ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ- Holy Trinity University

ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ- Holy Trinity University ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ- Holy Trinity University

የሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ልዑካን ቅድስት ሥላሴ  ዩኒቨርሲቲን ጎበኙየሞስኮ ፓትርያርክ የውጭ አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት መምሪያ ሊቀ መንበር፥ የቮሎኮላምስኩ ሜትሮፖሊታን ብፁዕ አቡ...
06/06/2026

የሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ልዑካን ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲን ጎበኙ

የሞስኮ ፓትርያርክ የውጭ አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት መምሪያ ሊቀ መንበር፥ የቮሎኮላምስኩ ሜትሮፖሊታን ብፁዕ አቡነ አንቶኒ የሚመሩት ልዑካን ቡድን ትናንት ግንቦት ፳፰ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲን ጎብኝተዋል።

በልዑካን ቡድኑ ውስጥ የሊቀ መንበሩ ረዳት ሂሮሞንክ (አባ) እስጢፋኖስ (ኢጉምኖቭ) እና ካህን አሌክሳንደር ኤርሾቭ ተካተዋል።

ልዑካኑ በዩኒቨርሲቲው ቆይታቸው፥ ከዩኒቨርሲቲው ፕሬዚደንት እና ከደቡብ ኦሞና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስና ልዑካቸው ጋር ፍሬያማ ውይይት ያደረጉ ሲሆን፥ በዩኒቨርሲቲው አዳራሽም ከተማሪዎች ጋር ተጨማሪ ውይይት አድርገዋል። በውይይቱ ወቅት በሩሲያ በሚገኙ የነገረ መለኮት ት/ቤቶች አሠራር እና ትምህርታዊ አሰጣጥ ዙሪያ ሰፊ ማብራሪያ ሰጥተዋል።

በተጨማሪም ብፁዕ ሜትሮፖሊታን አንቶኒ እና አባሎቻቸው፥ ከዩኒቨርሲቲው ሓላፊዎችና ከተማሪዎች ለቀረቡላቸው የተለያዩ ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት በሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት መካከል ስላለው ግንኙነትና ስለ ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ማብራሪያ ሰጥተዋል።

የዚህ ጉብኝት ዋነኛ ዓላማ በሁለቱ ሀገራት የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያለውን የነገረ መለኮት ትምህርት እና የወንድማማችነት ግንኙነት ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ እንደሆነ ተመላክቷል።

በመጨረሻም ከሁለቱም አብያተ ክርስቲያናት የተወከሉት ልዑካን የተለያዩ ሥጦታዎችን አበርክተዋል።

የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ሕዝብ ግንኙነት

የራሺያ ቤተክርስቲያን ልኡካን በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጉብኝት አደረጉ። ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ምልኡካኑ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳ...
03/06/2026

የራሺያ ቤተክርስቲያን ልኡካን በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ጉብኝት አደረጉ።
ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም

ልኡካኑ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት እና ከብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ፣ የራያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እንዲሁም ከብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ጋር ሰፊ ውይይት አድርገዋል ።
ከልኡካኑ መካከል የሞስኮ ፓትርያርክ የውጭ አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት መምሪያ ሊቀመንበር የሆኑት የቮሎኮላምስክ ሜትሮፖሊታን አንቶኒ የራሺያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጋር ያላትን መንፈሳዊ አና ታሪካዊ ግንኙነት አንስተው በቀጣይም የጋራ ሥራዎች እንዳሏቸው ገልጸዋል ።
አያይዘውም በሩሲያ የቲዎሎጂ አካዳሚዎች ከፍተኛ ትምህርታቸውን ለመከታተል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አባቶች ወደ ራሺያ ማቅናታቸው በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን ግንኙነት ለማጠናከር መቻሉን ገልጸዋል።

ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ፣የደቡብ ኦሞ እና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በበኩላቸው የራሺያ ቤተክርስቲያን እና የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ያለፋበት መንገድ ተመሣሣይነት ያለው መሆኑን አንስተው በበርካታ ጉዳዮች ላይ በጋራ ለመሥራት መወያየታቸውን ተናግረዋል ።
©EOTC TV

🇪🇹🇷🇺 President Taye Atske Selassie Receives Russian Orthodox Delegation in Ecclesiastical and Bilateral TalksAddis Ababa...
03/06/2026

🇪🇹🇷🇺 President Taye Atske Selassie Receives Russian Orthodox Delegation in Ecclesiastical and Bilateral Talks

Addis Ababa, June 3, 2026 (FMC) — President Taye Atske Selassie on Tuesday received Metropolitan Anthony of Volokolamsk, Chairman of the Department for External Church Relations of the Moscow Patriarchate of the Russian Orthodox Church, at the National Palace in Addis Ababa.

During the meeting, Metropolitan Anthony congratulated Ethiopia on the successful conduct of its recent general election, describing the process as peaceful, free, and stable.

