03/02/2026
ቤተክርስቲያን የማትፈቅዳቸው በቤተክርስቲያን ውስጥ የሚሰሩ ሊወገዙ የሚገባቸው አሁናዊ ሕገ ወጥ (አሳፋሪ) አሰራሮች"
፩, በየጎዳናው የጥሬና የቆሎ ሽያጭ፣
ይህ ነገር አሁን አሁን በየመንገዱ የተለመደ እየሆነ መጥቷል፡ የሰው ፍሰት በሚበዛበትና መኪኖቹ በሚንቀሳሱበት አካባቢ (በመስመር ጥግ) የሚገነባም የማይገነባም ቤተክርስቲያን ካለ ወጣቶች የደንብ ልብስ የመሰለ የሆነ ቢጫና ቀይ ወይም አረንጓዴና ቀይ ከለር ያለው ልብስ ይለብሱና መኪና አስቁመው የበቆሎ ንፍሮ ይይዙና ዓርብም ይሁን ረቡዕ ዐቢይ ጾምም ይሁን ጾመ ነነዌ ለበረከት ያዙ ይላሉ አንዱ ጥሬ ሲያሳፍስ አንዱ የሳንቲም መለመኛውን ይዞ ጠጋ ይላል ።
የሚገርመው ደግሞ ስሙ ለበረከት ያዙ ነው የምን በረከት?
👉ጥሬ እየሸጡ በረከት አለ እንዴት?
👉 ጾም እያሻሩ በረከት አለ እንዴት?
👉በሥርዐትውጭ የገንዘብ ልመና የምን በረከት?
👉ሰውን እያሸማቀቁ ሽያጭ እንጂ? በረከት የለም።
ምን አይነት የልመና ስልት ነው? ያሳፍራል ያሸማቅቃልም ሕገ ቤተክርስቲያንም አይደለም።
ይህ ድርጊት ፈጽሞ ሊቆም የሚገባው ነው ።
፪, በየመንገዱ ጥላ ዘቅዝቆ መለመን።
ማንኛውም ንዋየ ቅድሳት የገንዘብ መለመኛ መሆን አይችልም። ምክንያቱም በዓለም ገበያ ላይ የሚውለው ማንኛውም እቃ ወደቤተክርስቲያን እስኪገባ ተራ እቃ ነው ወደቤተክርስቲያን ከገባ በኋላ ግን ቅዱስ ንዋይ ነው። ልብሱም ታቦቱም መስቀሉም ጥናውም... ሁሉም ነገር የቤተ መቅደስ ቅዱስ እቃ የእግዚአብሔር መገልገያ እንጂ የገንዘብ መሰብሰቢያ ሊሆን አይገባም።
ማንኛውም ሰው የክህነት ልብስ መልበስ የክህነት ጥላ ማንጠልጠል? ሥርዐተ ቤተክርስቲያን መጣስ ነው እኮ ስለዚህ በየኬላው ተሰልፋችሁ ቅዱሱን ስዕል በፀሐይ እያከሰላችሁ የአቧራ ማራገፊያ እያደረጋችሁ ጥላውን እየዘቀዘቃችሁ ያለመዓርጋችሁ ይዛችሁ የገንዘብ ድቃቂ የልብስ እላቂ የምትለምኑ ሰዎች እባካችሁ ቤተክርስቲያንን አታዋርዷት?
፫,መስቀል ጨብጠው በየመኪናው እየገቡ ገንዘብ ካላመጣችሁ እያሉ ሃይማኑቱን ስንኳን ሳይለዩ ገንዘብ የሚለምኑ ካህናት ማቆም አለባቸው።
በጣም የሚገርመው ደግሞ መኪናው ውስጥ ገብተው የግድ መስቀል ካልተሳለማችሁ ይላሉ የሚያሳዝነው ሙስሊም ይሁን ፕሮቴስታንት ፓጋን ይሁን ይሁዲዝም ሳይለዩ መስቀሉን ወደያንዳንዱ ግንባር ይልኩታል ጎበዝ በጣም አፈርን እኮ!!?
ምን አለ ለገንዘብ እንዲህ ከመፋጠን ለወንጌል አገልግሎት እንዲህ ብትፋጠኑ ? ምዕመናንም እባካችሁን ለምን የሚል ጥያቄ አንስታችሁ አባሯቸው ይህ የቤተክርስቲያንን ክብር ማስጠበቅ ነው።
በመናኸሪያው መስቀል ይዞ ልመና
በየኬላው ጥላ ዘቅዝቆ ልመና
በየመኪናው መስቀል ጨብጦ ልመና
በየፌርማታው ቃጭል ይዞ ልመና .... በቃን።
፬, በቅዳሴ ወንጌል መሳለም ጊዜ ሙዳየ ምጽዋት ይዞ መዞር፣
በየጊዜው ቤተክርስቲያንን ውጫዊ ፈተና ባያጣትም አሁን ላይ ያለው ውስጣዊ ፈተና ግን ነውርም መሳለቂያም እያደረገን መጥቷል ሥርዐተ ቅዳሴው አልቆ ወንጌል ተነቦ ጻዑ ንዑሰ ክርስቲያን ተብሎ ሕዝቡን ወንጌል ለማሳለም አንዱ ሲወጣ ሁለተኛው ሙዳየ ምፅዋት ይዞ ገንዘብ ይለምናል።
👉ከመቼ ወዲህ የመጣ ሕግና ሥርዐተ ነው?
👉ወንጌል መሳለም ገንዘብ እየከፈሉ የሆነስ መቼ ነው?
👉ወንጌል ተሸክሞ ሙዳየ ምፅዋት ማስከተል ማን የሰራው ሥርዐት ነው?
👉ተዉ እንጂ የሚያስቀድሰውን ሕዝብ አታሳቁት?
👉እኔ እነዚህን ፈጽሜ እቃወማለሁ።
ዘመልአክ ዳግም