስቲያን ሕንፃ 2ኛ ፎቅ ቤተ ጳውሊ የጉዞ ወኪል ቢሮ ውስጥ።

ማሳሰቢያ፦ ከላይ ከተጠቀሱት ቦታዎች
በሰዓቱና በጊዜው ሳትወስዱ ቀርታችሁ ሌላ ጊዜ በሌሎች ገድላትና ድርሳናት በሚሸጡባቸው ቦታዎች ላይ ስትገዙ ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ ቢያጋጥማችሁ ገዳሙም ኾነ እኛ ሓላፊነት አንወስድም።

ከነፋስ ማዕበል የሚታደገው ታላቅ ሰማዕት!ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ቅዱስ ፋሲለደስን በክንፎቹ ተሸክሞ ወደ ሰማይ እንዳሳረገውና በጌታችን ፊት እንዳቆመው ዘላለማዊ ማረፊያውንም እንዳሳየው ገ...
21/09/2025

ከነፋስ ማዕበል የሚታደገው ታላቅ ሰማዕት!

ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ቅዱስ ፋሲለደስን በክንፎቹ ተሸክሞ ወደ ሰማይ እንዳሳረገውና በጌታችን ፊት እንዳቆመው ዘላለማዊ ማረፊያውንም እንዳሳየው ገድሉ ይናገራል፡፡ ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ በሚገዛበት አገር ሁሉ ክርስቶስን ያልካዱትን ምእመናን ማስገደልና ማሳደድ ጀመረ፡፡ ብዙ ሰማዕታትም ወደ ንጉሡ የሰማዕትነት አዳባባይ እየመጡ በጌታችን ስም ደማቸውን አፈሰሱ፡፡ ቅዱስ ፋሲለደስም ሰማዕት ይሆን ዘንድ ወደጌታችን ይጸልይ ጀመር፡፡ በመኝታም ሳለ ቅዱስ ሚካኤል ታዞ ወደ እርሱ መጥቶ ሰላምታ ሰጠውና ‹‹በምድር አለቃ ሆነህ ሁሉን እንደምታዝ በሰማይም የክርስቶስ ወታደሮቹ የሆኑ የሰማዕታት አለቃ ሆነሃልና ደስ ይበልህ›› አለው፡፡ ዳግመኛም ‹‹ወደ ጌታህ ዘንድ አደርስህ ዘንድ ተነሥ›› አለውና በክንፎቹ ተሸክሞ ወደ ሰማይ አሳረገውና በጌታችን ፊት አቆመው፡፡

ጌታችንም ለቅዱስ ፋሲለደስ ሰላምታ ከሰጠው በኋላ ስለ ስሙ ይቀበል ዘንድ ስላለው መከራና በሰማይም ስለሚያገኘው ዘላለማዊ ክብር ነገረው፡፡ በእርሱም ላይ የሚደረስበትን መከራና በኋላም የሚያገኘውን ክብር በዝርዝር ከነገረው በኋላ ቃልኪዳንም ገብቶለታል፡፡ ዳግመኛም ጌታችን ለቅዱስ ፋሲለደስ የሰማዕታትንና የቅዱሳንን ሁሉ መኖሪያ ካሳየው በኋላ ሰማዕትነቱን ሲፈጽም የሚያገኘው ክብር መሆኑን ነግሮት በገነት ውኃ በመልአኩ እጅ እንዲጠመቅ ካደረገው በኋላ ተጋድሎውን እንዲፈጽም ወደ ምድር መልሶታል፡፡ ሰማዕትነቱንም ከፈጸመ በኋላ ጌታችን በአካል ተገልጦለት ታላቅ የምህረት ቃልኪዳን ገብቶለታል፡፡

የሰማዕቱ የቅዱስ ፋሲለደስ ቃልኪዳን፡- ‹‹…ከዚኽም በኋላ በመስከረም ወር የሰማዕትነቱ መጨረሻ በሆነ ጊዜ የቅዱስ ፋሲለደስን ሰውነት በመጋዝ ሰንጥቀው በዘይት ማውጫ ውስጥ ጨመሩት፡፡ ዳግመኛም ሥጋውን በየጥቂቱ ቆራርጠው በቅርጫት ውስጥ አደረጉት፡፡ ቅርጫቱን በእሳት አቃጠሉት፣ አመድም ሆነ፡፡ ያንጊዜም ዝናብ መጥቶ የከበረ የቅዱስ ፋሲለደስን አመድ የሆነ ሥጋውን ከበበ፣ ከባድ ዝናብም ዘነመ፡፡ ምድርንና መሠረቶቿንም ሁሉ እስኪያነዋውጥ ድረስ መብረቅና ነጎድጓድ ሆነ፡፡ እነሆም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኪሩቤል ሠረገላ ተቀምጦ ከሰማይ ወረደ፡፡ ሱራፌልም ከእርሱ ጋር መጡ፣ ሚካኤል በቀኙ ገብርኤል በግራው ነበሩ፡፡ ከእርሱም ጋር ክብርት እመቤታችን ድንግል ማርያም መጣች፡፡ ጌታችን የቅዱስ ፋሲለደስ ሥጋ ካለበት ሆኖ ሚካኤልን ‹የወዳጄ የፋሲለደስን ሥጋ አቅርብልኝ› አለው፡፡ መልአኩም ያንጊዜ አመድ የሆነውን የቅዱስ ፋሲለደስን ሥጋ ለጌታችን አቀረበ፡፡ መድኃኒታችንም ‹ወዳጄ ፋሲለደስ ሆይ! እነሆ የገድልህ መጨረሻ ጊዜ ደርሷልና ተነሣ፣ አትፍራ› ብሎ አልዓዛርን ጠርቶ ከሞተ ከ4 ቀን በኋላ በስሙ ጠርቶ እንዳስነሣው ሁሉ (ዮሐ 11፡11-43) ቅዱስ ፋሲለደስንም ከመቃብር ሦስት ጊዜ ጠራው፡፡ ያንጊዜም ቅዱስ ፋሲለደስ ያለጥፋት ተነሣ፡፡ ጌታችንም በፊቱ የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት፡፡ ከእርሱም ፍርሃትን አስወገደ፡፡ ካረጋጋውም በኋላ ‹የመረጥኩህ ፋሲለደስ ሆይ! ንዑድ ክቡር ነህ፣ የአባቴና የመንፈስ ቅዱስም ወዳጅ ነህ፡፡ አባትና እናቱን፣ ቤቱንና ልጆቹን፣ ሚስቱንና ገንዘቡን ትቶ ያልተከተለኝ ደቀ መዝሙሬ መሆን አይችልም ያለውን የወንጌል ቃል ፈጽመሃልና እነሆ በችግሩ ጊዜ በስምህ የሚለምነኝን ሰው ሁሉ ፈጥኜ እንድሰማው ከችግሩም እንዳድነው በራሴ ቃል ገባሁልህ፤ በመከራ ውስጥ ያለ ሰው ‹የፋሲለደስ አምላክ ከመከራ አድነኝ› ብሎ የለመነኝን ሁሉ እኔ ፈጥኜ ጸሎቱን ሰምቼ ከመከራው አድነዋለሁ፣ በደረቅ ምድር ላይ ይልቁንም በባሕር ውስጥ በመርከብ ሲሄዱ በአንተ ስም ቢለምኑኝ ከነፋስ ማዕበል አድናቸዋለሁ፣ ወደምታድናቸው ወደብ አደርሣቸዋለሁ፡፡ ሴትም በወሊድ ሕማም ተይዛ በተጨነቀች ጊዜ የአንተን ስም ጠርታ ብትለምነኝ እኔ ፈጥኜ ጸሎቷን ሰምቼ ያለ ሕማም ፈጥና እንድትወልድ አደርጋታለሁ፡፡ በዕረፍትህ ዕለት እንደችሎታው ዝክርህን የዘከረ ሰው ሁሉ ነፍሱ ፈጽማ ሲኦልን አታይም፡፡ …እነሆ በመንግሥተ ሰማያት ሦስት አክሊላትን አዘጋጀሁልህ፡፡››
ከቅዱስ ፋሲለደስ ረድኤት በረከት ይክፈለን!

