03/06/2026
በሃይማኖት ላይ የተመሠረተ ጭፍን ጥላቻ፣ የአርሲው በክርስቲያኖች ላይ የተፈጸመ ዘግናኝ ጭፍጨፋ፣ ግድያ
ከመቶ ዓመታትን የተሻገረው የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ቃጠሎ እንዲሁም የመድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን ዝርፊያ፣ የበርካታ ክርስቲያኖች ስደት.....
ሰዎች በሃይማኖትና በብሔር ልዩነት ምክንያት ብቻ በሌላው ላይ የጭካኔ እና የጥላቻ በትረ-ሙሴ የሚያነሱት ለምንድን ነው? ይህ ዓይነቱ ጥላቻ ከሰው ልጅ ሰብዓዊነት መውረድ፣ ከጽንፈኝነት እና ሌላውን ወገን ለመጨቆን እንዲሁም ለማስፈራራት ከማሰብ የሚመነጭ የድንቁርና ጥግ ነው ብዬ አምናለሁ። ሰው ሆኖ በሰው ሕይወት ላይ መጨከን ሌላ ምን አንድምታ ይኖረዋል?!
በአርሲ ሀገረ ስብከት በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች ብbእንጹሃን ኦርቶዶክሳዊያን እንዲሁም በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሰው አሰቃቂ ጥቃት ልብ ሰባሪ ነው። የእምነት ነፃነት ተደፍሮ መቶ ዓመታት ያስቆጠረው የጠላታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተቃጠለበት፣ እንዲሁም የካራ ኩፍቴና መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በተዘረፈበት በዚህ ክፉ ቀን፤ በርካታ ምእመናን በግፍ መሰዋታቸውና በመቶዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ከቀዬያቸው መፈናቀላቸው በእጅጉ የሚያዝንና ልብ የሚሰብር ድርጊት ነው። ዘመናት በፍቅር እና በሰላም አብሮ በኖረው ሕዝብ መካከል እንዲህ ያለውን የጥፋት ዘር መዝራት፣ የጋራ ማኅበራዊ እሴቶቻችንን እና ሰብዓዊነታችንን የሚንድ እኩይ ተግባር ነው።
የሰላም፣ የፍቅርና የታሪክ ማህደር የሆነችው ቤተ ክርስቲያን በምድራዊ መከራ ውስጥ ያሉትን ምእመናን በምታጽናናበት በዚህ ወቅት ራሷ በፈተና ውስጥ ሆና ከመቸገሯም በላይ በአርሲ ምድር በተደጋጋሚ የሚስተዋለው በደልና ግፍ በሁላችንም ልቡና ውስጥ "እስከ መቼ?" የሚል የቁጭት እና የኀዘን ጥያቄን ፈጥሯል።
ይህ በእምነት ማዕቀፍ ውስጥ የማይወድቅ፣ ሰላማዊ ሰዎችን ለሞትና ለስደት የዳረገው አሰቃቂ ጥቃት የነቢዩ ዳዊትን መዝሙር ያስታውሰናል፦
‹‹ወረሰዩ አብድንቲሆሙ ለአግብርቲከ መብልዐ ለአዕዋፈ ሰማይ፣ ወሥጋሆሙኒ ለጻድቃኒከ ለአራዊተ ገዳም፦ የአገልጋዮችህንም በድኖች ለሰማይ ወፎች መብል አደረጉ፥ የቅዱሳንህንም ሥጋ ለምድር አራዊት።›› (መዝሙረ ዳዊት ፸፰፥፪) (መዝ. 78፥2)
የቅዱሳን እና የንጹሐን ደም በግፍ ሲፈስ፣ ታሪካዊ መቅደሶች ሲፈርሱ ዝምታው ሊያበቃ ይገባል። ሃይማኖትም ሆነ ሰብዓዊነት ንጹሐንን መግደልንና የእምነት ቦታዎችን ማውደምን አያስተምሩም። ይህንን አስነዋሪ ድርጊት ሁላችንም በአንድ ድምፅ ልናወግዘው እና ለተጎዱ ወገኖቻችን ከጎናቸው ልንቆም ይገባል።
"ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች ተብሎ ተጽፏል እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችኋት!።” ማቴ. ፳፩÷፲፫ (ማቴ. 21፥13) ያለው ክርስቶስ የበቀል ጅራፉን ያንሳ እንጂ ሌላ ምን ሊባል ይችላል!!!
ለተጎዱትና ውድ ሕይወታቸውን ላጡት ወገኖቻችን ዕረፍተ ነፍስን እንዲሁም መጽናናትን፣ ለሀገራችን ደግሞ ዘላቂ ሰላምን እመኛለሁ!