29/05/2025
በእንተ ንድየት ………….ስለ ድኽነት
ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነኝ አንድ ወንድሜ ስለ ድኽነት በማኅበራዊ ድረ ገጹ ላይ ያሰፈረው ሀሳብ ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ድኽነትን ሲያሽሞነምኑ ግርም ይለኛል የሚል የትዝብት ቃል በ Facebook ገጹ ላይ አጋርቶናል፡፡ ትዝብቱ በገደምዳሜም ቢሆን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮን የመሞገት ዓላማ ያለው ይመስላል፡፡ እኛም በቻልነው መጠን ወንድማችንን ሳይሆን ሀሳቡን በጨዋነት እንሞግታለን፡፡ ድኻ ከዚኽ ዐለም ሀብት ቍርጭኝ ድኻን የኾነ ምናምን የሌለው ቍርጭኝ ድኻ። ደከታም ፣ ድክቱም ፣ ነዳይ. በእንግሊዘኛው ደግሞ needy poor የምንለው ቃል ይወክላል፡፡ መቼም ቢሆን ሰዎች ቤተ ክርስቲያንን ለመሞገት ረጅም ርቀት እስከተጓዙ ድረስ ቤተ ክርስቲያን ለምዕመኖቿ ድምጽ ማሰማቷ የማይቀር ጉዳይ ነው፡፡ በዚህ ረገድ የኔን ጽሑፍ እንደ አንድ የቤተ ክርስቲያን ድምጽ አድርጋችሁ ታዩልኝ ዘንድ እማጸናለሁ፡፡ ወዳጄ ሆይ ቤተ ክርስቲያን እኮ ምስካየ ህዙናን ናት፡፡ በሀዘን የተጨቆኑትን ፣ መውጪ መግቢያ ያጡትን፣ መረጋጋት የተሳናቸውን፣ ደዌ የጸናባቸውን ሁሉ ሰብስባ መያዟ አልፋም ለድሆች መጠጊያ መሆኗ የአምላኳን ፈቃድ መፈጸሟን እንደሆነ ልታውቅ ይገባል፡፡ እሷ ለድኾች መቆምን የተማረችው እኮ ከአምላኳ ነው፡፡ በመሆኑም ለወንድሜ ምላሽ ይሆን ዘንድ ንድየት ወይም ድኽነት በሚል ርዕስ የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ምን ይመስላል? የሚለውን ወደ መፈተሽ እንሂድ፡፡ አምላከ ቅዱሳን ፣ የድኾች አምላክ በመካከላችን ሆኖ እንዲያስተምረን የእርሱ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡
አዎ ድኽነት አስከፊ ገጽታ አለው፡፡ ደስም አይልም፡፡ ጉስቁልና ምን መልካም ነገር አለውና? ለመሆኑ ድኽነትን መጠየፍ አለብን ስንል ድኻን ወደ መናቅ እና ማዋረድ ደረጃ መድረስ አለብን ማለት ነው ወይ? በፍጹም ፡፡ በተለይ ለአንድ በክርስትና እኖራለሁ ለሚል ሰው ድኻን ማክበር አስፈላጊ ስለመሆኑ ክብርና ምሥጋና ይግባውና የጌታችን እና የአምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምድራዊ ሕይወት ዋቢ ምስክሩ ነው፡፡ አምላካችን ኑሮው ሁሉ የድኽነት ነበር፡፡ ድኻን መናቅ ለድሆች የመንፈስ ዕረፍት ሲሰጣቸው አልፎ ተርፎም ሲፈውሳቸው የነበረው የአምላካችን ተግባሩን እንደመናቅ ይቆጠራል፡፡ ጌታ የሞተላቸው እኛ የናቅናቸውን ድኾችን ጭምር ነጻ ሊያወጣቸው መሆኑ ልብ ልንል ይገባል፡፡ ጌታ በመዋዕለ ሥጋዌው በቤተ መንግሥት ከሚኖሩ ነገሥታት ጋር መገኘትን አልመረጠም፡፡ ከዚያ ይልቅ ምስኪኖችን በፍቅሩ ሰበሰባቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱ በዘመኑ ከነበሩ ሀብት ንብረት ከሌላቸው የሚቆጠሩ ድኾች የሚል ስያሜ የተሰጣቸው ነበሩ፡፡ ስለሆነም ድሀ በእግዚአብሔር ዘንድ ዋጋ እንዳለው ካላወቅህ ከራስህ ክርስትና ጋር በተቃራኒ ቆመሃል ማለት ነው፡፡ ፈጣሪ ከእንዲህ ካለው ተቃርኖ ይሰውረን…………
የተወደደ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በተለይም ክርስቲያን ሆነህ ድኾችን የምትንቅ ከሆነ ክርስቶስን እየሰደብክ እንደሆነ አስተውል ይለናል፡፡ የሰው ልጅ በአንድም በሌላም መንገድ ድኻ ሊሆን ይችላል፡፡ ዛሬ አግኝቶ ከሆነ ነገ ሊያጣ ይችላል፡፡ ድኽነት በሰው ልጅ የዕለት ተዕለት ሕይወት ውስጥ የምናየው የአዘቦት ክስተት ነው፡፡ በሀብት የከበሩ ከዘመን በኋላ ነዳያን የሆኑ ብዙዎች አሉ፡፡ ከታች ተነስተው በሀብት የከበሩም ብዙዎች ናቸው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሳይቀር በዚህ ከፍታ እና ዝቅታ የነበሩትን ግለሰቦችን ታሪክ ሲያወሳ አንመለከታለን፡፡ ድኽነትን ማሽሞንመን የሚለው ቃሉን ማጉላት የተፈለገው በዋናነት ነዳያን በማትጥየፈው ቤተ ክርስቲያን ላይ ስላቅ ለመናገር ከሆነ ስህተት ነው፡፡ እኛ ኦርቶዶክሳውያን ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳትሆን እግዚአብሔርንም ጭምር አምላከ ነዳያን ወተስፋ ቅቡጻን እንለዋለን፡፡ እግዚአብሔር የምስኪኖች አምላክ በቀቢጸ ተስፋ ላሉት ተስፋቸው ነው ማለታችን ነው፡፡ ታዲያ ጌታ ያልተጠየፋቸውን ድኾች ቤተ ክርስቲያን የምትጠየፋቸው ስለምንድነው?
ሊቃውንት ከእንስሳት እና ከዕጸዋት ይልቅ የሰው ልጅ የበለጠ ድኽነት ይስማማዋል ሲሉ ያስተምሩናል፡፡ ዕጸዋት እስከ ምግቦቻቸው ተፈጠሩ፡፡ እንስሳት እስከ ልብሶቻቸው ተፈጠሩ፡፡ የሰው ልጅ ደግሞ ለመብሉ እና ለልብሱ ከዕጸዋቱ እና ከእንስሳቱ ላይ ጥገኛ ሆኖ ተፈጠረ ይላሉ፡፡ ሲወለድ ጀምሮ የሰው ልጅ በእቅፍ ውስጥ ያለ በእንክብካቤ የሚያድግ አቅመቢስ እንደሆነ ያሰምሩበታል፡፡ እንዲህ አይነት ድኻና ምስኪን ሆነህ ተወልደህ ሳለህ ሌሎችን በድኽነት ለመፈረጅ የሚያስችል አቅም ከየት እንዳገኘህ የምታውቀው አንተ ብቻ ነህ፡፡ ወገኖቼ እምብዛም መታበይ አያስፈልግም፡፡ በሚያልፍ እንደ ህልም እና እንደ ጤዛ በሆነ ጊዜያዊ ሀብት መመካት ሞኝነት ነው፡፡ ድኾች ሁሉ ልጆቻችን፣ ወንድሞቻችን፣ እህቶቻችን፣ አባቶቻችን፣ እናቶቻችን እና ወገኖቻችን ናቸው፡፡ እኛ ለክርስቶስ ህዋሱ እንደሆነው ሁሉ ድኾችም ለክርስቶስ ህዋሶቹ ናቸው፡፡ ይህን ተላልፈን ድኾችን የምንንቅ ከሆነ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ ሲል ይገስጸናል፡፡ ወንድምህን ድኻ ነው ብለህ የምትንቅ ከሆነ አንተ ባደባባይ ጌታን ካስገረፈው ጲላጦስ ወገን ነህ፤ ይህም ብቻ ሳይሆን ጌታን ዕራቁቱን ከሰቀሉት፣ ሐሞት እና ከርቤን ቀላቅለው ካጠጡት፣ በፊቱ ላይ ምራቅ ከተፉበት አይሁዳውያኑ ከፈጸሙት ግፍ ያልተናነሰ አንተም በወንድምህ ላይ በደል ፈጽመሃል ይለናል፡፡ ድኾች ላይ ከመሳለቅ ይልቅ የእነርሱ መራቆት የእኔ መራቆት ነው ልንል በተገባ ነበር፡፡ የእነሱ መራብ የእኔ መራብ፣ መጠማታቸው የእኔ መጠማት፣ መቸገራቸው የእኔ መቸገር ካላልን የምናመልከው የትኛውን ጌታ ይሆን?
ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ እንዲህ አለ፡፡ በመንፈስ ደሆች የሆኑ ብጹአን ናቸው፡፡/ማቴ 5፡1/ ይልቁንም በሀብት ብትሰለጥንም በድኽነት ሕይወት ውስጥ ብትኖርም ከእነዚህ ሁሉ የመንፈስ ድህነትን መምረጥ ይሻልሃል፡፡ ሀብት ኖሮህ እኔ ሀብት የለኝም፤ ብዕለ ጸጋ ሊባል የሚገባው እግዚአብሔር ነው ማለት በመንፈስ ድኻ መሆን ነው፡፡ በሰው ዘንድ የተማረ ጠቢብ ተብለን ከሆነ ከእኔ ይልቅ ብቸኛ አዋቂ እርሱ እግዚአብሔር ብቻ ነው የምንል ከሆነ ያ መንፈስ ድኽነት ነው፡፡ ሹመት ቢኖረን በሥልጣን ሁሉን ብንገዛ ከእኔ ይልቅ ሥልጣን እና ገዢነት የባሕርይው የሆነው እግዚአብሔር ብቻ ነው የምንል ከሆነ ወደ ብጽእና የሚያደርስ የመንፈስ ድኽነት ከዚህ ሌላ የለም፡፡ የመንፈስ ድኽነት ካለህ የሞላልህን እና የተትረፈረፈልህን ምድራዊ ሥጦታ ለፈጣሪ ሰጥተህ አንተ ባዶ ሆነህ መኖርን ትመርጣለህ፡፡ ይህንን ሕይወት ከቅዱሳን ወገን እነ አብርሐም፣ ኢዮብ፣ ቅዱስ ዳዊት፣ ንጉሥ ሰሎሞን ወዘተ ኖረውታል፡፡