በረከቱ ይደርብንና በዚህች ዕለት መስከረም 11 ቀን በበዓለ ዕረፍቱ ታስቦ የሚውለው ታላቁ ሰማዕት ቅዱስ ፋሲለደስ ያደረገው ተአምር ይህ ነው፡- ‹‹አፍራቅያ በሚባል አገር አንድ ሹም ነበር፣ እሱም በዚህ ዓለም ገንዘብ እጅግ ባለጸጋ ነበር፡፡ በዘመኑም ቅዱስ ፋሲለደስ እጅግ ብዙ አሠቃቂ መከራዎችን ከተቀበለ በኋላ በእሥር ቤት ታሥሮ ነበር፡፡ ይኽም ባለጸጋ ሹም ሁለት ዐይኖቿ የታወሩ አንዲት ሴት ልጅ ነበረችው፡፡ ልጁንም ይዞ ሰማዕቱ ቅዱስ ፋሲለደስ ካለበት ወህኒ ቤት ገብቶ ‹ጌታዬ የእግዚአብሔር ቅዱስ ሆይ! ይቅርታህ በልጄ ላይ ይድረስ፤ ለዐይኖቿም ብርሃንን ይሰጣት ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለምንልኝ› ብሎ ለመነው፡፡ ቅዱስ ፋሲለደስም ያንን ባለጸጋ ሹም መልሶ ‹ክርስቶስ ኢየሱስ ልጅህን እንደሚፈውሳት ታምናለህን?› አለው፡፡ ባለጸጋውም ‹ጌታዬ ሆይ! አዎን እግዚአብሔር ኃይልና ሥልጣን እንዳለው በሥራውም ሁሉ የሰለጠነ የሚሳነው እንደሌለ አምናለሁ› አለው፡፡ የከበረ ፋሲለደስም ‹እንዲህ ያለውን የጸና ሃይማኖት ከየት አገኘህ?› ብሎ ስለእምነቱ ጥንካሬ ካደነቀው በኋላ እጆቹን ዘርግቶ እንዲህ ብሎ ጸለየ፡- ‹ኹሉን የያዝህ ፍጥረታትን ሁሉ የፈጠርህ፣ ሰውን በምሳሌህና በአርዐያህ የፈጠርኸውና ፍጹም ጥበብህ ይገለጥ ዘንድ ክብርህንና ድንቆችህንም አይተው ሥልጣንና ታላቅነት ገንዞችህ እንደሆኑ ያውቁ ዘንድ አንካሶችንና ዐይነ ሥውራንን፣ ዲዳዎችንና መስማት የተሳናቸውን ሁሉ የፈጠርህ እግዚአብሔር አምላክ ሆይ! አቤቱ አንተ ፍጹም ጥበብን በሥጋ በምድር ላይ በተገለጥህ ጊዜ ፈጸምክ፡፡ በባሕርያችን የምንወድቅበትን ውድቀታችንንና ድካማችንን አንተ ታውቃለህ፤ አቤቱ አንተ በመለኮታዊ አንደበትህ ‹የሰናፍጭ ቅንጣት ያህል ሃይማኖት ያለው ይህን ተራራ ማፍለስ ይችላል› ብለሃልና ዳግመኛም በምራቅህ ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ ዕውር ሆኖ ለተወለደው ብርሃንን እንደሰጠኸው አቤቱ አሁንም ለዚህች ብላቴና ብርሃንን ትሰጣት ዘንድ እለምንሃለሁ፤ እነሆም በዐይኖቿ እንድታይ ሕዝቡም ሁሉ ከአንተና ከይቅር ባይ አባትህ ማኅየዊ ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስ በቀር ሌላ አምላክ እንደሌለ ያውቁ ዘንድ ስለዚህች ብላቴና ለአገልጋይህ ጸጋን ስጠኝ› ለዘላለሙ አሜን!›

ቅዱስ ፋሲለደስም ልመናውን በፈጸመ ጊዜ ምራቁን በምድር ላይ ተፍቶ ከትቢያ ጋር ከለወሰ በኋላ የብላቴናይቱን ዐይኖች በክርስቶስ ትእምርተ መስቀል አምሳያ ቀባቸው፡፡ ያንጊዜም የብላቴናይቱ ዐይኖች ተከፍተው ማየት ቻለች፡፡ ስሟም እስምያና ይባል ነበር፡፡ የአባቷ ስም አበሙድዮስ ሲሆን እናቷም ዮና ትባል ነበር፡፡
ሹሙም ልጁ ፈጽማ እንደዳነችለት ባየ ጊዜ በግንባሩ ወድቆ ለከበረ ፋሲለደስ ሰገደለት፡፡ ‹ለነፍሳችን የድኅነት መንገድ የሆንከን ድውዮቻችንን የምትፈውሰን አንተን የላከልን እግዚአብሔር ይመስገን› በማለት ካመሰገነ በኋላ ልጁን ይዞ ‹ኑ እውር የነበረች ልጄን በፋሲለደስ ጸሎት እንደዳነች እዩአት…› ብሎ እየመሰከረ ሔደ፡፡ የአፍራቅያ ሰዎችም የሹሙ ባለጸጋ ሴት ልጅ ፈጽማ እንደዳነችና ዐይኖቿ እንደበሩላት ባዩ ጊዜ በከተው ያሉ ድውያንን ሁሉ ሰብስበው ወደ ወህኒ ቤት በማምጣት በቅዱስ ፋሲለደስ ፊት አስቀመጧቸው፡፡ አጋንንትም ያደሩባቸውን ሰዎች ሁሉ አመጧቸው፡፡ ሰማዕቱም ወደ አምላኩ እየጸለየ ሁሉንም ይፈውሳቸው ነበር፡፡ አንገቱንም ተሰይፎ ሰማዕትነቱን በክብር እስከፈጸመ ድረስ እንዲሁ ድውያንን ሲፈውስና ሲያስምር በሥጋውም እጅግ አሠቃቂ መከራዎችን እየተቀበለ ቆየ፡፡ የከበረች በረከቱ ትደርበን በጸሎቱ ይማረን!!!

ደቡብ ጎንደር እስቴ የሚገኘው ርእሰ አድባራት ወገዳማት ቆማ ቅዱስ ፋሲለደስ ቤተ ክርስትያን በ1597 ዓ.ም በንጉሥ ሱስኒዮስ ሚስት በዐፄ ፋሲል እናት በንግሥት ወልደ ሳህላ የተመሠረተ ቤተ ክርስትያን ነው፡፡ ዐፄ ሱስኒዮስ ሃይማኖታቸውን ሲቀይሩ ንግሥት ወልደ ሳህላ ግን ‹‹ሃይማኖቴን አልቀይርም ገዳም መሥርቸ የኢትዮጵያን ሃይማኖት ማጽናት አለብኝ›› ብለዉ ብራደጌ (ብሩ አደጌ) ወደ ተባለ ቦታ በመምጣት ቤተ ክርስትያን ይሠራሉ፡፡ ቤተ ክርስትያኑ ተሠርቶ ካልቀ በኋላ ለክብረ በዓሉ ነጭ በሬ ታርዶ እያለ የታረደው በሬ ተነሥቶ ይሮጣል፤ ህዝቡም በሬዉን ለመያዝ ሲሮጥ ንግሥቲቱ ‹‹በሬዉን አትያዙት ዝምብላችሁ የሚቆምበትን ቦታ ተከተሉት›› ይሏቸዋል፡፡ ህዝቡም በሬውን ይከተሉታል፡፡ በመቀጠል ንግስቲቱ በሬው የት ደረሰ ብለው ይጠይቃሉ ህዝቡም ቆመ ይላል፡፡ በዚህ ምክንያት በሬው የቆመበት ቦታ ስያሜ ቆማ ይባላል፡፡ ንግስቲቱ በሬው የቆመበትን ቦታ ላይ ‹‹ፈቃደ እግዚአብሔር ሆኖ ነው›› ብለዉ በመጀመሪያ እድሞ (አጥር) እና ዕቃ ቤት በኖራና በድንጋይ አሠሩ፡፡ በመቀጠል ቤተ ክርስትያን አሠርተዋል፡፡ ቤተ ክርስትያን ሲሠሩ እስከ ግማሽ ድረስ በኖራና በድንጋይ እንዳሠሩ አንድ የበቁ ባሕታዊ ‹‹ዕድሜሽ አጭር ነው፣ በጭቃ አስጨርሽው…›› ብለዋት ከግማሽ በላይ በጭቃ ነው ያሠሩት፡፡
ቤተ ክርስትያኑን በ1624ዓ.ም ዐፄ ፋሲል የደብርና የገዳም ሥርዓት እንዲፈጸምበት ርዕሰ አድባራት ወገዳማት ቆማ ቅዱስ ፋሲለደስ ብለው ሰይመውታል፡፡ ታቦቱ ከትውልድ ሀገሩ ከአንጾኪያ የመጣ ሲሆን ክብረ በዓሉ መስከረም 11 እና ታኅሣሥ 11 ነው፡፡ ከተወሰኑ ዓመታት በፊት ክብረ በዓሉን ሙስሊሞችም ያከብሩ ነበር፡፡
በቤተ ከርስትያኑ ከተደረጉ ተአምራትና አስደናቂ ነገሮች ውስጥ በ1928 ዓ.ም. በጣሊያን ወረራ ግዜ በቤተ ክርስትያኑ ላይ ቦንብ ተወርውሮ ምንም ጉዳት ሳያደርስ ከቤተክርስትያኑ ቅፅር ውጭ ወድቆል፡፡ የቤተክርስትያኑ ጉልላት እና እቃ ቤቱ ላይ ያሉ መስቀሎች ከርቀት እያብረቀረቁ የሰው ዐይን እስከ ማጥፋት ይደርሱ ነበር፡፡ በቀደምት ዘመናት በቤተ ክርስትያኑ ውስጥ ያለው ነጋሪት ለክብረ በዓል ሲመታ ድምፁ እስከ ጎጃም ድረስ ይሰማ ነበር፡፡ በቤተክርስትያኑ ጉልላት እና እቃ ቤቱ ላይ ያሉ መስቀሎችን ለመስረቅ ሙከራ ተደረጎ ሌቦቹ መስቀሉን ሳይወስዱት አንዱ ሌባ ላይ የሞት አደጋ ደርሶበት መስቀሎቹ በተዓምራት ተርፈዋል፡፡ በጣሊያን ወረራ ዘመን ፈረንጆች ጫማቸውን ሳያወልቁ ቤተ ክርስትያን ሊገቡ ሲሉ እባብ እግራቸውን ላይ ተጠምጥሞባቸው ሳይገቡ ቀርተዋል፡፡ በኋላም ተፀፅተው ስለት አስገብተዋል፡፡
የቆማ ፋሲለደስ የቆሜ ዜማ ማስመስከሪያ አብነት ትምህርት ቤት፡- በዚህ ቤተ ክርስትያን የቆሜ ዜማ ማስመስከሪያ አብነት ትምህርት ቤት የሚገኝ ሲሆን የቆሜ ዜማ ከአራቱ የዜማ ይትባህሎች አንዱ ሲሆን ጥንታዊ የመጀመሪያዉዊ ያልተከለሰ ያልተቀየረ ቀጥ ያለ በመሆኑ ቆሜ ተብሎል፡፡ የቆሜ ዜማ የመጀመሪያው ዜማ ከቅዱስ ያሬድ የመጣ ሲሆን በሂደት ቤተልሄም፤ ተጉለት፤ አጫብር ዜማዎች መጥተዋል፡፡ የቆሜ ዜማ ከሌሎች የዜማ ይትባህሎች የሚለየው ርክርኩ(ጉሮሮ) ረዥም በመሆኑ አንዳንድ ቦታ ላይ ዘሩ(ቁጥሩ) የሚለይ መሆኑ እና ዜማውን ለመማር ክብደት ያለው በመሆኑ ከሌሎች ዜማዎች ይለያል፡፡ የቆሜ ዜማ ድጓ መጻሕፍት በታላላቅ ገዳማትና አድባራት የሚገኝ ሲሆን በአክሱም፤ በላሊበላ እና በመካነ ኢየሱስ ይገኛል፡፡ የቆሜ ዜማ ምስክርነት የሚሰጠው በቆማ ፋሲለደስ ቤተክርስትያን ነው፡፡

(ምንጭ፡- ገድለ ቅዱስ ፋሲለደስ፣ የሣርክታ ፋሲለደስ ቤ/ክ እትም ገጽ 183፣ የምጽሌ ፋሲለደስ ቤ/ክ እትም ገጽ 31 እና 69)

(ፎቶ፦ ደቡብ ጎንደር የሚገኘው ቆማ ቅዱስ ፋሲለደስ እና ጣና ሐይቅ ላይ የሚገኘው የሰማዕቱ ገዳም)

Address

Addis Ababa

Telephone

+251912063211

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ከገድላት አንደበት-ke gedilat andebet posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Place Of Worship

Send a message to ከገድላት አንደበት-ke gedilat andebet:

Share