21/08/2016
ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር
እንኳን ለጾመ ፍልሰታ ለማርያም በሰላምና በጤና አደረሳችሁ።
ጾመ ፍልሰታ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ ኦርቶዶክሳውያን የእመቤታችን ወዳጆች ሁሉ የእመቤታችን የድንግል ማርያምን በረከት ለማግኘት በጉጉት የሚጠብቋት፣ሕጻናት ሳይቀሩ ወደ ቤተክርስቲያን ለመሄድ የሚቸኩሉባት፣ገዳማውያን አበው በዓታቸውን ዘግተው ከሰው ተለይተው ከእግዚአብሔር ጋር ብቻ በጸሎት የሚነጋገሩባት፣ ካህናቱ ቀን ከሌሊት በጸሎት የሚተጉባት፣ ብዙ ሰዎች በዓለም ያለውን ነገር ሁሉ እርግፍ አድርገው ትተው ወደ ገዳማት በመሄድ ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙባት የተመረጠችና ፍጹም በረከት የምታስገኝ የጾም ጊዜ ናት። ምድራዊ ያይደለ ሰማያዊ ፣ሥጋዊ ያይደለ መንፈሳዊ፣ አፍአዊ ያይደለ ውሳጣዊ የሆነ እውነተኛውን ምግብ እውነተኛውን መጠጥ ያስገኘችልን እመቤታችንን በፍጹም መንፈሳዊ ፍቅር የምናስብባት፣ሐዋርያት ለእመቤታችን ያላቸውን ፍጹም ፍቅር በጾም የገልጹባት ናት። / ኦ ማዕዶት ዘበኃቤኪ ዐደዉ አበው ቀደምት እሞት ውስተ ሕይወት/ የቀደሙት አበው ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገሩብሽ መሸጋገሪያ ድልድይ ተብላ የተመሰገንች ምልዕተ ጸጋ ምልዕተ ክብር፣ ነቢያት ትንቢት የተናገሩላት፣ ምሳሌ የመሰሉላት፣ የነቢያት ትንቢታቸው፣ ሐዋርያት ወንጌልን የሰበኩለትን ጌታ የወለደችላቸው የሐዋርያት ሞገሳቸው፣ ስደትን ለሰማዕታት ያስተማረች የሰማዕታት እናታቸው፣ መላእክትን በንጽሕና በቅድስና የምትመስላቸው የመላእክት እኅታቸው፣ ተብላ በቅዱሳን አንደበት የተመሰገነች እመቤታችን በድንግልና በቅድስና የወለደችው የልጅዋን ፍጹም በረከት ይዛ የተገለጸችበት ጊዜ ነው። ጌታም የሐዋርያትን ጾምና ጸሎት ተቀብሎ ለደቀ መዛሙርቱ እመቤታችንን በክብር የገለጸበት ናት። ጌታ እነኋት እናትህ ብሎ በቀራንዮ በመስቀሉ ስር ለዮሐንስ ካስረከበ ጊዜ ጀምሮ አብረው ሲኖሩ በጥር ፳፩ እሑድ ቀን በ፷፬ ዓመቷ አረፈች። ደቀ መዛሙርቱም ጌታ ካረገ በኋላ በምድር ላይ በሥጋ ከነሱ ጋር የቀረች እናት ሆና የተሰጠቻቸው ናትና ስትለያቸው አዝነው አልቅሰው ሊቀብሩ ወደ ጌቴሴማኒ ይዘው ሲሄዱ ልጅዋን በግፍ የገደሉት አይሁድ ዛሬም ከምቀኝነት አያርፉምና ነገ እንደ ልጅዋ ተነሳች አረገች እያሉ ያውኩናል ብለው ደቀ መዛሙርቱን አሳደዷቸው ። በዚህ ጊዜ በሐዘን ልባቸው ተነካ ሳያስቡት በክብር ሳይቀብሯት ተበታተኑ። የደርሰችበትን ሳያውቁ ቀሩ ከዮሐንስ በስተቀር። ከዚህ የተነሳ በነሐሴ ፩ ቀን ሱባኤ ጀመሩ ጌታም በ፲፬ኛው ቀን አምጥቶ ሰጣቸው በክብር ቀበሯት ። በሶስተኛው ቀን ተነስታ አርጋለች። የአይሁድ ጫጫታ ጩኸትና ምቀኝነት እመቤታችንን በመቃብር ሊያስቀር አልቻለም በ፩ኛ ቆሮ ፲፭፥፶፭ ላይ ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ እንዲል ሞትን የገደለው ልጅዋ እርሷንም በክብር አስነስቷል። ዛሬም ይህንን ፍጹም የበረከት ጾም እንድናጣ በረከታችንን በመቃብር ሊያስቀሩ የሚፈልጉ ብዙ የተረፈ አይሁድ ጫጫታዎች በበዙበት ዓለም የምንኖር ክርስቲያኖች ከእግዚአብሔር ጋር ፍጹም ኅብረት እንዲኖረን፣ የእመቤታችንን በረከት እንድንቀበል፣ በመብል ሳይሆን በጾም በጸሎት፣ በምሥጋና በውዳሴ በቅዳሴ የእግዚአብሔርን ይቅርታና ምሕረት እያሰብን በአግባቡ ጾመን የበረከቱ ተከፋዮች ልንሆን ይገባል። ጾማችንን የበረከት፣ የሰላም፣ የይቅርታ፣ የምሕረት ጾም ያድርግልን። በሰላም አስጀምሮ በሰላም ያስፈጽመን። እመቤታችን ድንግል ማርያም በምልጃዋ አትለየን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር።
በአባ ገ/ሕይወት