26/05/2026
!
====================
ግንቦት 18 ቀን 2018 ዓ/ም፣ አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ (የኢሃተጉ) የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለ1ሺ 447ኛው የኢድ አል–አድሃ (አረፋ) ክብረ በዓለ በሰለም እና በጤና አደረሳችሁ ሲል በዛሬው ዕለት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፏል፡፡
የጉባኤው የእንኳን አደረሳችሁ ሙሉ መልዕክት እንደሚከተለው ለንባብ ቀርቧል፡፡
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዬች በሙሉ እንኳን ለ1ሺ 447ኛው ታላቁ የኢድ አል–አድሃ (አረፋ) ክብረ በዓለ በሰላም እና በጤና አደረሳችሁ በማለት የአክብሮት የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክቱን ያስተላልፋል፡፡
የዒድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል ታላቅ መስዋዕትነትን፣ ልባዊ ጽናትን፣ ትዕግስትን ከሁሉ በላይ ለፈጣሪ መገዛትን እና በእርሱ ላይ ያለ እውነተኛ መተማመንን የሚያመለክት መንፈሳዊና ማሕበራዊ ጥልቅ ትርጉም ያለው ድንቅ ክብረ በዓል ነው፡፡
ይህ ክብረ በዓል የእስልምና እምነት ተከታዮች በሙሉ ያለ ልዩነት ከምንጊዜውም በላይ በመተሳሰብ፣ በመጠያየቅ፣ በመርዳዳት እና በደስታ የሚያከብሩት ታላቅ የፍቅርና የአብሮነት ክብረ በዓልም ነው፡፡
ነብዩ ኢብራሂም በሕልማቸው የበኩር ልጃቸውን ለፈጣሪ መስዕዋት አድርገው ሲያቅርቡ ከተመለከቱ በኋላ ለውድና እና ለበኩር ልጃቸው እንዲህ ሲሉ ተናገሩ፤ ልጄ ሆይ እኔ በሕልሜ የማርድህ ሆኘ አይቻለሁ፣ አንተስ ምን ታስባለህ ብለው ይጠይቁታል፡፡ ልጃቸውም አባቴ የታዘዝከውን ሳታጓድል ፈጽም በማለት ያለ ማቅማማት ይመልስላቸዋል፡፡ (ሱረቱ–ሳፋት፤ 120)
ነብዩ ኢብራሂም የልጃቸውን ምላሽ ከሰሙ በኋላ ልጃቸውን ለፈጣሪ መስዕዋት አድርገው ወደ ሚሰውበት ቦታ ከልጃቸው ጋር ጉዞ ይጀምራሉ፡፡ በጉዞአቸውም ልጃቸው ምንም አይነት ተቃውሞ ሳያሰማ ይልቁኑ ነብዩ የታዘዙትን እንዲፈጽሙ በሚየበረታታ መንፈስ ወደ መስዕዋቱ ቦታ ጉዞአቸውን አቀኑ፡፡ ምንም እንኳን ልጃቸው ቢያበረታታቸውም የታላቁን አላህ ትዕዛዝ እንዳይፈጽሙ በመንገዳቸው ላይ ብርቱ ፈተና አጋጥሟቸው ነበር፡፡
ያጋጠማቸውን ሁሉም ፈተና በጽናት አልፈው ነብዩ ኢብራሂም ከአንዴም ሁለቴ ልጃቸውን ለማረድ/ ለመሰዋዕት ቢሞክሩም ቢላዎው ሊቆርጥላቸው አልቻለም፡፡ በዚህ መሀል ነው ታላቁ ፈጣሪ ነብዩ ኢብራሂም ለፈጣሪ ትዕዛዝ ያላቸውን ጥልቅ መገዛት በመመስከር በልጃቸው ላይ ምንም እዳያደርጉ በምትኩ ግን የመስዕዋት በግ ማዘጋጀቱን የገለጸላቸው፡፡
ነብዩ ኢብራሂም እጅግ ፈታኝ ትዕዛዝ እና ፈተና ቢገጥማቸውም ፈጣሪን የሁሉ የበላይ እና የሕይወታቸው ዋና አድርገው በፍጹም ልባቸው ለፈጣሪ የተገዙ በመሆናቸው ከባዱን ትዕዛዘ እና እጅግ አስቸጋሪውን ፈተና በጽናት አልፈው እስከ ዛሬ ድረስ የሚታውስ፣ የሚተረክ እና የሚተነተን የእምነት፣ የመስዕዋትነት፣ የመታዘዝ ገድል መፈጸም ችለዋል፡፡ ይህ ታሪክ እስከ ዓለም ፍፃሜ ድረስ ለሰው ልጆች ትምህርት ሲነገር ይኖራል፡፡