He underscored the deep historical and spiritual links between Ethiopia and Russia, noting that relations between the two countries are rooted in their shared Christian heritage. He also highlighted long-standing educational and ecclesiastical exchanges, including the training of Ethiopian clergy and students at Russian Orthodox theological institutions over several decades.

Metropolitan Anthony expressed confidence that cooperation between the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church and the Russian Orthodox Church would continue to strengthen broader relations between the two countries.

The delegation leader also noted that the visit was undertaken with the blessing of Patriarch Kirill of Moscow and All Rus’ and at the invitation of the Holy Synod of the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church.

For his part, the President underscored the longstanding historical relationship between Ethiopia and Russia and reaffirmed Ethiopia’s commitment to further strengthening cooperation across various fields.

The two sides exchanged views on issues of mutual interest and emphasized the importance of deepening ecclesiastical engagement between the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church and the Russian Orthodox Church, alongside broader bilateral cooperation between Ethiopia and Russia.

Earlier in the day, Metropolitan Anthony arrived in Addis Ababa, where he visited Holy Trinity Cathedral and was received by senior clergy, including Archbishop Philippos of Southern Omo, Co-Chair of the Commission for Dialogue between the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church and the Russian Orthodox Church, as well as representatives of the Ethiopian Patriarchate.

During his three-day visit, he is expected to hold further meetings with Patriarch Abune Mathias, members of the Holy Synod of the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church, government officials, and members of the Russian community in Ethiopia.

©FBC

የኀዘን መግለጫ"እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤ የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ” (ራእይ ፪፥፲) በአርሲ ሀገረ ስብከት በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች በክርስቶስ ...
03/06/2026

የኀዘን መግለጫ

"እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤ የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ” (ራእይ ፪፥፲)

በአርሲ ሀገረ ስብከት በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች በክርስቶስ ክቡር ደም በተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ላይ በደረሰው አስከፊ ጥቃት፣ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን በግፍ በተሠዉበት እና አብያተ ክርስቲያናት በወደሙበት አሳዛኝ ክስተት በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ እና በደቡብ ኦሞና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ስም የተሰማንን እጅግ መሪር ኀዘን እንገልጻለን።

የሰው ልጅ በእግዚአብሔር አርአያ የተፈጠረ፣ ክብሩም ከሁሉ በላይ የሆነ ነው። በአርሲ ምድር የተፈጸመው ግፍ፣ የሰብአዊነትን ክብር የተጋፋና የሰላምን ተስፋ ያጨለመ ነው። ነገር ግን እኛ ክርስቲያኖች በመከራ ውስጥ እንኳን ተስፋ የምንቆርጥ አይደለንም። መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስተምረን፣ ፈተናው የቱንም ያህል ቢከብድ ለጽድቅና ለእምነት የሚከፈለው ዋጋ በሰማይ የሚያሰጠው ክብር ታላቅ ነው።

የዛሬው ኀዘናችን የነገው የትንሣኤያችን መሠረት ነው። በግፍ የተሠዉ ወገኖቻችን እንደ መጀመሪያዎቹ ሰማዕታት የሕይወትን አክሊል እንደሚቀዳጁ ሙሉ እምነታችን ነው። በዚህ አስቸጋሪ ወቅት፣ ቤተ ክርስቲያናችን ለዘመናት ጸንታ የቆየችው በደም ሳይሆን በምሕረት፣ በክፋት ሳይሆን በይቅርታ መሆኑን አምነን፣ ምእመናን በዚህ ፈተና ውስጥ እንደ አለት የጸና እምነት እንዲኖራቸው አጥብቀን እናሳስባለን።

የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ማኅበረሰብ እና የደቡብ ኦሞና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት በዚህ የፈተና ወቅት ከተጎዱ ወገኖች፣ ከቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን ጎን በመቆም፣ የጸሎትና የሞራል ድጋፋቸውን ያደርጋሉ። በኃይል የሚመጣ ጥቃት ጊዜያዊ ነው፤ የእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ግን እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ጸንታ ትኖራለች።

አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ለተጎዱት ቤተሰቦች መጽናናትን ይስጥልን፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይጠብቅልን።

ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ
የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት፣ የደቡብ ኦሞና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡፡ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫየእግዚአብሔር ሕዝብ ጉባኤ፣ የጌታችንና የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክ...
14/05/2026

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፡፡

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

የእግዚአብሔር ሕዝብ ጉባኤ፣ የጌታችንና የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አካልና የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ የሆነችው ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ሲኖዶሳዊ በመሆኗ አበው ቅዱሳን በፍትሕ መንፈሳዊና በጉባኤ አድያም ዘአንጾኪያ “ወይኩን ሲኖዶስ ዘጳጳሳት ፪ተ ጊዜያተ በበዓመት - የጳጳሳት ጉባኤም በዓመት ሁለት ጊዜ ይሁን” ብለው በደነገጉት ቀኖና መሠረት፤ በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የሚመራው፣ የሐዋርያት መንበር ወራሽ የሆነው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የርክበ ካህናት ምልዓተ ጉባኤውን በኅብረተ መንፈስ ቅዱስ ከሚያዝያ 28 እስከ ግንቦት 6 ቀን 2018 ዓ/ም ድረስ አካሄዷል፡፡

