25/11/2020
+ ሁለቴ የወጣ ስም +
መቼም ባል ሚስቱን የሚጠራበት ስም ቁጥሩ ባይበዛ እንኳን ቢያንስ ሁለት ስም መሆኑ አይቀርም፡፡ የመጀመሪያው ስም ያው ስትወለድ በወላጆችዋ የወጣላት ስም ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ወደ ትዳር ገብተው ሦስት ጉልቻ ሠርተው የፍቅርን እሳት ‘እፍ ሲሉ’ ፍቅሩን ለመግለጽ የሚጠራበት ስም ማውጣቱ አይቀርም፡፡ ፍቅራቸው በጸና መጠን ታዲያ የሚጠራበት ስም ሁሉ አልበቃት አልመጥናት እያለ ይቸገራል፡፡ ‘አካሌ’ ‘እናቴ’ ‘እኅቴ’ ‘ውዴ’ ወዘተ ይላታል፡፡ በፍቅር መካከል ጠብ አይቀርምና ደግሞ ሲጣሉ የሚጠራበት ስም በፊት ለፊትም በጀርባም መቀየሩ አይቀርም፡፡
አዳምና ሔዋን የመጀመሪያዎቹ ባልና ሚስት ናቸው፡፡ ከእርሱ አካል በመገኘትዋ ‘አካሌ’ ፤ አብረው በመፈጠራቸው ‘እኅቴ’ ፤ ከጎኑ ተወስዳ በመገኘትዋ ሕመሜ ፣ እርሱ በተኛ ሰዓት በመፈጠርዋ ሕልሜ ሊላት የሚገባ ብቸኛዋ ረዳቱ እርስዋ ነበረች፡፡ ረዳቱ ናት ሲባል አገልጋዩ ናት ማለት አለመሆኑን ‘እግዚአብሔር ረዳቴ ነው’’ የምንልበት የዳዊት መዝሙር ምስክር ነው፡፡ አዳም እርስዋን ባየ ጊዜ ደስ ብሎት ወደዳት፡፡ ስለዚህም የመጀመሪያውን ስም አወጣላት፡፡ ‘ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል’ አለ፡፡
በእርግጥ ሴት የሚለው ስም አሁን እርስዋን በጾታ ለሚመስሉ ሁሉ መጠሪያ ነው፡፡ በዓለም ላይ አንዲት ሴት ብቻ በነበረችበት ሰዓት ግን ሴት ስም ነበር፡፡ እንደ ዕብራይስጡ ከሆነ እንዲያውም ከወንድ ተገኝታለችና ሴት ትባል የሚለው ዐረፍተ ነገር ‘ከ‘Ishah’ ተገኝታለችና ‘Ish’ ትባል’ የሚል ሲሆን ከጾታ ይልቅ ሴት የወንድ አካል መሆንዋን በቃላቱ ድምፀትም የሚያጎላ ስም ነበር፡፡
ይህች ሴት ግን ለአዳም ውድቀት መነሻ የሆነ መታለልን ተታለለች፡፡ ሰይጣን በዕባብ ሥጋ ተሰውሮ ያለውን ሰምታ አምና ተቀበለች፡፡ ‘ከዛፉ ብትበሉ ዓይናችሁ ይከፈታል ክፉና መልካሙን ታውቃላችሁ’’ የሚለውን የዕባብ ምክር ያለ ጥርጣሬ ሰማች’’ እንደ ጎመን እርሻ የዘሩባትን የምታበቅል የዋሂት ሆና ነው እንጂ ‘ዛፍ ተበልቶ አምላክ መሆን ከተቻለ ምነው አንተ በልተህ አልሆንህም?’ ብላ በጥያቄ ማፋጠጥ በቻለች ነበር፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ እንዲህ ይላል፦ ‘ዕባብ ‘ከዛፉ ብትበሉ ዓይናችሁ ይከፈታል ፣ ክፉና መልካሙን ታውቃላችሁ’ ሲላት ‘ቀድሞውኑ ያልተዘጋ ዓይኔ እንዴት ሊከፈት ይችላል ትለኛለህ? ዓይኖቼ ካልተከፈቱ አንተን እንዴት ለማየት ቻልሁ? የማያቸው ነገሮች ሁሉስ እንዴት ሊታዩኝ ቻሉ? መልካሙንና ክፉን መለየት የማልችል ከሆንሁ የአንተስ ምክር ክፉ ይሁን ደግ በምን አውቃለሁ?’ አላለችም፡፡ ባሪያ ነህ ነጻ? ሰማያዊ መልአክ ነህ ወይንስ አውሬ? አላለችም’ አምና ተቀበለች እንጂ’’ ይላል፡፡ እናም ከዛፉ ፍሬ እርስዋ በልታ ባልዋንም አበላችው፡፡ ሁለቱም ጸጋቸው ተገፈፈ፡፡ በዚህ ምክን ያት በባልና ሚስቱ ላይ ታላቅ እርግማን ወረደባቸው፡፡ በእርስዋ ላይ ምጥና መከራን ፣ በአዳም ላይ ደግሞ የተረገመ መሬት ገበሬነትን ፈረደበት ፣ ‘አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ’ የሚል ከባድ ርግማንን ፈረደበት፡፡ ሁለቱም ከገነት ተባረሩ፡፡
እስቲ ሁኔታውን ልብ እንበለው! አብረው ከገነት ሲወጡ አዳም ሚስቱን እንዴት የሚያናግራት ይመስላችኋል? በዚህ ዘመን በሚስቱ ምክንያት እንደ ገነት ካለ ቦታና ክብር የተዋረደ ባል ሚስቱን እንዴት ብሎ የሚያናግራት ይመስላችኋል? እንደቀድሞው ‘አካሌ ሥጋዬ አጥንቴ’ ይላት ይሆን? በፍጹም አያደርገውም! ካልገደልሁ ካላለም ተመስገን ነው! በእርግጠኝነት ይጣላሉ፡፡ ሚስቱን እንኳን በስምዋ ሊጠራት ከተባረረበት ገነት ብዙ ሳይርቅ እዚያው ሲኦል መፍጠሩ አይቀርም፡፡ አዳም ግን ያደረገው ለማመን የሚከብድ ነገር ነበር፡፡
ክብሩን አጥቶ ፣ ከፈጣሪው ተጣልቶ ፣ እርግማኑን ሰምቶ ፣ ጸጋውን ተነሥቶ ከእርስዋ ጋር ሲወጣ የመጀመሪያ ሥራው ለሚስቱ ስም ማውጣት ነበረ፡፡ ‘ሴት ትባል’ ብሎ ያወጣላትን ስም ቀይሮ በአዲስ ስም ሊጠራት ወሰነ፡፡ ከነበረበት ሁኔታ አንጻር ኀዘን የተቀላቀለበት ፣ ቂም ያዘለ ፣ ወቀሳ ያረገዘ ስም ቢያወጣ ትርጉም ይሠጥ ነበር፡፡ አዳም ግን ለሚስቱ ያወጣው ስም በፍቅር የሚነድዱ አዲስ ሙሽሮች የሚጠራሩበት የሚመስል ስም ነበር፡፡ ሚስቱን ያላት ሕይወቴ ፤ የሕይወትም ሁሉ እናት! ነው፡፡
ሞት አከናንባው እየወጣ ሕይወት ብሎ መጥራት እንዴት ያለ ነው? ‘ረዳት ትሁንህ ብለህ የሰጠኸኝ ሴት ከዛፉ ሠጠችኝና በላሁ’’ የሚለው ክስ የት ሔዶ ነው? ካላችሁ አዳም የሚናገረው አጠገቡ ስላለችው ሔዋን ሳይሆን ደግማ ስለምትወልደውና ሕይወትን ወልዳ ስለምሠጠው ስለ ሁለተኛዋ ሔዋን ስለ ድንግል ማርያም ነበር፡፡ ስለዚህ ‘አዳም እመቤታችን ማርያም ከእርሱ አብራክ እንድትከፈል ከሔዋንም ማኅፀን እንድትወለድ አውቆ ሔዋንን ሕይወቴ ነሽ ይላት ነበር’ እንዲል /መቅድመ ተአምረ ማርያም/
ሕይወቴ / የሕያዋን ሁሉም እናት ያላት ሁለተኛይቱ ሔዋን ድንግል ማርያም ናት፡፡ ይህችኛዋ ሔዋን የተለየች ሔዋን ናት፡፡ ሞትን ያመጣች ሳትሆን ሕይወትን የወለደች ሔዋን ፣ ከአዳም የተገኘች ሳይሆን አዳምን ያስገኘች ሔዋን ፣ አዳም ስም ያወጣላት ሳትሆን ለሁለተኛው አዳም ‘ኢየሱስ’ ብላ ስም ያወጣች ሔዋን ፣ ከአዳም ሥጋን የወሰደች ሳትሆን አዳም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍስዋ ነፍስ ነሥቶ የተገኘባት ሔዋን ናት፡፡
ይህች ሔዋን የዚያችኛዋ ሔዋን መድኃኒት የሆነች ሔዋን ናት፡፡ በምጥ ትወልጃለሽ የተባለች ሳትሆን ሳታምጥ የወለደች ሔዋን ፣ አዝዛለሁ ብላ ታዛዥነት የተፈረደባትና ‘ፈቃድሽ ወደ አዳም ይሆናል’ የተባለችዋ ሔዋን ሳትሆን ‘እነሆኝ ባሪያው’ ብላ ልትታዝ ቀርባ ሁለተኛው አዳም ‘ይታዘዛት ነበር’ የተባለላት ሔዋን ናት፡፡ ያችኛዋ ሔዋን በዕፀ በለስ ዛፍ ላይ የተሰቀለውን የዛፉን ፍሬ አይታ የተመኘች በልታ ባልዋን ያበላች ፣ ዕርቃን ሆና ባልዋንም ዕርቃን ያደረገች ሔዋን ነበረች፡፡ ይህችኛይቱ ሔዋን ድንግል ማርያም ግን በመስቀሉ ዛፍ ላይ የተሰቀለውን የማኅፀንዋን ፍሬ መልካም እንደሆነ አይታ ለእርሱ ሆድዋን ማደሪያ አድርጋ ሠጥታ ለሁላችንም አበላችን፡፡ የሁላችንም ዓይኖች ያን ጊዜ ተከፈቱ ፣ ያን ጊዜም ዕርቃናችንን እንዳልሆንን አወቅን ፤ የተጠመቅን ሁላችን ልጅዋን ለበሰናልና ቅጠል ሰፍቶ ማገልደም አላስፈለገንም፡፡
የቀደመችዋን ሔዋን የገዛ ባልዋ አዳም በፈጣሪ ፊት ‘‘ከእኔ ጋር እንድትሆን የሰጠኸኝ ሴት እርስዋ ከዛፉ ሠጠችኝና በላሁ’’ ብሎ ከስሷት ነበር፡፡ እኛ ግን ስለ ድንግል ማርያም ምንም ክስ የለንም:: ስለእርስዋም እግዚአብሔርን እንዲህ ስንል እናመሰግነዋለን ‘ከእኛ ጋር እንድትሆን ‘እነኋት’ ብለህ የሰጠኸን ሴት የማኅፀንዋን ፍሬ አንተን ሠጠችንና በላን ፤ ከዕጸ ሕይወትም እንበላ ዘንድ አደልከን ይኸውም የከበረ ሥጋና ደምህ ነው’’ እያልን እናመሰግነዋለን፡፡ እኛ ግን ሁለተኛዪቱን ሔዋን ድንግል ማርያምን እንኳን እንደ ቀደመችው ሔዋን ልንወቅሳት ይቅርና እንዲህ አመስግነናትም አንጠግብም፡-
‘‘እንደ እመቤታችን ማርያም የአብ ማረፊያ የሆነ ማን ነው? እንደ እመቤታችን ማርያም የወልድ ማደሪያ የሆነ ማን ነው? እንደ እመቤታችን ማርያም የመንፈስ ቅዱስ ንጹሕ አዳራሽ የሆነ ማን ነው? ለሰው ኃጢአት ሳይሠራ መኖር ይቻለዋልን? ... እመቤታችን ማርያም ንጽሕት በመሆንዋ አምላክ እንዲያድርባት አደረገችው ...
እመቤታችን ማርያም ከአዳም ጀምሮ በነቢያት ትነገር ነበር ... አዳም እመቤታችን ማርያም ከእርሱ አብራክ እንድትከፈል ከሔዋንም ማኅፀን እንድትወለድ አውቆ ሔዋንን ሕይወቴ ነሽ ይላት ነበር .. የሔዋን የሚጎዳ ማሠሪያዋ በአንቺ የተቆረጠላት እመቤቴ ማርያም ሆይ ደስ ይበልሽ ... እግዚአብሔር በብሩሕ ደመና ተጭኖ በማኅፀንሽ ያደረ እመቤቴ ማርያም ሆይ ደስ ይበልሽ ... እኔ ለምእመናን ወንጌልን የማስተምርለት የጌታዬ እናቱ እመቤቴ ማርያም ሆይ ደስ ይበልሽ ... እኛ ከምንወደው እርሱም ከሚወድደን ከልጅሽ ዘንድ ኃጢአታችንን ያስተሰርይልን ዘንድ ለምኚልን’ /መቅድመ ተአምረ ማርያም/
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ጥር 21 2012 ዓ ም
አቃቂ ፤ አዲስ አበባ
ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ጸልዩ!
ሌሎች እንዲያነቡትም የሚከተሉት አድራሻዎች Like, Subscribe እና Share ያድርጉ :-
የፌስቡክ ገጽ :- https://www.facebook.com/officialHenokhaile/
የቴሌግራም ቻናል : https://t.me/deaconhenokhaile
የዩቲዩብ ገጽ: https://www.youtube.com/channel/UCOaVsWC05aUjeqIEW3fWj7g