28/04/2026
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ እና የኢፌዲሪ ጤና ሚኒስቴር ለሕዝብ ጤና ጥበቃ በጋራ ለመሥራት ተስማሙ
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ ጠቅላይ ጸኃፊ ሊቀ ትጉኃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ የተመራ የልዑካን ቡድን ከኢፌዲሪ ጤና ሚኒስቴር ሚኒስትር ክቡርት ዶ/ር መቅደስ ዳባ ጋር ሚያዝያ 19 ቀን 2018 ዓ.ም በሁለቱ ተቋማት የትብብር ሥራዎች ዙሪያ ፍሬያማ ምክክር አደረጉ።
በውይይታቸውም ቀደም ሲል በጋራ በመሥራት የኮቪድ-19 ወረርሽኝን እና የማርበርግ ቫይረስ ስርጭትን ለመከላከል የተከናወኑ ተግባራት ውጤታማ እንደነበሩ ተገምግሟል።
ሀገራችን በራሷ አቅም የተሟላ የጤና አገልግሎት ለመስጠት ለጀመረችው ጉዞ፣ የሃይማኖት ተቋማት ያላቸውን ተፅዕኖ በመጠቀም ግንዛቤ የመፍጠርና የማህበረሰብ ጤናን የመጠበቅ ሥራቸውን አጠናክረው እንደሚቀጥሉ ተስማምተዋል።
የጤና ተቋማትን ከጉባኤው ቅርንጫፍ መዋቅሮች ጋር በማስተሳሰርና በቀጣዩ የበጀት ዓመት የሁለቱ ተቋማትን ትብብር ይበልጥ የሚያጠናክሩ ተግባራትን በመለየት በተደራጀ መልኩ ለመሥራት አቅጣጫ ተቀምጧል።
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ የማህበረሰብን ጤና ለማስጠበቅ እና ወረርሽኞችን ፈጥኖ ለመቆጣጠር ከጤና ሚኒስቴር ጋር ያለውን ትብብር አጠናክሮ ይቀጥላል።
ለኢቫንጀሊካል ዜና ሩት ዋቅጅራ
የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ
የሕዝብ ግንኙነትና ሚዲያ አገልግሎት