18/11/2025
+*" አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ "*+
[በሕይወተ ሥጋ የሌለ ወዳጃችሁን ሻማ በማብራት በአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ስም ዘክሩት፥ ትምህርቱን ለብዙ ሰው share በማድረግ አዳርሱት።]
=>አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ አባታቸው መልአከ ምክሩ : እናታቸው ወለተ ማርያም ይባላሉ፡፡ የተወለዱበት ልዩ ቦታው ወሎ ክፍለ ሀገር ዳውንት ነው፡፡ በተወለዱ ዕለትዐተነስተው በእግራቸው ቆመው ሦስት ጊዜ "ስብሐት ለአብ: ስብሐት ለወልድ : ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ" ብለው አመስግነዋል፡፡
+የስማቸው ትርጓሜ "የአብ : የወልድ : የመንፈስ ቅዱስ እስትንፋስ" : አንድም "የክርስቶስ እስትንፋስ" ማለት ነው፡፡
ቅዱስ ሚካኤል እየጠበቃቸውና በመንገዳቸው ሁሉ እየመራቸው ነው ያደጉት፡፡ መንፈስ ቅዱስ ልቡናቸውን ብሩህ አድርጎላቸው በ5 ዓመታቸው የቅዱሳት መጽሐፍት ቃላትን፣ ብሉያትንና ሐዲሳትን፣ ድርሳናትንም ጠንቅቀው ዐውቀዋል፡፡
+በተወለዱ በ14 ዓመታቸው ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ደብረ ሐይቅ ገዳም ሄደው ከባሕር ዳር ቆመው የሙሴን ጸሎት ወደ እግዚአብሔር በጸለዩ ጊዜ የታዘዘ መልአክ መጥቶ ባህሩን አሻግሯቸው ወደ ቤተክርስቲያን ገብተዋል፡፡ ለ3 ዓመትም በኃይቅ ገዳም ለመነኮሳት
እንጨት በመልቀምና ውሃን በመቅዳት : ለአባቶች መነኮሳት ምግብ ሊሆናቸው ከባህር ውስጥ አሳን በማውጣት አገልግለዋል፡፡
+አባታችን እስትንፋሰ ክርስቶስ 40 መዓልትና 40 ሌሊት ከጾሙ በኋላ ምንም እህል ሳይቀምሱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ለሙሴ በደብረ ሲና እንደሰጠው ለአባታችንም ወደ እርሳቸው መጥቶ ዓሥሩን ቃላተ ኦሪትና ስድስቱን ቃላተ ወንጌል በውስጣቸው የተጻፈባቸው ሁለት
ጽላቶችን ሰጥቷቸዋል፡፡
+አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ከሠሩ በኋላ ዕለቱን ስንዴ ዘርተው፣ ወይን ተክለው፣ ጽድን ወይራንና ግራርን ተክለው በአንዲት ቀን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ዕለቱን አድርሰዋል፡፡ ስንዴውን ለመስዋዕት
ወይኑን ለቁርባን በታምራት አድርሰዋል፡፡
+አባታችን በጸሎት ላይ እንዳሉ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተልኮ መጥቶ አባታችንን በደመና ጭኖ ወስዶ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ፊት አቆማቸው፡፡
ጌታንም በቅዱሳኖቹ ሁሉ እንዲባረኩ ካደረጋቸው በኋላ መልአኩን ‹‹ወደ ተወለድኩባትና ወደ ኖርኩባት ቦታ ወደ ኢየሩሳሌም አድርሰው›› ብሎት ኢየሩሳሌምን አሳልሞ ሀገራችን መልሶ አምጥቷቸዋል፡፡ ሁሉንም የኢትዮጵያን ቅዱሳት ገዳማትንም ተዘዋውሮ ሲጎበኙ በሕይወተ ሥጋ
የሌሉት የየገዳማቱ ቅዱሳን ሁሉ በአካል ይገለጡላቸው ነበር፡፡
+ጎጃም ውስጥ እያስተማሩ፣ እያጠመቁ፣ የታመሙትን እየፈወሱ፣ የዕውራንን ዐይን እያበሩና ሙታንን እያስነሱ ብዙ ካገለገሉ በኋላ ለዘጠኝ ዓመታት በባሕር ውስጥ ገብተው ቁልቁል ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ጸልየው የምሕረት ቃልኪዳን ተቀብለዋል፡፡ ከዘጠኝ ዓመት በኋላ ጌታችን መጥቶ ‹‹ከመነኮሳት ሁሉ ብልጫ ያለህ ወዳጄ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ምሬልሃለሁ ከዚህች ባሕር ውጣ›› በማለት በሞት የሚያርፉበትን ቦታ ነግሯቸዋል፡፡
+ጻድቁ ወደ ደብረ አስጋጅ በሚሄዱበት ጊዜ ጸሐይ ልትገባ ስትል ‹‹በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አውግዤሻለሁ፡፡ ለመስፍን ኢያሱ በገባኦን እንደቆምሽ አሁን ቀጥ ብለሽ ቁሚ›› ብለው ገዝተው ፀሐይን
አቁመዋል፡፡
+አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስም ደብረ አስጋጅ ሲደርሱ ፀሐይ አፍ አውጥታ ‹‹አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ሆይ እገባ ዘንድ ፍታኝ›› ስትላቸው ‹‹እግዚአብሔር ይፍታሽ›› ባሏት ጊዜ ጠልቃለች፡፡
ጻድቁ ሌላው በእጅጉ የሚታወቁበት አንድ ትልቅ ቃል ኪዳን አላቸው፡፡
+በአምላክ ፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ፣ በቅዱስ ሚካኤልና በቅዱስ ገብርኤል ልቡና የሚገኝ እንደ መልክአ ኢየሱስ ያለች እጅግ አስገራሚ ጸሎት አለቻቸው፤ እርሷን ጸሎት በጸለዩ ጊዜ እልፍ ነፍሳትን ከሲኦል ያወጣሉ፡፡ ጸሎቷም የመድኃኔዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች እያንዳንዱ የሰውነት ክፍሎቹ የተቀበሉትን ጸዋትዎ መከራዎች ሁሉ ታዘክራለች፡፡ በእያንዳንዱ ክፍልም የጸሎት ማሳረጊያ አቡነ ዘበሰማያት ይደግማሉ፡፡
+ንስሓ የገባ ኃጢአተኛ ሰው እንኳን ቢሆን ይህችን የአቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስን ጸሎት በጸለየ ጊዜ ሺህ ነፍሳትን ከሲኦል እንደሚያወጣ ጌታችን በማይታበል ቃሉ ለአባታችን ነግሯቸዋል፡፡ እያንዳንዱን የመድኃኔ ዓለምን የሰውነት ክፍሎች በሙሉ እየጠቀሰች መከራዎቹን
የምታዘክረውን ይህቺን በአምላክ ልቡና ያለች ግሩም የሆነች ጸሎት "ነፍሳትን ከሲኦል አታወጣም" ብሎ የሚጠራጠር ቢኖር ግን መንግስተ ሰማያትን አያያትም፡፡
+ጻድቁ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ ታህሳስ 9 ቀን ተወልው ሚያዝያ 9 ቀን በታላቅ ክብር ዐርፈዋል፡፡
(ገድለ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ)
=>አምላከ ቅዱሳን በጻድቁ አማላጅነት ሃገራችንን
ይጠብቅልን:: ከበረከታቸውም ይክፈለን::
††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††
አቤኔዘር ዘተዋሕዶ ገፅ 2