ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት-Nehemiah Christian Service Ministry

ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት-Nehemiah Christian Service Ministry Contact information, map and directions, contact form, opening hours, services, ratings, photos, videos and announcements from ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት-Nehemiah Christian Service Ministry, Religious Center, Addis Abeba, Addis Ababa.

29/01/2026

ቀለሜ!

(በዘመኑ ዮሀንስ የተፃፈ)

ትዝ ይለኛል ያኔ...!

በእሳር መሃል ባለች ቀጭን መንገድ ሄጄ፥
ወደ ፀሎት ቤቴ ምመጣው ማልጄ።

ከነ ታተይ ጋራ በማልዳው ተጉዘን፥
አንድ ራስ በቆሎ ለስጦታ ይዘን።

ባባየም ቸኩሎ ፀሎት ቤት ሲመጣም፥
የፈለገ ቢሆን ባዶ እጁን አይወጣም።

መንደርተኛው ሁሉ በጠዋት ተጠራርቶ፤
ፀሎት ቤት ይገኛል ሁሉም ቤቱን ዘግቶ።

በየደጃፉኮ ሰው ነበረ ያኔ፤
ለፀሎት ማይተኛው የዋሁ ወገኔ።

ይፀልይ ነበረ ቃል አይጠፋም ከአፉ፤
ወዙ ይታይ ነበር ክርስትና ዘርፉ።

ዛሬ ሁሉም ቀረ ተቀየረ አለሙ፤
እነ ባባ ታተይ ጥለውን ተመሙ።

እየተጠራሩ ሄዱና አንድ ሰሞን፤
ሁሉም ዘመም አለ ጠፋ ሚከውነን።

ክርስትናችንን በደም ነው ያቆዩት፤
ይህን ክፉ ዘመን እንኳንም አላዩት።

እላለሁ አንዳንዴ... ሲጨንቀኝ በምሬት፤
ሁኔታው በሙሉ ሲሆንብኝ እሬት።

በገበታ ዙሪያ ቤተሰብ ይቀርባል፤
በአንድ መስሪያ ብቻ አብሮ ይመገባል።

ቤት ያፈራውን እየተቋደሰ፤
በአንድነትኮ ነው ከቀን የደረሰ።

የአባት ተረት ተረት ነበር ማታ ማታ፤
የነሙሴን ታሪክ ሰምተን በደስታ።

ነበር እድገታችን...

ዛሬ ሁሉም ነገር ቀለሙን ቀይሯል፤
አንድነትን ፈርቶ ሰው ብቻውን አድሯል።

ተረት የሚነግር ትልቅ ሰውም አልቋል፤
ሰሚ ጆሮም የለ ሁሉም ተናንቋል።

እኔ አላውቅም እንጃ...
ቀለሙ ተሟጧል ሁሉም በደረጃ።

የነባባ ምክር የታተይ ጨዋታ፤
የምሽቱ ድባብ የጎረቤት ደስታ።

አርሂቡ ሚባለው ቃሉም ተዘንግቷል፤
እኔ እንጃ ሰው ሁሉ አብሮ መሆን ጠልቷል።

ልጆች እንደቀድሞው እደጅ አይዘምሩም፤
ምክር ለመቀበል ትልቅ ሰው አይጠሩም።

ልጆች ጎምበስ ብለው ያባት እግር አያጥቡም፤
እኔ እንጃ ወጣቶች ቤት በግዜ አይገቡም።

እናቶች ፀሎት ቤት የሉም አይታዩም፤
እነ ታይቶ አላቂ እስኪመሽ አልቆዩም።

አባቶች በመንደር አይጎበኛኙም፤
ፀሎት ቤት በአንድ ላይ በጠዋት አይገኙም።

ጥለውን ሄደዋል..
ምክር ለመቀበል ከማን ጋር እንዋል?

የፀሎት ቤት ወምበር ስነ ስርአት ጎድሎታል፤
ከእነታተይ ጋራ መቃብር ወስዶታል።

መሪና ተመሪ እኩል ነው ሰልፋቸው፤
አንተም ተው አንችም ተይ የሚል ጠፍቶባቸው።..ይነታረካሉ፤
ሰላም ያየንበት ትዝ አለኝ ገጠሩ፤..ትዝ አለኝ!

መፅሀፍ ቅዱሴ ከእጄ ማይለየው፤
ከወፎች ጋር እኩል ማልዳ ምፀልየው።

ጠርገውኝ ማልጠፋ ነበርኩ ከመቅደሱ፤
አስታውሰዋለሁ ሲቀርበኝ መንፈሱ።

እኔ አላውቅም እንጃ ዛሬ ሁሉም ደክሟል፤
የሰው ልብ በጭንቀት በድንግዝግዝ ታሟል።

እኔ አላውቅም እንጃ..

ቀለሜ ተፍቆ ገረጣሁ መሰለኝ፤
አያስጨንቀኝም ድካም ሲሰልለኝ።

መካሪ አያሳጣህ የሚባለው ነገር፤
ዛሬም ሰው አልገባው በድካም ሲቸገር።

እስኪ እንመካከር ትልቅ ሰው እንስማ፤
በሬው አይደለም ወይ ወይፈን የሚያቀና።

እንኳን ጆሮ ቀርቶ ምጣድም ይሰማል፤
አባቶችን መስማት ለብዙ ይጠቅማል።

አቃታቸው መሰል እነሱም ዝም አሉ፤
በዚህ ክፉ ዘመን አውሩ ዝም አትበሉ።

ያስጨንቃል እንጅ መንፈሱም ይሸሻል፤
የአባቶች ዝምታ ትውልድ ያበላሻል።

የነባባ ለበቅ የታተይ ቁንጥጫ፤
ለዚህ ዘመን ነበር ስነስርዓት ማጠጫ።

አባቶች ምከሩ ዝምታ ይጎዳል፤
ይህን አዲስ ትውልድ ወደ ሞት ይነዳል።

በመላው አለም ላይ በህይወት ያላችሁ፤
ያን የቀድሞ ዘመን ይመልስላችሁ።
ያን የቀድሞ ፍቅር ይመልስላችሁ።

የነህምያ የአገልግሎት ሕብረት  ታሪካዊ ዳራ….(ከነህምያ የአገልግሎት ሕብረት መመሪያ ሰኔ 2015 ዓ.ም ገፅ 2 ላይ የተወሰደ )ለአሁኑ የነህምያ የአገልግሎት ሕብረት እንቅስቃሴ እንደ እርሾ ...
19/01/2026

የነህምያ የአገልግሎት ሕብረት ታሪካዊ ዳራ….

