03/08/2017
ስምንትና መጽሐፍ ቅዱስ (8 8 8)
8/ 8/ 08 ዓ.ም. ተጻፈ
በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ
አበው በብኂላቸው ሰኔና ሰኞ እንዲሉ ብዙዎች ዛሬ ቀኑ 8
ወሩ 8 ዓመቱ 2008 ነውና ሲወያዩበት ሐሳባቸውን
ሲሰጡበት ሳይ እስቲ እኔም ስለ ስምንት ቊጥር በጥቂቱ
ልጻፍ አልኍ፤ በቅዱስ መጽሐፍ ላይ ቊጥሮች በምሳሌነት
በብዙ ስፍራ ላይ ተጠቅሰው እናነብባለን፤ ሰባት እንደ
ፍጹም ቊጥር ቀዳሚውን ስፍራ ሲይዝ ሌሎችም
ቊጥሮች ብዙ ነገራትን ለምሳሌ ሱባኤያትን፣ የአንድን
ምስጢር በማጉላት የሚያመላክቱ ሲኾኑ ለምሳሌ ያኽል
እንኳ 666 የሚለውን ቊጥር ዮሐንስ በራእዩ በምዕ 13፡
16-18 የአውሬውም ስም ወይም የስሙ ቍጥር አድርጎ
ሲገልጽ ይልቁኑ አእምሮ (ዕውቀት) ያለው የአውሬውን
ቍጥር ቈጥሮ እንዲረዳው ይጽፋል፡፡
መጻሕፍተ ብሉያት የተጻፈበት የዕብራይስጥ ቋንቋ፣
መጻሕፍተ ሐዲሳት የተጻፈበት የግሪክ፣ ቋንቋና ጥንታዊዉ
የኢትዮጵያ የግእዝ ቋንቋ (አ. በ፣ ገ፣ ደ …) ወደ (ሀ፣ ለ፣
ሐ፣ መ…) ሳይቀየር ፊደላቱ እያንዳንዳቸው ፊደላት
ቊጥርም ጭምር ናቸውና በውስጣቸው ብዙ ረቂቅ የኾኑ
ምስጢራትን እንዳመቁ ዛሬ ድረስ እነዚኽ ጥንታውያን
ቋንቋዎች የአጥኚ ያለኽ እያሉ ዮሐንስ እንዳለው አእምሮ
(ዕውቀት) ያላቸው ልባሞችን ይጣራሉ፡፡
1ኛ) መነሻዬ 8 ቊጥር ነውና ይኽ ቊጥር በመጽሐፍ
ቅዱስ ላይ የተጠቀሰ ሲኾን፡- ከዚኽ መኻከል የጥፋት
ውሃ በምድር ላይ በወረደ ጊዜ ከመጣው መቅሠፍት
በመርከብ ውስጥ ኾነው የተረፉት የሰዎች ብዛት 8 ብቻ
ነበር፤ ይኸውም ኖኅ ከነሚስቱ፤ ሦስቱ ልጆቹ ሴም፣ ካም፣
ያፌት ከነሚስቶቻቸው በአጠቃላይ ስምንት ነፍሳት ነበሩ፤
ከመርከብም ከወጡ በኋላ እግዚአብሔር “ብዙ ተባዙ
ምድርንም ምሏት” ብሎ ስምንቱንም ባርኳቸዋል (ዘፍ 8፡
18፤ 9፡1)፤ ቅዱስ ጴጥሮስም በመልእክቱ “ጥቂቶች
ማለት ስምንት ነፍስ በውሃ የዳኑበት መርከብ ሲዘጋጅ፥
የእግዚአብሔር ትዕግሥት በኖኅ ዘመን በቈየ ጊዜ ቀድሞ
አልታዘዙም” በማለት ስምንቱንም ያነሣቸዋል (1ኛ ጴጥ
3፡20)፡፡ ስምንቱ ሰዎች የዳኑባት መርከብ በወንጌል፣
በጥምቀት፣ በእመቤታችን፣ በመስቀል፣ በትንሣኤ
ስትመሰል ስምንቱ ደግሞ ባመኑ በምእመናን ተመስለው
ይተነተናሉ፡፡
2ኛ) ቀደምት ሊቃውንትም የእያንዳንዱን ሰዓት ምሳሌነት
በተነተኑበት ድንቅ የብራና መጽሐፍ ላይ፤ ስምንትን
በስምንቱ ሰዎች፣ በስምንቱ የምድር መኣዝናት ሲመስሉ፡-
“፰ ሰዓተ መዓልት ይተረጐም በ፰ ነፍሳት እለ ድኅና
እምአስራበ እይኅ ወበ፰ አጽናፈ ዓለም ዘውእቶሙ ጽባሕ፤
