29/01/2026
የድንግል ማርያም ሞትና ታሪካዊ ማስረጃዎቹ
ድንግል ማርያም ምንም እንኳ የአምላክ እናት ብትሆንም እንደ ማንኛውም ሰው የሞትን ጽዋ ቀምሳለች። ጥንታውያን አባቶች እንደሚሉት ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ሲል በሥጋ እንደሞተ ሁሉ እናቱም የሰው ልጅ በመሆኗ የሞትን መንገድ አልፋለች። ይህ "ተፈጥሯዊ ሞት" ይባላል።
በቤተክርስቲያን ታሪክ "ዶርሚሽን" [Dormition] ወይም መኝታ/እንቅልፍ ተብሎ ይጠራል። ይህም ሞቷ እንደ ሌላው ሰው አስፈሪ ሳይሆን፣ በልጇ እቅፍ ውስጥ የሆነ የሰላም እንቅልፍ መሆኑን ለማሳየት ነው። በመጀመሪያ መታወቅ ያለበት መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ድንግል ማርያም ሞት ዝም ማለቱ በወቅቱ የነበሩ ክርስቲያኖች ትኩረታቸው በክርስቶስ ትንሳኤ እና በወንጌል መስፋፋት ላይ በመሆኑ እንዲሁም በነበረው ስደት ምክንያት የታሪክ መዝገቦችን በይፋ ለመያዝ አስቸጋሪ ስለነበር ነው። ሆኖም ግን ከመጀመሪያዎቹ መቶ ክፍለ ዘመናት ጀምሮ ጠንካራ ማስረጃዎች አሉ። የእረፍቷ (ሞቷ) ማስረጃዎችን በሦስት ዋና ዋና ክፍሎች ማለትም፦ በጽሑፍ [ድርሳናት]፣ በታሪክ [የአባቶች ምስክርነት] እና በአርኪኦሎጂ [ቁፋሮ] ከፋፍለን ማየት እንችላለን።
ትራንሲተስ ማሪያ [Transitus Mariae] ድርሳናት
እነዚህ ድርሳናት በብዙ ጥንታዊ ቋንቋዎች የሚገኙ ሲሆን ዋነኛውና ጥንታዊው የሲርያክ ስሪት በሚከተለው መጽሐፍ ውስጥ በዝርዝር ተተርጉሞና ተተንትኖ ይገኛል፦ ይህም፦ ድንግል ማርያም በኢየሩሳሌም በሞተች ጊዜ ሐዋርያት መገኘታቸውንና ሥጋዋን ወደ ጌቴሴማኒ ወስደው እንደቀበሩት የሚገልጹ የመጀመሪያ ምንጮች ትንታኔ።ሐዋርያት ከቆጵሮስ፣ ከኤፌሶንና ከሌሎች ቦታዎች በደመና ተጭነው መምጣታቸውን፣ ማርያም በሰላም ማረፏንና ሥጋዋን በጌቴሴማኒ በአዲስ መቃብር እንደቀበሯት የሚገልጹትን ጥንታዊ ድርሳናት በዝርዝር ያቀርባል።¹
የቤተክርስቲያን አባቶች ምስክርነት[Patristic evidence]
ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ዘሳልሚስ፦ እርሱ እንደሚለው ምንም እንኳን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለ አሟሟቷ በግልጽ ባይቀመጥም ማርያም መሞቷና መቃብሯም መታወቁ የማይካድ እውነታ መሆኑን ይገልጻል። በወቅቱ "አንቲዲኮማርያናውያን" [Antidicomarianites] ተብለው የሚጠሩ ወገኖች ለድንግል ማርያም ክብር ባለመስጠታቸው ሲወቅሳቸው እርሷ ግን በክብር እንዳረፈችና እንደተቀበረች የታወቀ ታሪክ መሆኑን በምክንያትነት ይጠቅሳል።²
ኢየሩሳሌሙ ኤጲስ ቆጶስ ጁቬናል (Juvenal of Jerusalem)፦ በ451 ዓ.ም በኬልቄዶን ጉባኤ ወቅት፣ ለንጉሥ ማርክያን የሰጠው ምስክርነት ትልቅ የታሪክ ማስረጃ ነው። ማስረጃውም ንጉሡ የድንግል ማርያምን ሥጋ ፈልጎ በነበረበት ወቅት ጁቬናል "እርሷ በሐዋርያት ፊት ማረፏን፣ ነገር ግን መቃብሯ ባዶ ሆኖ መገኘቱን" በይፋ መስክሯል። ይህም በ5ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ስለ ሞቷና ትንሳኤዋ የነበረው እምነት የጸና መሆኑን ያሳያል።³