(ከነህምያ የአገልግሎት ሕብረት መመሪያ ሰኔ 2015 ዓ.ም ገፅ 2 ላይ የተወሰደ )

ለአሁኑ የነህምያ የአገልግሎት ሕብረት እንቅስቃሴ እንደ እርሾ ሆነው ያገለገሉ የተለያዩ መንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ቀደም ሲል ይደረጉ ነበር። ከእነዚህ እንቅስቃሴዎች የመጀመሪያው በ1994-1995 ዓ.ም ሲደረግ የነበረው የመነቃቃትና ተሃድሶ የወንጌል ጥረት በአቶ አማረ ሞላ፣ አቶ አዳነ ጣፈጠ፣ በአቶ ምህረቴ ብርሃኑ፣ በአቶ ግርማ አበባው፣ በአቶ ደሳለኝ መሰለ እና ሌሎችም በርካታ አስተባባሪዎች በምሳሌነት ይጠቀሳል።

እነዚህ ወጣት ተማሪዎች ከወልቂጤ ከተማ የትምህርት ቆይታ በኁላ ለዕረፍት ወደ ቤተሰብ በሄዱበት ጊዜ የገጠር አብያተ ክርስቲያናትን ለማገልገል ያደረጉትን ጥረት እግዚአብሔር እንደባረከው በወቅቱ ከነበሩ ምስክሮች ማረጋገጥ ይቻላል። ይህ ስም የለሽ ውጤታማ እንቅስቅሴ አገልግሎቱን ባካሄደበት ሁለተኛው ቦታ በመዳሎ 7ተኛ ቀን አድቬንቲስት ቤተ ክርስቲያን የተደረገውን በጣም የሚባርክ ፕሮግራም ተከትሎ የወቅቱ የቤ/ክኗ መሪ የነበረው ፓ/ር ተስፋሁን ተገኘ ነህምያ ብያችኋለሁ ሲል ለእንቅስቅሴው ስም አወጣለት።

ይህ ነህምያ የሚል ስያሜ ያገኘው መንፈሳዊ ግለት የነበረበት እንቅስቅሴ ቀጥሎ በተለያዩ ቤተ ክርስቲያናት ባደረጋቸው አገልግሎቶች በእርሻ ድንበር የተጣሉትን ለማስታረቅ፤ የደከሙትን ምዕምናን ለማጠናከር፤ የፈረሱ ቤ/ክናትን ለማደስ ያደረገው ጥርት ዛሬም ድረስ የሚታወስ ነው።

አሁን ላለው የነህምያ የአገልግሎት ሕብረት መመስረት የማይናቅ አስተዋጻዖ አድርጓል ተብሎ የሚታሰበው ሌላኛው ተጠቃሽ እንቅስቅሴ በ2007-2008 ዓም በወልቂጤ ቁጥር ሁለት 7ተኛ ቀን አድቬንቲስት ቤ/ክ የቀድሞ ዘማሪዎች አስተባባሪነት የተከናወነው አነቃቂ ፕሮግራም ሲሆን ይህም በዋናነት በዶ/ር አበበ ምህረት፣ ዋለለኝ ተገኘ፣ ፈንታሁን መላኩ እና ጓደኞቻቸው አስተባባሪነት ሲደረግ የነበረ ነው። ይህ አገልግሎት ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት የሚል ስያሜ ያልነበረው ሲሆን ይህም እንቅስቃሴ በወቅቱ በገጠመው በቤተ ክርስቲያንዋ መሪዎች እና በአንዳንድ አገልግሎቱን በተሳሳተ መንገድ በተረዱ ግለሰቦች ተቃውሞ ምክንያት ለመዳከም እና ለመቆም ተዳርጓል።

እነዚህን ከላይ የተጠቀሱትን መልካም እርሾዎች እንደ መነሻ አድርጎ የአሁኑ የነህምያ አገልግሎት ሕብረት እንቅስቃሴ በወቅቱ ምንም አይነት የሚያደፋፍር ነገር ሳይኖር ይልቁንም የነበሩትን ተግዳሮቶች ሳይፈራ በአቶ ግርማ አበባው እና በአቶ እንየው አበባው ዋና አስተባባሪነት ከድሮው በተለየ ሁኔታ ሁሉንም አሳታፊና ሰፊ የሆነ ኮንፍረንስ በጩመሌ 7ተኛ ቀን አድቬንቲስት ቤ/ክ ለማከናወን ወስኖ መዘጋጀት ጀመረ።

