14/07/2026
"ቤተክርስቲያን የሌላቸው የቤተክርስቲያን አቃቤ እምነቶች"
(Churchless Apologists)
በአሁኑ ዘመን በክርስቲያኑ ዓለም ውስጥ እያደገ የመጣ አንድ ትልቅ ትዝብት አለ፤ እርሱም ስለ ክርስትና እውነትነት በአደባባይና በማህበራዊ ሚዲያ የሚሟገቱ፣ ነገር ግን ራሳቸው ከተጨባጩ የቤተክርስቲያን ኅብረትና ሥርዓት ውጪ የሆኑ ወገኖች ጉዳይ ነው።
"ብልት ያለ አካል" አይኖርም ፦ ሐዋርያው ጳውሎስ ቤተክርስቲያንን ከአካል ጋር ያነጻጽራታል ።
ዐይን ወይም እጅ ብቻውን ሊኖር እንደማይችል ሁሉ ፣ አማኝም ምንም ያህል እውቀት ቢኖረው ከአካሉ (ከቤተክርስቲያን) ተለይቶ ሕያው ሊሆን አይችልም (፩ኛ ቆሮ. ፲፪፥፲፬-፳፯) ።
ቤተክርስቲያን "የእውነት ዓምድና መሠረት" ናት (፩ኛ ጢሞ. ፫፥፲፭ ) ።
ራስን ከዚህ ዓምድ አውጥቶ እውነትን ለመከላከል መሞከር መሠረተ-ቢስ መሆን ነው ።
የጥንት አባቶች ለእውነት ሙግት ትልቅ ቦታ ቢሰጡም፣ ከቤተክርስቲያን ውጪ የሚደረግን ሩጫ ግን ፈጽሞ አይቀበሉትም ነበር ።
ሰማዕቱ ቅዱስ ቆጵሪያኖሱ (Cyprian of Cahtrage ) ፦ "ቤተክርስቲያንን እናቱ ያላደረገ፣ እግዚአብሔርን አባቱ ሊያደርግ አይችልም።"
ቅዱስ አውግስጢኖስ (St Augustine of Hippo) ፦ በሰዎች ድክመት ምክንያት ሰበብ ፈጥሮ ከጉባኤ መውጣትና በውጪ ሆኖ መሟገት መንፈሳዊ ዕውርነት ነው ።
ጆን ካልቪን (John Calvin ) ፦ ለእግዚአብሔር ልጆች ሁሉ ቤተክርስቲያን "እናት" መሆኗንና ከእሷ ጉባኤ መለየት እጅግ አደገኛ ነው ።
የአውግስበርግ መግለጫ (1530) ፦ እውነተኛ ቤተክርስቲያን ወንጌል በንጽሕና የሚሰበክባትና ቅዱሳት ምስጢራት (Sacraments) በአግባቡ የሚታደሉባት ስፍራ ናት ።
ከዚህ ውጪ "የክርስቲያን ኑሮ" የለም።
💭 የእኔ ትዝብት ፦ "የቤትን ችግር እየተከላከሉ በሜዳ ላይ ማደር የብስለት ችግር ነው "
ቤተክርስቲያን የሌለው አቃቤ እምነት መሆን፣ ስለ አንድ ቤት ጥንካሬ በጽኑ እየተከራከሩ ፣ ራስ ግን በሜዳ ላይ በብርድ ከመቀመጥ ጋር ይመሳሰላል ።
በማህበራዊ ሚዲያ ተከታይ ማፍራት ለአጥቢያ እረኞች የመገዛትን አስፈላጊነት አሳጥቶታል ።
ክርስትናን ከተግባራዊ የፍቅር ሕይወት ይልቅ ወደ ፍልስፍናዊ ሙግት ብቻ ማሳነስ ።
በአጥቢያ ውስጥ ካሉ "ደካማ" ወንድሞች ጋር መኖር ትሕትናን ይጠይቃልና ።
አቃቤ እምነትነት (Apologetics) የሚጀምረውና የሚጠናቀቀው በቤተክርስቲያን ውስጥ ነው ።
እውነተኛ አቃቤ እምነትነት በቃላት ጥበብ መርታት ብቻ ሳይሆን ፣ ክርስቶስ በደሙ በዋጃትና ድክመት ባለባት የአጥቢያ ቤተክርስቲያን ውስጥ ፍቅርን በተግባር በመኖር የሚገለጥ ሕይወት ነው ።
ለሌሎችም እንዲደርስ ሼር (Share) ያድርጉት !