ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ /Hamere Tewahedo Media

ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ /Hamere Tewahedo Media ይህ በኢ.ኦ.ተ.ቤ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ይፋዊ የፌስቡክ ገጽ ነው።
This is the official page of the Eastern Showa Diocese of the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church.

Magaalaa Batuutti Dhagaan Bu'uuraa Mana Barumsaa Sadarkaa Tokkoffaa Mana Kiristaana Edoo Qonxolaa Dabra Medahaaniit Medh...
21/05/2026

Magaalaa Batuutti Dhagaan Bu'uuraa Mana Barumsaa Sadarkaa Tokkoffaa Mana Kiristaana Edoo Qonxolaa Dabra Medahaaniit Medhaani'alam kaa'ame.

Caamsa , 2018 A.L.H [ ]

— Biyya Lallabaa Shawaa Bahaa jalatti, Mana Lubummaa Aanaa Batuu fi Adaamii Jiddoo Kombolchaa jalatti kan argamu, Mana Kiristaana Magaalaa Batuu Edoo Qonxolaa Dabra Medahaaniit Medhaani'alamiitti, ijaarsi mana barumsaa hawaasni naannichaa yeroo dheeraaf hawwaa fi eegaa ture Caamsa 11, 2018 A.L.H itti-ana kantiiba Magaalaa Batuu fi Hogganaa Hojii Mana Lubummaa Aaniichaan waliin ta'uun dhagaan bu'uuraa kaa'ameera.

Pirojektiin mana barumsaa sadarkaa duraa (KG irraa kaasee hanga sadarkaa 1ffaatti) kan gaaffii ummataa yeroo dheeraa ture kana dhugoomsuuf, Bulchiinsi Magaalaa Batuu fi Manni Lubummaa Aaniichaa qindoomina cimaan waliin hojjechuun isaanii ibsameera.

Hogganaan Hojii Mana Lubummaa Aaniichaa Liqa Kaahinaat Alaqaa Ermiyaas H/Giyoorgis sagantaa kana irratti hoggantoota mootummaa hunda kan galateeffatan yoo ta'u, ijaarsi kun dafee akka xumuramuuf qajeelfama fi hayyama Eebbifamoo Abbaa keenya Abuna Gorgooriyoos (Angafa phaaphaasii biyyaa lallabaa Shawaa bahaa, hoggaanaa Koolleejii Kawaala Ziwaay (Baatuu) Hamara Birhaan Qullulluu Gabreeliifi Mana Barnootaa Leenjii Luboota, miseensa dhaabataa qulqulluu Sinoodosii akkasumas walitti qabaa boordii hojii raaawachiiftu dhaabilee amantaa Itiyoophiyaa) irraa kennamuun, haalli mijeessuuf carraaqqii barbaachisu hunda akka taasisan beksisaniiru.

Hogganaan Hojii kun dabalaniis, pirojektiin kun karoora yeroo dheeraa Eebbifamoo Abbaa keenya Abuna Gorgooriyoos ta'uu caqasuun, har'a deggersa abbaa-lummaa isaaniitiin, deggersa bulchiinsa magaalaa Batuu fi deggersa ummata naannichaan dhagaan bu'uuraa kaa'amuu isaatti gammachuu guddaa itti dhaga'ame ibsaniiru.

Guyyaa sana irratti Kantiiba Itti-anaan Magaalaa Batuu Kabajamoo Obbo Usmaan Tusee ergaa dabarsaniin, sektera barnootaaf xiyyeeffannoo addaa kennitee gara hojiitti kan galte Mana Ortodoksii Tawaahidoo Itoophiyaa haalan galateeffataniiru.

Ijaarsi mana barumsaa kun ariitiin xumuramee bara barnootaa 2019 A.L.I dhufutti yoo xiqqaate kutaan KG barattoota simachuu akka danda'uuf bulchiinsi magaalaa deggersa, hordoffii fi tumsa barbaachisu hunda akka taasisu kantiiba itti-anaan kun waadaa galaniiru.
Dabalataan, Waajjirri Poolisii Bulchiinsa Magaalaa Batuu ergaa dabarseen "Ijaarsi misoomaa fi barnootaa bakka maraatti taasifamu kun nuhi qaama nageenyaatiif boqonnaa guddaadha; biyya lammilee gaarii fi barateen ijaaruuf carraaqqiin taasifamu kun yakka dursanii ittisuuf furmaata ijoodha" jedheera.

Waajjirri Poolisii kun itti dabaluun, Batuun magaalaa nageenyaa, dalagaa fi misoomaa ta'uu ishee gochaan ragaa bahaa jirti jedhee, hojiin gaariin jalqabame kun akka itti fufu jajjabeessaa bulchiinsa magaalichaa fi dhaabbaticha amantiitiif kabajaa fi galata guddaa dhiyeesseera.
Sirna naqinsa dhagaa bu'uuraa seena qabeessa kana irratti, Bulchaan Bataskaanichaa Liqa Siyumaan Qeesis Solomoon Ababbe, Hogganaan Waajjira Barnoota Magaalaa Batuu Obbo Bulbuloo Gadaa, Af-yaa'iin Mana Maree Magaalaa Batuu Obbo Robaa Eerresoo, Bulchaan Ganda Ilkaa Edoo Obbo Gamadoo Kadir, Abbootan Gadaa kabajamoof, maanguddoonni biyyaa, abbootni fi haadhotni amantii akkasumas jiraattonni naannichaa hedduun argamaniiru.

Diyaaqon Ayyalaa dhaan

Biyya Lallabaa Shawaa Bahaa
Hamaree Tawaahidoo Miidiyaa

Oduu kana kan nu dhaqqabsiise Barsiisa Asnaaqeedha.

