የደብረ ኃይል ቅዱስ ሚካኤል ፍሬ ስብሀት ሰንበት ትምህርት ቤት ገፅ

  • Home
  • Ethiopia
  • Addis Ababa
  • የደብረ ኃይል ቅዱስ ሚካኤል ፍሬ ስብሀት ሰንበት ትምህርት ቤት ገፅ

የደብረ ኃይል ቅዱስ ሚካኤል ፍሬ ስብሀት ሰንበት ትምህርት ቤት ገፅ በምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት የለኩ ከታ ደብረ ኃይል ቅዱስ ሚካኤል ፍሬ ስብሐት ሰንበት ትምህርት ቤት

13/08/2025
ዘወረደ ትርጕሙ ‹ከሰማየ ሰማያት የወረደ› ማለት ነው፡፡ ከሰማየ ሰማያት የወረደውን፣ ከድንግል ማርያም የተወለደውን በጥንት ስሙ ወልድ፣ ቃል በኋላ ስሙ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ አማኑኤል የተባለውን...
19/02/2023

ዘወረደ
ትርጕሙ ‹ከሰማየ ሰማያት የወረደ› ማለት ነው፡፡ ከሰማየ ሰማያት የወረደውን፣ ከድንግል ማርያም የተወለደውን በጥንት ስሙ ወልድ፣ ቃል በኋላ ስሙ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ አማኑኤል የተባለውን ሰው የኾነውን አምላክ ለማመስገን ርደቱን (ከሰማየ ሰማያት መውረዱን) ለመዘከር የሚጾም ጾም ነው፡፡ ጌታችን ጾመ ከማለት አስቀድሞ ከሰማየ ሰማያት መውረዱን ከድንግል ማርያም መወለዱን መናገር አስፈላጊ ነውና የመጀመሪያው ሳምንት ‹ዘወረደ› ተብሏል፡፡ ‹‹አንተ በሰማይ ወአንተ በምድር ወአንተ በባሕር ወአንተ በየብስ፤ አንተ በሰማይ አለህ፤ በምድር በባሕርም በየብስም አለህ፤›› የተባለውን በሰማይ በምድር ምሉዕ የኾነውን አምላክ ‹ወረደ፤ መጣ› ብሎ መናገር ‹ሰው ኾነ› ማለት ነው፡፡ ሰው ኾኖ መገለጡን ለማስረዳት ነው እንጂ መውረድ መውጣት የሚባሉ ቃላት በዅሉ ምሉዕ ለኾነው መለኮት አይስማሙትም፡፡ ቃላቱ ሰውኛ አነጋገርን የሚያመለክቱ ናቸውና፡፡ መተርጕማን አበው ‹‹‹ዘወረደ› ማለት ‹ሰው የኾነ› ማለት ነው›› ብለው ይተረጕማሉ፡፡ አምላካችን ሰው ከኾነ በኋላ ‹መጣ፤ ሔደ፤ ወረደ፤ ዐረገ› የሚሉ ቃላት ይስማሙታል፡፡ ምልዓቱን ሳይለቅ በሰው አካል ተወስኖ ታይቷልና፡፡ ስለዚህ ‹ወረደ› እግዚአብሔር ሰው ኾኖ መገለጡን፤ ‹ዐረገ› ደግሞ የሰውነቱን ሥራ መፈጸሙን ያሳያል፡፡ ዐረገ ስንልም ቀድሞ በሰማይ የለም ለማለት አይደለም፤ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመለኮቱ በዓለሙ ዅሉ ምሉዕ ነውና፡፡
ጾሙን ሐዋርያት፣ ስያሜውንና የምስጋናውን ሥርዓት ቅዱስ ያሬድ አዘጋጅተዋል፡፡ ቅዱስ ያሬድ ነቢያትን በንባብ፤ ሐዋርያትን በስብከት፤ ሊቃውንትን በትርጓሜ፤ መላእክትን በዜማ ይመስላቸዋል፡፡ ቅዱስ ያሬድ የመላእክትን የምስጋና ሥርዓት ወደ ምድር አምጥቷል፡፡ የነቢያትን ትንቢት፣ የሐዋርያትን ትምህርት በሚገባ ተርጒሞ፣ አብራርቶ፣ አመሥጥሮ አዘጋጅቶታል፡፡ ሐዋርያት ጾሙን ጾመው የጾም ሕግ ደንግገዋል፤ ቅዱስ ያሬድም ለጾሙ ስያሜ ሰጥቶ ምስጋና ከነሥርዓቱ አዘጋጅቶ አቅርቧል፡፡ቤተ ክርስቲያናችንም የመጀመሪያው የዐቢይ ጾም ሳምንትን (ዘወረደን) ስያሜ እንደ ቅዱስ ያሬድ ከሐዋርያት ተቀብላ ታስተምራለች፡፡ ይህ የመጀመሪያው ሳምንት ‹ጾመ ሕርቃል› እየተባለም ይጠራል፡፡ ሕርቃል (ኤራቅሊዮስ) በ፮፻፲፬ ዓ.ም የነበረ የቤዛንታይን ንጉሥ ነው፡፡ ለክርስቲያኖች ባደረገው ርዳታ ምክንያት አንድ ሳምንት ጾመውለት ነበር፡፡ ያላወቁ ‹ጾመ ሕርቃል› ብለው አንድ ጊዜ ጾመው ትተውታል፡፡ ጥንቱን የቅዱሳን ሐዋርያት መኾኑን ያወቁ ምእመናን ግን ዅልጊዜ በየዓመቱ ይጾሙት ነበር፡፡ ዛሬም ድረስ ጾመ ሕርቃል እየተባለ ይጠራል፡፡ ሙሉ ታሪኩ በፍትሐ ነገሥት ትርጓሜ አንቀጽ ፲፭ ላይ ይገኛል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ፓትርያርክ የአቢይ ጾምን ምክንያት በማድረግ ያስተላለፉት መልዕክት ሙሉ ቃ...
17/02/2023

