25/03/2023
ዛሬ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸን ከቀናት በፊት ከዚህ ዓለም ድካም ያረፉ ሁለት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን በክብር የምትሸኝበት ከባድ ቀኗ ነው።
የብፁዕ አቡነ ባስልዮስ እና የብፁዕ ዶ/ር አቡነ አረጋዊ የሽኝት ስነ ስርዓት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ቤተሰቦቻቸው እና ምእመናን በተገኙበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም እየተከናወነ ይገኛል።
የአባቶቻችን በረከት ይደርብን።
ፎቶ፦ የኢኦቴቤ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ
ብፁዕ አቡነ ባስልዮስ
መጋቢት 1/2015 ዓ.ም በሥጋ እረፍት የተለዩንና ዛሬ መጋቢት 16/2015 ዓ.ም አስከሬናቸው ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ በክብር አቀባበል የሚደረግለት የብፁዕ አቡነ ባስልዮስ ሣልሳይ የሮቸስተር ቅድስት ኪዳነ ምህረት ቤተ ክርስቲያን የበላይ ጠባቂ የሕይወት ታሪክ ይህንን ይመስላል።
“መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ ሩጫዬንም ጨርሻለሁ፣ ሃይማኖቴን ጠብቄአለሁ፣ ከእንግዲህ ወዲህ የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶ ይጠብቀኛል” 2ኛጢሞ. 4፥6-8
ብፁዕ አቡነ ባስልዮስ፡ በቀድሞ ስማቸው መ/ር ሐረገ ወይን በቀለ መሸሻ ከአባታቸው ከግራዝማች በቀለ መሸሻና ከእናታቻው ከወ/ሮ ደብሬ እንግዳ በ1939 ዓ/ም በቀድሞ አጠራር በጐጃም ጠቅላይ ግዛት በእንጅባራ ወረዳ ዳንጊያ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አጥቢያ ተወለዱ። ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ በአካባቢያቸው በሚገኙ የአብነት ትምህርት ቤቶች በመግባት ፊደል፣ ንባብና የቃል ትምህርት እንዲሁም ከመሪጌታ ዴንሳ ወንድምሁነኝ፣ ጾመ ድጓ፣ ድጓ፣ መዋሥዕትና ዝማሬ በሰከላ ወረዳ ባሕር ዛፋ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አጥቢያ ተምረዋል።
መ/ር ሐረገ ወይን በቀለ የጾመ ድጓና የድጓ ትምህርታቸውን ወደ መምህርነት ደረጃ ለማሳደግ ስለፈለጉ ወደ ደጋ ዳሞት በመሄድ ከመሪጌታ ብርሃኑ ደግመው ከልሰዋል። መ/ር ሐረገ ወይን በቀለ ሁሉንም የአብነት ትምህርቶች ለመማር ባላቸው ጽኑዕ ፍልጎት ወደ ሰከላ ወረዳ ሮቢት ጽዮን በመሄድ ከመሪጌታ መሠረት ቅኔ ከነአገባቡ ተምረው አጠናቀዋል። በመቀጠልም የአቋቋም ትምህርታቸውን በባሕርዳር ከተማ ከሊቀ ኅሩያን ተስፋ ዳኘው በኋላም ወደ ጎንደር ደብረ ኃይል ወደብረ ጥብብ በዓታ ለማርያም ገዳም በመሄድ ከየኔታ ወላዴ አእላፍ ሔኖክ ወልደ ሚካኤል የአቋቋም ትምህርታቸውን በሚገባ አጠናቀዋል።
ከዚያም ወደ ባሕርዳር በመመለስ በወቅቱ የፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የደብሩ አስተዳዳሪ ከነበሩት ከታላቁ አባት መምህር አባ ኃይለማርያም አየለ ቅዳሴና ባሕረ-ሐሳብ ተምረዋል።
መምህር ሐረገ ወይን በቀለ ፍላጎታቸው ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል በመሆኑ የአብነት ትምህርታቸውን ካጠናከሩ በኋላ በ1959 ዓ/ም በባሕር ዳር ጣና ሐይቅ ክብራን ገብርኤል ገዳም በመምህር አባ ኃይለማርያም ምንኩስናን ተቀብለዋል።
መምህር አባ ሐረገ ወይን በቀለ ቤተ ክርስቲያንንና ምእመኖቿን በይበልጥ ለማገልገል ይችሉ ዘንድ በማሳብ ወደ ደብረ ማርቆስ በመሄድ ሥልጣነ ክህነት ከሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ከብፁዕ አቡነ ማርቆስ ተቀብለዋል።
መምህር አባ ሐረገ ወይን በቀለ የአብነት ትምህርታቸውን ከተለያዩ መምህራን ካጠናቀቁ በኋላ ብስለታቸውንና እውቀታቸውን የተገነዘቡት የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ በባሕር ዳር ከተማ በሚገኘው የሽንብጥ ሚካኤል አስተዳዳሪ አድርገው ሾመዋቸዋል።
መምህር አባ ሐረገ ወይን በቀለ የጊዜውን ትውልድ በሰፊው ለማገልገል ከአብነት ትምህርት በተጨማሪ በጊዜው እንደ እንግዳ ነገር የሚታየውን ዘመናዊ ትምህርት መቅሰም አስፈላጊ መሆኑን በመገንዘብ ቤተክርስቲያንን እያገለገሉ ጎን ለጎን የአስኳላ ትምህርት ቤት በመግባት ከ1ኛ እስከ 8ተኛ ክፍል ትምህርታቸውን በፋሲሎ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት፤ ከ9 እስከ 12ኛ ደግሞ በጣና ሀይቅ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተከታትለዋል።