21/05/2026

21/05/2026
በአዳማ መንበረ ጵጵስና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን በዓለ ዕርገቱ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ  ዓመታዊ ክብረ በዓል በታላቅ መንፈሳዊ ድምቀት ተከበረ። ግንቦት 13 ቀን 2018 ዓ....
21/05/2026

በአዳማ መንበረ ጵጵስና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን በዓለ ዕርገቱ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ዓመታዊ ክብረ በዓል በታላቅ መንፈሳዊ ድምቀት ተከበረ።

ግንቦት 13 ቀን 2018 ዓ.ም [ ]

#አዳማ — የጌታችን፣ የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም ላይ የነበረውን የማዳን ሥራ ፈጽሞ፣ ትንሣኤውን በገለጸ በዐርባኛው ቀን ወደ ሰማያዊ ዙፋኑ በክብርና በምስጋና ማረጉን የምንዘክርበት ታላቁ በዓለ “ዕርገት” (ዕርገተ እግዚእ) በአዳማ ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሣሕል ቀሲስ ነጋሽ ሀብተ ወልድ በተገኙበት በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ-ሥርዓት ተከብሯል።

በበዓሉ ዕለት አባታዊ ቡራኬና ትምህርተ ወንጌል ለመስጠት የተገኙት የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሣሕል ቀሲስ ነጋሽ ሀብተ ወልድ፣ "ወእሙንቱሰ ሰገዱ ሎቱ፡ ወተሠውጡ ኢየሩሳሌም በዐቢይ ፍሥሓ - እነርሱም ሰገዱለትና በብዙ ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ" (ሉቃ. 24፥52) በሚለው አምላካዊ ኃይለ ቃል መነሻነት ለተሰበሰቡት በርካታ ምዕመናንና ምዕመናት ጥልቅ የሆነ የወንጌል ትምህርት አስተላልፈዋል።

ዋና ሥራ አስኪያጁ በትምህርታቸው የጌታችንን የማዳን ሥራና የዕርገቱን ምስጢር ከሥር ከመሠረቱ አብራርተው ሲያስተምሩም፦ "የመጀመሪያዎቹ ሰዎች አዳምና ሔዋን አትብሉ የተባሉትን ዕፀ በለስ በመብላታቸው ምክንያት የሞት ሞት ተፈርዶብን በነበረበት ጊዜ፣ ምሕረቱና ይቅር ባይነቱ የበዛ ልዑል እግዚአብሔር በአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ባለው አምላካዊ የተስፋ ቃል መሠረት፣ በቅዱስ ገብርኤል ብሥራት ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ በግርማ መለኮቱ ተወለደ።

ለእናቱ እየታዘዘ በየጥቂቱ አደገ፤ የእኛን ሥጋ በመልበሱ ተራበ፣ ተጠማ፣ በቀራንዮ መስቀል ላይ ተሰቀለ ጎኑ በጦር ተወጋ፣ ስለ እኛ በገዛ ፈቃዱ ሞቶ በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተነሣ። ሐዋርያቱ በፍርሃት ሆነው በዝግ ቤት ተሰብስበው ሳለ ‘ሰላም ለእናንተ ይሁን’ ብሎ ብርሃነ ትንሣኤውን ገለጠላቸው፤ ፍርሃታቸውንም አስወግዶ ተስፋቸውን አጸናላቸው"በማለት በወንጌል የተገለጸውን ምሥጢሩን በመግለጽ አስተምረዋል።

አያይዘውም ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ የሰው ልጅ በሕይወቱ ውስጥ ለሰው የማይነገሩ በርካታ ተስፋ የሚያስቆርጡ ውጣ ውረዶች ቢኖሩትም፣ የሰው ልጅ ሞት ይሞት ዘንድና በነቢያት የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ጌታ በገዛ ቁስሉ እኛን መፈወሱን ገልጸዋል።

ከዚህም በኋላ ሐዋርያቱን ወደ ቢታንያ አውጥቶ ሥልጣነ ክህነትን እንደሰጣቸው፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን እንዳስተማራቸውና ‘ኃይል ከአርያም እስክትለብሱ ድረስ በዚሁ ቆዩ፤ አጽናኝ የሆነውን መንፈስ ቅዱስ እልክላችኋለሁ’ ብሎ ወደ ሰማይ ከፍ ከፍ እያለ ከአይናቸው መሰወሩን አብራርተዋል።

ምዕመናንም ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሚመጡበት ጊዜ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን፣ የቅዱሳን መላእክትን፣ የነቢያትን፣ የሐዋርያትን፣ የጻድቃንንና የሰማዕታትን ረድኤት፣ ጸጋና በረከት እንደሚያገኙና ከስሞች ሁሉ በላይ በሆነው በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ኃይልን እንደሚቀበሉ አሳስበዋል።

በመርሐ ግብሩ ማጠቃለያ ላይ የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ መዊዕ አባ ላዕከ ማርያም ንጉሤ በደብሩ ውስጥ በአሁኑ ወቅት በስኬት እየተከናወኑ የሚገኙትን የልማት ሥራዎችና በቀጣይም በስብከተ ወንጌል ተደራሽነት ዙሪያ ሊሠሩ የታቀዱትን ዋና ዋና ዕቅዶች ሪፖርት በዝርዝር አቅርበዋል።

በዋና ሥራ አስኪያጁ መልካም ፈቃድ መልአከ ብርሃናት ቆሞስ አባ ገብረ ሕይወት ንጉሤ የሀገረ ስብከቱ የካህናት አስተዳደር ክፍል ኃላፊ ቃለ ምዕዳን ቡራኬ በዓሉ በሰላም ተጠናቋል።

የሀገረ ስብከቱ የየክፍሉ ኃላፊዎች ፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፡ የሰንበት ት/ቤት ዘማርያን ፡ በርካታ ኦርቶዶክሳውያን ምዕመናን በበዓሉ ላይ ታድመዋል ።

በዲ/ን አየለ

የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት
ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ

❖ ግንቦት ፲፫ ፦ ዕርገተ ክርስቶስ ❖ (Ascension) “አምላክ በእልልታ፥ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ” (መዝ. ፵፮፥፭)። የጌታችን፣ የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶ...
21/05/2026

❖ ግንቦት ፲፫ ፦ ዕርገተ ክርስቶስ ❖
(Ascension)

“አምላክ በእልልታ፥ እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ” (መዝ. ፵፮፥፭)።
የጌታችን፣ የአምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ በተከበረ በዐርባኛው ቀን የሚውለው ዐቢይ በዓል “ዕርገት” ይባላል። ዕርገት ከጌታችን ዘጠኙ ዐበይት በዓላት አንዱ ሲሆን፣ በዚህ ዓለም የነበረውን የማዳን ሥራ ጨርሶ ወደ ሰማያዊ ዙፋኑ በክብርና በምስጋና መመለሱን የምንዘክርበት ታላቅ በዓል ነው።

በዓለ ዕርገት በየዓመቱ የሚውልበት ዕለት ሐሙስን ባይለቅም፣ ቀኑ ግን የአጽዋማትና በዓላት ማውጫ ቀመርን (ባሕረ ሐሳብን) ተከትሎ ከፍ እና ዝቅ ይላል። በዚህ መሠረት በ፳፻፲፰ ዓ.ም በዓሉ የሚውለው ግንቦት ፲፫ ቀን ነው። ከዕርገት በዓል ጀምሮ እስከ በዓለ ጰራቅሊጦስ ዋዜማ (እስከ ዐርባ ዘጠነኛው ቀን) ያለው ወቅት “ዘመነ ዕርገት” ተብሎ ይጠራል።
በዚህ ዘመን ውስጥ በሚገኘው እሑድ ሌሊት ሊቃውንቱ የሚያደርሱት መዝሙር “በሰንበት ዐርገ ሐመረ ገሠፀ ባሕረ ወገሠፆሙ ለነፋሳት ወይቤሎሙ ኢትናፍቁ ወኢይምጻእ ኑፋቄ ውስተ ልብክሙ በከመ ፈነወኒ አቡየ አነኒ እፌንወክሙ ውስተ ቤተ አቡየ ብዙኅ ማኅደር ቦቱ ካዕበ እመጽእ ወእነሥአክሙ ከመ ተሀልዉ ምስሌየ በመንግሥተ አቡየ ዘበሰማያት።

ትርጕም፦
በሰንበት ወደመርከብ ወጣ ባሕርን ጸጥ አደረገ ነፋሳትንም ገሠፀ አትጠራጠሩ ወደልባችሁ ጥርጥር አይግባ አባቴ እኔን እንደላከኝ እኔም እልካችኋለሁ በአባቴ ቤት ብዙ ማደሪያ አለ አላቸው በሰማያት ባለ በአባቴ መንግሥት ትኖሩ ዘንድ ዳግመኛ መጥቼ እወስዳችኋለሁ። ” የሚል ሲሆን፣ ይኸውም ጌታ በታንኳ ላይ ሆኖ ማዕበሉን እንደገሠጸና ሐዋርያቱን በሃይማኖት እንዳጸናቸው ያስገነዝባል።

ጌታችን ከተነሣ በኋላ ዕለቱን ወደ ሰማይ አላረገም። ለአርባ ቀናት ያህል ለደቀ መዛሙርቱ እየተገለጠ፣ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ምሥጢራትን፣ ሕግጋትንና ቀኖናተ ቤተ ክርስቲያንን አስተምሯቸዋል።

በዐርባኛው ቀን ሐዋርያትን ወደ ቢታንያ (ደብረ ዘይት ተራራ) አውጥቶ፣ እጆቹን አንሥቶ ባረካቸውና የሥልጣነ ክህነትን ጸጋ ሰጣቸው። ዓለምን ዞረው እንዲያስተምሩ መመሪያ ከሰጣቸው በኋላ፣ የኃይል ቃል የተባለውን መንፈስ ቅዱስን እስኪልክላቸው ድረስ ከኢየሩሳሌም እንዳይወጡ አዘዛቸው። ይህንን ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት በአካልና በሥጋ ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው። ደቀ መዛሙርቱ ወደ ሰማይ ትኩር ብለው ሲመለከቱ ሳሉ፣ ነጫጭ ልብስ የለበሱ ሁለት መላእክት ተገልጠው፣ የገሊላ ሰዎች ሆይ፥ ወደ ሰማይ እየተመለከታችሁ ስለ ምን ቆማችኋል? ይህ ከእናንተ ወደ ሰማይ የወጣው ኢየሱስ ወደ ሰማይ ሲሄድ እንዳያችሁት፥ እንዲሁ ይመጣል (ሐዋ. ፩፥፲-፲፩) በማለት የዳግም ምጽአቱን ምሥጢር አበሰሩ።

አምላካችን ምሉዕ በኩለሄ (ሁሉን የሞላ) በመሆኑ በባሕርዩ መውጣትና መውረድ የለበትም። ወረደ ሲባል ሰማይ አልጎደለችም፣ መውረዱ ፍጹም ሰው መሆኑንና የትሕትና ሥራ መፈጸሙን ያመለክታል።

ዐረገ ሲባልም ከሰማያዊ ዙፋኑ ተለይቶ ነበር ማለት ሳይሆን፣ በምድር ላይ ሊሠራ ያለውን የማዳን ሥራ መፈጸሙንና በሥጋው ማረጉን ያሳያል።

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይህንን ምሥጢር በሁለት ከፍለው ያሳዩናል፤ የመጀመሪያው የቃል ዕርገት በማኅፀን ሲሆን፣ ሉዓላዊው ቃል የሰውን ሥጋ በመዋሐድ ራሱን ዝቅ ማድረጉን፣ የሥጋ ገንዘብ ለቃል፣ የቃልም ገንዘብ ለሥጋ መሆኑን ያረግጣል። ሁለተኛው ደግሞ የሥጋ ዕርገት በዓርባ ቀን ሲሆን፣ መከራ የተቀበለው፣ የሞተውና የተነሣው የሰውነታችን (የሥጋችን) ባሕርይ ከሁሉ በላይ ከፍ ከፍ ማለቱን ያሳያል።

የጌታችን ዕርገት አስቀድሞ በብሉይ ኪዳን ነቢያት የተነገረ ነበር። ነቢዩ ዳዊት በጥልቀት ከመሰከራቸው መካከል፣ “እግዚአብሔር በመለከት ድምፅ ዐረገ” (መዝ. ፵፮፥፭) በማለት የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት የመሰከረበት የልዕልናው ቃል ይጠቀሳል። በተጨማሪም “ወደ ላይ ዐረግህ ምርኮን ማረክህ፥ ስጦታዎችንም ለሰዎች ሰጠህ” (መዝ. ፷፯፥፲፰) በማለት በኃጢአት የተማረከውን የአዳምን ዘር ነጻ አውጥቶ ወደ ገነት ማሻገሩንና ለሐዋርያት የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ መለገሱን በምስጢረ ድል ገልጾታል። የአቅጣጫውንም ምሥጢር ሲያስረዳ “በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ላረገ ለእግዚአብሔር ዘምሩ” (መዝ. ፷፯፥፴፫) ብሏል። እዚህ ላይ ምሥራቅ የተባለችው አምላክን በጀርባዋ የተሸከመችው እመቤታችን ድንግል ማርያም ስትሆን፣ ከእርሷ በተዋሐደው ሥጋ ማረጉን በጥልቀት ያጠይቃል።

የኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት አስቀድመው ካረጉት እንደ እነ ሄኖክና ኤልያስ ካሉ ቅዱሳን ዕርገት ፍጹም ይለያል። ቅዱሳኑ በራሳቸው ሥልጣን ሳይሆን እግዚአብሔር በኃይሉ ወሰዳቸው፤ ለምሳሌ ኤልያስ በሠረገላና በዐውሎ ንፋስ ታግዞ ነው የወጣው። ጌታችን ግን አሳራጊ ሳይሻ በገዛ አምላካዊ ኃይሉና በባሕርይ ሥልጣኑ ዐረገ። ቅዱሳኑ የተወሰዱት ወደ ሰማየ ሰማያት ሳይሆን ወደ ፍጡር ቦታ (ወደ ብሔረ ሕያዋን) ሲሆን፣ ጌታችን ግን ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ወደሆነው ወደ ቀደመ ክብሩ፣ ወደ ባሕርይ አባቱ ዙፋን ወጣ። ሄኖክ ሞትን እንዳያይ ተሰወረ፣ ኤልያስም ለአምላክ ክብር ምስክር ለመሆን ተወሰደ፤ ጌታችን ግን ሞትን በሞቱ ቀጥቅጦ፣ ትንሣኤን አብስሮ፣ የሰውን ባሕርይ አክብሮ ለማስገባት የበኩር ሆኖ ማረጉ የዕርገቶቹን ልዩነት ግልጽ ያደርገዋል።

በጸሎተ ሃይማኖት ላይ “ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ” (በክብር ወደ ሰማይ ዐረገ በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ) ተብሎ እንደተደነገገው፣ “ቀኝ” መባሉ ለእግዚአብሔር ግራና ቀኝ ኖሮት አይደለም። ይህ አገላለጽ በሥልጣን፣ በክብርና በልዕልና ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እኩል መሆኑን ያስረዳል።

በአጠቃላይ ዕርገት የድኅነታችን ማጠናቀቂያ ማኅተም ነው። ጌታችን ባይወለድ ኖሮ ሰው አይቀደስም ነበር፤ ባይሰቀል ኖሮ የዕዳ ደብዳቤአችን አይቀደድም ነበር፤ ባይነሣ ኖሮ መቃብር አይሸነፍም ነበር፤ ባያርግ ኖሮ ደግሞ የሰው ልጅ ተፈጥሮ ወደ ሰማይ አይገባም ነበር።

ጌታችን፣ መድኃኒታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የማዳን ሥራህን ፈጽመህ በታላቅ ክብርና በደመና ወደ ሰማይ እንደ ዐረግህ፣ የሁላችንንም ሕይወት፣ ሐሳብና ምኞት ከምድራዊውና ከጠፊው ነገር ወደ ሰማያዊው ክብርህ ከፍ አድርግልን።

የበዓለ ዕርገትህን በረከትና ረድኤት በሁላችን ላይ አኑር። በቅዱስ ሥጋህ የሰውን ባሕርይ አክብረህ በአብ ቀኝ እንዳስቀመጥከው፣ እኛንም ከውርደትና ከኃጢአት ማዕበል አውጥተህ በጸጋህና በምሕረትህ አክብረን። ወደ ሰማይ ስታርግ ለሐዋርያትህ የሰጠኸውን ሰላም፣ ዛሬም ለሀገራችን፣ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንና ለቤተሰቦቻችን አድለን።

የኃይል ቃል የተባለውን መንፈስ ቅዱስን እስክትልክ ድረስ ደቀ መዛሙርትህ በትዕግሥትና በጸሎት እንደቆዩ፣ እኛንም በሃይማኖት፣ በትዕግሥትና በፍቅር አጽናን። በጭንቅ፣ በስደት፣ በረኃብና በሕመም ላይ ያሉትን ወገኖቻችንን ሁሉ በምሕረትህ ጐብኛቸው፤ ከችግራቸውም አሳርፋቸው።

​የሰላም ባለቤት እግዚአብሔር ሆይ! ሰላምህንና ምሕረትህን ከእኛ አታርቅ። ለበጎ ሥራ ለመቆም የበቃን አድርገን። ጸሎታችንንና ልመናችንን ተቀብለህ፣ በበዓሉ ረድኤት ሁላችንንም ባርከን፣ ቀድሰን። አሜን

እንኳን ለብርሃነ ዕርገቱ በሰላምና በጤና አደረሳችሁ!