ወዓረብ፤ ሰሜን ወደቡብ፤ መስዕ ወአዜብ ባሕር
ወሊባ” (ስምንተኛው የቀን ሰዓት ከጥፋት ውሃ በዳኑ
በስምንቱ ነፍሳት (ሰዎች) ይተረጐማል፤ ዳግመኛም
በስምንቱ የዓለም ዳርቾች እኒኽም ምሥራቅና ምዕራብ፣
ሰሜንና ደቡብ፣ መስዕ (ሰሜን ምሥራቅና)፣ አዜብ
(ደቡብ ምዕራብ)፤ ባሕር (ሰሜን ምዕራብና) ሊባ (ደቡብ
ምሥራቅ) ይተረጐማል) ብለው ተንትነውታል፡፡ በመኾኑም
ቊጥር 8ን ስናስብ አራቱን ዐበይት መኣዝናት አራቱን
ንዑሳን መኣዝናትን የፈጠረውን አምላክ እናመሰግናለን፡፡
3ኛ) ሌላው ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብ
እንደምንገነዘበው ልዑል እግዚአብሔር አብርሃምን
ከወገኖቹ ለይቶ ከመረጠውና ቃል ኪዳኑን በርሱና በዘሩ
እንደሚያደርግ ከነገረው በኋላ የዚኽ ምልክት እንዲኾን
ወንዶች ኹሉ በስምንተኛው ቀን እንዲገዘሩ ትእዛዝን
ሰጥቶታል፡፡ ይኸውም በዘፍ 17፡12 ላይ “የስምንት ቀን
ልጅ ይገረዝ በቤት የተወለደ ወይም ከዘራችሁ ያይደለ
በብርም ከእንግዳ ሰው የተገዛ፥ ወንድ ሁሉ በትውልዳችሁ
ይገረዝ” ብሎ፡፡ በስምንተኛው ቀን ግዝረት እንዲፈጸም
የታዘዘው የብሔረ ኦሪት ትእዛዝ ሥጋዊና መንፈሳዊ
ጥቅሞችን ይዟል፡፡ በቅዱሳት መጻሕፍት ምስጢር
የተራቀቁ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን
መተርጒማን ሊቃውንት ከፍ ብሎ በዘጠኝ በዐሥር ዝቅ
ብሎ በስድስት በሰባት ሳይል ስለምን ሰው በተወለደ
በስምንት ቀን ይገዘር ብሎ ያዘዘበትን ምክንያት ሲተነትኑ
“ከፍ ብሎ በዘጠኝ በዐሥር ቀን ቢኾን አካሉ
ይጠነክራልና ጸንቶ ባመመው ነበርና ቊስል እንዳይኾንበት
ነው፤ ዝቅ ብሎ በስድስት በሰባት ቀን ቢኾን አካሉ
ልሕሉሕ (ስስ) ነውና ደም አፍትቶበት ይሞታል ብሎ ስለ
ርኅራኄ ሲኾን ምስጢሩ ግን የስምንቱ ብሔረ ኦሪት ሕገ
ምግብና ሲፈጸም ግዝረተ ነፍስ ለሰው እንዲሰጥ
ለማጠየቅ” በማለት ያመሰጥሩታል፡፡
በ፲፱፻፴፭ (1935) እ.ኤ.አ ፕሮፌሰር ኤች ሀም ስለ
ቫይታሚን ኤ ባጠናው ጥናት ላይ እንደገለጸው ቫይታሚን
ኤ ጉበታችን ፕሮትሮምቢን የሚባል ንጥረ ነገር
እንዲያመርት የመደገፍ ሐላፊነት አለበት፤ የቫይታሚን ኤ
ዕጥረት ካለብን የፕሮትሮምቢን ዕጥረት ይከሠትና ደም
መፍሰስ ሊከሠት ይችላል፡፡ እንደ ጥናቱ ገለጻ ዐዲስ
በተወለደ ወንድ ልጅ ሕይወት ውስጥ ከዐምስተኛው ቀን
እስከ ሰባተኛው ብቻ ቫይታሚን ኬ (በአንዠታችን ውስጥ
በሚገኝ ባክቴሪያ የሚመረተው) በበቂ መጠኖች ብቻ
ሲኾን የሚገኘው ይኽ ቫይታሚን ኬ ከፕሮትሮምቢን ጋር
በመቀናጀት የደም መርጋትን ይረዳል፤ ይኽም
በማንኛውም የቀዶ ጥገና ሥነ ሥርዐት ውስጥ በጣም