ከዚያም ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሚሰጠውን መደበኛ ትምህርት ተከታትለው ተመርቀዋል፡፡
መምህር አባ ሐረገ ወይን በቀለ የአብነት ትምህርትን ከዘመናዊ ትምህርት ጋር ማዛመዳቸውን የተገነዘቡትና በጊዜው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ የነበሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለሃይማኖት ለከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት ወደ ጀርመን ልከዋቸው በጀርመን የሚጠበቅባቸውን የነገረ መለኮት ትምህርት ከጨረሱ በኋላ ለአገልግሎት ወደ ሀገር ቤት በመመለስ በተለያዩ ገዳማትና አድባራት በአስተዳዳሪነት አገልግለዋል።
ጥቂቶችን ለመጥቀስ ያህል፦ መልአከ ምሕረት በተባሉበት በድሬድዋ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን፣ በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሶዶሬ መድኃኔዓለም ገዳም፣ በምዕራብ ሸዋ መናገሻ ማርያምና በጋራው መድኃኔዓለም አንድነት ገዳም፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በኮተቤ ካራ አሎ መድኃኔዓለም እና ጻድቁ አቡነ ገሪማ ገዳም እንዲሁም የጉለሌ ጽርሐ አርያም ቅዱስ ሩፋኤል ደብር ዋና ዋናዎቹ ናቸው።
መልአከ ምሕረት አባ ሐረገ ወይን በቀለ በተለያዩ አድባራት በአስተዳዳሪነት ካገለገሉ በኋላ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ተሹመው በሰሜን አሜሪካ ኒውዮርክ ከተማ በሚገኘው ቅድስት ሥላሴና ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በአስተዳዳሪነት ለብዙ ዓመታት አገልግለዋል፡፡ በተጫማሪም በባፍሎ መድኃኔዓለምና በሮቸስተር ቅድስት ኪዳነ ምሕረት አብያተ ክርስቲያናት አገልግለዋል።
መልአከ ምሕረት አባ ሐረገ ወይን በቀለ በኒውዮርክ ክፍለ ሀገር አገልግሎት ላይ እንዳሉ ቅን አገልግሎታቸው፣ መንፈሳዊነታቸውና የቤተክርስቲያን ዕውቀታቸው ታይቶ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ 4ኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ጥር 11/ 1999 ዓ/ም ከሌሎች አባቶች ጋር በአንብሮተ ዕድ ብፁዕ አቡነ ባስልዮስ ተብለው ኤጲስ ቆጶስ ሆነው ተሹመዋል፡፡
ብፁዕ አቡነ ባስልዮስ ሣልሳይ ኤጲስ ቆጶስ ሆነው ከተሾሙ በኋላም የኒውዮርክ፣ ኒውጀርሲ፣ ቦስተንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በመሆን ለብዙ ዓመታት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ በትጋትና በአባትነት ክብር ሲያገለግሉ ቆይተዋል።
በዚህ የአገልግሎት ዘመናቸውም፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶችን በማስፋፋት፣ ዲቁናንና ቅስናን በመስጠት አገልጋዮች እንዲበዙ በማድረግ ፣ በሀገረ ስብከታቸው አብያተ ክርስቲያናትን በማቋቋም፣ ምእመናንን በማጽናናት መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን በማከናወን ላይ እንዳሉ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በሰሜን አሜሪካ ኒዮርክ ከተማ በሚገኝ ሆስፒታል በሕክምና ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ76 ዓመታቸው መጋቢት 1 ቀን 2015 ዓ/ም ከዚህ ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል።
የብፁዕ ዶ/ር አቡነ አረጋዊ የሕይወት ታሪክ
#ውልደት
የቀድሞው አባ ኃይለ ማርያም መለሰ የኋላው ብፁዕ አቡነ አረጋዊ (ዶ/ር) ከአባታቸው ከሊቀ መዘምር መለስ አየነው ደስታና ከእናታቸው ከወ/ሮ ፀሐይ ገብረ አብ በሰሜን ጎንደር ደብረ ሰላም ሎዛ ማርያም አካባቢ በ1961 ዓ.ም ተወለዱ።
#ትምህርት
• ፊደል፥ ንባብ፥ ዳዊትና ቅዳሴ ከመርጌታ ሙሴ ብፅዐ ጊዮርጊስ ተምረዋል።
• ቅኔ፥ ከግጨው መንከር ምንዝሮ ተክለ ሃይማኖት፥ ሐዲሳት፥ ከመጋቤ ሐዲስ ወልደ ሰንበት ግምጃ ቤት ማርያም ተምረዋል።
• 1ኛና 2ኛ ከፍተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በዐፄ ፋሲል፡ መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ደግሞ በዳግማይ ደብረ ሊባኖስ አዘዞ ተክለ ሃይማኖት ት/ቤቶች ተምረዋል።
• ከሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ በቴዎሎጂ ዲፕሎማ፥
• ከቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በቴዎሎጂ ዲግሪ፥
• ከኖርዌይ ስታቫንገር ስፔሻላይዝድ ዪኒቨርስቲ የማስተርስ ዲግሪ፥
• ከፕሪቶርያ ዩኒቨርስቲ በፍልስፍና የፒኤችዲ ዲግሪ አግኝተዋል።
#ቋንቋ
• ከእንግሊዝኛ በተጨማሪ የኖርዌይ፥ የስዊድንና የዴንማርክ ቋንቋዎችን ይችላሉ፡፡
• ዲቁና - በ1968 ዓ.ም. ከብፁዕ አቡነ እንድርያስ (ቀዳማዊ) በወቅቱ የሰሜን ጎንደር ሊቀ ጳጳስ ተቀብለዋል፥
• ምንኵስና - በ1984 ዓ.ም. በታዋቂውና ጥንታዊው ገዳም ጎንድ ተከለ ሃይማኖት ተቀብለዋል፥
• ቅስና - ከብፁዕ አቡነ ያዕቆብ (ኤርትራዊ) በወቅቱ የሰሜን ጎንደር ሊቀ ጳጳስ ተቀበለዋል፥
• ቁምስና - ከብፁዕ አቡነ ገብርኤል በወቅቱ የምዕራብ ሸዋ ሊቀ ጳጳስ ተቀብለዋል።
#አገልግሎት
• በሆለታ ደብረ ገነት ቅድስት ኪዳነ ምሕረት፥ በሆለታ ገነት ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል፥ በሆለታ ገነት ደብረ ሣህል መድኃኔ ዓለም፥ በወሊሶ ጻድቁ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አብያተ ክርስቲያናት በአስተዳዳሪነት ሠርተዋል።
• የወልመራ ወረዳ ቤተ ክህነት ምክትል ሊቀ ካህናት ሆነው በቅንንነት አገልግለዋል።
• በኖርዌይ ስታሻንገር መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪና የሕፃናትና ቤተሰብ መምሪያ የቦርድ ምክትል ሰብሳቢ በመሆን መርተዋል።
• የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር የቦርድ አባል፡ የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት የቦርድ አባል በመሆን እያገለገሉ አገልግለዋል።
• በቤተ ከህነት ጠቅላይ ጽ/ቤት ሲል በስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ኃላፊ፥
• በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በመጀመሪያ የሪሰርችና ምርምር ኃላፊና አካዳሚክ ዲን፥ ም/ዋና ዲን በመሆን አገልግሎት ሰጥተዋል።
• የቅድስት ልደታ የጤና ሳይንስ ኮሌጅ የቦርድ አባል በመሆንም ሠርተዋል።
• በዓለም አቀፍ ተሳትፎ ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ከርስቲያንን በመወከል የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ማእከላዊ ኮሚቴ አባል፥ የመላው ኦርየንታል ኦርቶዶስ አብያተ ከርስቲያናትን በመወከል የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል በመሆን ተሳትፈዋል፡፡
• የመንበረ ፓትርያርከ ጠቅላይ ጽ/ቤት ምክትል ሥራአስኪያጅ ሆነው አገልግለዋል።
«በጎ ነገር የሆነው ሁሉ ያለ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ፈቃድ ፍጻሜ ሊያገኝ አይችልም ተብሎ በተጻፈው መሠረት ምንም እንኳን ሁሉም ተመራጮች ቆሞሳት ከዕጩ ተወዳዳሪዎቻቸው ጋር የድምፅ ብልጫ በማግኘት ሊመረጡ የቻሉት በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ፈቃድ መሆኑ ቢታመንበትም ቅሉ ቆሞስ ዶ/ር ብፁዕ አቡነ አረጋዊ ግን ከእጩ ተወዳዳሪያቸው ጋር እኩል ድምፅ አግኝተው የተመረጠት በዕጣ ስለሆነ በእሳቸው ምርጫ በይበልጥ እደ መንፈስ ቅዱስ እንዳለበት ያሳያል፡፡
ብፁዕነታቸው ከሹመታቸው በኋላ የቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት እና የውጪ ግንኙነት መምሪያ የበላይ ኃላፊ እና የድሬደዋና ጅቡቲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሆን ቅድስት ቤተክርስቲያን ኃላፊ ሆነው አገልግለዋል።
ብፁዕ አቡነ አረጋዊ ያለፈውን ዓመት በሕመም ምክንያት በሀገር ውስጥ እና በውጪ ሀገር በሕክምና ሲረዱ ቆይተው ትናንት መጋቢት 12 /2015 ዓ.ም በተወለዱ በ54 ዓመታቸው ከእዚህ ዓለም ድካም አርፈዋል ።
የብፁዕ አባታችን በረከታቸው ይደርብን ።
ፎቶ:- መልአከ ሰላም አባ ኪሮስ ወልደ አብ
(የፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት)