18/06/2026
የሀኖቨር ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በከተማው በተካሄደው የአብያተ ክርስቲያናት የጰራቅሊጦስ በዓል ላይ ሀይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶችን በሰፊው በማስተዋወቅ የጎላ ተሳትፎ አደረገ።
በጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት የሀኖቨር ደብረ ይድራስ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ምዕመናን በዓለ ጰራቅሊጦስ (Pfingstmontag) አስመልክቶ በሀኖቨር ከተማ በተካሄደው አለም አቀፋዊ የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራም (interkultureller ökumenischer Gottesdienst) ላይ በመሳተፍ ሀይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶችን በሰፊው አቅርበዋል::
በፕሮግራሙ ላይ በሀኖቨርና አካባቢው የሚገኙ 12 አብያተ ክርስቲያናት ከመሳተፋቸው በተጨማሪ የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራሙ ግእዝና አማርኛን ጨምሮ በ 8 የተለያዩ ቋንቋዎች ተካሂዷል::
ዕለቱ በደብሩ የሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን ዝማሬዎች ደምቆ የዋለ ሲሆን በተለይም በፕሮግራሙ መክፈቻ ላይ የትንሣኤ ወረብ (አማን በአማን - ተንሥአ እምነ ሙታን) ሲቀርብ አጠቃላይ የፕሮግራሙ ታዳሚዎች በታላቅ ስሜት አብረው ሲያጨበጨቡና ሲያሸበሽቡ ማየት ደስ የሚያሰኝ ነበር::
እያንዳንዱ ተሳታፊ ቤተ ክርስቲያን የተለያየ ርዕስ መርጦ በየቋንቋው ጸሎት ያደረሰ ሲሆን የደብረ ይድራስ ካህናትና ምዕመናን ሰላምን በተመለከተ የዮሐንስ ወንጌል 14፥27 መነሻ በማድረግ ኦርቶዶክሳዊ የሰላም ጸሎት አድርሰዋል::
የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራሙ ከተጠናቀቀ በኋላ የደብሩ ምዕመናን ያዘጋጁትን ምግብና መጠጥ በማቅረብ የሀገራችን ባህላዊ እሴት ደምቆ እንዲታይ አድርገዋል::
የፕሮግራሙ ዋና አዘጋጅ ፓስተር ዶ/ር ሚካኤል ቮለርስ (Pastor Dr. Michael Wohlers) የደብረ ይድራስን ተሳትፎ በተመለከተ የሚከተለውን ብለዋል:-
„Die Mitwirkung Eurer Gemeinde ist ein großartiger Beitrag zur Ökumene im Stadtbezirk Hannover-Döhren und Wülfel. Sie ist außerdem ein Zeugnis lebendigen Glaubens und der Verbundenheit aller Christinnen und Christen in Hannover. Ich freue mich schon auf den ökumenischen Gottesdienst im nächsten Jahr.“
ትርጉም:-
በአለም አቀፋዊው የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራም ላይ መሳተፍ መቻላችሁ በሀኖቨር ከተማ ለሚኖሩ አጠቃላይ የክርስቲያን ማህበረሰብ ትልቅ መታደል ነው:: ተሳትፏችሁ የእምነታችሁን ጥንካሬ ከማሳየቱ በተጨማሪ በከተማችን ነዋሪ የሆኑ የተለያዩ የክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች ያላቸውን የጠበቀ ትስስር ማሳያ ነው። በመጪው ዓመትም ይህንን አለም አቀፋዊ የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራሙን አብረን እንደምናከብር ባለሙሉ ተስፋ ነኝ።
ዘገባና ፎቶዎች:- ዶ/ር ያሬድ ካሌብ (ከሀኖቨር የአጥቢያው ሚድያ)
የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሚድያ