12/12/2025
"ንስሓ ሳይገባ እንዳይሞት"
በኀጢአት ብንወድቅ እንኳን ቅዱሳን ለነፍሳችን ድኅነት ምን ያህል እንደሚተጉ ይኽ ታሪክ በእጅጉ ያስተምረናል። ንጉሥ ዓምደ ጽዮን በነገሠ ጊዜ እንደ አባቱ እግዚአብሔርን የሚወድ ሃይማኖቱ የቀና ነበር፡፡ ከዚኽም በኋላ ሰይጣን የዝሙትን ሥራ የሚያሠራው ሆነ፡፡ አንዲት የአባቱ ቅምጥ የነበረችውንም አመንዝራ ሴት አገባ፡፡ እርሷም ሰንበትን እስከሻረና ሃይማኖቱን እስከለመወጠ ድረስ ኀጢአትን አሠራችው፡፡ ስለዚህም የክቡር አባታችን የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ልጅ አባ ፊሊጶስ ንጉሡን አወገዘው፡፡ ንጉሡም አብያተ ክርስቲያናትን ዘጋቸው፡፡
በዚያም ወራት አባታችን ዜና ማርቆስ በደብረ ብሥራት ገዳም አልነበረም-በንጉሥ ዓምደ ጽዮን በአባቱ በይኩኖ አምላክ ዘመን ፈጽሞ ተሠውሮ ነበርና፡፡ ምክንያቱም ለንጉሥ ይኩኖ አምላክ የእኅቱ ልጅ ስለነበር ራስ ወይም ቢትወደድ አድርጎ በዓለም እንዳይሾመው ስለዚህ ከደብረ ብሥራት ሸሽቶ በምሁር ሀገር ወደሚገኝ የጎጎት ጫካ ውስጥ የይኩኖ አምላክ ዘመነ መንግሥት እንስከሚያልፍ ድረስ ተሠውሮ ኖረ፡፡
ንጉሥ ዓምደ ጽዮንም ሃይማኖቱን በካደ ጊዜ እስከ አርባ ዓመት በተሠወረበት ቦታ ኖረ፡፡ ልጆቹ ቅዱሳን መነኰሳትን ይጎበኛቸው ዘንድ በጣና ባሕር ወዳለች የደቅ ደሴት ሲሔድ በደመና ላይ ተጭኖ ነበር፣ ወደ ምሁር ሀገር ሲመለስም በአንበሶችና በነብሮች ጀርባ ላይ ሆኖ በሥውር ነበር፡፡ ንጉሥ ዓምደ ጽዮንም በነገሠ ጊዜ በ14ኛው ዓመት ጌታችን በሞት ሊወስደው ወደደ፡፡ ያንጊዜም ሰውን የምትወድ አምላክን የወለደች ክብርት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስለ ንጉሡ ልጇን መድኃኔዓለምን ማለደችው፡፡ ልጇ ያለ ንስሓ በቁጣው እንዳይቀሥፈው አባታችን ዜና ማርቆስ ይለምናት
ነበርና፡፡
አባታችንም በሚጸልይ ጊዜ እንዲህ ብሎ ለመናት፡- ‹ለሰው ዘር ሁሉ የምትራሪ አምላክን የወለድሽ በሁለት ወገን ድንግል የሆንሽ እመቤቴ ማርያም ሆይ! ባሪያሽ ዓምደ ጽዮን ከኃጢአቱ ተመልሶ ንስሓ ሳይገባ እንዳይሞት፤ የልጅሽ ጠላት ሰይጣን በዝሙት ሥራ ሳያስተው በፊት ወዳጅሽ ነበርና አስቢ፡፡ ልጅሽም ለጻድቃን ብቻ አልመጣምና ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ስለ ኃጢአተኞች ድኅነት ከአንቺ ከሥጋሽ ሥጋን ከነፍስሽ ነፍስን ነሥቶ ሰው ሆነ እንጂ፡፡ እርሱ ራሱ በቅዱስ ወንጌሉ ‹ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም ኃጥአንን ወደ ንስሓ ልጠራ መጥቻለሁ እንጂ› ብሏልና፡፡ እመቤቴ ሆይ! በልጅሽ ፊት ይህንን አሳስቢ፣ እርሱ እስከ ዘለዓለም ይቅርታ በማድረግ ምሕረቱ የበዛ መሐሪ ነው› እያለ ለመናት፡፡ በዚያም ወራት ክብርት እመቤታችን አባታችንን ዜና ማርቆስን ‹ወደ ዓምደ ጽዮን ሔደህ ንስሓ ግባ በለው› አለችው፡፡
የሕይወት እናት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ይህን ስለነገረችው አባታችን ዜና ማርቆስ ደስ አለው፡፡ እርሷ የምትራራ የሁላችን ተስፋ፣ የኃጥአን መዳኛቸው፣ ጻድቃንንም መልካም የሆነ ተጋድሏቸውን እስኪፈጽሙ ድረስ የምትረዳቸው ናትና፡፡ አባታችን አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም ‹‹እግዚአብሔር ሊምረው የወደደውን ሰው የማርያምን ፍቅር ያሳድርበታል›› ሲል የተናገረው ለዚህ ነው፡፡
ከዚኽም በኋላ አባታችን ዜና ማርቆስ ወደ ደብረ ብሥራት ገብቶ ከልጆቹ ጋር በ40 ዓመቱ ተገናኘ፡፡ እነርሱም ይህን ያህል ዘመን ሲጠፋባቸው ያረፈ መስሏቸው ነበርና አሁን
ባገኙት ጊዜ ተደንቀው ወዴት እንደነበር ሲጠይቁት አባታችንም ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው የሆነውን ነገራቸው፡፡ ከዚኽም በኋላ በትምህርትና በዕድሜ ከሌሎቹ
መነኰሳት ልጆቹ የሚበልጠውን ልጁን አባ እንድርያስን ወደ ንጉሥ ዓምደ ጽዮን ንስሓ እንዲገባ መልእክት ያደርስ ዘንድ ላከው፡፡ አባታችንም በገዳሙ ሆኖ ስለ ንጉሡ ሱባኤ ይዞ ስለነበር ንጉሡ ልቡናው ተመለሰለት፣ ያደረበት የዝሙት መንፈስም ለቆት ጠፋ፡፡ ንጉሡም የአባታችንን መልእክት ከሰማ በኋላ በተሰበረ ኅሊና ሆኖ ንስሓ ገባ፡፡ አባ እንድርያስንም ‹ኃጢአቴ ከሰው ሁሉ ኃጢአት የበዛ ነውና ከባድ ቀኖና ስጠኝ› አለው፡፡
ዳግመኛም ‹ለእኔ በማትገባኝ አመንዝራ ሴት ምክንያት የአባታችን የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ልጆች በግፍ እንድገድላቸውና ከመንበረ ክብራቸው እንዳሳድዳቸው ሰይጣን አስገድዶኛል፣ ስለዚህም የማትገባኝን አመንዝራ ሴት ስለማግባቴና ስለቅዱሳን ደም ፈጣሪዬ ተቆጥቶ ወደ ገሃነመ እሳት እንዳይጨምረኝ ከገጸ መዓቱ የተነሣ
እፈራለሁና› ብሎ መሪር እንባን አለቀሰ፡፡ አባታችን ዜና ማርቆስም በዚያች ሌሊት ስለእርሱ ከመስገድና ከመጸለይ
አላቋረጠም ነበር፡፡
ከዚኽም በኋላ ንጉሡ ከአባታችን ዜና ማርቆስ ረድእ ቀኖና ተቀብሎ በቀንም በሌሊትም በየሰዓቱ እልፍ እልፍ እየሰገደ በሌሊትም ከዙፋኑ ወደ መሬት ወርዶ እየሰገደ ያድራል። በቀንም በወርቅ ከተሠራ ልብሰ መንግሥቱ ሥር ከበግ ፀጉር የተሠራ ማቅ የሚለብስ ሆነ፡፡ ቀኖናም ከተቀበለ በኋላ የአባታችን ዜና ማርቆስ የጸሎቱ ኃይል ከአጋንንት ጦር እየረዳው በአንድ ዓመቱ ቀኖናውን ፈጽሞ በሰላም ዐረፈ፤ ወደ መንግሥተ ሰማያትም ገባ፡፡
(ገድለ አቡነ ዜና ማርቆስ ገጽ 248-254 )
የአቡነ ዜና ማርቆስ እመቤት አምላክን የወለደች ክብርት እመቤታችን እኛንም ታስምረን። ምንም እንኳን በከፋ ኀጢአት ብንወድቅ ለነፍሳችን ድኅነት የሚተጉ ቅዱሳን አባቶቻችንና ቅዱሳት እናቶቻችን የሰጠን ልዑል እግዚአብሔር ይክበር ይመስገን!!!