አስፈላጊ ነው፤ ሆልት እና ሚክንቶሽ ሆልት “ፔዲያትሪክስ”
በሚለው ሥራቸው ውስጥ እንደተነተኑት ዐዲስ የተወለደ
ሕፃን በሕይወቱ ኹለተኛውና ዐምስተኛው ቀናት ውስጥ
በልዩ ኹኔታ ለደም መፍሰስ የመጠቃት ዕድል አለው…
በዚኽ ጊዜ የሚከሠት የደም መፍሰስ ምንም እንኳን
ተጽዕኖ ባይኖረውም አንዳንድ ጊዜ በጣም ሰፊ ሲኾን
በውስጥ የሰውነት አካላት በተለይም በአንጐላችን ላይ
ከባድ ጒዳት የማድረስና እስከ ሞትም ሊዳርግ ይችላል
ብለዋል፡፡ በሚያስደንቅ መልኩ በስምንተኛው ቀን በትክክል
የሚገኘው የፕሮትሮምቢን መጠን ከመደበኛው መቶ በመቶ
100% ከፍ ይላል፤ ይኽም ቀዶ ሕክምና ማድረግ ካለበት
ስምንተኛው ቀን ትክክለኛው ጊዜ ነው፤ የቫይታሚን ኬ እና
የፕሮትሮምቢን ደረጃቸውን የሜዲካል ዶክተር የኾኑት
ኤስ. አይ. ማክሚለን “None of These Diseases”
በሚለው መጽሐፋቸው ላይ በትክክል ገልጸዋል፡፡
4ኛ) በተጨማሪ ስምንት ስናስብ የሚገርመው መጻሕፍተ
ሐዲሳትን የጻፉት ስምንቱ ማለት (ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣
ሉቃስ፣ ዮሐንስ፣ ጳውሎስ፣ ጴጥሮስ፣ ያዕቆብ፣ ይሁዳ)
ናቸውና ይኽነን እናስባለን፡፡
5ኛ) ስምንት ስናነሣ ሌላው የምናስበው ድንቅ ነገር
ጌታችን በተወለደ በስምንተኛው ቀን ስሙ አስቀድሞ
በመልአኩ ለእመቤታችን እንደተነገረ ኢየሱስ ተብሎ
መጠራቱን ወንጌላዊዉ ሉቃስ ገልጦልናልና ስምንትን
ስናስብ ይኽነንም እናስበዋለን (ሉቃ 2፡21)
በአቡሻሕር የቊጥር ትምህርት የተራቀቁት ቀደምት
የኢትዮጵያ መተርጒማን ሊቃውንት 666 የሚለው
የአውሬው (የሐሳዌ መሲሕ) ቊጥርና ስሙ
“መርምያዋዖስ” መኾኑን የዕብራይስጡን አልፋ ቤት
ቀመረ ምስጢር ቀድመው አውቀው (ሜም 40፤ ሬስ
200፤ ሜም 40፤ ዮድ 10፤ ዋው 6፤ ዔ 70፤ ሳን 350)
ቊጥር ናቸውና በድምሩ 666 እንደኾነ እንደደረሱበት
በራእይ ትርጓሜ ተጽፎልናል፡፡
የዚኽ ቊጥር ተቃናኒ ደግሞ 888 ነው ይላሉ ፤ በእጅጉ
የሚያስደንቀው በጥንት ጊዜ የነበሩት የግሪክ የነገረ
መለኮት ቀደምት 888 ቊጥርን የጌታችን ስሙ አድርገው
ይተረጒሙታልና፤ ይኸውም አስቀድመን እንዳየነው
በዕብራይስጥ፣ በግሪክ፣ የግእዝ (አ. በ፣ ገ፣ ደ …) ወደ
(ሀ፣ ለ፣ ሐ፣ መ…) ሳይቀየር ፊደላቱ እያንዳንዳቸው
ቊጥርም ጭምር ናቸው፤ በግሪክ ቋንቋ የፊደላት የቊጥር
ልኬት “ኢየሱስ” የሚለው በፊደል ሲጻፍ፡-
I H S O U S ተብሎ ነው (I H S O U S (iota, eta,
sigma, omicron, upsilon, sigma)) የፊደላቱም ሥያሜ
(አዮታ፣ ኢታ፣ ሲግማ፣ ኦሚክሮን፣ ኡፕሲሎንና ሲግማ)