ምልዓተ ጉባኤው ስለ ሀገር ሰላም፣ ስለ ቤተ ክርስቲያን አንድነት፤ ስለ ሰው ልጅ ሁሉ ደኅንነትና ክብር፣ በአጠቃላይ ወቅታዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ሰፊ ውይይቶችን በማድረግ ዘመኑን የዋጁ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡ ከውሳኔዎቹም መካከል፡-

የቤተ ክርስቲያናችንን አንድነት መጠበቅና ማስጠበቅ የቅዱስ ሲኖዶስ ተግባር በመሆኑ ጥንታዊትና ሐዋርያዊት የሆነችውን ቤተ ክርስቲያን በአንድነቷና በሉዓላዊነቷ እንደተረከብናት ለወደፊቱም ሉዓላዊ ክብሯ ተጠብቆ እንድትቀጥል በምልዓተ ጉባኤው የተሠየመው በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የሚመራው “የሀገራዊ ሰላምና የቤተ ክርስቲያን አንድነት” ኮሚቴ ሥራውን አጠናክሮ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

ሰባተኛው ሀገራዊ ምርጫ ፍጹም ሰላማዊ ሆኖ በተረጋጋ መንገድ እንዲካሄድ፣ ለሀገር ሰላምና ለሕዝብ አንድነት በሚጠቅም ሁኔታ እንዲጠናቀቅ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምትጸልይ ሲሆን ምርጫው በሁሉም ወገን ለኢትዮጵውያን ዘላቂ ሰላምንና መረጋጋትን የሚያስገኝ ሆኖ እንዲፈጸም ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት ያሳስባል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የአርሲ ሀገረ ስብከትን በሊቀ ጵጵስና በቋሚነት እንዲመሩ፣ ሕዝቡን እንዲያጽናኑ እየደረሰ ያለውን ችግር ከቋሚ ሲኖዶስና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከሚመራው የሰላም ኮሚቴ ጋር በመሆን የሚመለከተውን የመንግሥት አካል በማነጋገር ዘላቂ መፍትሔ እንዲያፈላልጉ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ወስኗል፡፡

ከጥንት ጀምሮ “ቅዱስ ሲኖዶስ” በሚል ርእስ እየተዘጋጀ ይታተም የነበረው ታሪካዊ መጽሔት የቅዱስ ሲኖዶስ ቀኖናዊ ውሳኔዎችን በማካተት በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት አስፈጻሚነት ሕትመቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

የቤተ ክርስቲያናችንን ደንቦች መመሪያዎች መርምሮ ማጽደቅ የቅዱስ ሲኖዶስ ሉዓላዊ ሥልጣን በመሆኑ፡-

የስብከተ ወንጌል ሐዋርያዊ ተልእኮ ማስፈጸሚያ ደንብ በብፁዕ አቡነ ማርቆስ ሰብሳቢነት

የአንድነት ገዳማት ኅብረት መተዳደሪያ ደንብ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስና ብፁዕ አቡነ ማርቆስ ባሉበት በድጋሚ እንዲታይና ሌሎቹም ለውሳኔ የቀረቡ ደንቦች በሊቃውንትና በሕግ ባለሙያዎች ታርመው ለጥቅምት 2019 ዓ/ም ምልዓተ ጉባኤ እንዲቀርቡ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል

የቀድሞው የሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ “የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ”ና “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ” በሚሉ አርእስት አዘጋጅተው ያሳተሟቸው መጻሕፍትን የማሳተምና የማሰራጨት የባለቤትነት መብት ከሚያዝያ 29 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ለዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም እንዲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

