05/09/2026
ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የዶክትሬት ዲግሪያቸውን መመረቃቸውን አስመልክቶ በቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ መርሐ ግብር ተካሔደ
________
ቅስዩ፣ ነሐሴ 30 ቀን 2018 ዓ.ም. — በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የበላይ ሓላፊ ሊቀ ጳጳስ/ፕሬዚዳንት ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ (ዶ/ር) የዶክትሬት ዲግሪ ምርቃት መርሐ ግብረሰ በዩኒቨርሲቲው አዳራሽ በልዩ ሁኔታ ተከበረ።
በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት የመምሪያና የድርጅት ኃላፊዎች፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅና የክፍል ኃላፊዎች፣ የቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ መምህራን፣ የአስተዳደር ሓላፊዎችና ሠራተኞች፣ የተጋበዙ እንግዶች፣ ቤተሰቦችና ወዳጆች ተገኝተዋል።
የበዓሉ መርሐ-ግብር በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሊቃውንትና ካህናት በቀረበ ጸሎተ ወንጌል ተጀምሯል። በመቀጠልም በመልአከ ኃይል አባ ጽጌ ድንግል ፈንታሁን የዩኒቨርሲቲው አስተዳደር ም/ፕሬዚዳንት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር ቀርቧል።
በመርሐ-ግብሩ የመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሊቃውንትና መምህራን ያቀረቡት ወረብ የዝግጅቱን መንፈሳዊ ድባብ ያጎላ ሲሆን፣ "ፍኖተ ሕይወት" መጽሔት ምርቃትም በመስተንግዶ ኮሚቴ አቅራቢነት በብፁዓን አባቶች ተከናውኗል።
በዕለቱ የብፁዕ አቡነ ፊልጶስን የትምህርት ጉዞ፣ የአካዳሚክ ዝግጅትና የዶክትሬት ምረቃ ሂደት የሚያስቃኝ ዘጋቢ ፊልም በራማ ሚዲያ ቀርቧል። ፊልሙም ብፁዕነታቸው በትምህርት የተጓዙበትን ሂደትና በእውቀት ፍለጋ ያሳለፉትን የትጋት ጉዞ በምስልና በድምፅ ዳስሷል።
በመቀጠልም የብፁዕነታቸው የዶክትሬት ዲግሪ መመረቂያ ጽሑፍ ዳሰሳ የዩኒቨርሲቲው የአካዳሚክ ም/ፕሬዚዳንት በሆኑት በፕሮፌሰር አባ ኃይለ ገብርኤል ግርማ፣ የዶክትሬት ጥናቱን ይዘትና አካዳሚክ ጠቀሜታ ያስቃኘ ሆኖ ቀርቧል።
በዚሁ መርሐ-ግብር መምህር ክነፈ ርግብ ያቀረቡት ቅኔ ለዝግጅቱ ያማረ ድባብ ሰጥቷል። ከዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብና ከተለያዩ አካላት የተዘጋጀው የስጦታ መርሐ-ግብርም ተከናውኗል።
ከስጦታ መርሐ-ግብሩ በኋላ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ (ዶ/ር) መልእክትና ምስጋና አስተላልፈዋል። ብፁዕነታቸው በመልእክታቸው በትምህርት ቆይታቸው ያሳለፉትን ሂደት፣ በጥናት ያገኙትን ዕውቀትና የዶክትሬት ጥናታቸውን በማስመልከት ገለጻ አድርገዋል። እምነት፣ እውነትና ዕውቀት የትምህርት መሠረታዊ መርሆች መሆናቸውንም አጽንዖት ሰጥተዋል።
በተለይም በትምህርት ሒደት ላይ ያለ ሰው ለስኬት ሊከተላቸው የሚገቡ አምስት ዋና ዋና ነጥቦችን አብራርተዋል። እነዚህም፦
1. ግልጽ ዓላማና ግብ መያዝ፤
2. ጽናትና ራስን መግዛት፤
3. ጊዜን በውጤታማነት መጠቀም፤
4. ትክክለኛ የጥናት ስልትና ዕቅድ መከተል፤
5. የአካባቢና የማኅበራዊ ድጋፍን በአግባቡ መጠቀም ናቸው።
ብፁዕነታቸው እነዚህ መርሆች በትምህርት ጉዞ ላይ ላሉ ተማሪዎችና ዕውቀትን ፍለጋ ላይ ለሚገኙ ሁሉ አስፈላጊ መሠረቶች መሆናቸውን ገልጸዋል።
በመጨረሻም ብፁዕነታቸው በዶክትሬት ትምህርታቸውና በምረቃው ሂደት የተሳተፉ መምህራንን፣ የዩኒቨርሲቲውን ማኅበረሰብ፣ በዕለቱ የተገኙ አባቶችን፣ ዕንግዶችንና በሒደቱ የተሳተፉትን ሁሉ አመስግነዋል።
የመርሐ-ግብሩ መጨረሻ ላይ ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስን ቃለ ምዕዳንና ቃለ በረከት እንዲሰጡ ጋብዘዋል።
ብፁዕ አቡነ ማርቆስም በቃለ ምዕዳናቸው ብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የደረሱበት የትምህርት ደረጃ ለሌሎች ወጣት ሊቃነ ጳጳሳትና ለትውልዱ አርአያ መሆኑን ገልጸዋል። ብፁዕነታቸው በትምህርትና በአገልግሎት የተገነባው የብፁዕ አቡነ ፊልጶስ ጉዞ፣ "ዘመኑን ዋጁ" የሚለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል በተግባር የሚያሳይ ምሳሌ መሆኑን መስክረዋል።
የዶክትሬት ዲግሪውን በማግኘታቸውም ብፁዕ አቡነ ፊልጶስን አድንቀውና አመስግነው፣ ይህ ስኬት ለሌሎች ወጣት ሊቃነ ጳጳሳትና ለቤተ ክርስቲያን ልጆች በትምህርት የበለጠ እንዲገሰግሱ የሚያነሣሣ አርአያ መሆኑን ገልጸዋል። ብፁዕነታቸውም ቃለ በረከት በመስጠት መርሐ-ግብሩን በጸሎት አጠናቀዋል።
ይቅድስት ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ ሕዝብ ግንኙነት