ይህንም ለማሳካት ይረዳው ዘንድ ሰዎችን ከየስፍራው ማሰባሰብ ተያያዘው። በወቅቱ ይህን ጥሪ ተከትሎ ሀሳቡን ተቀብለው የዚህ ታሪካዊ ኮንፍረንስ ዋና አካል ለመሆን ከፈቀዱት መካከል ዶ/ር ፈቃዱ በላቸው፣ ሀብታሙ አበባው፣ ታደል ጮራ፣ ባንቺአየሁ ምህረት፣ ምትኩ ሙላት፣ ስመኝሽ ወርቁ፣ መልካሙ በላቸው፣ ሲሳይ በቀለ፣ አቶ ጌጡ ደርሶ እና ሌሎችም በዝግጅት ሂደት ውስጥ ግንባር ቀደም ተሰላፊ የነበሩ ሲሆን ፕሮግራሙ ከተጀመረ በኋላ ደግሞ በተለያዩ መንገድ ያገለገሉና ከዛም በኋላ ባለው ሂደት አብረው የዘለቁ ፈንታሁን መላኩ፣ መታገስ አጋዤ፣ ፓ/ር አንጋው ጌታሁን፣ ብርሃኑ ሞገስ፣ ብርሃኑ ታከለ እና ሌሎች በርካታ ሰዎችን መጥቀስ ይቻላል። የሆነ ሆኖ ከላይ የተጠቀሰው ታሪካዊ እና በብዙ በረከት የታጀበው ፕሮግራም ተከናውኗል። በዚህ አንድ ሳምንት በፈጀው ታሪካዊ ኮንፍረንስ ከዝግጅቱ ጀምሮ እስከፕሮግራሙ ማብቂያ ድረስ በሂደቱ በርካታ ሠዎችን ያሳተፈ ሲሆን በጊዜው የቤት ለቤት ጉብኝት በተለያዩ ርዕሶች ደግሞ ጥልቅ ውይይት ከህዝቡ ጋር ተደርጓል። ለአመታት ከቤ/ክን ርቀው የነበሩ ሰዎች ወደ ቤ/ክን ተመልሰዋል። አነስተኛም ቢሆን የጤና አገልግሎት ተሰጥቷል። በቢሎ ዋዩ አድቬንቲስት ት/ቤት ግቢ በመገኘት ጉብኝት የተደረገ ሲሆን በሜዳው እግር ኳስ፣ መርብ ኳስን ጨምሮ በመጫወት የቧረቅን ሲሆን ሽማግሌዎች ጋርም በትምህርት ቤቱ ዙሪያ በስፍራው ውይይት ተደርጓል። በማጠቃለያው ፕሮግራም በውላጋ ባህር ጥምቀት ተከናውኗል።

ይህ ቅዱስ እንቅስቃሴ ምንም እንኳን የማደስ ፍላጎት መኖሩን የሚያሳይ ወደ ቀድሞው እንመለስ የሚል ዋና መሪ ቃል ይዞ ሁሉንም አገልግሎት ቢያደርግም ቡድኑ የራሱ የሆነ መጠሪያ ስም ግን አልነበረውም። ይህም እንቅስቃሴ እንደማንኛውም ድርጅት የራሱ የሆነ ስምና አደረጃጀት ያስፈልገው ስለነበር የመጀመሪያውን ውይይት በዛው ኮንፈረንስ በተድረገበት በውላጋ አካባቢ በአቶ ጌታሁን ሀብቴ ቤት በማድረግ ለስም ስያሜና ሌሎች ተያያዥ ነገሮች ውሳኔ ለመስጠት ባስቀመጠው የመገናኛ ቀነ ቀጠሮ መሰረት እንደገና በአቶ ጌጡ ደርሶ ቤት በመገናኘት በጥቅምት ወር 2010 ዓ/ም ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት የሚለውን ስያሜ አግኝቷል። ከዚሁ ጋር ተያይዞ ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት በእንግሊዝኛው አቻ ትርጉም ፍለጋ ውይይቶች የተደረገ ሲሆን በመጨረሻም Nehemiah Chrsitian Service የሚል ስያሜ የወጣለት ሲሆን ስያሜውን የተሰጠው በመታገስ አጋዤ አማካይነት ነው። እውቅና ካገኘ በኋላ “Ministry” የሚለው ቃል ተጨምሮበት Nehemiah Christian Service Ministry የሚል ስያሜ ይዟል።

# ኑ በፈረሰው በኩል አብረን እንገንባ

# ጥረቶቻችን ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ግብ ያመራሉ

10/01/2026

“ኤ ማን ኦፍ አፖርቹኒቲ…”

የሐካልያ ልጅ ነህምያ ገናና ዓለምን በሚገዛ የመንግስት መዋቅር ውስጥ ባለሟል ነበር። እግዚአብሔር በልቡ ላስቀመጠው አላማ ከልዕለ ሀያላን ሰገነት እስከ ተራ የህብረተሰብ ለውጥ አራማጅነት፤ ከተደላደለ የህይወት እጣ ፈንታ መዳረሻው እርግጠኛ ወዳልሆነ ህይወት ወርዷል።

ነህምያ በመንፈሳዊ እና በማህበራዊ ህይወት ቅርጽ ያጣን፣ ከአምላክ ፈቃድ የጐደለን ማሕበረሰብ ሁኔታ ለመቀየር ስራውን በጸሎት ጀምሯል። ተቃዋሚዎቹን በዕምነት ተቋቁሟቸዋል። የተነሱበትን የመልካም ነገር ጠሮች በስሜት ሳይሆን በመርህ፣ በተስፋ መቁረጥ ሳይሆን በእስራኤል አምላክ በነበረው እምነት ተዋግቷቸዋል። የህዝቡን ልብ ወደ ቃለ እግዚአብሔር መልሷል። የፈረሰውን አድሷል፤ ሰባራውን ጠግኗል።

በጥቅሉ ነህምያ ለራዕዩ ክንውን፣ በሰማይ የሆነችው የጌታ ፈቃድ በእርሱ ዘመንና ትውልድ ትሆን ዘንድ መልካሚቱን የእግዚአብሔርን እጅ ተደግፎ ያገኛትን መልካም አጋጣሚ ሁሉ ተጠቅሞባታል።

በውጤቱም “ጥበበኞቹም እንደ ሰማይ ጸዳል ብዙ ሰዎችን ወደ ጽድቅ የሚመልሱ እንደ ከዋክብት ለዘላለም ይደምቃሉ” ከተባለላቸው የእምነት ምስክሮች እንደ አንዱ ሆኖ ተጽፎልን ይገኛል።