ከተለያዩ አህጉረ ስብከት በቀረቡ ጥናቶችና የማጣራት ውጤቶች መሠረት፡-

የደቡብ ሱዳን ሀገረ ስብከት ከምሥራቅ አፍሪካ ሀገረ ስብከት ጋር ተደርቦ በብፁዕ አቡነ ማቴዎስ ሊቀ ጳጳስ እንዲመራ፤
ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል ሊቀ ጳጳስ የጋምቤላንና የቤንሻንጉል ጉምዝ አህጉረ ስብከትን ብቻ እንዲመሩ፤
ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጰስ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከትን እንደያዙ እንዲቀጥሉ፤
ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም የቡኖ በደሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቄለም ወለጋ ሀገረ ስብከትን ደርበው በአባትነት እንዲመሩ፣
የኮንታ ዞን ሀገረ ስብከት እንዲሆን የቀረበው ጥያቄ የጸደቀ በመሆኑ ሀገረ ስብከቱ ራሱን ችሎ እንዲደራጅና በብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ሊቀ ጳጳስ እንዲመራ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤
የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የልማት ተግባራትን ምልዓተ ጉባኤው በከፍተኛ ደረጃ በማድነቅ፣ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የመ/ፓ/ጠ/ቤ/ክ/ ዋና ሥራ አስኪያጅ የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ሲቲ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ በአባታዊ አመራር የፈጸሙት አስደናቂ የሥራ አፈጻጸም በጉልህ የሚታይ ለውጥ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የሚጠቅም፣ ሉዓላዊ ክብሯን የሚያስጠበቅ፣ ለሁሉም አበው ምሳሌነት ያለው በመሆኑ ምልዓተ ጉባኤው እጅግ ከፍ ባለ ክብር አመስግኗል፡፡

በዚህም መሠረት በብፁዕ ጠቅላይ ዋና ሥራ አስኪያጁ አባታዊ መሪነት እየተከናወኑ ያሉት ተግባራት ማለትም፡-

የቤተ ክርስቲያንን ቀደምት ሠነዶች በዲጂታል ቴክኖሎጅ እንዲደራጁ የተደረገበት ሥልት ተጠናክሮ እንዲቀጥል፤

ከ1970 ዓ/ም ጀምሮ በመጋዝን ተከማችተው የቆዩ በርካታ ልዩ ልዩ መጻሕፍትን የማሠራጨት ሂደት በተጀመረው መንገድ እንዲጠናቀቅ፤

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የኢንፎርሜሽንና ኮምኒኬሽን ተጠቃሚ እንድትሆን የተጀመረው ዘመኑን የዋጀ ቴክኖሎጂ በሁሉም የቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር በየደረጃው ተጠናክሮ ተግባራዊ እንዲሆን፤

በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥር የተጀመሩ የሕንፃ ግንባታዎችና አጠቃላይ የልማት ሥራዎች በተያዘላቸው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ተጠናቀው ለአገልግሎት እንዲበቁ ሁሉም አህጉረ ስብከትና ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን አስተዋጽኦና ትብብር እንዲያደርጉ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንዖት ያሳስባል፡፡

በሰሜን አሜሪካ የሰሜን ካሊፎርኒያ፣ ኔቫዳና አሪዞና ሀገረ ስብከት ኆኅተ ሰማይ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስና ቅድስት አርሴማ ገዳም የመንፈሳዊ ኮሌጅ፣ የአብነት ት/ቤት ሥርዓተ ትምህርት የቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖና፣ ታሪክና ትውፊት በጠበቀ መልኩ ተጠናክሮ መዋቅራዊ ተጠሪነቱም በአግባቡ ተጠብቆ ሥራ ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ያቀረበውን የ2019 ዓ/ም በጀት በማጽደቅ በተገቢው መንገድ ሥራ ላይ እንዲውል ምልዓተ ጉባኤው ወስኗል፡፡

በመጨረሻም ቅዱስ ሲኖዶስ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት በተነጋገረባቸው ጉዳዮች በትኩረት የተወያየው የቤተ ክርስቲያናችንን ሁለንተናዊ ዕድገትና ተቋማዊ ሕልውና ስለማስጠበቅ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ሀገራችንን ጨምሮ በመላው ዓለም እየታየ ያለው ግጭትና የሰላም መታጣት በእጅጉ አሳስቦታል፡፡

በመሆኑም ስለ ዓለምና ስለ ሀገራችን ሰላም፣ ስለ ሰው ልጆች ደኅንነት፣ በየቦታው በሃማኖታቸው ምክንያት መከራ የሚደርስባቸውን በየቦታው የሚገኙና ግጭት ባለባቸው ቦታዎች ያሉ ኦርቶዶክሳውያንን በማሰብ በመጪው የ2018 ዓ/ም ጾመ ሐዋርያት በመላው ዓለም ባሉ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት፣ አድባራትና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ጸሎተ ምሕላ እንዲደርስ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በመላው ዓለም፣ በደቡብ አፍሪካና በሳውዲ ዐረቢያ የሚኖሩ ዜጎቻችን ሰብዓዊ መብት እንዲከበር፣ የርኅራኄ ምሕረትና ፍትሕ እንዲያገኙ የሚመለከታቸው አካላት ተገቢውን ክትትል እንዲያደርጉ ቅዱስ ሲኖዶስ ሐዋርያዊ ጥሪውን በማቅረብ ለሰባት ቀናት ሲያካሂድ የሰነበተውን ቀኖናዊ ጉባኤ ዛሬ ግንቦት 6 ቀን 2018 ዓ.ም. በጸሎት አጠናቋል፡፡

“እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ”

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም
ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት
አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ

ግንቦት 6 ቀን 2018 ዓ/ም

ሰላም እንደምን ሰነበታችሁ ውድ የ2018 ዓ.ም ተመራቂ  ደቀመዛሙርት። ተመራቂዎችን የተመለከቱ መልእክቶች እንዲተላለፉበት በምርቃት ኮሚቴው የቴሌግራም ገጽ ተከፍቷል። በመሆኑም ተመራቂዎች  መ...
12/05/2026

ሰላም እንደምን ሰነበታችሁ ውድ የ2018 ዓ.ም ተመራቂ ደቀመዛሙርት። ተመራቂዎችን የተመለከቱ መልእክቶች እንዲተላለፉበት በምርቃት ኮሚቴው የቴሌግራም ገጽ ተከፍቷል። በመሆኑም ተመራቂዎች መልእክቶችን በቀጥታ ከአንድ ቋት ብቻ እንዲከታተሉ ተመራቂ ደቀ መዛሙርትን ብቻ Add በማድረግ ወይም ይህን Link https://t.me/htugc18 በመላክ እንድትተባበሩን እናሳስባለን።

የ2018 ዓ.ም የተማሪዎች ምርቃት ኮሚቴ

የጥናታዊ ጽሑፍ መድረክቀን፦ ረቡዕ ግንቦት 5 ቀን 2018 ዓ.ምቦታ፦ በዩኒቨርሲቲው አዳራሽሰዓት፦ ከ11:30-2:00 ሰዓት #ማሳሰቢያ፦ መድረኩ ለሁሉም ክፍት ነው!!
11/05/2026

የጥናታዊ ጽሑፍ መድረክ
ቀን፦ ረቡዕ ግንቦት 5 ቀን 2018 ዓ.ም
ቦታ፦ በዩኒቨርሲቲው አዳራሽ
ሰዓት፦ ከ11:30-2:00 ሰዓት

#ማሳሰቢያ፦ መድረኩ ለሁሉም ክፍት ነው!!

፻፴፬ ኛው  የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልአተ ጉባኤ ላይ  በቅዱስነታቸው የተላለፈ አባታዊ መልእክት ሚያዝያ ፳፳/፳፻፲፰ ዓ.ምብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት...
06/05/2026

፻፴፬ ኛው የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ምልአተ ጉባኤ ላይ በቅዱስነታቸው የተላለፈ አባታዊ መልእክት

ሚያዝያ ፳፳/፳፻፲፰ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ የግንቦት ርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የመክፈቻ አባታዊ መልእክት አስተላልፈዋል።
መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ ኣምላክ ኣሜን!
ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ
የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤
ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ
የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤
ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣
ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ ኣባላት፣
በአጠቃላይ በዚህ ዓመታዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የተገኛችሁ በሙሉ፦
ማሕየዊት በምትሆን ሞቱ ሰማያውያንና ምድራውያንን ያስታረቀ፣ በቅድስት ትንሣኤውም የሙታንን ሕይወት በተስፋ ያለመለመ ጌታችን፣ ኣምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ እንኳን ለዓመታዊው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ አደረሰን አደረሳችሁ!
“እስመ ተዋለጠ እግዚአብሔር ዓለመ በክርስቶስ አናኅስዮ ኃጢአቶሙ ወኢነጺሮ ጌጋዮሙ፤ ወረሰየ ላዕሌነ ቃለ ሥምረቱ፤ ወወሀበነ መልእክተ ሣህሉ፤ እግዚአብሔር በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር ያስታርቅ ነበርና በደላቸውን አይቈጥርባቸውም ነበር፤ በእኛም የማስታረቅ ቃል አኖረ” (2ኛቆሮ. 5፥19)
የእግዚአብሔርም ልጅ፣ የሰውም ልጅ የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም ሰው ሆኖ ሲገለጽ ግልጽ የሆነ ዓላማና ግብ እንደነበረው ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል፤ እርሱም በሰማይም፣ በምድርም ያሉትን በሙሉ ማስታረቅ፣ ማገናኘትና አንድ ማድረግ ነበረ፤
ጌታችን ይህንን ሲያደርግ ሰማያውያኑንና ምድራውያኑን የለያየውን ምክንያት በማስወገድ ነው፤ የመለያየቱ ምክንያት ክፉ ኅሊና አምጦ የወለደው በደልና እርሱን ተከትሎ የተከሠተው ኃጢኣት ነበረ፤ በኃጢኣት ምክንያት የገባው ሞት ደግሞ የቅጣቱ ማሳያ ፍርድ ነበረ።
የመጀመሪያዎቹ ሰዎች በፈጸሙት ስሕተት መነሻነት ምድርንና ምድራውያንን ለከባድ ቅጣትና መርገም የዳረገው ይህ መለያየት ለሰማያውያኑም ተርፎአል።
ምክንያቱም መለያየቱ በእግዚአብሔርና በሰው፣ በመላእክትና በሰው፣ በሰውና በሰው፣ በነፍስና በሥጋ ጭምር የጥል ግድግዳን ገንብቶ እስከ ክርስቶስ ዕለተ ስቅለት መዝለቁን በቅዱስ መጽሐፍ የምናውቀው ስለሆነ ማለት ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!

ቀዳማዊና ዘላለማዊ የሆነው ወልደ እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰብእናችንን ተዋሕዶ በዚህ ዓለም የተገለጸው ሰማያውያንንና ምድራውያንን የለያየው የጥል ግድግዳን ለማፈራረስ ነው።
ለመለያየት ምክንያት የሆነችውን ኃጢኣት በሰውነቱ በመቅጣት የሕግን ትእዛዝ ከፈጸመ በኋላ የዕርቁን ተግባር በወሳኝ መልኩ አከናውኖታል።
በክርስቶስ ቤዛነት የሆነው ይህ ዕርቅ በእግዚአብሔር ዘንድ እጅግ የተወደደ ነበረና እሱ ራሱ በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር አስታረቀ።
ለዚህም ነው ተበዳይ እርሱ፣ ቤዛዊ መሥዋዕት ሆኖ የቀረበው እርሱ፣ ኣስታራቂ እርሱ፣ ታራቂ እርሱ ሆኖ የምናገኘው፤ ለእርሱ የሚሳነው ነገር የለምና ለእኛ ግር የሚል ቢመስልም ለእርሱ ቀላል ነበረ።
በዚህ የዕርቅ ተግባር ሰውና እግዚአብሔር፣ ሰውና መላእክት፣ ሰውና ሰው፣ ነፍስና ሥጋ ታርቀው በይፋ ተገናኙ፤ በኅብረትና በአንድነትም መኖር ቻሉ፤ በቀኙ ለተሰቀለው ወንበዴ “ዛሬውኑ ከእኔ ጋር በገነት ትኖራለህ” የሚለው ቃለ ምሕረትና “አባት ሆይ፥ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” የሚለው ቃለ አማኅፅኖ የዕርቁ፣ የግንኙነቱና የኣንድነቱ ማሳያ ኣስረጅ ናቸው።
ስቅለተ ክርስቶስ ነፍሶቻችን ወደ ግዞት ቤት ሳይሆን ወደ ገነት እንዲገቡ፣ የሚቀበላቸውም ራሱ እግዚአብሔር እንዲሆን ያስቻለ ታላቅ መለኮታዊ ፍጻሜ ነው።
እኛ “ክርስቶስ መድኃኒታችን ነው፤ አድኖናል” ብለን በፍጹም ልባችን አምነን የምንመሰክረው፣ እርሱም በመስቀል ላይ ውሎ “ሰላሜን ሰጠኋችሁ” በማለት በመስቀሉ ስላዳነን አጽናኝ መንፈስ ቅዱስንም ስለላከልን ነው።
ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት!
የድኅነታችንና የሰላማችን መሠረት የሆኑትን የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ለዓለም ማኅበረሰብ የማብሰርና የማሥረጽ ተግባር የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቍጥር አንድ ተልእኮ ነው፤
ነገረ ሞቱና ነገረ ትንሣኤው በአስተውሎት፣ በጥልቀትና በተመሥጦ ስናስተምር በውስጡ የምናገኘው የዕርቅ፣ የሰላምና የኣንድነት ምስጢር ነው፤
እንደ እውነቱ ከሆነ እኛ የክርስቶስ መልእክተኞች እንደ ቃሉ ራሳችንን ክደን በሚጠበቀው መጠን ተልእኮኣችንን መወጣት ብንችል ኖሮ፣ ኣሁን በዓለማችን የተፈጠረው መለያየትና ግጭት አይኖርም ነበር።
ችግሩን ሙሉ በሙሉ ማስቀረት ባንችልም በእጅጉ መቀነስና ዓቅሙን ማዳከም እንችል ነበር፤ ነገር ግን ተልእኮአችንን በአግባቡ አለመወጣት ኣንድ ነገር ሆኖ የዓለሙ መሣሪያ ሆነን መገኘታችን “በዕንቅርት ላይ…” ሆኖ ይስተዋላል።
ይሁንና አሁንም ሕዝቡን ወደ አንድነት፣ ወደ ፍቅር፣ ወደ ሰላም፣ ወደ ዘላቂ የጋራ ጥቅምና ወደ ፈሪሀ እግዚአብሔር ማምጣት የጉባኤያችን ዐቢይ ተግባር ሊሆን ይገባል፤ እነዚህ ካሉ የምናጣውም ሆነ የሚያመልጠን የለምና ነው፤
ሀገርን በኀላፊነት ተረክባችሁ በላዕላዊ፣ በማእከላዊና በታሕታዊ መዋቅር የምትገኙ፣ እንደዚሁም አማራጭ ሐሳብ አለን ብላችሁ የምትንቀሳቀሱ ልሂቃነ ሀገር ፣ ሁላችሁም እግዚአብሔርን ከሚያውቅ፣ ከሚያመልክና ከሚፈራ ሕዝብ የተገኛችሁ ናችሁና በልባችሁ እግዚአብሔርን ፍሩ፤ ድምፁንም ስሙ፤ የእርሱ ገንዘብ በሆኑ ፍጡራንም አትጨክኑ፤ ሰውን መያዝ የሚቻለው ኅሊናን በመርታት እንጂ በሌላ አይደለምና፣
የሕዝቡን ፍላጎትና የልብ ትርታ በሚገባ አዳምጡ፤ ሕዝቡ የሚፈልገው በአንድነትና በእኩልነት መኖር፣ በሰላም ወጥቶ መግባት፣ ፍትሕን ማስፈን፣ ለኑሮው የሚበቃ ምጣኔ ሀብትን ማግኘት፣ የእምነት ነፃነትና እኩልነት መረጋገጥ የመሳሰሉት ናቸው።
ሕዝቡ እነዚህ ከተሟሉለት ተደመጠ ማለት ነው፤ ከተደመጠ ደግሞ እርሱም በበኩሉ ያደምጣል፤ ይከተላልም።
ስለሆነም ለሁሉም ልጆቻችንና ወገኖቻችን የምናስተላልፈው ወቅታዊ ጥሪ ሁሉንም ችግሮቻችንን በሰላም ብቻ ለመፍታት ተባበሩ የሚል ነው፤ ከዚህ ውጭ የሚደረገው አማራጭ ሁሉ ለዘላቂ ሰላማችን አይበጅም እንላለን።
በመጨረሻም፦
በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ከበዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን የሚካሄደው ዓመታዊው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዕለት የተጀመረ መሆኑን ለሕዝበ ክርስቲያኑና ለመላው ኢትዮጵያውያን እናበሥራለን!!!
እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ!
እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤
አሜን!!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤
ሚያዝያ ፳፰ ቀን ፳፻፲፰ዓ.ም
አዲስ አበባ - ኢትዮጵያ

ዘገባው የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ መገናኛ ብዙኃን አገልግሎት ሥርጭት ድርጅት ነው።

የብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን  የመገናኛ ብዙኃን ሥርጭት አገልግሎት ድርጅት እና የአፋን ኦሮሞ መገናኛ ብዙኃን ቴሌቪዥን ማሰራጫ ድርጅት  የበላይ ኃላፊ የ...
27/04/2026

የብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የመገናኛ ብዙኃን ሥርጭት አገልግሎት ድርጅት እና የአፋን ኦሮሞ መገናኛ ብዙኃን ቴሌቪዥን ማሰራጫ ድርጅት የበላይ ኃላፊ የምስራቅና ሰሜን አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ወላጅ እናት እማሆይ አስካለ ማርያም በዓለም ስማቸው ወይዘሮ አምሳለ ማሞ በ85 ዓመት እድሜያቸው ከዚህ ዓለም ድካም አርፈዋል።
ሥርዓተ ቀብራቸው ሚያዝያ 20 ቀን 2018 ዓ.ም በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ኢጀሬ ደብረ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት ይፈጸማል።
የመገናኛ ብዙኃን ሥርጭት አገልግሎት ድርጅት በእማሆይ እማሆይ አስካለ ማርያም እረፍት የተሰማውን ኃዘን እየገለጸ ለወዳጅ ዘመዶቻቸው መጽናናትን ለእርሳቸውም እረፍተ ነፍስ ይመኛል።

ምንጭ:- ኢኦተቤ ቴቪ

በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የ2018 ዓ.ም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል የእንኳን አደረሰዎ መርሐ ግብር  ተካሔደ           (ሚያዚያ 13 ቀን 2018 ዓ.ም...
21/04/2026

በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የ2018 ዓ.ም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል የእንኳን አደረሰዎ መርሐ ግብር ተካሔደ

(ሚያዚያ 13 ቀን 2018 ዓ.ም)
የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ መምህራን፣ የአስተዳደር ሠራተኞች እና ደቀመዛሙርት ለብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የዩኒቨርሲቲው ፕሬዚደንት እና የደቡብ ኦሞና አሪ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የእንኳን አደረሰዎት መርሐ ግብር በዛሬው ዕለት ተካሂዷል።

በእንኳን አደረሰዎት መርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን ድርጅት የበላይ ሓላፊ እና የምሥራቅና ሰሜን አፍሪካ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት እና የሀድያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ገሪማ የጌዲኦ፣ አማሮና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የቦርድ ሰብሳቢ፣ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ የዳውሮና ኮንታ ዞን ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ በፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሶማሌ ክልልና የአርሲ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የዩኒቨርሲቲው የቦርድ አባላት፣ የዩኒቨርሲቲው የሴኔት አባላት፣ ሊቀ ትጉኃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጠቅላይ ጸሐፊ፣ የገዳማትና የአድባራት አስተዳዳሪዎችና ጥሪ የተደረገላቸው ዕንግዶች ተገኝተዋል።