በዚህ ዘመን የምንኖር እኛ አማኞች የፈጣሪን ስም ከመጥራት ባሻገር በፈጣሪ ላይ በፍጹም ልባችን በመታመን፣ ፈጣሪ ለሰጠን መንፍሳዊ እና ማሕበራዊ ትዕዛዞች በመገዛትና በመፈጸም መኖር ብንችል በምድር ሰላም በሰማይ ታላቅ ደስታ ይሆናል፡፡
ምክንያቱም የፈጣሪ ትዕዛዝ መረዳዳት፣ መተጋጋዝ፣ መዋደድ፣ አንዳችን ለአንዳችን በጎ ማስብ እና ማድረግ ስለሆነ ነው፡፡ እነዚን መንፍሳዊ እና ማሕበራዊ እሴቶች በሚጠብቁና በሚያስጠብቁ አማኞች ሕይወት ፈጣሪ እጅጉን ይደሰታል፡፡ በምድርም በረከት እና ሀሴት እጅጉን ይበዛል፡፡
ዓለም የፈጣሪን ትዕዛዝ እና ፈቃድ ወደ ጎን በመግፋት ለእኔ ብቻ በሚል መንፈስ ተለክፋለች፡፡ አንድ ሰው አንድን ነገር ጥቅም ያስገኝልኛል ብሎ ካሰበ በፈጣሪ በክብር የተፈጠረውን የሰውን ልጅ ሕይወት እሰከማጥፋት የሚደርስ እርምጃ ይወስዳል፡፡ የሰው ልጆች የመለያየት እና የመጠላላት አንዱና ዋንኛ ምክንያት ለእኛ የምንፈልገውን ነገር ለሌላው እንዲሆን አለመፍቀድ ወይም መከልከል ነው፡፡
ለሰው ሁሉ ርህራሄ፣ ቸርነት፣ ምህረት፣ ፍቅር ወዘተ ይገባል፡፡ እኛም ሁላችን ለሰው ልጆች የሚገባውን መልካም ሁሉ ነገር በማድረግ የስጋችንን ክፉ ምኞት ዕለት ተዕለት ልንገድል ይገባል፡፡ የዚህ በዓል አንዱና ዋንኛ መገላጫ ለስው ልጆች ማስብ፣ ፍቅር ማሳየት እና እንክብካቤ ማድረግ ነው፡፡
የኢድ አል–አድሃ (አረፋ) ክብረ በዓለ በውስጡ የያዛቸው የመታዘዝ፣ የመረዳዳት፣ የርህራሄና የፍቅር እሴቶች የሰው ልጆች ያላቸውን ጠንካራ የእርስ በእርስ ትስስር ይበልጥ የሚያጸኑና የሚያጠናክሩ ከመሆናቸውም ባለፈ ካለፈው የበደል ታሪክ በመወጣት ለወደፊት ዕርቅና ሰላም እንዲሁም አብሮነት ቅድሚያ በመስጠት ሕይወታችንን መምራት እንደሚገባን የሚያስገነዝቡ ሕያው ትምህርቶች ናቸው።
ይህ የመሰዋትነት እና የታላቅ ፍቅር መግለጫ ክብረ በዓል ሲከበር የተቸገሩ ወገኖች ካልተቸገሩ ወገኖች እኩል በዓሉን በተመሳሳይ እንዲያከብሩ የሚደረግበት፤ የመረዳዳት መንፍሳዊ ትዕዛዝ የሚከወንበት፣ ሰው ሁሉ በፈጣሪ ፊት እኩል መሆኑን የሚገነዘብበት ነው፡፡
ኢድ አል አድሃ የችግረኞች ቤተ የሚደምቅበት፣ ልጆቻቸው ከምጊዜውም በላይ የሚደሰቱበት፣ መደጋገፍ ፣ መረዳዳት፣ ፍቅር የሚልቅበት ክብረ በዓል ነው፡፡
በመሆኑም የኢድ አል አድሃ (አረፋ) ክብረ በዓልን ስናከብር በተለመደው ኢትዮጵያዊ ጨዋነት እና በሃይማኖታዊው መመርያ መሰረት የታመሙትን እና በችግር ላይ ያሉትን በመጠየቅ እና በመርዳት ከሁሉ በላይም ለሀገራችን ኢትዮጵያ ሰላም እና እድገት ዱዓ በማድረግ እንዲሆን የአደራ መልክታችንን እያስተላለፍን በድጋሜ ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች በሙሉ እንኳን ለ1ሺ 447ተኛው የኢድ አል አደሃ (አረፋ) በዓል አደረሳችሁ፣ በዓሉ የሰላም፣ የጤናና የፍስሃ በዓል እንዲሆንላችሁ ከልብ እንመኛለን፡፡
ፈጣሪ ኢትዮጵያን እና ሕዝቦችዋን ይባርክ!
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ
ግንቦት 18 ቀን 2018 ዓ/ም አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
ስልክ፡ +251-115-52-58-11
Website: www.ircethiopia.et
Facebook: https://web.facebook.com/irce7