በዚህ ዘመን ለምንገኝ ለእኛም የዘመኑ ነህምያዎች እግዚአብሔር ተመሳሳይ አላማ አለው። ለእያንዳንዳችን በሰፊው የጌታ የወይን አትክልት ስፍራ ህይወት በኤደን ትታደስ ዘንድ የሚያስችል የከበረ የስራ መስክ አለው።

# ኑ በፈረሰው በኩል አብረን እንገንባ

# ጥረቶቻችን ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ግብ ያመራሉ

የነህምያ የአገልግሎት ሕብረት አርማ ትርጉም….የነህምያ የአገልግሎት ሕብረት አርማ መሠረታውያን ሶስት ሲሆኑ እነሱም የሱፍ አበባ ፣ የዓለም ካርታ እና ዓለምን የሚዞሩ ሶስት ቢጫ መስመሮች ናቸ...
09/01/2026

የነህምያ የአገልግሎት ሕብረት አርማ ትርጉም….

የነህምያ የአገልግሎት ሕብረት አርማ መሠረታውያን ሶስት ሲሆኑ እነሱም የሱፍ አበባ ፣ የዓለም ካርታ እና ዓለምን የሚዞሩ ሶስት ቢጫ መስመሮች ናቸው።
በአርማው ውስጥ ጥቅም ላይ የዋሉት ምልክቶች የየራሳቸው ትርጉም አዝለዋል።

፩. የሱፍ አበባ

በሺህ የሚቆጠሩ የትናንሽ አበባዎች ስብስብ ሲሆን የፀሀይ ብርሃንን እንቅስቃሴ እየተከተለ የሚፈካ፤ በፀሀይ ሀይል እየታገዘ የሚደምቅ አበባ ነው። አንድ የሱፍ አበባ እስከ 2000 የሚጠጉ የየራሳቸው ልዩ ገፅታ ያላቸው ፍሬዎችን ሲያፈራ ልክ እንደማንኛውም ተክል ከፀሀይ የሚያገኘውን ሀይል በመጠቀም በአረንጓዴ ቅጠሉ ምግቡን ያሰናዳል። እኒህ ባለ ልዩ ልዩ ገፅ ፍሬዎችም ለምግብነትና ለመድሃኒትነት የሚውል ዘይት ያመነጫሉ።

ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት የሀይል ምንጭ የሆነውን ክርስቶስን ብቻ በመመልከት በተግባር-ተኮር ሁለንተናዊ የፍቅር አገልግሎት መሰረት ላይ ቆሟል። የሱስን ብቻ ትኩር ብሎ በመመልከት ጌታን ወደሚመስል ክቡር ህይወት ለመለወጥ ይተጋል።

የነህምያ ቤተሰቦች ልክ እንደ ሱፍ አበባዋ ፍሬዎች ልዩ ልዩ ብንሆንም በአንድ ሃሳብ በአንድ ልብ ሆነን በአንዱ መንፈስ አንዱን ጌታ እያገለገልን ሰብአዊነትን ከፍ ለማድረግ እና እግዚአብሔርንን ለማክበር እንኖራለን። በየቀኑ ብዙ ብርሃን ለመቀበል ሳናቋርጥ (የማያቋርጠዉ ፀሎት) በእግዚአብሔር ፊት እንቀርባለን። በእግዚአብሔር ቃል ብርሃን በህይወት ምግብ እየታገዝን ለጌታችን ክቡር መንግስት እናድጋለን። በተስፋው ቃል ተስፋችንን እንጥላለን።

፪. የዓለም ካርታ

የሱፍ አበባው የአፍሪካ አህጉርን (ኢትዮጵያን ) የፊቱ ገፁ ባደረገ የዓለም ካርታ ላይ አርፏል። ኢትዮጵያ የክርስትና ቀደምት አገር ፣ የጊዩን ምንጭ ፣ ፈጣሪ ፈሪ አገር ናት። ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት ምንም እንኳን ጅምሩ በአንድ ስፍራ ቢሆንም ልክ እንደ ጊዩን ውሃ እንደ ጅረቱ ከኢትዮጵያ ተነስቶ ለሰብአዊ ዘር ሁሉ በፍቅር ላይ የተመሰረተው ተግባር- ተኮር የአገልግሎት አድማሱ እንዲሰፋ ይሰራል ።

፫. ሶስት መስመሮች

በነህምያ አርማ ላይ ሶስት ቢጫማ መስመሮች በዓለም ላይ እየዞሩ ተመልላክተዋል ። ቢጫ ቀለም የተስፋ፣ የደስታና የአውንታዊነት ምልክት ሲሆን ሶስት ደግሞ የሙሉነት፣ የፍርድና የፍፅምና መለያ ነው። በመሆኑም ሶስቱ ቢጫማ መስመሮች በመጨረሻው ዘመን ለዓለሙ ሁሉ ሊታወጅ የተገባውን የሶስቱን መላእክት መልእክት ያመላክታሉ። ይህ የዘላለሙ ወንጌል ለሰዎች ሁሉ ይደርስ ዘንድ እግዚአብሔር ለስጋ ለባሽ ከሰጠው ሀላፊነት ሁሉ እጅግ ክቡር ሃላፊነት ነው።

በዚህ ወንጌል የተባረከውን ተስፋችንንና የዘላለም ደስታችንን ይመሰረታል። በማእበል ብንናጥም እግዚአብሔርን ፍሩ ክብርንም ስጡት የተሰኘውን ሀያል ማስጠንቀቂያ በሙሉ ሀይል እናውጃለን።

(ከነህምያ የአገልግሎት ሕብረት መመሪያ
2015 ዓ.ም ገፅ 5 ላይ ተመሰርቶ የተፃፈ )

# ኑ በፈረሰው በኩል አብረን እንገንባ

# ጥረቶቻችን ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ግብ ያመራሉ

አንተ ምንጭ ሆይ.........................…………….እንደ ዮሴፍ ያለ ትንሽ ችግኝ እንዲበቅልልን እንዲያድግልን እንዲያፈራልን አለምልመው 'ስራችንን' እንደገናአንተ ምንጭ ሆይ ፍለ...
30/12/2025

አንተ ምንጭ ሆይ.........................…………….