ፍቅረ ነዋይ ያጠቃቸው ሰለ መንፈስ ድኽነት እምብዛም ላይገባቸው ይችላል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ፍቅረ ነዋይ በሚመለከት የተናገረውን አድምጥ፡፡ "ፍቅረ ነዋይ ክፉ ነው፡፡ ፍቅረ ነዋይ ዓይነ ልቡናን ያሳውራል፡፡ እዝነ ልቡናን ያደነቁራል፡፡ ሰዎችን ከሰውነት አስወጥቶ እንደ አውሬ እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚህ ፍቅረ ነዋይ ደዌ የተያዘ ሰው ሰማይ ወርቅ ታዘንብለት ዘንድ፣ ምድርም የብር ጋኖች ታፈራለት ዘንድ፣ ጳዝዮን የተባለውንም ጥሩ ዕንቁ ታመነጭለት ዘንድ፣ ተራሮችም ወደ ወርቅ ይለወጡ ዘንድ ይወዳል፡፡ ይሰጣቸው ዘንድ ይፈራልና ጦም አዳሪዎችንም ይጸየፋል፡፡ ወንድሞቹንና ዘመዶቹን፣ ወዳጆቹንና ወገኖቹንም ይክዳል፡፡ የገዛ ነብሱም ላይ እንዲጨክን ያደርጋል፡፡ ሁለንተናው የዚህ ገንዘብ ባርያ ያደርጋል፡፡ የባርነቱ አስከፊነት ደግሞ ይህ ሰው በዚህ ገንዘብ ተድላ ደስታ እንደሚገኝ ማሰቡ ነው፡፡" ወገኔ በመንፈዊ ዓይን ካየነው ፍቅረ ነዋይ በራሱ ደዌ እና የማይድን በሽታ ነው፡፡ ግያዝን ዓይኑን ያሳወረው ነቢይ ከመሆን የከለከለው ፍቅረ ነዋይ ነው፡፡ ፍቅረ ነዋይ አናንያን ከሚስቱ ጋር አስጠፍቶታል፡፡ የአይሁድ ረበናት በክርስቶስ ላይ ልቦናቸው እንዲደነድን ያደረገው ይኸው ፍቅረ ነዋይ ነው፡፡ በዓለማችን የብዙ ጦርነት መነሻ ይኸው ፍቅረ ነዋይ ነው፡፡ ስንቶች ንጹሐን በፍቅረ ነዋይ ምክንያት ሕይወታቸው ተቀጨ? ምድር በሰዎች ደም የጨቀየው ፣ ሕዝብ በለቅሶና በዋይታ ሕይወቱን የሚገፋው በዋናነት በፍቅረ ነዋይ በተጠቁ ሰዎች ምክንያት ነው፡፡ ይሁዳ በፍቅረ ነዋይ አምላኩን እስከመሸጥ ደርሷል፡፡ ፍቅረ ነዋይ አእምሮን ያሳጣል፡፡ ዓይነ ልቡናን ያጨልማል፡፡ የሃይማኖት መልክ ያጠፋል፡፡ የክርስቶስ ልብስ ከመሆን ያራቁታል፡፡ በኃጢአት ባሕር ውስጥ እንድንሰጥም ያደርገናል፡፡ በመጨረሻም ከሰይጣናት ጋር እንድንቆጠር ያደርገናል፡፡
ዛሬ በፍቅረ ነዋይ ጉጉት የወደቁ ካሉ ሰውን ያማከለ የክርስትና ሕይወት ቢኖራቸው መልካም ነው፡፡ ድኽነትን መጠየፍ ይገባል፡፡ ድኾችን መጥላት መናቅ ግን አልተፈቀደልንም፡፡ ሀብት ያላቸውም ቢሆን ካላቸው አውጥተው እንዲመጸውቱ በድኾች ላይ የተሾሙ ባለሥልጣናት ናቸው፡፡ የተሰጣቸው ከፈጣሪ መሆኑን ቢያውቁም መልካም ነው፡፡ እዚህ ጋር በሕጋዊ መንገድ ሀብት ያፈሩትን ማለቴ ነው፡፡ በሕገወጥ መንገድ በምድራዊ ሀብት የበለጸጉት ካሉ በምድርም በሰማይም የሚጠየቁ ወንጀለኞች መኾናቸው ልብ ይሏል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሀብት ያላቸውንም የሌላቸውንም ምዕመናን እና ምዕመናትን በእኩል ታያለች፡፡ ሀብት ስላላቸው የምታፍራቸው ምድራውያን ብዕለጸጋዎች የሏትም፡፡ በድኽነት የሚኖሩትንም ስለድህነታቸው ሳትሳቀቅ በቃለ እግዚአብሔር ትገስጻቸዋለች፡፡ ይልቁንም በምዕመናኑ ላይ ስለ ሰማያዊ ብልጽግናቸው ይበልጥ አበክራ ትሰራለች፡፡
