26/02/2019
ሠላም ውድ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች፣ በያላችሁበት የአግዚአብሔር አብ ጸጋ፣ የእግዚአብሔር ወልድ ፍቅር የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ቸርነት ከእናንተ ጋር ይሁን፡፡
ውዶች ሆይ ከዚህ በፊት በአንዲት ዕምነት ተዋህዶ እና በ ወደ ምስራቅ ተመልከቱ ገጽ በለቀኩት የመግባቢያ መልዕክቴ ላይ በገለጽኩላችኁ መሠረት የዛሬዎቹን የምንፍቅና ትምህርቶች በግልጽ እንድንረዳ ይረዳን ዘንድ አባቶች ውሃን ከጥሩ ነገርን ከስሩ እንዲሉ ከመጀመሪያዎቹ የመናፍቃን ጽንስ ጀምሮ እስካሁን ድረስ በግብር ልጆቻቸው ሲተላለፍ የመጣውን አስተምህሮ ለመመርመር ከጉባኤ ኒቂያ በፊት ከነበሩት ጥንተ መናፍቃን ዋና ዋናዎቹን በአጭር በአጭሩ ወደ እናንተ ይዤላችሁ ቀረብኩ፡፡
1. Gnosticism/ ግኖስቲክ
ግኖስቲክ ማለት የዕውቀት ሰው (አዋቂዎች) ማለት ሲሆን ቃሉን የወሰዱት ግኖሲስ ከሚለው የጽረዕ ቋንቋ ነው፡፡ ግኖስቲኮች ክርስትናን ከተቀበሉ በኋላ አዋቂዎች ነን በማለት በዘመናቸው የነበረውን የጥንቆላና የምሕታት እንዲሁም ደግሞ የፍልስፍናን ትምህርት ከክርስትና ትምህርት ጋር በማደባለቅ የሚያስተምሩ፣ ከክርስትናው ይልቅ እምነታቸውን በፍልስፍና ላይ ለመመስረት ትግል ያደርጉ የነበሩ ‹‹ፍልስፍና በራሱ ጎጂ አይደለም›› የሚል ከአህዛብ ዕምነት ወደ ክርስትናው ከተመለሱት ክርስቲያኖች የወረሱትን የሐሰት ትምህርት የሚያስተምሩ Gnosticism religion የሚባለውን ተቋም ለመፍጠር የቻሉ ናቸው፡፡ ግኖስቲኮች ምንታዌን (Dualism) የሚያስተምሩ ናቸው፡፡ ስለ አምለክ ሲያስተምሩ:- ሁለት አማልክቶች አሉ እነሱም ክፉ አምላክና ደጉ አምላክ ይላሉ ከዚህም ጋር አያይዘው ሥጋንና የሚታየውን ግዑዙን ነገር የፈጠረው ክፉ አምላክ ነው፣ ነፍስንና የማይታየውን ረቂቁን ነገር የፈጠረው ደግሞ ደጉ አምላክ ነው፣ ጭለማን ክፉ አምላክ ብርሃንን ደግሞ ደጉ አምላክ ፈጠረ የሚል ፍልስፍና የተቀላቀለው ትምህርት ነበራቸው፡፡ ከስነ ፍጥረቱም ጋር አያይዘው ፈጣሪና ፍጡር በምንም አይነት ሁኔታ እንደማይገናኙ በመግቦቱም አለምን እንደማይመግብ ሲናገሩ ይህንንም አምላክ the silence or the depth በማለት ይገልጹታል፡፡ እነዚህም የመጀመሪያዎቹ የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነት፣ የአምላክን ሰው መሆን የካዱ ርዕሰ መናፍቃን ናቸው፡፡ ስለ ሰው ልጅ ተፈጥሮ በሚያስተምሩት ትምህርታቸው የሰውን ልጅ በሦስት ደረጃ ከፋፍለው ያስቀምጣሉ፡፡ እራሳቸውን መንፈሳዊ፣ ክርስቲያኖችን ነፍሳዊ ሲሉ አህዛብንና አይሁድን ደግሞ ስጋዊ በማለት ያስቀምጣሉ፡፡ የግኖስቲክን የክህደት ተምህርት ካስፋፉ መናፍቃን መካከል ሲሞን መሠርይ፣ ሜናንድሮስ፣ ሳቶሪኖስ፣ ኬሪንቶስ፣ ኒቆላዎስ፣ በስሊድስ፣ ቫላንቲኖስ እና መርቂያን ይገኙበታል፡፡ የእነዚህን የምንፍቅና ትምህርት ምን እንደነበር በየክፍል በየክፍሉ እያነሳን ወደፊት ለማየት እንሞክራለን፡፡
2. ኢቦኒስት
ወንድሞች በአንጾኪያ ክርስቲያን የሚለው ስያሜ ከተሰጣቸው በኋላ ሐዋ 11፡26 በዚህ ጊዜ የተነሱት መናፍቃን ደግሞ ቢጽ ሐሳዊያን (ሐሰተኛ ወንድሞች) በመባል ይጠሩ ነበር፡፡ በትምህርታቸው ክርስቶስ በድንግልና መወለዱን ቢቀበሉም አምለክ ግን አይደለም፣ ክርስቶስ እሩቅ በእሲ ስለሆነ ማርያምም ወላዲተ አምላክ ሳትሆን ወላዲተ ሰብእ ናት በማለት ይናገራሉ፡፡ እነዚህ ኢቦኒስቶች ከአይሁድ ክርስትናን ከተቀበሉና ካመኑ በኋላም የመጡበትን የአይሁድን እምነት ይከተሉ ስለነበር የአይሁድን ሀይማኖት ያዙ ጥምቀት ያለ ግዝረት፣ ክርስቶስ ያለ ሙሴ፣ ወንጌል ያለ ኦሪት አይራባችሁም እያሉ በሚያስተምሩት የሐሰት ትምህርት የክርስቶስን ደቀ መዛሙርት ሲያስቸግሩ የኖሩ ዳሩ ግን በ50 ዓ.ም በመጀመሪያ ጊዜ በተደረገው የሐዋርያት ሲኖዶስ ጉባኤ ተወግዘው እንዲለዩ ተደርገዋል፡፡ ይህ ትምህርታቸው ዛሬ ላይ ላሉት ለብዙ የዕምነት ድርጅቶች በተለይም ለአረብ ሰዎች ዕምነት መሠረት የሆነ ቢሆኒም ኢቦኒሲዝም ግን በአምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጠፍቷል፡፡
3. Docetism/ ዶሴቲሰት
እነዚህ ቢጽ ሐሳዊያን ደግሞ ልክ እንደ ዛሬዎቹ መናፍቃን ህሙማንን እንፈውሳለን፣ ለምጻምን ከለምጹ እናነጻለን እያሉ በምትሀት እና በጥንቆላ መንፈስ የሚሰሩ፣ ነገር ግን ክርስቶስ በሥጋ አልመጣም፣ አልተገለጠም በማለት የውሸት ትምህርታቸውን የሚያሰራጩ እራሳቸውን ነቢያት እያሉ የሚጠሩ ናቸው፡፡ ለእነዚህ መናፍቃን ትምህርትም