እንደ ዮሴፍ ያለ ትንሽ ችግኝ
እንዲበቅልልን
እንዲያድግልን
እንዲያፈራልን
አለምልመው 'ስራችንን' እንደገና
አንተ ምንጭ ሆይ ፍለቅና

………………….//……..………

(ዘሁልቁ 21:17፣ ዘፍ 49:22-26፣ ዩሐንስ 4:14)

# ኑ በፈረሰው በኩል አብረን እንገንባ

# ጥረቶቻችን ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ግብ ያመራሉ

20/12/2025

ከሰማይ ፈለቀ....

የሱስ ዝቅ ብሎ በበረት ሲወለድ
እንደ እኔ ያለውን ሀጥዕ ለሁሌ ሲዛመድ
መላእክት ግሩም አሉ ፍጥረት ተደነቀ
የዘላለም ሳይንስ የዘላለም ታሪክ ከሰማይ ፈለቀ
……………………//…………………

# ኑ በፈረሰው በኩል አብረን እንገንባ

# ጥረቶቻችን ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ግብ ያመራሉ

ልጅነትየጠዋት ጮራ ደማቅ ብርሃን፣የተስፋ ማብቀያ የህይወት ውጋገን፣ቡቃያ ነው ለጋ ተክል፣አረንጓዴ ቀንበጥ ለአይን የሚያማልል፣የነገ ሰው የነገ ታሪክ፣ዛሬ በቅሎ የሚያድግበት፣ቡቃያ ነው ትንሽ ...
06/12/2025

ልጅነት

የጠዋት ጮራ ደማቅ ብርሃን፣
የተስፋ ማብቀያ የህይወት ውጋገን፣
ቡቃያ ነው ለጋ ተክል፣
አረንጓዴ ቀንበጥ ለአይን የሚያማልል፣
የነገ ሰው የነገ ታሪክ፣
ዛሬ በቅሎ የሚያድግበት፣
ቡቃያ ነው ትንሽ ተክል የዘር ቦቆልት፣
ቸል ካልነው ካልጠበቅነው፣
ተራ ችግኝ ተራ ዛፍ ነው፣
ግን
የነፍስ ምግብ የነፍስ ጸሃይ ከመገብነው ከሰጠነው፣
ልጅነት የወፍ የአራዊቱ መጠለያ መሸሸጊያ፣
ትልቅ ዋርካ ትልቅ ዛፍ ነው፡፡
……………………….//……………

# ኑ በፈረሰው በኩል አብረን እንገንባ

# ጥረቶቻችን ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ግብ ያመራሉ

'አቤት' እንላለን... እኛ የታሪክን መንኮራኩር በእጁ በጨበጠው ፤  "በሰዎች መንግሥት ላይ በሰለጠነው" በልዑል አምላክ ፈቃድ እንኖራለን፡፡ እንወጣለን፡፡ እንገባለን፡፡ በማያባራ የፍትህ ጉ...
08/11/2025

'አቤት' እንላለን...

እኛ የታሪክን መንኮራኩር በእጁ በጨበጠው ፤ "በሰዎች መንግሥት ላይ በሰለጠነው" በልዑል አምላክ ፈቃድ እንኖራለን፡፡ እንወጣለን፡፡ እንገባለን፡፡
በማያባራ የፍትህ ጉድለት እና የሰላም እጦት፤ በማይተነበይ ዓለም እና እርግጠኛ ባልሆነ ነገ ብንመላለስም አሁንም ረደኤታችን ከስጋና ከደም ሳይሆን ሰማይና ምድርን ከሰራው ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደሆነ እናምናለን፡፡

በእርግጥ የፍትህ ጎጆ ሲንጋደድ የሕብረተሰብ ዋልታና ማገር የሆኑ መልካም ፅንሰ ሀሳቦች በአደባባይ ሲወድቁ ለምን? ብለን እንጠይቃለን፡፡
በታላቁ ተጋድሎ ጥላ ስር በብዙ ሴራና ፍላጎት በተሞላ ዓለም መኖራችንን ብናውቅም ለተገፉ መቆም ፣ ለድሀ አደጎች እና ለመበልቶች 'አቤት' ማለት የጌታችን ልብ ነውና እኛም 'አቤት' እንላለን፡፡

በእያለንበት ቀዪ ያለነው እንደኛው ሟች በሆኑ ሰዎች በጎ ፈቃድ ወይም በአጋጣሚ ሳይሆን በእግዚአብሔር ፈቃድ ነውና መሸ አዳሪዎች በሆንባት ዓለም በየተዘራንበት በቅለን ፍሬያማ ሆነን ለማለፍ እንመርጣለን፡፡ ለምንኖርበት ከተማ/አገር ሰላም እንፀልያለን ፡፡ ከመልካም መልዕክተኞች ጋር ሆነን 'አቤት' ማለታችን እንቀጥላለን፡፡

ፊት አይተው ወደሚያደሉ አባይ ሚዛን ወደ ያዙ ሰዎች ሳይሆን ወደ እውነተኛው ዳኛ ወደ እግዚአብሔር አምላክ 'አቤት' እንላለን፡፡ በእግዚአብሔር እናምናለን። እሱን ብቻ እንይዛለን። በቃሉ ብርሃን፣ በንስሃ ፤ በጸሎት 'አቤት' እንለዋለን፡፡ በእውነት ይህንን በማድረግ አባቶቻችን በጌታ ችሎት ጸንተዋልና እኛ ልጆቻቸውም በእርሱ ችሎት እንጸናለን።

'አቤት' እንላለን ...