በግንባታ ላይ ባለው ሕንፃ ምድር ቤት (Ground Floor) ላይ በተከናወነው በዚህ መርሐ ግብር፣ በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት/ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ ተቋሙን ለማሳደግ እያደረጉት ያለው ሐዋርያዊ አገልግሎት ጉብኝት የተደረገ ሲሆን በተለይ በብፁዕነታቸው መመሪያ ሰጪነት በግንባታ ላይ ስላለው በ2700 ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ ባለ 10 ወለል ግዙፍ ሕንጻ የደረሰበትን ደረጃ ለክብር እንግዶችና ለዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ ተዘዋውረው እንዲጎበኙና ግንዛቤ እንዲያገኙ ተደርጓል።

በመርሐ ግብሩ የዩኒቨርሲቲው ደቀ መዛሙርት በግዕዝ፣ በእንግሊዝኛና በተለያዩ ቋንቋዎች ያሬዳዊ መዝሙራትን ያቀረቡ ሲሆን፣ ለዕለቱ የሚመጥን ቅኔም ቀርቧል።

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ የግንባታውን ሂደት ከክርስቶስ ትንሣኤ ጋር በማያያዝ ባስተማሩት ትምህርት "ይህ ሕንፃ ለሁላችንም፣ አሁን ላለነውና ለሚመጣው ትውልድ ምሳሌ ሲሆን የገጠመው ፈተና ሳይበግረው ወደ ሚታይ ግዙፍ አካልነት መቀየሩ በአስተሳሰብና በሕሊና ለሞቱ አካላት እንደ ትንሣኤ የሚሆን ነው" ብለዋል። አክለውም ሕንፃው የቤተክርስቲያናችን እንጂ የግለሰብ አለመሆኑን በመግለጽ፣ አባቶች ሁሉ ሊጎበኙትና ሊደግፉት እንደሚገባ አሳስበዋል።

የሥነ-ሕንፃ ዲዛይኑን (Architectural Design) የሠራው አትሮንስ ኮንሰልት አማካሪ መሐንዲሶችና አርክቴክቶች የሕንፃውን ሙሉ ገጽታና የወደፊት ቅርጽ በሚንቀሳቀስ ምስል (Animation Video) የታገዘ ገለጻ ለታዳሚው አቅርቧል።

የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብ በዩኒቨርሲቲው የአስተዳደር ጉዳዮች ም/ፕሬዚዳንት መልአከ ኃይል አባ ጽጌ ድንግል አቅራቢነት በብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በኩል ለዩኒቨርሲቲው ፕሬዚዳንት ለብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ሥጦታ ያበረከቱ ሲሆን የተለያዩ የአድባራት አስተዳዳሪዎችም ለትንሣኤ በዓል የመልካም ምኞት መግለጫ ለብፁዕነታቸው ሥጦታዎችን አበርክተዋል።

ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ባስተላለፉት መልእክት፦ መርሐ ግብሩን ያዘጋጁት አካላት በግንባታ ላይ ባለው ሕንፃ ማድረጋቸውን ሲመለከቱ ሕንጻው እንደዚህ ዓይነት አገልግሎቶች መስጠት መጀመሩ ብዙ ነገሮችን ያቀልልናል ካሉ በኋላ ብፁዓን አባቶች በዚህ ቦታ ተገኝተው መባረካቸውና መጸለያቸው እንደቀላል የሚታይ ነገር አይደለም ብለዋል። ብፁዕነታቸው አክለውም ፕሮጀክቱን እያገዙ ያሉ ብፁዓን አባቶችን፣ ባለድርሻ አካላትንና እንግዶችን አመስግነዋል።

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ "ወጣኔ ኩሉ ወፈጻሜ ኩሉ" በሚል መሪ ቃል ባስተላለፉት ቃለ ምዕዳን፣ ሕንፃው እንደ ሰው ልጅ በምሥጢር ተጸንሶ አሁን ለታየበት ደረጃ መብቃቱን ገልጸው፣ "ከዚህ በኋላ የምንለምነው አካል አይኖርም ሕንጻው ራሱ አጋዦቹን ይጣራላችኋል አስጀማሪው እግዚአብሔርም በድል ለማስፈጸም ያብቃችሁ፤ በሚቀጥለው ዓመት የምርቃቱን ሪቫን ለመቁረጥ ያብቃን" በማለት መርሐ ግብሩን በጸሎት ዘግተዋል።

መረጃዎችን በቴሌግራም ለማገኘት ይኽን ይጫኑ https://t.me/holytrinitypr

የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ሕዝብ ግንኙነት

Address

Holy Trinity University
Addis Ababa

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ- Holy Trinity University posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share