በዲ/ን አየለ

#ዕርገት #ኦርቶዶክስ #ተዋሕዶ +ሚዲያ

በባቱ ከተማ ኤዶ ቆንጠላ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት የመሠረት ድንጋይ ተቀመጠ። ግንቦት 12 ቀን 2018 ዓ.ም [ ]  #አዳማ  — በምሥራቅ ...
20/05/2026

በባቱ ከተማ ኤዶ ቆንጠላ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት የመሠረት ድንጋይ ተቀመጠ።

ግንቦት 12 ቀን 2018 ዓ.ም [ ]

#አዳማ — በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት በባቱና አዳሚ ጂዶ ኮምቦልቻ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር በሚገኘው የባቱ ከተማ የኤዶ ቆንጠላ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን፣ ለብዙ ዘመናት የአካባቢው ማኅበረሰብ ሲመኘውና ሲጓጓለት የነበረው የትምህርት ቤት ግንባታ ግንቦት 11 ቀን 2018 ዓ.ም የወረዳ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ እና የባቱ ከተማ ም/ከንቲባ በጋራ የመሠረት ድንጋዩን በጋራ አስቀምጠዋል ።

የረጅም ጊዜ የሕዝብ ጥያቄ የነበረውን ይህንን ከቅድመ መደበኛ (KG) እስከ መጀመሪያ ደረጃ የሚደርስ የትምህርት ቤት ፕሮጀክት እውን ለማድረግ የባቱ ከተማ መስተዳድር እና የወረዳው ቤተ ክህነት እጅና ጓንት ሆነው በጋራ መሥራታቸው በመሥራታቸው መሆኑ ተመላክቷል።

የወረዳ ቤተ ክህነቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ካህናት አለቃ ኤርሚያስ ኃ/ጊዮርጊስ በመርሐ ግብሩ ላይ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችን በሙሉ ያመሰገኑ ሲሆን፣ ግንባታው በፍጥነት ፍጻሜ እንዲያገኝ ወረዳ ቤተ ክህነቱ ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ከብፁዕ አባታችን አቡነ ጎርጎርዮስ በሚሰጠው መመሪያና መልካም ፈቃድ መሠረት ሁኔታዎች ሁሉ እንዲመቻቹ አስፈላጊውን ጥረት እንደሚያደርጉ አሳውቀዋል።

ዋና ሥራ አስኪያጁ አክለውም ይህ ፕሮጀክት የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የረጅም ጊዜ ዕቅድ መሆኑን ጠቅሰው፣ ዛሬ ላይ በብፁዕነታቸው አባታዊ ድጋፍ፣ በባቱ ከተማ መስተዳድርና በአካባቢው ሕዝብ ትብብር የመሠረት ድንጋዩ በመቀመጡ የተሰማቸውን ታላቅ ደስታ ገልጸዋል።

በዕለቱ የባቱ ከተማ ምክትል ከንቲባ ክቡር አቶ ኡስማን ቱሴ ባስተላለፉት መልእክት፣ ለትምህርት ዘርፍ ልዩ ቅድሚያ ሰጥታ ወደ ተግባራዊ እንቅስቃሴ የገባችውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በአጽንኦት አመስግነዋል።

የትምህርት ቤቱ ግንባታ ተፋጥኖ ለሚመጣው የ2019 ዓ.ም የመማር ማስተማር ዘመን ቢያንስ የቅድመ መደበኛ (KG) ክፍል ደርሶ ተማሪዎችን መቀበል እንዲችል መስተዳድሩ አስፈላጊውን እገዛ፣ ክትትልና ትብብር ሁሉ እንደሚያደርግ ክቡር ምክትል ከንቲባው ቃል ገብተዋል።

በተጨማሪም የባቱ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያ በበኩሉ ባስተላለፈው መልእክት "ይህ በየሥፍራው የሚደረግ የልማትና የትምህርት መሻት ለእኛ ለጸጥታ አካላት ትልቅ እፎይታ ነው፤ ሀገርን በጥሩ እና በተማረ ዜጋ ለመቅረጽ የሚደረጉ መሰል ጥረቶች ወንጀልን አስቀድሞ ለመከላከል የሚረዱ ዋና መፍትሔዎች ናቸው" ብሏል።

አያይዞም ባቱ ከተማ የሰላም፣ የቱሪዝምና የልማት አምባሰደር መሆኗን በተግባር እያስመሰከረች መሆኑን የጠቀሰው የፖሊስ መምሪያው፣ ይህ የተጀመረው በጎ ተግባር ቀጣይነት ይኖረው ዘንድ እያበረታታ ለከተማው አስተዳደርና ለሃይማኖት ተቋሙ ያለውን ከፍ ያለ አክብሮትና ምስጋና አቅርቧል።

በዚህ ታሪካዊ የመሠረት ድንጋይ ማስቀመጥ ሥነ ሥርዓት ላይ የደብሩ አስተዳዳሪ ሊቀ ሥዩማን ቀሲስ ሰሎሞን አበበ፣ የባቱ ከተማ ትምህርት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ቡልቡሎ ጋዳ፣ የባቱ ከተማ ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ ሮባ እሬሶ፣ የኢልካ ኤዶ ቀበሌ አስተዳዳሪ አቶ ገመዶ ከድር፣ የተከበሩ አባ ገዳዎች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ የሃይማኖት አባቶችና እናቶች እንዲሁም በርካታ የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል ።

በዲ/ን አየለ
የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት
ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ

መረጃውን ያደረሰን መምህር አስናቀ ነው።

#መድኃኔዓለም

20/05/2026

ፍልሰተ ዐጽሙ ለአቡነ ተክለሃይማኖት ዓመታዊ ክብረ በዓል በአዳማ ደብረ አሚን

#አቡነ #ተክለሃይማኖት

በአዳማ ደብረ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን የጻድቁ አባታችን የፍልሰተ ዐጽም ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል በታላቅ መንፈሳዊ ድምቀት ተከበረ። ግንቦት 12 ቀን 2018 ዓ.ም [  ]  ...
20/05/2026

በአዳማ ደብረ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን የጻድቁ አባታችን የፍልሰተ ዐጽም ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል በታላቅ መንፈሳዊ ድምቀት ተከበረ።

ግንቦት 12 ቀን 2018 ዓ.ም [ ]

#አዳማ — በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘንድ በታላቅ ድምቀት የሚታሰበውና የሚከበረው የጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖት የፍልሰተ ዐጽም ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል (ግንቦት 12 ቀን) በአዳማ ደብረ አሚን አቡነ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሣሕል ቀሲስ ነጋሽ ሀብተ ወልድ በተገኙበት በልዩ መንፈሳዊ ሥነ-ሥርዓት ተከብሯል።

