03/06/2026
የኢትዮጵያ ወንጌላውያን አብያተ ክርስትያናት ኅብረት፥ ፕሮፌሰር ክሬግ ኪነር የለገሱትን የመጻሕፍት ስጦታ ለአብርሆት ቤተ መጻሕፍት ግንቦት26 ቀን 2018 ዓ.ም አበረከተ።
የኢትዮጵያ ወንጌላዊያን አብያተ ክርስትያናት ኅብረት ፕሬዚዳንት ፓስተር ደረጀ ታፈሰ፥ በፕሮፌሰር ክሬግ ኪነር የተጻፉ፥ ፕሮፌሰሩም ለኢትዮጵያ መልካሙን የተመኙበት ጽሑፍና ፊርማቸው ያረፈበትን መጻሕፍት ለአብርሆት ቤተ መጻሕፍት በስጦታ ባበረከቱበት ወቅት ባደረጉት ንግግር፥
በአሜሪካን አገር ከሚገኙ ወዳጆች የተገኙት እነዚህን የመጻሕፍት ስጦታዎች በአገር ውስጥ በግዥ ለማግኘት እንደሚያስቸግር፥ መጻሕፍቱ በአንድ ሥፍራ ከሚሆኑ በአብርሆት ቤተ መጻሕፍት ቢቀመጡ በርካታ አጥኚዎችንና አንባቢያንን ሊጠቅሙ እንደሚችሉ ገልጸው፥ ትውልድ እውቀት አልባ ሊሆን እንደማይገባ፥ በመልካም እውቀት የተገነባ ትውልድ ደግሞ ለአገር እድገት ሁነኛ አስተዋጽዖ ማድረግ እንደሚችል፥ ይህ እንዲሆን ደግሞ ኅብረቱ የበኩሉን ድርሻ እያበረከተ መሆኑን ገልጸው ፥ ስጦታውን ከአሜሪካን ድረስ ያመጡትን ዶክተር ፈቃዱ አመኑን አመስግነዋል።
መጻሕፍቱን ከፕሮፌሰር ክሬግ ተረክበው ወደ ኢትዮጵያ በማምጣት ለአብርሆት ቤተ መጻሕፍት እንዲሰጥ መነሻውን የወጠኑት ዶክተር ፈቃደ አመኑ፥ በታዋቂው የነገረ መለኮት ሊቅ የተጻፉት እነዚህ መጻሕፍት፥ የተለያየ የእምነት አመለካከት ያላቸውን ሰዎች ለምርምር ተግባር ሊያግዝ የሚችል፥ ወደየ ቤተ እምነቱ ሄደው ለማንበብ ለሚከብዳቸው አጥኚዎችም አብርሆት አማካይና አመቺ ከመሆኑ አንጻር መመረጡን ገልጸው፥ እነዚህን ውድ መጻሕፍት የለገሱትን ፕሮፌሰርና ሌሎች ወዳጆቻቸውን ከልብ አመስግነዋል። አክለውም፥ የመጻሕፍቱ ስጦታዎች በዚህ እንደማይገደቡና ተጨማሪ መጻሕፍትን ለቤተ መጻሕፍቱ ለማበርከት ቃል ገብተዋል።
በመጨረሻም የአብርሆት ቤተ መጻሕፍት ዳይሬክተር አቶ ሙሉቀን ታሪኩ፥ ስለተደረገው የመጻሕፍት ስጦታ ከልብ አመስግነው፥ በቤተ መጻሕፍቱ ስም ለኢትዮጵያ ወንጌላውያን አብያተክርስቲያናት ኅብረት እና ለፕሮፌሰር ክሬግ ኪነር የምስጋና ምስክር ወረቀት አበርክተዋል።