29/01/2026
ቀለሜ!
(በዘመኑ ዮሀንስ የተፃፈ)
ትዝ ይለኛል ያኔ...!
በእሳር መሃል ባለች ቀጭን መንገድ ሄጄ፥
ወደ ፀሎት ቤቴ ምመጣው ማልጄ።
ከነ ታተይ ጋራ በማልዳው ተጉዘን፥
አንድ ራስ በቆሎ ለስጦታ ይዘን።
ባባየም ቸኩሎ ፀሎት ቤት ሲመጣም፥
የፈለገ ቢሆን ባዶ እጁን አይወጣም።
መንደርተኛው ሁሉ በጠዋት ተጠራርቶ፤
ፀሎት ቤት ይገኛል ሁሉም ቤቱን ዘግቶ።
በየደጃፉኮ ሰው ነበረ ያኔ፤
ለፀሎት ማይተኛው የዋሁ ወገኔ።
ይፀልይ ነበረ ቃል አይጠፋም ከአፉ፤
ወዙ ይታይ ነበር ክርስትና ዘርፉ።
ዛሬ ሁሉም ቀረ ተቀየረ አለሙ፤
እነ ባባ ታተይ ጥለውን ተመሙ።
እየተጠራሩ ሄዱና አንድ ሰሞን፤
ሁሉም ዘመም አለ ጠፋ ሚከውነን።
ክርስትናችንን በደም ነው ያቆዩት፤
ይህን ክፉ ዘመን እንኳንም አላዩት።
እላለሁ አንዳንዴ... ሲጨንቀኝ በምሬት፤
ሁኔታው በሙሉ ሲሆንብኝ እሬት።
በገበታ ዙሪያ ቤተሰብ ይቀርባል፤
በአንድ መስሪያ ብቻ አብሮ ይመገባል።
ቤት ያፈራውን እየተቋደሰ፤
በአንድነትኮ ነው ከቀን የደረሰ።
የአባት ተረት ተረት ነበር ማታ ማታ፤
የነሙሴን ታሪክ ሰምተን በደስታ።
ነበር እድገታችን...
ዛሬ ሁሉም ነገር ቀለሙን ቀይሯል፤
አንድነትን ፈርቶ ሰው ብቻውን አድሯል።
ተረት የሚነግር ትልቅ ሰውም አልቋል፤
ሰሚ ጆሮም የለ ሁሉም ተናንቋል።
እኔ አላውቅም እንጃ...
ቀለሙ ተሟጧል ሁሉም በደረጃ።
የነባባ ምክር የታተይ ጨዋታ፤
የምሽቱ ድባብ የጎረቤት ደስታ።
አርሂቡ ሚባለው ቃሉም ተዘንግቷል፤
እኔ እንጃ ሰው ሁሉ አብሮ መሆን ጠልቷል።
ልጆች እንደቀድሞው እደጅ አይዘምሩም፤
ምክር ለመቀበል ትልቅ ሰው አይጠሩም።
ልጆች ጎምበስ ብለው ያባት እግር አያጥቡም፤
እኔ እንጃ ወጣቶች ቤት በግዜ አይገቡም።
እናቶች ፀሎት ቤት የሉም አይታዩም፤
እነ ታይቶ አላቂ እስኪመሽ አልቆዩም።
አባቶች በመንደር አይጎበኛኙም፤
ፀሎት ቤት በአንድ ላይ በጠዋት አይገኙም።
ጥለውን ሄደዋል..
ምክር ለመቀበል ከማን ጋር እንዋል?
የፀሎት ቤት ወምበር ስነ ስርአት ጎድሎታል፤
ከእነታተይ ጋራ መቃብር ወስዶታል።
መሪና ተመሪ እኩል ነው ሰልፋቸው፤
አንተም ተው አንችም ተይ የሚል ጠፍቶባቸው።..ይነታረካሉ፤
ሰላም ያየንበት ትዝ አለኝ ገጠሩ፤..ትዝ አለኝ!
መፅሀፍ ቅዱሴ ከእጄ ማይለየው፤
ከወፎች ጋር እኩል ማልዳ ምፀልየው።
ጠርገውኝ ማልጠፋ ነበርኩ ከመቅደሱ፤
አስታውሰዋለሁ ሲቀርበኝ መንፈሱ።
እኔ አላውቅም እንጃ ዛሬ ሁሉም ደክሟል፤
የሰው ልብ በጭንቀት በድንግዝግዝ ታሟል።
እኔ አላውቅም እንጃ..
ቀለሜ ተፍቆ ገረጣሁ መሰለኝ፤
አያስጨንቀኝም ድካም ሲሰልለኝ።
መካሪ አያሳጣህ የሚባለው ነገር፤
ዛሬም ሰው አልገባው በድካም ሲቸገር።
እስኪ እንመካከር ትልቅ ሰው እንስማ፤
በሬው አይደለም ወይ ወይፈን የሚያቀና።
እንኳን ጆሮ ቀርቶ ምጣድም ይሰማል፤
አባቶችን መስማት ለብዙ ይጠቅማል።
አቃታቸው መሰል እነሱም ዝም አሉ፤
በዚህ ክፉ ዘመን አውሩ ዝም አትበሉ።
ያስጨንቃል እንጅ መንፈሱም ይሸሻል፤
የአባቶች ዝምታ ትውልድ ያበላሻል።
የነባባ ለበቅ የታተይ ቁንጥጫ፤
ለዚህ ዘመን ነበር ስነስርዓት ማጠጫ።
አባቶች ምከሩ ዝምታ ይጎዳል፤
ይህን አዲስ ትውልድ ወደ ሞት ይነዳል።
በመላው አለም ላይ በህይወት ያላችሁ፤
ያን የቀድሞ ዘመን ይመልስላችሁ።
ያን የቀድሞ ፍቅር ይመልስላችሁ።