# ኑ በፈረሰው በኩል አብረን እንገንባ

#ጥረቶቻችን ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ግብ ያመራሉ

ባለራእይ፣ ልበ ሙሉና ተስፈኛ...(የነህምያ የሥራ ፈጠራ ዘርፍ ፅንሰሃሳብ )"አምላካችን እግዚአብሔር የፈጠራ ሊቅ ነው። ከዘለዓለም እስከ ዘላለም ባለው ጥበቡ ስራዎችን ይነድፋል፤ በፍፅምና ይ...
26/10/2025

ባለራእይ፣ ልበ ሙሉና ተስፈኛ...

(የነህምያ የሥራ ፈጠራ ዘርፍ ፅንሰሃሳብ )

"አምላካችን እግዚአብሔር የፈጠራ ሊቅ ነው። ከዘለዓለም እስከ ዘላለም ባለው ጥበቡ ስራዎችን ይነድፋል፤ በፍፅምና ይከውናል። በዘመናት በሸመገለ እውቀቱ አለማትን ሁሉ አፅንቶ ያቆማል። ይህንን የማሰብና የማሰላሰል እንዲሁም የመፍጠርና የማቀናጀት ( to invent, innovate and coordinate ) ክህሎትን ለሰው ልጆች አካፍሏል። ሁላችንም እግዚአብሔር በተለየ ሁኔታ ያበረከተልን ተፈጥሮአዊ ክህሎቶች አሉን"

በዚህ አውድ ታዳጊዎች እነኚህን መክሊቶች በማዳበር ለእግዚአብሔር ክብርና ለሰው ልጆች ሁሉ ጥቅም ለማዋል ባለራእይ፣ ልበ ሙሉና ተስፈኛ ይሆኑ ዘንድ ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት በሀይል ያበረታታል።

24/10/2025

"ጠባቂ ሆይ ከሌሊቱ ስንት ስዓት ነው ሌሊቱ ሊነጋ ምን ያህል ቀረው?"

(ግርማ አበባው እንደፃፈው )

ጋዜጠኛው አንድ ጥያቄ ከጠየቀ እነሆ ዛሬ ሩብ ክፍለ ዘመን ሞላው ። ጊዜው እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር 2001 መስከረም 11 ነበር።

እለቱ ታላቂቱ የምድራችን ልዕለ ሃያል አገር የተባበረችው አሜሪካ እራሷ ከአሸባሪዎች የደረሰ ባለችው አስከፊ ጥቃትን አስተናግዳ እየተናጠች የነበረችበት ጊዜ፤ እኛ ኢትዮጵያዊያን ደግሞ አዲስ ዘመንን ተቀብለን ፌሽታ ላይ የነበርንበት።

አሜሪካኖቹ ግን በደረሰው አሰቃቂ ሽብር ምክንያት በድንጋጤና በሐዘን ተውጠው ራሳቸውን ያገኙበት ጊዜ ነበር እለቱ። አስደንጋጩ ዜና ክስተቱን ተከትሎ በዓለም ዙሪያ በናኘ ጊዜ ዓለምም በድንጋጤ ክው ብሎ ነበር። ፍርሃትና ውጥረትም በዓለም ላይ ነገሰ።

የጀርመኑ ዶቼቬሌ ሬዲዮ የአማርኛው ክፍል አዘጋጅ የሆነው ጋዜጠኛ ነጋሽ መሃመድ " ከእንግዲህ ዓለም እንደድሮው ተመሳሳይ ሆና ትቀጥል ይሆን?" በዕለቱ ማንም የማይመልሰው ጥያቄ አቅርቦ የዕለቱን መርሐግብር ሲደመድም ቸር ያሰማን ብሎ ተሰናበተ። በዕርግጥ ከዚያ የሽብር ክስተት በኋላ አለም እጅጉን እንደተለወጠ አብዛኞቻችን ምስክሮች ነን።

ዓለም በለየለት የምጥ መፋፋም ውስጥ እንዳለች ነፍሰ ጡር ሴት እያቃሰተች ትገኛለች። የምጥ ልምምድ ያላቸው ሴቶች መገላገላቸውን በመናፈቅ በብዙ ጣርና ስቃይ የሞላበት ህመም ሲያልፉ በዚያች ጊዜ ነገሮች ሁሉ ይጨልምባቸዋል። መንፈሳቸው ስሜታቸው እጅግን ይረበሽና መጨረሻው የቀረበ ይመስላቸዋል።

ነገር ግን ብዙም ሳይቆዩ በመጨረሻ ይገላገላሉ አምጣ የማትወልድ ሴት የለችም። ዛሬ ግን ወንድ ልጅም በምጥ ውስጥ እያለፈ ይገኛል። ጋዜጠኛው የጠየቀው ጥያቄ ባለፉት ሩብ ክፍለ ዘመን ውስጥ እንዴት መልስ እንዳገኘች ለመረዳት ለሁላችንም ብዙ አዳጋች የሚሆን አይመስልም።

ልዕለ ሃያሏ ባለጸጋዋ ሐብታሟ ሃገር ተብላ የምትጠራው አሜሪካ ምንም ጊዜ ሳታጠፋ ዓለም አቀፍ የጸረ ሽብር ዕቅድ አውጥታ መንግስታትን በማስተባበር አሸባሪ የምትላቸውን ግለሰቦች ቡድኖችና ሽብርተኝነትን ይደግፋሉ በሚባሉት መንግስታት ላይ የመደምሰስና የመደፍለቅ ዘመቻዋን ጀመረች።

ዓለም 1ኛውንና 2ኛውን የዓለም ጦርነት ባስተናገደች ጊዜ ወደ 100 ሚሊዮን የሚደርሱ ሰዎች በጦርነቱና ጦርነቱ ባስከተለው ዳፋ ለህልፈት ሕይወት እንደተዳረጉ ብዙ ዘገባ ተሰርቶለታል። በብዙ ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ንብረት ወድሟል። ስለሆነም ዓለም በጊዜው ጦርነት ያንገፈገፋት ትመስል ስለነበር የተባበሩት መንግስታት አንድነት ድርጅትን አቋቁማ አለምን ዳግመኛ ወደ እልቂት እንዳትገባ ለማድረግ በብዙ አውርታ ነበር ነገር ግን ሁሉም ነገር ከወሬ ሳያልፍ ቀረ።

ብዙም ሳይቆይ ከጥቂት አመታት በኋላ ቀዝቃዛው የአለም ጦርነት ጀመረና እንደገና ዓለም ከሁለት ተከፍላ ረጅም አመታትን ባስቆጠረ እሰጣ ገባና ቁርቋዞ ውስጥ ተዘፈቀች። አንድ የነበሩ ተለያይተው ጎራ በመያዝ እርስ በእርስ ተፋለሙ። ምስራቅና ምዕራብ ጀርመን፤ ሰሜን ኮሪያ ደቡብ ኮሪያ አንድ የነበሩ ወደ ሁለት በመከፈል እርስ በዕርስ የሚፎካከሩ አገራት ሆነው ቀላል የማይባል በአስርት የሚቆጠሩ አመታትን አሳልፈዋል።

የተባበረችው አሜሪካ በአንድ በኩል የቀድሞዋ ሶቬት ሕብረት በሌላ ጎራ በመሆን ሜዳውን እየቀያየሩ በእጅ አዙር ተፋለሙ። አንዱ ሌላውን ለማዳከም ሁሉንም አማራጭ ተጠቅመዋል። በዚህ ሁሉ ዓለም ያለ ዕረፍት እያቃሰተች ብትኖርም ነገር ግን የሚታደጋትን ገና አላገኘችም።

ይህ በእንዲህ እንዳለ መንግስታት አሁንም ከባድ ጅምላ ጨራሽ መሳሪያን የመያዝ እሽቅድምድም ውስጥ እንደገቡ ናቸው ። የኒውክለር ቦንብ ከጥቂት አመታት በፊት በአለም ውስጥ ዘጠኝ አገራት ብቻ ነበር የነበራቸው አሁን ግን ከሃምሳ አገራት በላይ ይህ አደገኛ መሣሪያ እንዳላቸው የተለያዩ ዘገባዎች ይጠቁማሉ። ይህ ስጋት እንዳለ ነው እንግዲህ አሜሪካ የምታስተባብረው አለምአቀፉ የጸረሽብር ዘመቻ የተጀመረው።

በዚህ ዘመቻ በቀጥታ በተከፈተባቸው ጦርነት ምክንያት የአፍጋኒስታንና የኢራቅ መንግስታት ተወግደዋል። ዋና ዋና ናቸው የሚባሉ ግለሰቦች ተይዘው ተገድለዋል ወይም ለፍርድ ቀርበዋል። በባራክ ሁሴን ኦባማ ዘመን ደግሞ የሽብርተኝነት ዋና አቀነባባሪ የተባለው ግለሰብ ኦሳማ ቢላደን ፓኪስታን ውስጥ በአሜሪካ ልዩ ሃይሎች ተገድሎ በባህር ውስጥ ተቀብሯል ተብሏል።

ይህ ሁሉ ቢሆንም እንኳን ዓለም አሁንም በከፋ ምጥና ጣር ውስጥ ቀጥላለች። ለአለም ችግር ምንም ያልፈየደው የጸረ ሽብር ዘመቻ እየተካሄደ ጎን ለጎን ዓለም ከባባድ የተፈጥሮ ክስተት አደጋዎችን እያስተናገደች በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንዲሉ እየተንገታገተች ትገኛለች። ለ280,000 ሰዎች ሕይወት መጥፋት ምክንያት የሆነው ሱናሚ ማዕበል ከአሰቃቂ የቅርብ ትዝታዎቻችን መካከል አንዱና ዋናው ነው። ከ2006 አካባቢ ጀምሮ ዓለምን የመታው የኢኮኖሚ ቀውስ እስካሁን የረባ መፍትሔ አላገኘም።

ዓለምን ከተፈታተኗት ችግሮች መካከል የኤች አይቪ አዲስ፣ ኢቮላና ኮረና ለመሳሰሉት ከባባድ የጤና እክሎች እዚህ ግባ የሚባል መፍትሔ አልተገኘላቸውም። የአረቡ አለም አቢዮት ተቀጣጥሎ ብዙ እልቂት እያስከተለ 13 አመታትን ተሻግሯል። ለአብነትም ያህል ሊቢያን፣ የመንና ሶሪያን ማየት ይቻላል። በዚህ ጊዜ በደረሰባት የሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋ ምክንያት ዓለም በአሳዛኝ ሁኔታ ክፉኛ ተደቁሳ በማቃሰት ላይ ሆና ግራ በመጋባትና በተስፋ መቁረጥ ደረጃ ላይ ትገኛለች።