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ፓትርያርክ የአቢይ ጾምን ምክንያት በማድረግ ያስተላለፉት መልዕክት ሙሉ ቃል እነሆ፦

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፤

• በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገር የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ምእመናት እንዲሁም ኢትዮጵውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ!
እንደ ስሑትና ደካማ ሰብአዊ ባሕርያችን ሳይሆን እንደ አባታዊ ቸርነቱ ሁል ጊዜ በምሕረቱ የሚጐበኘን አምላካችን እግዚአብሔር እንኳን ለጾመ ኢየሱስ አደረሰን፤ አደረሳችሁ!
• “ንጹም ጾመ፣ ወናፍቅር ቢጸነ፣ እስመ ከማሁ አዘዘነ፡- ጾምን እንጹም፣ ባልንጀራችንንም እንውደድ፣ እንዲህ አዞናልና” (ቅዱስ ያሬድ)
እግዚአብሔር በዚህ ዓለም ስንኖር፣ እንድናደርገው ያዘዘን ዓቢይ ነገር ቢኖር ፍቅር ነው፡፡ እግዚአብሔር ፍጥረታትን ፈጥሮ እየመገበ የሚገኘው በፍቅር ነው፡፡ እኛንም ከፍዳ ኃጢአት ያዳነን በፍቅር ነው፡፡ ሕይወታችንና ንብረታችን ተጠብቆ የሚኖረው ፍቅር ሲኖር ነው፡፡

ግላዊና ማኅበራዊ ኑሮአችን እንዲሁም ሃይማኖታዊ አምልኮአችንና የተግባር እንቅስቃሴአችን በሙሉ ውጤታማ ሊሆን የሚችለው ፍቅር ሲኖር ነው፡፡
በፍቅር ውስጥ በረከት እንጂ ጉድለት የለም፤ በፍቅር ውስጥ ጤና እንጂ በሽታ የለም፤ በፍቅር ውስጥ ጽድቅ እንጂ ኃጢአት የለም፤ በፍቅር ውስጥ እግዚአብሔር እንጂ ዲያብሎስ የለም፡፡ ይህም በመሆኑ ቅዱስ መጸሐፍ ፍቅርን ‹‹የሁሉም ነገር ማሰሪያ ነች›› በማለት ይገልጻታል፡፡
ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከሁሉም የምትበልጠው ታላቋ ትእዛዝ ‹‹ፍቅር›› እንደሆነች ከመግለፁም በላይ ኦሪትና ነቢያት ሁሉ በእሷ እንደሚጠቃለሉ አስተምሮናል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
ፍቅርን እንደ ዓይን ብሌን ስንጠብቃት በእጅጉ የምትጠቅመንን ያህል ጣል ጣል ስናደርጋት ደግሞ በእጅጉ ትጎዳናለች፡፡ በፍቅር እጦት የሚደርሰው ጉዳት በተወሰነ ነገር ብቻ ሳይሆን በነፍስም ሆነ በሥጋ፣ በምድርም ሆነ በሰማይ እጅግ በጣም የገዘፈና የሰፋ ነው፡፡

በሀገራችን የሆነውና እየሆነ ያለውም ይኸው ነው፡፡ ፍቅርን ባጣንባቸው ዓመታት ከየት ወዴት እንደደረስን ሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚገነዘበው ነው፡፡ ያተረፍነው ነገርም ምን እንደሆነ የምናውቀው ነው፡፡

ይሁንና የፍቅር እጦት ምን ያህል እንደጎዳን ራሳችን ተገንዝበን ወደ ሰላሙ መንገድ መመለሳችን የተሻለ አማራጭ መሆኑን ሳንመሰክር አናልፍም፡፡ የተጀመረው የፍቅርና የሰላም ጉዞም ተጠናክሮ እንዲቀጥል ልባዊ ምኞታችንና ጸሎታችን ነው፡፡

ይህንን ሰላም እንዲመጣ ያደረጉ ወገኖችም ሁላቸውን ሳናመሰግን አናልፍም፡፡ ምክንያቱም በሰዎች መካከል ፍቅርንና ሰላምን የሚያደርጉ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉ ብሎ ጌታ እንደ አስተማረን ብፅዕና ይገባቸዋልና ነው፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
የፍጹም ፍቅር መገኛ የሆነው ቅዱስ ወንጌል የሚያስተምረው ፍቅር፣ ራስን ማፍቀር ወይም መውደድ ሳይሆን ራስን መጥላት ባልንጀራን ግን መውደድ ነው፡፡ ወንጌላዊ-ፍቅር ፍጹም ነው የሚያሰኘውም ቅሉ ይህ ነው፡፡

ለሁለት ሺሕ ዘመናት ያህል በቅዱስ ወንጌል አስተምህሮ ላይ የተገነባው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ባህልም ይህን ፍቅር ጠብቆ የሚጓዝ ነው፡፡
ይህም በመሆኑ የኢትዮጵያ አበው መነኮሳት ከነበራቸው ፍቅርና ትሕትና የተነሣ፣ የሹመት ሽሚያ አያውቁም ነበር፡፡ ከዚህ አንጻር ትልቁን ሥልጣን ይቅርና የአንድ ገዳም መሪ ለመሆንም በእግር ብረት ታስረው በግድ ካልሆነ በቀር እሺ ብለው በፈቃደኝነት ሹመትን አይቀበሉም ነበር፡፡
ራሱን በራሱ መሾም ወይም እኔን ሹሙኝ ብሎ መናገርና የሌላን ድጋፍ መጠየቅ ለኢትዮጵያውያን መነኮሳት ጭራሽ ነውርና ጸያፍም ነበር፡፡