"ወጻድቃንሰ ይወርስዋ ለምድር፤ ወይነብሩ ውስቴታ ለዓለመ ዓለም - ጻድቃን ምድርን ይወርሳሉ፥ በእርስዋም ለዘላለም ይኖራሉ።" (መዝ 37፥29) በሚል ርዕስ በቃለ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሣህል ቀሲስ ነጋሽ ሀብተ ወልድ፣ በኪዳኑ ታቦት ፊት በበዓሉ ላይ ለታደሙ ምዕመናንና ምዕመናት ትምህርተ ወንጌል አስተምረዋል።

ዋና ሥራ አስኪያጁ በትምህርታቸው የጻድቁን ታሪክ ከሥር ከመሠረቱ አንስተው ሲያብራሩም፦ "አቡነ ተክለሃይማኖት በእግዚአብሔር ድንቅ ጥበብ፣ በሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ብሥራት በሰሜን ሸዋ ኢቲሳ ከተባለ ቦታ ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኃረያ ተፀንሰው ተወለዱ። በተወለዱ በሦስተኛው ቀን ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው 'አሐዱ አብ ቅዱስ፤ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፤ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ' በማለት ሥላሴን ያመሰገኑ አባት ናቸው።

ሕይወታቸውን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ ይህንን ዓለም ንቀው፣ በጾም በጸሎትና በምናኔ ኖረዋል። አንድ እግራቸው እስኪቆረጥ ድረስ በአንድ ቦታ ቁመው ለ22 ዘመናት፣ እግራቸው ከተሰበረ በኋላም በአንድ እግራቸው ለ7 ዓመታት በበዓት ውስጥ ጸልየዋል። እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፣ በዳሞት አውራጃ የነበረውን ገዢ ሞተለሚን ታሪክ የለወጡ፣ ጠንቋዮችን ያጠፉና ሃይማኖታችንን ወደ ከበረ ሥፍራዋ የመለሱ ሐዋርያ ናቸው" በማለት በገድሉ ላይ ያለውን ታሪክ አንስተዋል።

በተጨማሪም ዋና ሥራ አስኪያጁ ጻድቃን የሚወርሷት ምድር የተባለችው ይህች ኃላፊዋ ዓለም ሳትሆን የእግዚአብሔር መንግሥት መሆኗን አብራርተው፤ ምዕመናን ስለ ስሙ ብለው የተራቡትን በማብላት፣ የተጠሙትን በማጠጣትና የታረዙትን በማልበስ ምዕመናን በጻድቁ ምልጃ እንዲጸኑ በአባታዊ ምክራቸው አሳስበዋል።

የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ምሕረት ቆሞስ አባ ፀሐይ ስመኝ በበኩላቸው፤ በጻድቁ ስም ቀዝቃዛ ውሃ ያቀመሰ ሁሉ የቃል ኪዳኑ ተጠቃሚ እንደሚሆን ገልጸው፣ አቡነ ተክለሃይማኖት ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር የሥላሴን መንበር ያጠኑ ታላቅ አባት መሆናቸውንና ጻድቁ ባለበት ሥፍራ ሁሉ በረከት፣ ጤና፣ ሰላም፣ አንድነትና ፍቅር ይሰፍናል ።

ቆሞስ አባ ፀሐይ ስመኝ መልእክታቸውን ሲቀጥሉም፤ የዛሬው የፍልሰተ ዐጽም በዓል አባ ሕዝቅያስ በሕልም ተገልጦላቸው በታዘዙት መሠረት ‘የአባታችሁን ዐፅም ከዋሻው ወደ ታላቁ ቤተ ክርስቲያን ታፈልሱ ዘንድ ኑ፤ ተሰብሰቡ’ ብለው መልእክት በላኩት መሠረት ምዕመናንና አሥራ ሁለቱ መምህራን ከአራቱም አቅጣጫ ተሰብስበው ዐፅማቸው የፈለሰበትን ታሪካዊ ዕለት የምናስብበት ድንቅ ዕለት ነው በማለት በዓሉ በጸሎተ ቡራኬ ተጠናቋል።

የሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ በበዓሉ ዕለት እንደተመለከተው፤ በደብሩ እየታነጸ ያለው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ግንባታ በፍጥነቱ፣ በጥራቱና በአሠራር ቴክኒኩ እጅግ የሚያስገርምና በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሥር ላሉ አድባራት ሁሉ እንደ ትልቅ ሞዴል የሚቆጠር መሆኑን ነው።

በደብሩ ውስጥ የጻድቁ አቡነ ተክለሃይማኖት ታቦት ብቻ ሳይሆን የጻድቁ አቡነ ሐራ ድንግል እና የካህናተ ሰማይ የቃል ኪዳን ታቦታት የሚገኙ ሲሆን፣ የጻድቁ አቡነ ሐራ ዓመታዊ በዓል በሕዳር 19 እና በጥር 11 ቀን፣ ወርሃዊ በዓላቸው ደግሞ ወር በገባ በ11 ቀን እንዲሁም የካህናተ ሰማይ ዓመታዊ ክብረ በዓል በሕዳር 24 ቀን በታላቅ ድምቀት ይከበራል።

የአዳማ ከተማና አካባቢው ምዕመናንም በተጠቀሱት የበዓላት ቀናት ሁሉ በዚህ ታሪካዊ ሥፍራ በመገኘት የበረከቱ ተካፋይ እንዲሆኑ ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ ጥሪውን ያስተላልፋል።

በበዓሉም ላይ የአድባራት አስተዳዳሪዎች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፡ የሰንበት ት/ቤት ዘማርያን ፡ በርካታ ኦርቶዶክሳውያን ምዕመናን ተገኝተዋል ።

በዲ/ን አየለ
የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት
ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ

ለኢትዮጵያዊቷ ጻድቅ ለቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ዓመታዊ ክብረ በዓል (ግንቦት 12) እንኳን በሰላምና በጤና በሰላም አደረሳችሁ አደረሰን ። ቅድስት እናታችን ክርስቶስ ሠምራ ዓለምንና ክብሯን፣ ...
20/05/2026

ለኢትዮጵያዊቷ ጻድቅ ለቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ዓመታዊ ክብረ በዓል (ግንቦት 12) እንኳን በሰላምና በጤና በሰላም አደረሳችሁ አደረሰን ።

