20/06/2026
ቅዱስ ሩፋኤል ከክፉ ነገር ሁሉ ይከልለን፤ ምልጃ እና ረድኤቱም አይለየን🙏
ቊጥሩ ከሰባቱ ሊቃነ መላእክት ሲሆን፤ “ሩፋ” ማለት ሐኪም፤ ኤል ማለት እግዚአብሔር ማለት ሲኾን ሩፋኤል ማለት “እግዚአብሔር ሐኪሜ ነው” ማለት ነው፡፡
ቅዱስ ኤጲፋንዮስም በመጽሐፈ አክሲማሮስ “በራማ ሰማይ የሚገኘውን ሁለተኛውን ዐሥሩን ነገድ መናብርት ሲላቸው አለቃቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፤ እነዚህም ረቂቅ የሆነ የመብረቅ ጋሻ የእሳት ጦር ይዘው ከነፋስ ይልቅ የፈጠኑ ሲሆኑ በራማ በሁለተኛው ክፍል ላይ አስፍሯቸዋል፡፡
ቅዱስ ሩፋኤል ነገደ መናብርት የሚባሉትን ራማ በሚባለው ሰማይ የሚኖሩትን ነገደ መላእክት የሚመራቸው ናቸው፡፡ አባ ጊዮርጊስም በሰዓታቱ “ጽርሐ አርያም አዳራሹ፤ የትጉሃን መኖሪያ ቦታው የሚኾን እግዚአብሔር ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ ተብሎ በአንድነት በሦስትነት ይመሰገናል፤ ካህናተ ሰማይ በዙሪያው ይቆማሉ፤ በዙፋኑ ፊት እየሰገዱ አክሊሎቻቸውን ያወርዳሉ፤ እሳትነቱ በሚበርቅ፣ በሚል ጊዜ እንዳይመታቸው ይንቀጠቀጣሉ” ይላል፡፡
ቅዱስ ሩፋኤል ከሚመራው ከዚህ ነገድ 24ቱ ካህናተ ሰማይ ወጥተዋል፡፡” ይለናል፡፡ በመጽሐፈ ሄኖክ 6÷3 ላይም “በሰው ቁስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው” ተብሏል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ባስልዮስም “በፊቱ የሚቆሙ የመላእክት ሰራዊትም ሁሉ ጩኸው ያመሰግኑታል፤ የመላእክት አለቆችም ለማይታይ ለባለዚህ ስም ዘንበል ብለው ይሰግዳሉ፤ ዙፋኑን የሚሸከሙ አርባዕቱ እንስሳ ጩኸው ያመሰግኑታል፤ ዕጣንን የተመሉ የወርቅ ማዕጠንት በእጆቻቸው ያለ ሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ይኸውም የቅዱሳን ጸሎት ነው እስከ ዘላለሙ ሕያው በሆነው ፊት የሚቀበለው መሥዋዕት አድርገው ወደ ላይ ያሳርጋሉ” በማለት አስተምሯል፡፡ በ720 ዓ.ዓ ዐሥሩ ነገደ እስራኤል ሲማረኩ ጦቢት የተባለ ጻድቅ ሰው ዐብሮ ተማርኳል፡፡ ቅዱስ ሩፋኤል ይህን ጦቢትን የተራዳ መልአክም ነው፡፡
በመጽሐፈ ጦቢት 2÷14 እንደተጻፈው ሰውን በመርዳት በደግነቱ የታወቀው ጦቢት ከመንገድ ወድቆ የተገኘ በድን ቀብሮ፤ በዚያው ሌሊት ከቅጥሩ አጠገብ ፊቱን ተገልጦ ተኝቶ ሳለ አዕዋፍ ትኩስ ኩስ ዐይኑ ላይ ጥለውበት እንደ ብልዝ ያለ ወጥቶበት ዐይኑ ጠፋ፤ ሚስቱም ባለማስተዋል “በጐነትህ ምጽዋትህ ያዳነህ ወዴት ነው?” በማለት ስትናገረው ዐዝኖ ሞትን ተመኘ፡፡ ቅዱስ ሩፋኤልም አይኑን ሲፈውሰው፣ በላይዋ ላይ ያደረ ጋኔን ባሎቿን ይገድልባት ቤተሰቦቿ ያንቋሽሿት የነበረችውን የራጉኤል ልጅ ሳራን ያደረባትን ርኩስ መንፈስ አስወጥቶ የጦቢት ልጅ ጦብያ እንዲያገባት አድርጓል፡፡ ቅዱስ ሩፋኤልም ከዚህ በኋላ ወደ ጦቢት በመኼድ ረዥም ዘመን የታወረ ዐይኑን አብርቶለት ከሰብዐቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሩፋኤል እኔ ነኝ ብሏቸው ተሰውሯል፡፡
ጦቢት 12÷15፡፡ የመላዕክት ተራዳኢነት በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ትልቅ ስፍራ አለው፡፡ ፈታሔ ማኀፀን ወሰፋድል። መወለድ መንፈሳዊ። ወሐኪም ሰማያዊ ይባላል። የወላድ ማኀፀን እንዲፈታ በእግዚአብሔር ስለተሾመ አዋላጅ ብትኖርም ባትኖርም ቅዱስ ሩፋኤል በዚያ አይታጣም፡፡ በተለይ በባላገር ያሉ ሴቶች በምጥ ጊዜ ሁሉ መልክአ ሩፋኤል በአንገታቸው ያነግታሉ፣ ይጸልያሉ፣ የተጸለየበትንም ጸበል ይጠጣሉ፤ በፍጥነትም ይወልዳሉ። በየወሩ በ13 ቀን መታሰቢያ በዓሉ የሚከበር ሲሆን ጳጉሜ 3 ደግሞ ዓመታዊ በዓሉ ነው፡፡ የቅዱስ ሩፋኤል በረከትና ረድኤቱ አይለየን፤ ምልጃው ይጠብቀን፡፡ ገዳማውያንም ይህን ተራዳኢነቱን በመታመን ዘወትር በጸሎታቸው ይጠሩታል፡፡ ገዳማቸውን በመደገፍና በዓታቸውን በማጽናት የበረከታቸው ተሳታፊ እንሁን፡፡
ድጋፍ ለማድረግ:- ሙትአንሳ ማር ቅዱሰ ሚካኤል አንድነት ገዳም
ኢትዮጲያ ንግድ ባንክ
1000442598391
ወይም
አቢሲኒያ ባንክ
141029444
የገዳሙ ስልክ ቁጥር:-0918077957 ወይም 0938644444