ያም በመሆኑ ነው ከዘመነ ብሉይ ጀምሮ ለሦስት ሺሕ ዘመናት የዘለቀው ሃይማኖታችን ምንም ዓይነት መለያየት ሳያጋጥመው አንድ ሆኖ ሊዘልቅ የቻለው፡፡
ይህ የቤተ ክርስቲያናችን ጠንካራ አንድነት ለሕዝቡም በመትረፉ የሀገሪቱን አንድነትና ነጻነት አስጠብቆ እስከ ዘመናችን ሊደርስ ችሎአል፡፡ በዚህም ቤተ ክርስቲያናችን የሕዝብንና የሀገርን አንድነትና ነጻነት ለማስጠበቅ ያደረገችውና የምታደርገው ጥረት ሊያስመሰግናት እንጂ ሊያስወቅሳት አይገባም፡፡


የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት!
ከቅርብ ቀናት ወዲህ በቤተ ክርስቲያናችን ተከሥስቶ የነበረውን ሕጋዊ ያልሆነ ድርጊት የቤተ ክርስቲያናችንን ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና ባሕላዊ መርሕን የናደ፣ እንደዚሁም በኢትዮጵያ ይቅርና በዓለም ታሪክ ተደርጎ የማያውቅ ድርጊት እንደሆነ ቤተ ክርስቲያናችን በአጽንዖት ስትገልጽ ቆይታለች፡፡
ይህንን የቤተ ክርስቲያን ድምፅ በመስማትና በመቀበል ሕዝበ ክርስቲያንና ኢትዮጵያውያን ሁሉ ለእግዚአብሔር ባቀረቡት ኃዘንና ጸሎት እንደዚሁም ባደረጉት መጠነ ሰፊና ዙርያ መለስ የሆነ የድጋፍ ርብርብ ስሕተቱ ሊታረም ችሏል፡፡

ለተገኘው መንፈሳዊ ውጤትም ክቡር ጠቅላይ ሚንስትርና መንግሥታቸውን፣ የቤተ ክርስቲያን አንድነትና ሉዓላዊነት እንዲከበር ከፍተኛ መሥዋዕትነት ለከፈለው መላው ሕዝበ ክርስቲያን እንዲሁም ይህ ስሕተት እንዲታረም ከቤተ ክርስቲያናችን ጎን ተሰልፈው ድምፃቸውን ላሰሙ ኢትዮጵያውያንና የውጭ አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ በቤተ ክርስቲያናችን ስም ከፍ ያለ ምስጋና እናቀርብላቸዋለን፡፡
በዚህ አጋጣሚ ለሁሉም ኢትዮጵያውያን ልጆቻችን ግልፅ ማድረግ የምንፈልገው ከቤተ ክርስቲያናችን ዶግማ፣ ቀኖና እና ሥርዓት መከበር እንደዚሁም ከሉዓላዊ አንድነቷ መጠበቅ በመለስ ያለው ጥያቄ ለማስናገድ ቤተ ክርስቲያናችን ዝግጁ መሆኗን ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ሕዝቦች በቋንቋቸው የመማር፣ የማስተማርና የማምለክ እንዲሁም የመተዳደር መብትን ካሁን በፊትም፣ አሁንም፣ ካሁን በኋላም የምትነፍግበት መሠረት እንደሌለም ሁሉም ሊያውቀው ይገባል፡፡
ይህም በመሆኑ በቋንቋ የመጠቀም መብት በሕገ ቤተ ክርስቲያናችን ምዕራፍ 2 አንቀጽ 5 ከቁጥር 1-3 ባለው አንቀጽ በሚገባ ተቀምጦ ይገኛል፡፡ ስለሆነም በቋንቋ የመጠቀም ጥያቄ በሕግ ደረጃ ተመልሶ በተግባር እየተሰራበት የሚገኝ መሆኑን ሁሉም ሊገነዘበው ይገባል፡፡

የተወዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት፤
ዛሬ ታላቁን ጾማችን በፍቅር ሆነን የምንጾምበት ወቅት ነው፡፡ ሁላችንም እንደምናውቀው ጾም ማለት ስጋዊ ፈቃድን በመግታት ከእግዚአብሔር ጋር ጥብቅ ግንኙነት ለማድረግ የሚካሄድ መንፈሳዊ ተጋድሎ ነው፡፡
በጌታችን ጾም በተግባር እንዳየነው ጾም ማለት ዲያብሎስ የሚሸነፍበት በአንጻሩ ደግሞ የእግዚአብሔር ሕዝብ አሸናፊዎች የሚሆኑበት ኃይል ነው፡፡
ስለሆነም ጾም የተጋድሎና የሙዓት ሜዳ ነው ማለት ይቻላል፡፡ የምንታገለውም ልቡሰ ሥጋ ሰውን ሳይሆን ረቂቅ ፍጡር የሆነው ሰይጣን በሰው አድሮ የሚነዛውን አጥፊ ሐሳቡንና ድርጊቱን ነው፡፡

ከዚህም ጋር ሰውነታችን ለዚህ ክፉ መንፈስ ታዛዥ እንዲሆን የሚገፋፉ ጥሉላት መባልዕትን መተው፤ ኃይለ ሥጋን መቈጣጠር፤ ኃይለ መንፈስን ደግሞ ማጎልበት ያስፈልጋል፡፡ በጾም ወቅት የተራቡትን ማጉረስ የታረዙትን ማልበስ የተበደሉትን መካስ፣ ፍትሕና ርትዕ በማኅበረ ሰብ ውስጥ ማንገሥ ያስፈልጋል፡፡

በጾም ወቅት ኅሊናችን ማሰላሰል ያለበት ሰው ምን አለ? ወይም ምን አደረገ? በሚለው ሳይሆን እግዚአብሔር በፊቱ ምን ዓይነት ሰው እንድንሆንለት ይፈልጋል? በሚለው ላይ ነው፡፡

ስለዚህ ጾማችን በዚህ መንፈስ የተቃኘ ፍቅረ፣ እግዚአብሔርንና ፍቅረ ቢጽን ማእከል ያደረገ፣ መጠራጠርንና አለመተመማንን ያስቀረ፣ የተለያዩትን ያቀራረበ፣ የተሳሳቱትን ያረመ በአንጻሩ ደግሞ ሁላችንን በሰላምና በፍቅር አንድ አድርጎ ያስተሳሰረ ይሆን ዘንድ በዚህ መንፈስ ተነቃቅተን እንድንጾመው አባታዊ ጥሪያችንን ለሕዝበ ክርስቲያኑ እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም፤
በሀገራችን እየታየ ያለው የሰላም ጭላንጭልና ችግሮችን በውይይት የመፍታት ዝንባሌ በእጅጉ ጠቃሚና ለሁለንተና ልማታችንና ለዕድገታችን እንደዚሁም ለተሟላ አንድነታችን ጠቃሚነቱ የጎላ ስለሆነ እግዚአብሔር ለዘለቄታው እንዲያሳካልን ከልብ እንድናዝንና ወደ አምላካችን በተመሥጦ እንድንጸልይ በአጽንዖት በማሳሰብ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡
መልካም የጾም ወራት ያድርግልን!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር! አሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስምወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
የካቲት ፲፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

11/02/2023

የካቲት 5 በነገው እለትም ሕዝበ ክርስቲያኑ ሁለም በየአጥቢያችሁ
በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ዓውደ ምሕረት ላይ ባለመቅረት
የተለመደውን የእለተ ሰንበት የሥርዓተ ቅዳሴ፤ የጸሎት፣
የምሕላ እና የትምህርተ ወንጌል ከወትሮው በተለየ የመንፈሳዊ
ሥርዓት በማከናወን እንድታሳልፉ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜንከኢትዮጵያ ኦርቶደክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ አዋጅበመንፈስ ቅዱስ የሚመራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክር...
04/02/2023

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
ከኢትዮጵያ ኦርቶደክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ አዋጅ
በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በጥር 18 ቀን 2015 ዓ.ም ባደረው አስቸኳይ ምልዐተ ጉባኤ በኢትዮጵያ የኦሮሚያ እና የብሔር ብሔረሰቦች ቅዱስ ሲኖዶስ በሚል በሕገ ወጥነት በቀድሞ ስማቸው አባ ሳዊሮስ የተባሉ ግለሰብ መሪነት ይህ መግለጫ እስከተሰጠበት ቀን ድረስ በተለያዩ ክልሎች እና የፌዴራል መንግሥት በሚመራቸው ቦታዎች ውስጥ በሚገኙ የቤተ ክርስቲያኗ አህጉረ ስብከት የሆኑትን ሥርዓተ አምልኮዋን የምትፈጽምባቸው በየመዋቅሩ የሚገኙ አስተዳደር ቢሮዎችን ከሕግ አግባብ ውጭ የቤተ ክርስቲያኗ እምነት ተከታይ ያልሆኑ ግለሰቦችን በማካተት በመንግሥት ልዩ ኃይል ድጋፍ በመውረር እና በመስበር የሕግ አግባብነት በሌላቸው እንዲሁም መብት እና ጥቅም ሳይኖራቸው በማሸግ ቤተ ክርስቲያን ላይ ወረራ እየተፈጸመባት የሚገኝ መሆኑን ቅዱስ ሲኖዶስ ለመረዳት ችሏል፡፡
መንግሥትም ሰላም እና ደህንነትን ከማስጠበቅ ባለፈ የሕይወት እና የአካል ደህንነት መብትን እንዲሁም የመንቀሳቀስ መብትን በመገደብ ያለአግባብ ታግተው መቆየታቸውን ከሊቃነ ጳጳሳት ውስጥ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስን ከዚህ ቀደም መግለጻችን የሚታወቅ ሲሆን ከዚህ ድርጊታቸውም ሳይታቀቡ በጥር 26 ቀን 2015 ዓ.ም ከምሽቱ 3፡30 አካባቢ የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሆኑትን ብጹዕ አቡነ ያሬድን በሕገ ወጥ መልኩ የዜግነት መብታቸው ተጥሶ በደረቅ ሌሊት በማሰር እና በማዋከብ ከሀገረ ስብከታቸው ለቀው እንዲወጡ የተደረጉ ሲሆን እንዲሁም የተለያዩ አህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳትን ወደየ አህጉረ ስብከታቸው እንዳይሄዱ ማስፈራሪያ በመላክ የቤተ ክርስቲያችንን ክብር እና ልዕልና እጅጉን የሚጎዳ እና አሳዛኝ ድርጊት እየተፈጸመባት ይገኛል፡፡ በተጨማሪም የየሀገረ ስብከት ሥራ አኪያጆችንና ሠራተኞችን፤ አገልጋይ ካህናትንና ምእመናን በሕገ ወጥ መልኩ በማሰር እንደ መንግሥት የሚጠበቅበትን ኃላፊነት ባለመወጣቱ ቤተ ክርስቲያናችን እጅጉን አዝናለች፡፡
ከዚህም አልፎ መንግሥትም በቤተ ክርስቲያችን በኩል በተደጋጋሚ የተሰጠውን ማሳሰቢያ ችላ በማለቱ ምክንያት በምዕራብ አርሲ ሀገረ ስብከት በሻሸመኔ ከተማ ሕገ ወጦቹ መንግሥትን ተገን በማድረግ የቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደብረ ስብሐት ቅዱስ ሚካኤል አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በሕገ ወጥ መልኩ ወረራ ለመፈጸም ባደረጉት እንቅስቃሴ ቤተ ክርስቲያንችንን ለመጠበቅ በወጡ ምእመናን ላይ ፖሊስ በወሰደው እርምጃ ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ የአደባባይ የግድያ ወንጀል ተፈጽሟል፡፡ ሌሎች በቁጥር ያልታወቁ ምእመናንም ላይ ከፍተኛ እና ቀላል የአካል ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡
ይህንንም ሕገ ወጥ ተግባር በተመለከተ ተገቢውን ሕጋዊ የሰላም እና የደህንነት ከለላ እንዲያደርጉ ለሚመለከታቸው የፌዴራል እና የክልል መንግሥታት በተደጋጋሚ ማሳሰቢያ ቤተ ክርስቲያናችን ብትሰጥም ይህንን ማሳሰቢያ ወደጎን በመተው መንግሥት ሕገ ወጡን ቡድን በመደገፍ እና በማስፈጸም ከላይ የተገለጹትን አሳዛኝ ድርጊቶች በይፋ በአደባባይ ፈጽሟል፡፡
ስለሆነም የኢትዮጵያ ኦርቶደክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በጠራው አስቸኳይ ጉባዔ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አስተላልፏል፡፡
1. በብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት እና የአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፤ የክፍል ኃላፊዎች፤ ካህናት፤ አገልጋዮች እና ምእመናን ላይ የተፈጸመውንና እና እየተፈጸመ ያለውን ሕገ ወጥ እስር እና ወከባ ቅዱስ ሲኖዶስ በፅኑ አውግዟል፤
2. በጥር 27 ቀን 2015 ዓ.ም በምዕራብ አርሲ ሀገረ ስብከት በሻሸመኔ ከተማ በደብረ ስብሐት ቅዱስ ሚካኤል አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን፤ ቤተ ክርስቲያንን ለመጠበቅ የወጡት ምዕመናን ላይ ጭካኔ በተሞላ ሁኔታ የተፈጸመው ሕገ ወጥ የሰብዓዊ መብት ጥሰት እና የተፈጸመው አሰቃቂ የሞት ድርጊትን ፍጹም ታወግዛለች፤ ተገቢውን ሲኖዶሳዊ እና ሃይማኖታዊ ጸሎት በማድረግ በሁሉም አጥቢያ ሥርዓተ ፍትሐት እንዲፈጸም ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤
3. ቅዱስ ሲኖዶስ በጥር 26 ቀን 2015 ዓ.ም ባስተላለፈው ውሳኔ እና በሰጠው መግለጫ መላው የቤተ ክርስቲያኒቱ ተከታዮች ጾመ ነነዌን ሙሉ የሱባዔ ጊዜ በማድረግ ጥቁር ልብስ ያለውን ትርጓሜ በመግለጥ እንድንሰነብት መግለጫ መሰጠቱ ይታወሳል፡፡
3.1. ለዚህም ዝርዝር አፈጻጸም መመሪያ ማውጣት አስፈላጊ ሆኖ በመገኘቱ ከጥር 29 ቀን 2015 ዓ.ም ጀምሮ ባሉት 3 ቀናት በመላው ዓለም የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ የምትገኙ ማናቸውም ካህናት እና ምዕመናን ሙሉ ጥቁር ልብስ በመልበስ በየአብያተ ክርስቲያናት እና በገዳማት ያለውን ሥርዓተ ጸሎት እንድትመሩ እና እንድትከታተሉ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤
3.2. በየትኛውም እንቅስቃሴ ይህንን ጥቁር ልብስ በመልበስ የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ንቁ በመሆን እንድትፈጽሙ፤ ሆኖም ግን ቅዱስ ሲኖዶስ ይህንን ዓለም አቀፍ የጸሎትና የምህላ መርሐ ግብር ካወጀበት ቀን በኃላ በተለያዩ ከተሞች የጥቁር ልብስን ሆነ ተብሎ ከገበያ እንዲወጣ እየተደረገ መሆኑን በመረዳታችን ምዕመናን ያላችሁን ተመሳሳይ አልባሳት በመጠቀም የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔን በእንቅስቃሴያችሁ ሁሉ እንድትፈጽሙ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤
3.3. በነዚህ ቀናት ውስጥ አገልግሎቱ በድምጽ ማጉያ እንዲከናወን እና የሙሉ ጊዜ ሆኖ በሰባቱ የጸሎት ሰዓታት እየተጠበቀ በተመሳሳይ ሰዓታት ለአምስት ደቂቃ ያህል በማያቋርጥ ደወል በመደወል የማስተጋባት ሥራ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤
3.4. ይህንንም የየአህጉረ ስብከት፤ የወረዳ ቤተ ክህነት እና የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ሰበካ ጉባኤያት በመከታተል እንድታስፈጽሙ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
3.5. የአኃት አብያተ ክርስቲያናት፤ የኦርቶዶክስ ዓለም፤ እውነቱን የምታውቁና የምትደግፉ ማናቸውም ኃይማኖታዊም ሆነ ማህበራዊ ተቋማት እና ግለሰቦች የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ጥሪ በመደገፍ በአንድነት ትቆሙ ዘንድ ጥሪያችንን እናስተላፋለን፡፡
4. በነዚህ የጸሎትና የምሕላ ጊዜያት የደነደኑ ልቦች ወደ ልቦናቸው ተመልሰው የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥሪ ሰምተው የማይፈጽሙ እንደሆነ
4.1. በየካቲት 5 ቀን 2015 ዓ.ም በሀገር ውስጥ እና ከሀገር ውጭ የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ካህናት እና ምእመናን ከጠዋቱ 11፡00 ጀምሮ በየአጥብያቸው በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት እስከ ጠዋቱ 1፡30 ድረስ ሥርዓተ ቅዳሴው ከተፈጸመ በኃላ ከጠዋቱ 2፡00 ላይ ሁሉም ገዳማት፣ አድባራት እና አብያተ ክርስቲያናት በተመሳሳይ ሰዓት ደወል በመደወል ምእመናን በሙሉ እስከ ጠዋቱ 2፡30 ድረስ እንዲሰባሰቡ በማድረግ ከየአጥቢያው በመነሳት የጥምቀተ ባህር ወይም የመስቀል አደባባይ ላይ ታቦተ ሕጉን በማክበር፤ በማጀብ በዝማሬ እና በእልልታ በአንድ ቦታ በመሰባሰብ ሰላማዊ ሰልፍ እንዲደረግ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡
4.2. የዚህ ሰላማዊ ሰልፍ ዝርዝር አፈጻጸም መመሪያን በተመለከተ በአጭር ጊዜ ውስጥ የምናሳውቃችሁ መሆኑን አውቃችሁ ዝግጅት እንድታደርጉ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡
5. ማንኛውም የመንግሥት የጸጥታ ኃይል ቤተ ክርስቲያን ያዘዘችውን ሰላማዊ ጥያቄ በሚከወንበት ማንኛውም የአገልግሎት ጊዜ ተግባራቱ ሰላማዊ መሆናቸውን በመገንዘብ ተገቢውን ጥበቃ የማድረግ ግዴታ እንዳለበት አውቆ እንዲያስፈጽም ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፤

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ
ጥር 27 ቀን 2015 ዓ.ም
አዲስ አበባ
ኢትዮጵያ

Address

Addis Ababa

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when የደብረ ኃይል ቅዱስ ሚካኤል ፍሬ ስብሀት ሰንበት ትምህርት ቤት ገፅ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Place Of Worship

Send a message to የደብረ ኃይል ቅዱስ ሚካኤል ፍሬ ስብሀት ሰንበት ትምህርት ቤት ገፅ:

Share