ቅድስት እናታችን ክርስቶስ ሠምራ ዓለምንና ክብሯን፣ ትዳሯንና ንብረቷን ንቃ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ሙሉ ሕይወቷን ለጸሎትና ለተጋድሎ የሰጠች፤ በተለይም ደግሞ ስለ ሰው ልጆች ሁሉ ድኅነትና ምሕረት ሌሊትና ቀን በጣና ባሕር ውስጥ ቆማ በመጸለይ የምሕረት ቃል ኪዳን የተቀበለች ታላቅ የፍቅርና የንሥሐ እናት ናት።

የእናታችን የቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ቅዱስ ጸሎቷ፣ ትሕትናዋ፣ ረድኤትና በረከቷ ከሁላችን ጋር ይሁን።

ልዑል እግዚአብሔር ሀገራችንም ሰላምን፣ ፍቅርንና አንድነትን ይስጠን።

#ግንቦት12 #ጻድቅ #ኦርቶዶክስ #ተዋሕዶ

❖ ግንቦት ፲፪፦ የታላቁ ጻድቅ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ፍልሰተ ዐፅም በዓል ግንቦት ፲፪ ቀን በዚህች ቀን ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት፣ ኢትዮጵያዊው ንጉሥ እስክንድር፣ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ...
20/05/2026

❖ ግንቦት ፲፪፦ የታላቁ ጻድቅ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ፍልሰተ ዐፅም በዓል

ግንቦት ፲፪ ቀን በዚህች ቀን ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት፣ ኢትዮጵያዊው ንጉሥ እስክንድር፣ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቅዱስ መስቀል፣ ቅዱስ ሚናስ፣ ቅዱስ እስጢፋኖስ፣ የመላልዔል ልጅ ያሬድ፣ እንደዚሁም ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ይታሰባሉ።

በመጽሐፈ ገድላቸው እንደተጠቀሰው ቅዱስ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ዓለም የኖሩበት ጠቅላላ ዕድሜ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከዐሥር ወር ከዐሥር ቀን ነው።

ገድላቸው ዕድሜያቸውን በመከፋፈል በእናት አባታቸው ቤት ፳፪ ዓመት፣ በከተታ ፫ ዓመት፣ በዊፋት ፱ ወር፣ በዳሞት ፲፪ ዓመት፣ በአማራ ፲ ዓመት፣ በሐይቅ ፲ ዓመት፣ በደብረ ዳሞ ፲፪ ዓመት፣ በትግራይ ገዳማት በመዘዋወርና ወደ ኢየሩሳሌም በመመላለስ ፩ ዓመት፣ ዳዳ በሚባል አገር ፩ ወር፣ በአሰቦ ገዳም (አሁን ደብረ ሊባኖስ) ፳፱ ዓመት ከ፲ ቀን መቆየታቸውን ይናገራል።

ጻድቁ ሕይወታቸውን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ ይህንን ዓለም ንቀው በጾም በጸሎት ተወስነው በብሕትውና የኖሩ ሲሆን፣ እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ሰብከዋል። በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ታላቅ ሐዋርያ ናቸው።

ጻድቁ ለሰባት ዓመታት ያህል ያለምግብና ያለውኃ በትኅርምት ሌትና ቀን እንቅልፍ በዓይናቸው ሳይዞር እንደ ምሰሶ ጸንተው፣ በአንድ እግራቸው በመቆም ለሰው ዘር ሁሉ ድኅነትን ሲለምኑ ኖረዋል። ከሰባቱ ዓመታት ውስጥ ጥቂት ውኃ የቀመሱት በአራተኛው ዓመት ብቻ ነበር።

በዚህ ጊዜ ውስጥ ጌታችን ተገልጦ ስለ ቀናች ሃይማኖታቸው፣ ሃይማኖትን ለማስተማር መላዋን ኢትዮጵያን ስለመዞራቸው፣ ከአረማውያን ሕዝብ ጋር በሃይማኖት ስትታገል ደማቸውን ስለማፍሰሳቸው፣ ወደ ኢየሩሳሌም ወርደው ልዩ ልዩ የቅዱሳን ቦታዎች ስለመሳለም፣ በሰባት ዓመታት ቊመት የአንዱ አገዳ እግራቸው ስለመሰበሩ፣ ስለብዙ ጾም ጸሎታቸውና ስግደታቸው፣ እንዲሁም ስለ ልባቸው ንጽሕናና ቅድስና በመስቀል ምልክት የተጌጡ ሰባት የሕይወት አክሊላትን አቀዳጅቷቸዋል።

ምድራዊ ሕይወታቸውን በተጋድሎና በሐዋርያዊ አገልግሎት ከፈጸሙ በኋላ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ የሚያልፉበት ቀን በተቃረበ ጊዜ፣ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን መላእክት፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ወደ እርሳቸው በመምጣት የሚያርፉበትን ዕለት ነገራቸው። በስማቸው መታሰቢያ ለሚያደርጉ፣ ለነዳያን ለሚመጸውቱ፣ ቤተ ክርስቲያን ለሚያሠሩና ዝክራቸውን ለሚያዘክሩ ሁሉ በዚህ ዓለምም ሆነ በወዲያኛው ፍጹም ዋጋና ፍጹም ክብር እንደሚሰጣቸው ጌታ ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል።

አቡነ ተክለ ሃይማኖትም የዕረፍታቸው ጊዜ መቃረቡን ባወቁ ጊዜ የመንፈስ ልጆቻቸውን ጠርተው ጌታችን የነገራቸውን ሁሉ ካስረዱና አባታዊ ምክርና ተግሣፅ ከሰጧቸው በኋላ ነሐሴ ፳፬ ቀን ከዚህ ዓለም ድካም ዐረፉ። በዕረፍታቸውም ሰዓት ልጆቻቸው በማኅሌት፣ በዝማሬና በምስጋና በክብር ቀበሯቸው፤ ጌታችንም ነፍሳቸውን «የጠራሽ፣ ንጽሕት ነፍስ ሆይ ወደእኔ ነዪ» ብሎ በክብር ተቀበላት።