በዚህ ጊዜ ከባድ የአስፈሪ የአደጋ ምልክት ድምፆች እየተሰሙ ነው።
ኢሳይያስ 21
¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯
¹ በባሕር አጠገብ ስላለው ስለ ምድረ በዳ የተነገረ ሸክም። ዐውሎ ነፋስ ከደቡብ እንደሚወጣ፥ እንዲሁ ከሚያስፈራ አገር ከምድረ በዳ ይወጣል።
² ከባድ ራእይ ተነገረኝ፤ ወንጀለኛው ይወነጅላል አጥፊውም ያጠፋል። ኤላም ሆይ፥ ውጪ፤ ሜዶን ሆይ፥ ክበቢ፤ ትካዜውን ሁሉ አስቀርቻለሁ።
³ ስለዚህ ወገቤ ሕመም ተሞላ፤ እንደምትወልድ ሴት ምጥ ያዘኝ፤ ከሕመሜ የተነሣ አልሰማም፥ ከድንጋጤም የተነሣ አላይም።…
¹¹ አንዱ ከሴይር፦ ጕበኛ ሆይ፥ ሌሊቱ ምን ያህል ነው? ጕበኛ ሆይ፥ ሌሊቱ ምን ያህል ነው? ብሎ ጠራኝ።
¹² ጕበኛውም፦ ይነጋል ድግሞም ይመሻል፤ ትጠይቁ ዘንድ ብትወድዱ ጠይቁ፤ ተመልሳችሁም ኑ አለ።

ማን ነው ንጋት ያልናፈቀው? ማን ነው ሊነጋ ምን ያህል እንደቀረው ማወቅ የማይፈልገው?

- “ፍጥረት ሁሉ እስከ አሁን ድረስ አብሮ በመቃተትና በምጥ መኖሩን እናውቃለንና።”
— ሮሜ 8፥22

- በዚህ ብርቱ ሌሊት በሆነው ጊዜ ቤተክርስቲያን በምን ሁኔታ ላይ ትገኛለች?

“የማታስተውሉ የገላትያ ሰዎች ሆይ፥ በዓይናችሁ ፊት ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ ነበር፤ ለእውነት እንዳትታዘዙ አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?”
— ገላትያ 3፥1

ማቴዎስ 25
⁵ ሙሽራውም በዘገየ ጊዜ ሁሉ እንቅልፍ እንቅልፍ አላቸውና ተኙ።
⁶ እኩል ሌሊትም ሲሆን፦ እነሆ፥ ሙሽራው ይመጣል፥ ትቀበሉት ዘንድ ውጡ የሚል ውካታ ሆነ።

- በዚህ ንጋት እየተናፈቀ ባለበት የእኩለሌሊት ድቅድቅ ጨለማ ሰአት ምን ማድረግ ነው ያለብን?

— ዳንኤል 12፥10
- “ብዙ ሰዎች ሰውነታቸውን ያጠራሉ ያነጡማል ይነጥሩማል፤ ክፉዎች ግን ክፋትን ያደርጋሉ፤ ክፉዎችም ሁሉ አያስተውሉም፥ ጥበበኞች ግን ያስተውላሉ።”

- 2ኛ ጢሞቴዎስ 3
¹³ ነገር ግን ክፉዎች ሰዎችና አታላዮች፥ እያሳቱና እየሳቱ፥ በክፋት እየባሱ ይሄዳሉ።
¹⁴ አንተ ግን በተማርህበትና በተረዳህበት ነገር ጸንተህ ኑር፥ ከማን እንደ ተማርኸው ታውቃለህና፤

“የሚቀጠቅጥ በአንተ ላይ ወጥቶአል፤ ምሽግን ጠብቅ፥ መንገድንም ሰልል፤ ወገብህን አጽና፥ ኃይልህንም እጅግ አበርታ።”
— ናሆም 2፥1

“ከሌሊቱም በሁለተኛው ወይም በሦስተኛው ክፍል መጥቶ እንዲሁ ቢያገኛቸው፥ እነዚያ ባሪያዎች ብፁዓን ናቸው።”
— ሉቃስ 12፥38

እንደመሸ አይቀርም ሌሊቱ ይነጋል
የአዲስ ቀን ጅማሮ በቅርብ ይታወጃል
እስከዚያው በትዕግሥት መጠበቅ ይበጃል።

18/10/2025

በዝለት እና ግራ በመጋባት ዘመን ድጋፍ ፤ በሴረኞችና በወደረኞች መካከል ፅናት፤ በአይቻልም ወራት ሁሉ ችሎት ናት፡፡ ከንጉሰ ነገስት አዋጅ ፤ ከሀያላን በጎ ፈቃድ ይልቅ የክንውን ምክንያት፤ የህይወት እርግጠኛ መተማመኛ አላት፡፡
መልካሚቱ የአምላካችን እጅ!

# ኑ በፈረሰው በኩል አብረን እንገንባ

#ጥረቶቻችን ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ግብ ያመራሉ

"አክት ሎካሊ..."በእርግጥ የአገልግሎት መስኩ ብዙ የመከሩ ቁጥር እልፍ ነው፡፡ ወንድሜ "እንደ ሰናህድሪን ያለ ሸንጎ ላይ ካልተሰየምኩ ፤ እንደ ቄሳር ያለ ዙፍን  ላይ ካልወጣሁ  የወገኔ ጠ...
13/10/2025

"አክት ሎካሊ..."

በእርግጥ የአገልግሎት መስኩ ብዙ የመከሩ ቁጥር እልፍ ነው፡፡ ወንድሜ "እንደ ሰናህድሪን ያለ ሸንጎ ላይ ካልተሰየምኩ ፤ እንደ ቄሳር ያለ ዙፍን ላይ ካልወጣሁ የወገኔ ጠኔ አይድን፣ የህዝብ ችግር አይፈታ!" አትበል፡፡ ይልቅስ ለጌታህ እንደምታደርገው እያሰብክ ለማህሕበረሰብ በረከት እና ለሰው ልጆች ሁሉ ኑሮ መቃናት በሚረባ አካባቢያዊ ተግባር ተሳተፍ ! በገራምነት ተባበር !

"አክት ሎካሊ..."

# ኑ በፈረሰው በኩል አብረን እንገንባ

# ጥረቶቻችን ሁሉ ወደ ዘላለማዊ ግብ ያመራሉ

Address

Addis Abeba
Addis Ababa

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ነህምያ የአገልግሎት ሕብረት-Nehemiah Christian Service Ministry posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share