19/09/2020
ስለ ጸያሔ ፍኖት ባሕታዊ ገብረ ሚካኤል ተገን
መንፈሳዊ ጉዞ እና ስለሚያስፈጽሙት
የዳግም ምጽአት ዝግጅት ሂደት ለጠየቃችሁ እና ወደፊትም ለምትጠይቁ ምእመናን
ከአክብሮት ጋር የቀረበ የማብራሪያ መልስ :-
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን ።
ጌታችን ና መድሀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት በተናገረው መልእክት "ተዘጋጅታችኹ ኑሩ (ጠብቁ) ፥ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና።" (ማቴ ፳፬÷፵፬) ብሏልና፣ የ አባታችን አገልግሎት ይህን መልእክት መሰረት ያደረገ ነው።
በማኅበረ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ዘነገደ ፻ አባላት ተሳትፎ እና በጸያሔ ፍኖት ባሕታዊ ገ/ሚካኤል ሰብሳቢነት እየተካሄደ ያለው የዳግም ምጽአት ዝግጅት " በጥምቀት በንስሐ እና በቅዱስ ቁርባን ተቀድሰን እንዲሁም የምጽአት በዓልን በድምቀት እያከበርን እንጠብቀው ቀኑን አናውቅምና፣ እንዲሁም ለበዓሉ ማስከበሪያና መታሰቢያ ታላቅ ደብር እንሥራለት " የሚል ነው ።
የዝግጅቱ አስፈጻሚ ጸያሔ ፍኖት ባሕታዊ ገ/ሚካኤል ተገን እምነቴን በገንዘብ አልቀይርም በማለት ና ተልእኮዬን ሳላውቀው ሀብት አይምጣብኝ ብለው በመጸለይ እና ለዘመናት በእውነተኛዋ መንገድ ጸንቶ በመቆየትና ለመንፈሳዊው ተልእኳቸው የሚያስፈልጉ ሥራዎችን በመሥራት እና በመዘጋጀት ለዘመናት ሲደክሙና ሲወጡ ሲወርዱ የቆዩና እግዚአብሔር የፈቀደው ጊዜ ሲደርስ ታላቅ መንፈሳዊ ተልእኳቸውን ይዘው ብቅ ያሉ አባት ናቸው ።
የተሰጣቸው ተልእኮ እና ዓላማ :-
፩) እንደ ጌታችን ልደት ጥምቀትና ትንሣኤው እንዲሁም እንደ መስቀል በዓሉ ታላቅ በዓል ፤ የጌታ መገለጥ የሆነ ነውና እንዲሁም ታላቅ ሥራ የሚሠራበት ፣ ስንዴውን ከገለባው የሚለይበት ፣ እንክርዳዱን የሚያበጥርበት፤ ዕለት የሆነውን ዳግም ምጽአትን ከላይ እንደተጠቀሱት ዐቢይ በዓላት በድምቀት ማስከበር ነው ።
ይህም ሲባል መጋቢት ፳፱ የሚከበረውን ደብረ ዘይትን የዳግም ምጽአት በዓል
በዓዋጅ በዓለም አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ
በበለጠ ድምቀት እናክብረው ለማለት ነው እንጂ ሌላ አዲስ በዓል እየፈጠሩ እንዳልሆነ ሊታወቅ ይገባል ።
፪) ለበዓሉ ማስከበሪያና መታሰቢያ የሚሆን እና እንደ ላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ታላቅና ታሪካዊ የሚሆን በከበረ ድንጋይ የሚሠራ በአንድ ዙሪያ ባለ ዓሥራ ሦስት ቤተ መቅደስ ያለው ቤተክርስቲያን ለማሠራት የታዘዙና የተነሡ አባት ናቸው ።
(አንዱ ና ዋናው መሐል ላይ የሚሆነው ለጌታችንና ለእመቤታችን ሲሆን በዙሪያው የሚሠሩት ዓሥራ ሁለቱ ደግሞ ለዓሥራ ሁለቱ ሐዋርያት የሚሆኑ ናቸው።)
ማሳሰቢያ :-
የጌታችን የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መምጫን ቀን አውቃለሁ አላሉም "ቀኑን አናውቅምና ተዘጋጅተን እንጠብቅ" ነው የሚለው መልእክታቸው ።
፪) የኢየሱስ መንገድ ጠራጊ ነኝ አላሉም ይልቁንም " የዳግም ምጽአት መንገድ ጠራጊ ነኝ ነው ያሉት" ምክንያቱም የተጠሩበት አገልግሎት ምጽአት የለም / አይደርስብንም በሚል ስሜት የተዘናጋውን ወገን በዳግም ምጽአት ላይ ይበልጥ ትኩረት በማድረግ መጽሐፍ ቅዱስንና የቅዱሳን አበውን ትምህርት መሠረት በማድረግ ማስተማርና ማዘጋጀት ነው ።
በእውነቱ የዚህን ታላቅ ሥራ መልእክት ላልደረሰው በማዳረስ ታሪካዊና መንፈሳዊ አስተዋፅኦ ልናደርግና የበረከቱ ተካፋይም ልንሆን ይገባል !
ባሕታዊ ገ/ሚካኤል ትሑትና ቡሩክ በሄዱበት ቦታ ሁሉ ማለት ይቻላል ቤተ ክርስቲያን የሚተክሉ አባት ሲሆኑ በአዲስ አበባና በዙሪያዋ እንዲሁም በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍለ ሀገሮችሁሉ በርካታ አብያተ ክርስቲያናትን ተክለዋል አስተክለዋል ። ጠበል በማጥመቅና እየሰየሙ በማንገሥም ታላላቅ አገልግሎትና አስተዋጽዖ በመስጠት ላይ የሚገኙ ናቸው ።
አባታችንን ከ1989 ዓ.ም ጀምሮ ይህን ዓላማ ይዘው ሲንቀሳቀሱ የነበረ ሲሆን፣ በ 1974 ዓ / ም ጀምረው በልጅነት እድሜአቸው የፈውስ አገልግሎት በሚሰጡበት ወቅት እሳቸውን የሚያውቁ ወላጆቻችን እና አንዳንድ አባቶች እንደ ነገሩን ከዚያን ዘመን ጀምሮ የምጽአቱን ዝግጅት እንዲያስፈጽሙ በበቁ ስውራን አባቶች አማካኝነት እንደተነገራቸውና ይህን በምንም የግል ጥቅም ሳይለውጡ ጸንተው እንደኖሩ ተገንዝበናል። እናም ሙሉ ሕይወታቸውን ለዚህ ዓላማ የሰጡ እንደሆኑና ትክክለኛ ታላቅ ቁም ነገሮች የያዙ ፣ ጊዜና ፈቃደ አምላክ የሚጠብቁ በትእግሥት ያሉ እንዲሁም በዓላማ ጽናት ተስፋ ሳይቆርጡ እመቤታችንን በሱባኤና በጸሎት እየተማፀኑ ፈቃደ እግዚአብሔርን የሚጠይቁ መሆናቸውንና ጊዜውም ገና መሆኑን አውቀው ለሠላሳ አምስት ዓመታት ገደማ ይህንኑ ዓላማ ይዘው በጸሎትና በዝግጅት ጸንተው ኖረዋል ።
ቀጥሎም ፈቃደ እግዚአብሔር መድረሱን የሚናገሩ መልእክቶች ና ምልክቶች ሲደርሳቸው በ ፪ሺ፯ /2007 አ.ም መልእክቱን ና ዝግጅቱን ለ ምእመናን ይፋ አድርገዋል። በአሁን ወቅት በርካታ የዝግጅቱ ሂደቶች እየተካሄዱ ነው።
ይህ ሁሉ ውዳሴ ከንቱ ሳይሆን የዓላማውን ምንነትና የአስፈጻሚውን አገልግሎት ና ተልእኮ በተመለከተ የተሰጠ መረጃና ምሥክርነት ነው።
(ማኅበረ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ዘነገደ ፻)