አዎ ለአንድ ክርስቲያን በዚህ ዓለም ሲኖር ዋና የሚስፈልገው ነገር ቢኖር ለሰማያዊ ብልጽግና የሚያበቃው የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ነው፡፡ አንዳንዶቻችን በፍቅረ ነዋይ አስተሳሰብ ውስጥ ሆነን እከሌ በገንዘብ የከበረ ነው፤ የሚኖርበት ቤት በልዩ አሰራር የተዋበ ነው፡፡ የሚሄድበት መኪና ልዩ እና ፍጹም ዘመናዊ ነው፤ እከሌ የተባለ ባለሥልጣን ዘመድ አለው፤ ያሻውን ማዘዝ የሚችልበት ምድራዊ ሥልጣን ተችሮታል ወዘተ የምንልላቸው ሰዎች ይኖሩናል፡፡ እንዲህ አይነት ንግግርን የሚናገሩ ሰዎች ያህል በዚህ ዓለም ምስኪኖች እንደሌሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያሰምሩበታል፡፡ ከላይ የተዘረዘሩት ገንዘብ፣ መኪና፣ ሥልጣን፣ የተዋበ ቤት ከእኛ ማንነት በአፍአ ያሉ ናቸው፡፡ እነዚህ ሁላ ለአንድ ሰው መንፈሳዊ ማንነቱ ገላጮቹ አይደሉም፡፡ እከሌ ትህትና፣ ቅድስና፣ ንጽሕና፣ በጎነት፣ ራስን መግዛት፣ ትዕግስት አለው ከተባለ ያ ሰማያዊ ብልጽግና ይባላል፡፡ በክርስትና የመኖራችን ምሥጢር ይኸው ሰማያዊ ብልጽግና ነው፡፡ የሚያሳዝነው ለእንዲህ ላለው ብልጽግና ሕይወታቸውን የሰጡ ጥቂቶች መሆናቸው ነው፡፡
እንግዲህ በሀቅ እና በእውነት ጠንክረው እንዲሰሩ ከምድራዊ በረከት እንዲካፈሉ ቤተ ክርስቲያን ምዕመኖቿን ትመክራለች፡፡ እርስበርስ እንዲረዳዱ አንዳቸው ለአንዳቸው በችግራቸው ጊዜ እንዲቆሙ የሰማያዊ አምላክ ትዕዛዛትን ታስተላልፋለች፡፡ በድኾች እና በድህነት መካከል ያለውን ድንበር በደንብ ትገነዘባለች፡፡ ከስስት ይልቅ ፍቅር በሰዎች መካከል እንዲናኝ ትለፋለች፡፡ በስስት ሕይወት ላለ ሰው ሲሰጥ ይጎድልበት ይሆናል፡፡ በፍቅር ስንኖር ግን እየሰጠን ይሞላልናል፡፡ በስስት ለሚኖሩ ስዝማውያን መመሪያቸው የዳርዊን the fittest only survive የሚለው መፈክር ነው፡፡ ይህ ከክርስቲያናዊ አስተምህሮ ያፈነገጠ ነው፡፡ የእኛ ጌታ ያስተማረን ወንድምህን እንደራስ አድርገህ ወደድ የሚለው ኃይለ ቃልን ነው፡፡ ድኸን መውደድ ድህነትን ማሽሞንመናችን አድርገው የሚያስቡ ካሉ መብታቸው ነው፡፡ እኛ ግን ድህነትን እንጠየፋለን፡፡ ድሆችን ግን በፍጹም አንጠላቸውም፡፡ ካለን ከፍለን እንመጸውታቸዋለን፡፡ ይህን እንድናደርግ ያዘዘን የአምላካችንን ቃል እንፈጽም ዘንድ ግዴታችን ነውና፡፡
አምላከ ቅዱሳን በረድኤቱ አይለየን፡፡
ወስብሀት ለእግዚአብሔር
ከመምህር ስንታየሁ