ናቸው፤ እነዚኽ የጽርዕ ቋንቋ ፊደላት የያዟቸው ቊጥር
ሲደመሩ 888 ይሰጣሉ፤ ይኸውም አዮታ- 10፤ ኢታ- 8፤
ሲግማ- 200፤ ኦሚክሮን- 70፤ ኡፕሲሎን- 400፤
ሲግማ-200 አጠቃላይ ድምር 10+8+200+70+400
+200= 888 ይሰጣልና፤ በጽርዕ ሊቃውንት 888 ቊጥር
ኢየሱስ የሚለው የፊደሉ ቊጥር ነውና፤ ለ888 ቊጥር
የተለየ ክብር ይሰጣሉ፡፡
በዕብራይስጥ ቋንቋ በነቢዩ በሚልክያስ በምዕ 3፡6 ላይ
“እስመ አነ አምላክ ዘኢይትዌለጥ” (እኔ እግዚአብሔር
አልለወጥም) የሚለው በዕብራይስጥ (Ani YHVH, Lo
shaniti) ሲኾን በዕብራይስጥ ቃላቱ ሲደመሩ 888ን
ይሰጣሉ፤ ይኸውም በቅዱስ ጳውሎስ ቃል “ኢየሱስ
ክርስቶስ ትናንትና ዛሬ እስከ ለዘላለምም ያው ነው” ተብሎ
ተነግሮለታልና (ዕብ 13፡8) የጌታችንን ስም ያጠይቃል
ብለው ያመሰጥራሉ፡፡ በተመሳሳይ መልኩ በመዝ 97፡3
ላይ በዕብራይስጡ (Yeshoth Elohenu) “የአምላካችንን
ማዳን አዩ” የሚለውም እንደዚኹ ይኽነን ቊጥር (888)
እንደሚሰጥ ይኽነን በጥልቀት ያጠኑ ይተነትኑታል፡፡
የትዕግሥት አባት ኢዮብ በምዕ 14፡5 ላይ “የሰው ዕድሜ
የተወሰነ ነው፥ የወሩም ቍጥር በአንተ ዘንድ ነው፥ ርሱም
ሊተላለፈው የማይችለውን ዳርቻ አደረግህለት” እንዳለ
በመቀጠልም ጠቢቡ ሲራክም “እግዚአብሔር ወሀቦሙ
ለሰብእ ዓመታተ ወመዋዕለ በኊልቊ” (እግዚአብሔር
ለሰዎች ዓመታትና ዘመናትን በቊጥር ሰጣቸው) እንዳለን
ምእመናን ሆይ በተሰጠን የዕድሜ ቊጥር ዕለት ዕለት
መልካም ሥራ እየሠራን ሥጋ ወደሙ እየተቀበልን መርዐዊ
ሰማያዊ ኢየሱስ ክርስቶስን መብራታችንን አብርተን
እንድንጠብቀው ያስፈልጋል፡፡
ይልቁኑ ሐሳዌ መሲሕን ድል የነሡ፣ ለምስሉ ያልሰገዱ፣
ዘመር ዘመስ የሚለውን የ666ን ምልክት በእጃቸው
ያልተከተቡ በግንባራቸው ያልጻፉ ኹሉ በእግዚአብሔር
መንግሥት ከብረው እንደሚኖሩ ዮሐንስ በራእዩ 15፡2 ላይ
“ወእምዝ ርኢኩ ባሕረ እንተ ትመስል ከመ
ማኅው…” (በእሳትም የተቀላቀለውን የብርጭቆ ባሕር
የሚመስለውን አየሁ፥ በአውሬውና በምስሉም በስሙም
ቍጥር ላይ ድል ነሥተው የነበሩት የእግዚአብሔርን በገና
ይዘው በብርጭቆ ባሕር ላይ ሲቆሙ አየሁ) እንዳለን ዛሬ
በዓለም የሐሳዌ መሲሕ መንገድ ጠራጊዎች እንደ አሸን
የፈሉበትና ምልክቱን በሰው እጅና ግንባር ለመቅበር
የተነሣሡበት ጊዜ ነውና ሰውነታችንን በመላ ለአውሬው
ንቅሳት ሳይኾን ለፈጣሪያችን ለክርስቶስ ብቻ መስጠት
የሚገባን ጊዜ ነው፡፡
የጊዜያት ባለቤት መድኀኔ ዓለም ክርስቶስ በምሕረቱ
ይጐብኘን፡፡
ከመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