የአርኪኦሎጂ ማስረጃ [Archaeological Evidence]
የጌቴሴማኒ መቃብር በኢየሩሳሌም የሚገኘው የድንግል ማርያም መቃብር ትልቁ ቁሳዊ ማስረጃ ነው። በ1972 ዓ.ም ቤላርሚኖ ባጋቲ [Bellarmino Bagatti] የተባለ ፍራንሲስካዊ አርኪኦሎጂስት በመቃብሩ ላይ ጥናት አድርጓል። በጥናቱም መቃብሩ በ1ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የአይሁድ የቀብር ሥርዓት መሠረት የተዘጋጀ "bench tomb" መሆኑን አረጋግጧል። ይህም መቃብሩ ከጥንት ጀምሮ ለድንግል ማርያም የተለየ መታሰቢያ ሆኖ ሲያገለግል እንደነበር ያሳያል።⁴
የኢትዮጵያ ስንክሳር (ጥር 21)
ይህ የቤተክርስቲያን የታሪክ መዝገብ በዕለቱ በሚነበበው ንባብ ላይ የሚከተለውን ሐሳብ ይዟል፦ ድንግል ማርያም ጥር 21 ቀን ማረፏን፣ ጌታ ነፍሷን መቀበሉን፣ ሐዋርያትም ሥጋዋን ይዘው ወደ ጌቴሴማኒ ሲሄዱ አይሁድ ሊቀሙና ሊያቃጥሉ እንደሞከሩ፣ ነገር ግን በመለኮታዊ ኃይል እንደተጠበቀችና በክብር እንደተቀበረች ይተርካል።⁵
የሐዋርያት ትምህርትና ትውፊት [Apostolic Tradition]
በቤተክርስቲያን ትውፊት መሠረት፣ ሐዋርያው ዮሐንስ [ድንግል ማርያምን እንዲጠብቅ አደራ የተሰጠው] እስከ እረፍቷ ድረስ አብሯት እንደነበር ይታመናል። ይህንንም ትውፊት ተከታዮቹ የቤተክርስቲያን አባቶች [ለምሳሌ ቅዱስ ፖሊካርፐስ እና አግናጥዮስ] በቃል ሲያስተላልፉት ቆይተዋል።
ምንም እንኳን መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሞቷ ዝርዝር ባይሰጥም፣ የጥንት ክርስቲያኖች በጽሑፍ (Manuscripts)፣ በመቃብሯ ቦታ (Archaeology) እና በቤተክርስቲያን በዓላት (Liturgy) አማካኝነት ድንግል ማርያም መሞቷን ለትውልድ አስተላልፈዋል። እነዚህ ማስረጃዎች ሁሉ የሚስማሙበት ነጥብ "ድንግል ማርያም በተጨባጭ መሞቷንና የተቀበረችበትም ስፍራ በኢየሩሳሌም ጌቴሴማኒ መሆኑን" ነው።
እኔም በመጨረሻ “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐፅብ ለኲሉ - ሞትስ ለሟች ይገባዋል የማርያም ሞት ግን ለሁሉ ያስደንቃል” ብዬ ጽሁፌን ዘግቼዋለው እንኳን አደረሰን አደረሳችሁ!
ዋቢ መዛግብት👇
¹ The Dormition and Assumption of the Virgin Mary
² The Panarion of Epiphanius of Salamis: De Fide. Books II and III
³ On the Dormition of Mary: Early Patristic Homilies
⁴ The Church of the Virgin Mary in Gethsemane,1975
⁵ ስንክሳር ዘወርኅ ጥር
https://t.me/orthodox_chrstianity