ወደ ፍልሰተ ዐፅማቸው ታሪክ ስንመለስ፣ መጽሐፈ ገድላቸው የሚነበበው የከበረና የተቀደሰ የአባታችን የተክለ ሃይማኖትን ክብሩንና ገናንቱን በሚናገረው፣ ዐፅሙ የፈለሰበትን ግንቦት ፲፪ ቀን ነው። ይኸውም ዕለት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓልና ከአባታችን ወዳጅ ከመላእክት አለቃ ከቅዱስ ሚካኤል በዓል ጋር የተባበረ ነው። እንደ ዮሐንስና እንደ ነቢዩ ኤርምያስ ከእናቱ ማኅፀን እግዚአብሔር የመረጠው የክቡር አባታችን ዐፅሙ የፈለሰበት ቀን ዛሬ ነው።
አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከዚህ ዓለም ከተለዩ በ፶፯ኛው ዓመት የካቲት ፲፱ ቀን ለመንፈስ ልጃቸው ለአባ ሕዝቅያስ ብርሃን ለብሰው በሕልም ተገለጡላቸውና «ወዳጄ ሕዝቅያስ ሆይ ሰላም ለአንተ ይሁን! ጌታዬ በኋለኛው ዘመን ከዚህ ሥፍራ ልጆችህ ሥጋህን ያፈልሳሉ ያለኝ ዘመን ደርሷልና ሳትዘገይ ልጆቼን ሁሉ ቅጠራቸውና እስከ ምፈልስበት ቀን ድረስ ግንቦት ፲፪ ቀን ይሰብሰቡ፤ እናንተም በምስጋና በጸሎት መንፈሳዊ በዓልን አድርጉ፤ አባቴ ተክለ ሃይማኖት የሚለኝ ሁሉ በዚህች በፍልሰተ ዐጽሜ ቀን ይምጣ፣ መንፈሳዊ በዓልንም ያድርግ፤ እኔና ቅዱስ ሚካኤል ከወዳጄ አባ ፊልጶስ ጋር ስለኔ ፍቅር የተሰበሰበውን ሕዝብ ልንባርክ እንመጣለን» ከአሏቸው በኋላ ተሠወሯቸው።

አባ ሕዝቅያስም እንደታዘዙት «የአባታችሁን ዐጽም ከዋሻው ወደ ታላቁ ቤተ ክርስቲያን ታፈልሱ ዘንድ ኑ፣ ተሰብሰቡ» ብለው የጻድቁን ወዳጆች በያሉበት ሀገር ሁሉ መልእክት ላኩ። ምእመናንም ጥሪውን ተቀብለው በዓሉን ለማክበር ከአራቱም አቅጣጫ ተሰበሰቡ። በዚህ ሥራው መምህራኑ ከአባ ሕዝቅያስ ጋር ለመተባበር መጡ፤ እነዚህም፡- የወረብ አገሩ አባ አኖሬዎስ፣ የፈጠጋሩ አባ ማትያስ፣ የእርናቱ አባ ዮሴፍ፣ የሞረቱ አባ አኖሬዎስ፣ የመርሐ ቤቴው አባ መርቆሬዎስ፣ የጽላልሹ አባ ታዴዎስ፣ የወገጉ አባ ሳሙኤል፣ የወንጁ አባ ገብረ ክርስቶስ፣ የድንቢው አባ መድኃኒነ እግዚእ፣ የዳሞቱ አባ አድኃኒ፣ የክልአቱ አባ ኢዮስያስ እና የመሐግሉ አባ ቀውስጦስ ናቸው።

እነዚህ አሥራ ሁለቱ ታላላቅ መምህራን ከአባ ሕዝቅያስ ጋር በመሆን የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ዐጽም ከዐረፈበት ዋሻ ባወጡት ጊዜ ዐፅማቸው በዚያው ዕለት እንደተገነዘ በድን ይመስል ነበር፤ መዓዛውም እጅግ ያማረ ሽቱ፣ ሽቱ ይሸት ነበር። በአባታችን ዐፅም ቀኝና ግራም መስቀል ተተክሎ የነበረ ሲሆን በዐጽማቸውም ብዙ ድንቅ ተአምራት ተደርገዋል። ይህንን የአባታችንን ዐፅም በሣጥን አክብረው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወስደው በመንበሩ ፊት ሦስት ጊዜ አዞሩት።

በዚህች ዕለት አስቀድመው ለአባ ሕዝቅያስ በሕልም እንደነገሯቸው ብፁዕ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከቅዱስ ሚካኤልና ከአባ ፊልጶስ ጋር ወደ ቤተ ክርስቲያኑ መጥተው ዐጽማቸው እስኪያረፍ ድረስ ከመንበሩ ተቀምጠው ቆይተው ዐጽማቸው ካረፈ በኋላ የተሰበሰበውን ሕዝብ ባርከው በክብር ወደ ሰማይ ዐረጉ። መምህራኑና ምእመናኑም በዓሉን በታላቅ ደስታ አክብረው በሰላም ወደ የቤታቸው ተመለሱ።

ከዚያ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በዓሉን በታላቅ ሃይማኖታዊ ሥነ ሥርዐትና በድምቀት ይከበራል ።

የጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ረድኤትና በረከት በሁላችን ላይ ይደር፤ አሜን።

በዲ/ን አየለ

ዋቢ
▶ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት

#ኦርቶዶክስ #ተዋሕዶ #ኢትዮጵያ #በረከት

እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ወርኃዊ በዓል በሰላም በጤና  አደረሳችሁ! አደረሰን!የመልአኩ ጥበቃ፣ ምልጃና በረከት አይለየን። ለሀገራችንም ሰላምንና ፍቅርን ያድልልን።​   #ሚካኤል ...
20/05/2026

እንኳን ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ወርኃዊ በዓል በሰላም በጤና አደረሳችሁ! አደረሰን!

የመልአኩ ጥበቃ፣ ምልጃና በረከት አይለየን። ለሀገራችንም ሰላምንና ፍቅርን ያድልልን።

​ #ሚካኤል

Address

Eastern Shoa Diocese Office
Adama
271

Telephone

+251941372168

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ /Hamere Tewahedo Media posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Place Of Worship

Send a message to ሐመረ ተዋሕዶ ሚዲያ /Hamere Tewahedo Media:

Share