EOTC Germany Archdiocese ፤ የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት

EOTC Germany Archdiocese ፤ የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት Verband der Äthiopisch-Orthodoxen Tewahedo Kirchen Erzdiözese von Deutschland und Umgebung e. V., Frankfurt a.

Main
Amtsgericht Frankfurt am Main VR 16730
Ethiopian Orthodox Tewahedo Church (EOTC) Germany Archdiocese
በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሚድያ በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የጀርመንና አካባቢ ሀገረ ስብከት የፌስቡክ ገጽ።
Official page of the Ethiopian Orthodox Tewahedo Church in Germany and surroundings Archdiocese

የባንክ ስም መረጃ

Bank Account: Volksbank, Frankfurt
IBAN : DE62 5019 0000 6201 1255 94
BIC: FFVBDEFF # # #

የሀኖቨር ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በከተማው በተካሄደው የአብያተ ክርስቲያናት የጰራቅሊጦስ በዓል ላይ ሀይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶችን በሰፊው በማስተዋወቅ የጎላ ተሳትፎ አደረገ።  በጀርመ...
18/06/2026

የሀኖቨር ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በከተማው በተካሄደው የአብያተ ክርስቲያናት የጰራቅሊጦስ በዓል ላይ ሀይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶችን በሰፊው በማስተዋወቅ የጎላ ተሳትፎ አደረገ።

በጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት የሀኖቨር ደብረ ይድራስ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ካህናትና ምዕመናን በዓለ ጰራቅሊጦስ (Pfingstmontag) አስመልክቶ በሀኖቨር ከተማ በተካሄደው አለም አቀፋዊ የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራም (interkultureller ökumenischer Gottesdienst) ላይ በመሳተፍ ሀይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶችን በሰፊው አቅርበዋል::

በፕሮግራሙ ላይ በሀኖቨርና አካባቢው የሚገኙ 12 አብያተ ክርስቲያናት ከመሳተፋቸው በተጨማሪ የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራሙ ግእዝና አማርኛን ጨምሮ በ 8 የተለያዩ ቋንቋዎች ተካሂዷል::

ዕለቱ በደብሩ የሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን ዝማሬዎች ደምቆ የዋለ ሲሆን በተለይም በፕሮግራሙ መክፈቻ ላይ የትንሣኤ ወረብ (አማን በአማን - ተንሥአ እምነ ሙታን) ሲቀርብ አጠቃላይ የፕሮግራሙ ታዳሚዎች በታላቅ ስሜት አብረው ሲያጨበጨቡና ሲያሸበሽቡ ማየት ደስ የሚያሰኝ ነበር::

እያንዳንዱ ተሳታፊ ቤተ ክርስቲያን የተለያየ ርዕስ መርጦ በየቋንቋው ጸሎት ያደረሰ ሲሆን የደብረ ይድራስ ካህናትና ምዕመናን ሰላምን በተመለከተ የዮሐንስ ወንጌል 14፥27 መነሻ በማድረግ ኦርቶዶክሳዊ የሰላም ጸሎት አድርሰዋል::

የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራሙ ከተጠናቀቀ በኋላ የደብሩ ምዕመናን ያዘጋጁትን ምግብና መጠጥ በማቅረብ የሀገራችን ባህላዊ እሴት ደምቆ እንዲታይ አድርገዋል::

የፕሮግራሙ ዋና አዘጋጅ ፓስተር ዶ/ር ሚካኤል ቮለርስ (Pastor Dr. Michael Wohlers) የደብረ ይድራስን ተሳትፎ በተመለከተ የሚከተለውን ብለዋል:-
„Die Mitwirkung Eurer Gemeinde ist ein großartiger Beitrag zur Ökumene im Stadtbezirk Hannover-Döhren und Wülfel. Sie ist außerdem ein Zeugnis lebendigen Glaubens und der Verbundenheit aller Christinnen und Christen in Hannover. Ich freue mich schon auf den ökumenischen Gottesdienst im nächsten Jahr.“

ትርጉም:-
በአለም አቀፋዊው የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራም ላይ መሳተፍ መቻላችሁ በሀኖቨር ከተማ ለሚኖሩ አጠቃላይ የክርስቲያን ማህበረሰብ ትልቅ መታደል ነው:: ተሳትፏችሁ የእምነታችሁን ጥንካሬ ከማሳየቱ በተጨማሪ በከተማችን ነዋሪ የሆኑ የተለያዩ የክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች ያላቸውን የጠበቀ ትስስር ማሳያ ነው። በመጪው ዓመትም ይህንን አለም አቀፋዊ የጸሎትና ምስጋና ፕሮግራሙን አብረን እንደምናከብር ባለሙሉ ተስፋ ነኝ።

ዘገባና ፎቶዎች:- ዶ/ር ያሬድ ካሌብ (ከሀኖቨር የአጥቢያው ሚድያ)

የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሚድያ

 !ልዩ የኹለት ሳምንት የምክረ አበው፣ የሱባኤ፣ የትምህርትና ማኅበራዊ ድጋፍ ሥልጠና ተጀመረ። “እናት አለን” በሚል መሪ ቃል በኢ/ኦ/ተ/ቤ ጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት አዘጋጅነት ትናን...
18/06/2026

!
ልዩ የኹለት ሳምንት የምክረ አበው፣ የሱባኤ፣ የትምህርትና ማኅበራዊ ድጋፍ ሥልጠና ተጀመረ።
“እናት አለን” በሚል መሪ ቃል በኢ/ኦ/ተ/ቤ ጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት አዘጋጅነት ትናንት ሰኔ 10 ቀን የተጀመረው ይህ ሥልጠና እስከ ሰኔ 23 ቀን 2018 ዓ/ም ድረስ ይከናወናል። በሀገረ ጀርመን ኖርድሃይን ቬስትፋለን ግዛት ዱልመን በሚገኘው ማሪያ ሃሚኮልት በተባለ የቀድሞ የካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን የሴቶች ገዳም በተጀመረው በዚህ ሥልጠና፤ ከኢትዮጵያ የመጡት አባ ቴዎድሮስን ጨምሮ ልዩ ልዩ ሊቃውንት ትምህርትና ሥልጠና የሚሰጡበት ሲኾን ከጀርመን ልዩ ልዩ ከተሞች፣ ከጣልያንና ከአሜሪካ የተመረጡ 36 የቤተ ክርስቲያን ልጆች በሠልጣኝነት እንደሚሳተፉበት ታውቋል።

መልአከ መዊዕ ልሳነ ወርቅ ውቤ የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅና የፍራንክፈርት ምስካዬ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ሥልጠናውን በጸሎትና በቡራኬ በይፋ ሲከፍቱ ባደረጉት ንግግር “ሀገረ ስብከታችን እንደዚህ ዐይነት ሥልጠናዎችንና ሌሎች ሰፊ አገልግሎቶችን የሚሰጥበትን ገዳም ለመመሥረት ሲያደርግ የቆየው ሰፊ እንቅስቃሴ ፍሬ ሊታይ ጫፍ ደርሷል። ሊገዛው ያለው ቦታ ደግሞ ይህ ዛሬ የተሰበሰብንበት የቀድሞ የካቶሊካውያን የሴቶች ገዳም ነው። በመኾኑም እግዚአብሔር ፈቅዶላችኹ ቤተ ክርስቲያን ወደፊት ለአካባቢው ብሎም በመላው ዓለም ለሚገኙ ኦርቶዶክሳውያን ሰፊ አገልግሎት ልትሰጥበት ባለው በዚህ ቦታ የመጀመሪያው ዙር ሠልጣኞች በመኾናችኹ እንኳን ደስ አላችኹ” ብለዋል። በመክፈቻ ሥነ ሥርዐቱም ላይ በዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የቀጨኔ ደብረ ሰላም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ሰላም ዐምደ ወርቅ ደሴ ከሥልጠናው ዓላማ ጋር የተስማማ ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል።

የሥልጠናውን ዓላማና ዝግጅት አስመልክቶ ለዝግጅት ክፍላችን ማብራሪያ የሰጡት የሀገረ ስብከቱ ዋና ጸሐፊና የገዳም ግዥ ክፍል ኃላፊ ሊቀ ኅሩያን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ “ኢትዮጵያውያን በልዩ ልዩ ምክንያት ሀገራቸውን፣ ወገን ዘመዳቸውን ትተው፣ ባሕር አቋርጠው በዓለም ተበትነው መኖር ከጀመሩ በርካታ ዐሠርት ዓመታት ተቆጥረዋል። በአሁኑ ወቅት በሀገረ ጀርመንና በአካባቢው ባሉ ሀገራት ብቻ በበርካታ ሺዎች የሚቆጠሩ የቤተ ክርስቲያን ልጆች የስደት ኑሯቸውን እየገፉ ይገኛሉ። ከእነዚህ ወገኖቻችን የስደት ሕይወት ሳያሸንፋቸው ያሰቡትን አሳክተው፣ ከእነሱ አልፎ ወገን ዘመዶቻቸውን እየረዱ ያሉ የመኖራቸውን ያህል፤ ኑሮው የሰው ሀገር፣ ባሕልና ቋንቋ፣ አኗኗሩም የስደት እንደመኾኑ ልዩ ልዩ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ብሎም ሥነ ልቡናዊ ጫና ደርሶባቸው በችግር ውስጥ የሚገኙም ይኖራሉ። እነዚህ ወገኖች የሀገሩን ባህልና ቋንቋ በአጠቃላይ የአኗኗር ይትበሃል ካለመቀበል እና/ወይም ካለመረዳት፣ ከሀገርና ወገን ናፍቆት፣ ከትዳር ሕይወት መበጥበጥ፣ ስለሀገርና ስለወገን ከሚሰማ አሉታዊ ዜና፣ ወዘተ. የተነሣ ለጭንቀት (Stress)፣ ለድባቴ (Depression)፣ ለሱስ (Addiction) ወዘተ. ተጋላጭ ኾነው ይታያሉ። ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በያሉበት ካህናትን አሰማርታ፣ አብያተ ክርስቲያናትን አቋቁማ በተጠቀሱትና ሌሎች በርካታ ችግሮች ውስጥ ያሉ ልጆቿን ለመርዳት በመጣር ላይ የምትገኝ ቢኾንም በልዩ ልዩ ነባራዊ ምክንያቶችና ከችግሩ ግዝፈት የተነሣ አንድ የተጠናከረ ማእከል (ገዳም) ማቋቋም አስፈላጊ ኾኖ ቆይቷል። በመኾኑም ሀገረ ስብከታችን ይህንንና ሌሎች ልዩ ልዩ አገልግሎቶችን የሚሰጥ አንድ የጽሙናና የትምህርት ማእከል (ገዳም) ለማቋቋም እንቅስቃሴ ሲያደርግ ቆይቶ ወደ ውጤቱ መዳረሻ ለመድረስ የመጨረሻውን እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ይገኛል። በመኾኑም በዚሁ በሀገረ ጀርመን ሊያቋቁመው ባለው ገዳም ሊሰጣቸው ካቀዳቸው ዘርፈ ብዙ አገልግሎቶች አንዱና ዋናው የኾነውን በልዩ ልዩ ሥነ ልቡናዊና ማኅበራዊ ጫና ውስጥ ያሉ የቤተ ክርስቲያንን ልጆች የማበርታትና የማጽናት አገልግሎት ለማስጀመር በሚል ይህ ሥልጠና ተዘጋጅቷል” ብለዋል።

በዚህ በመጀመሪያው ዙር ሥልጠና የተመረጡት ምእመናን ቁጥር 36 እንደኾነ የገለጡት ሊቀ ኅሩያን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ፤ “ሥልጠናው ሦስት ዐበይት ዓላማዎች አሉት። እነሱም የተመረጡት የቤተ ክርስቲያን ልጆች ምክረ አበውንና ትምህርተ ሊቃውንትን እንዲያገኙ ማድረግ፤ በስደት ሕይወታቸው የሚያጋጥሟቸውን ፈተናዎች ተቋቁመው ሊያልፉባቸው የሚችሉ ልዩ ልዩ የእውቀትና ክህሎት ግንባታ ሥልጠናዎችን በተለያዩ ባለሙያዎች እንዲያገኙ ማድረግ፤ ሠልጣኞች ከሥልጠናው በኋላ በዘላቂነት ሊጠቀሙበት የሚችሉት ማኅበራዊ ሀብት (Social Capital) እና ማኅበራዊ የእርስ በርስ ግንኙነት (Social Relationship) እንዲፈጥሩ ማስቻል ናቸው” ብለዋል።

በመጨረሻም ሀገረ ስብከቱ ይህንን ስልጠና ያዘጋጀው ከዶንኪ ቲዩብ (ጥንቅቅ መልቲ ሚድያ እና ኤቨንት ኦርጋናይዘር) ጋር በመተባበር እንደኾነ የገለጡት ሊቀ ኅሩያን ዶ/ር መርሻ፤ “በዚህ ዘመን ዘርፈ ብዙ ከኾኑት የቤተ ክርስቲያናችን ማኅበረ ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ውስጥ የቻለውን ያህል በመቅረፍ የድርሻውን እየተወጣ ያለው ኮሜድያን እሸቱ መለሰ፤ ብፁዕ አቡነ ዲዮናስዮስ የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሀገረ ስብከታቸው በምድረ አውሮጳ የመጀመሪያ የኾነ ገዳም ለማቋቋም እንዳሰበ ከገለጠበት ጊዜ ጀምሮ ከብፁዕነታቸውና ረዳቶቻቸው ጋር በቅርብ ሲወያይ ቆይቷል። ወደጀርመንም በመምጣት ሊገዛ የታሰበውን ቦታ ጎብኝቷል። በዚህም የፕሮጄክቱን አስፈላጊነት አምኖበት ከሀገረ ስብከቱ ጋር ከፍተኛ እንቅስቃሴ እያደረገ ይገኛል። በመኾኑም ይህ ሥልጠና ይዘጋጅ ዘንድ ሐሳቡን ከማመንጨት ጀምሮ ልዩ ልዩ እንቅስቃሴዎችን በማድረግ ላይ ይገኛል።” ብለዋል።

{ዜና ሀገረ ስብከት ሐተታ ፥ ጀርመን ፥ ሙንስተር ከተማ ፥ ሰኔ ፲፩ ቀን ፳፻፲፰ ዓ/ም ፥ Münster June 18, 2026}
የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሚድያ
| | | | | |

በሮማንያ ቡካሬስት ከተማ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ በተገኙበት ታላቅ መንፈሳዊ ጉባኤ በድምቀት ተከናወነ። በጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት በምስራቅ አውሮፖዊቷ በሮማንያ የቅድስት ኪ...
10/06/2026

በሮማንያ ቡካሬስት ከተማ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ በተገኙበት ታላቅ መንፈሳዊ ጉባኤ በድምቀት ተከናወነ።

በጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት በምስራቅ አውሮፖዊቷ በሮማንያ የቅድስት ኪዳነ ምሕረት ጽዋ ማኅበር ወርሃዊ ዝክር እና ታላቅ መንፈሳዊ ጉባኤ የሀገረ ስብከቱ ዋና ሥራ አስኪያጅና የፍራንክፈርት ምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ቤ/ክ ዋና አስተዳዳሪ ክቡር መልአከ መዊዕ ቀሲስ ልሳነወርቅ ውቤ በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ተከብሮ ዋለ ።

በክርስትና እምነት ጥንታዊት እና ከ80 በመቶ በላይ የሚሆነው ዜጎቿ የክርስትና አማኝ የሆነው በምስራቅ አውሮፓ የምትገኘው ሮማኒያ በዋና ከተማዋ ቡካሬስት ታላቅ መንፈሳዊ ጉባኤ እና የቅድስት ኪዳነ ምሕረት ዝክር በጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ በመልአከ መዊዕ ልሳነ ወርቅ ውቤ እየተመራ በሮማንያ የቅድስት ኪዳነ ምሕረት ጽዋ ማኅበር በአባቶች ካህናት ወዲያቆናት መምህራነ ወንጌል ተወዳጅ ዘማሪያን እንዲሁም ከሩቅ እና ከቅርብ የተሰባበሰቡ ማኅበረ ምዕመናን በተገኙበት እሑድ ሚያዚያ 16 ቀን2018 ዓ.ም በልዩ ድምቀት ተከብሮ ውሏል።

ባሳለፍነው እሑድ በቡካሬስት በተካሄደው መርሐ ግብር ካህናቱ ከምዕመናን ወምዕመናት በጋራ በመሆን ጸሎተ ኪዳን፣ ጸሎተ ወንጌል አድርሰው ዕለቱን በማሰብ በዝማሬ፣ በትምህርት ወንጌል፣ በሥነ ጽሑፍ እንዲሁም የቅድስት ኪዳነምሕረት ዝክር የቤተክርስቲያኗን ዶግማ እና ቀኖና በጠበቀ መልኩ ማከናወን ተችሏል።

እንዲሁም በዕለቱ በክቡር አባታችን በመልአከ መዊዕ ቀሲስ ልሳነ ወርቅ ውቤ "እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ ትእዛዜ ይህች ናት" የዮሐንስ ወንጌል 15:12 ላይ ያለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል መነሻ በማድረግ፣ ስለ ፍቅር ሰፊና ጥልቅ ትምህርተ ወንጌል ከአበው ብሂልና ምሳሌዎች ጋር አያይዘው አስተምረዋል።
ከዚሁ ጋር ተያይዞ ዘማሪ ዲያቆን ሙሴ አበራ ፣ ዘማሪት ጤናዬ አሰፋ እና ዘማሪ ዲያቆን አይንአየሁ በጋራ በመሆን በዕለቱ የተገኙትን ካህናት እና ምዕመናንን በእጅጉ ያስደሰተ ደማቅ ኦርቶዶክሳዊ ዝማሬ በመንፈሳዊ የዜማ መሳሪያ በክራር በማጀብ በዝማሬ ያገለገሉ ሲሆን፤ በመጨረሻም የማኅበሩ አባት ቀሲስ ሰሎሞን ገላው ጥሪያችንን በማክበር በዕለቱ የተገኙትን የሀገረ ስብከቱን ዋና ሥራ አስኪያጅ መልአከ መዊዕ ቀሲስ ልሳነወርቅ ውቤን በማመስገን እና በዋና ስራ አስፈፃሚው የተዘጋጀውን ማስታወሻ የሚሆን ስጦታ በማበርከት በተለየም የዕለቱ የቅድስት ኪዳነ ምሕረትን ፅዋ የዘከሩትን ፣ ለበዓሉ መሳካት አስተዋፅኦ ያደረጉትን እና በዕለቱ የተገኙትን ማኅበረ ምዕመናንን በአጠቃላይ በማመስገን መልዕክት ያስተላለፉ ሲሆን በመጨረሻም በክቡር አባታችን መልአከ መዊዕ ቀሲስ ልሳነወርቅ ውቤ አማካኝነት በምርቃት እና ጸሎተ ቡራኬ በመስጠት በደማቅ መንፈሳዊ ስነ ሥርዓት ተከብሮ የዕለቱ መርሐ ግብር በተሳካ መልኩ በሰላም መጠናቀቅ ችሏል።

ዘገባ እና ፎቶ፦ ተከስተ በረከት እና ዘማሪት ጤናዬ አሰፋ የጽዋ ማኅበሩ ሚዲያ ክፍል

 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮናስዮስ ለ11 ደቀ መዛሙርት የዲቁና፤ ለኹለት ዲያቆናት ደግሞ የቅስና መዐርግ ሰጡ...
07/06/2026



በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዲዮናስዮስ ለ11 ደቀ መዛሙርት የዲቁና፤ ለኹለት ዲያቆናት ደግሞ የቅስና መዐርግ ሰጡ። በሀገረ ስብከቱ ከተለያዩ አጥቢያዎች የመጡት ደቀ መዛሙርት የተሾሙትግንቦት 30 ቀን 2018 ዓ.ም ቀን በበርሊን ደብረ ገነት ቅዱስ አማኑኤል ነው።

በዓለ ሢመቱን ከፈፀሙ በኋላ ብፁዕነታቸው ለደቀ መዛሙርቱ ምክርን ሰጥተዋል። "በውጭው ዓለም ተወልዳችኹ አድጋችኹና ለክህነት የሚያስፈልገውን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ተምራችሁ ለዚህ በመብቃታችኹ ቤተ ክርስቲያን ተደስታለች" ያሉት ብፁዕነታቸው፤ "ምንም እንኳን ለዚህ ክብር ትበቁ ዘንድ ፈቃዱ የእግዚአብሔር ቢኾንም፤ ወላጆቻችኹ ከመደበኛ ትምህርታችኹ ጎን የቤተ ክርስቲያንን ትምህር እንድትማሩ ስላበረቷችኹ ምስጋና ይገባቸዋልና የካህናቱ ወላጆች እንኳን ደስ አላችኹ። ይልቁንም በሀገራቸው በብዙ ድካም በተማሩት ትምህርት በስደት ልጆቻቸውን ተከትለው በማስተማር ለዚህ ያበቁ የሀገረ ስብከታችን ሊቃውንት ምስጋና ይገባቸዋል። እናንተንም እንኳን ደስ አላችኹ" ብለዋል።

ዓመታዊውን የቅዱስ አማኑኤል በዐል በበርሊን ደብረ ገነት ቅዱስ አማኑኤል ሲከበር በተደረገው በዚህ ሢመተ ካህናት ክቡር መልአከ መዊዕ ልሳነ ወርቅ ውቤ፤ የሀገረ ስብከታችን ሥራ አስኪያጅና የፍራንክፈርት ምስካየ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ በተጨማሪ በሀገረ ስብከቱ የተለያዩ አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃወንትና በርካታ ምእመናን ተገኝተዋል።

የሀገረ ስብከቱ ሚድያ ክፍል

ከጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ስለማያባራው የአርሲ ኦርቶዶክሳውያንን ግድያ አስመልክቶ  የተሰጠ የሐዘን መግለጫ፣ በኢ.ኦ.ተ.ቤ. የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት
04/06/2026

ከጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት ስለማያባራው የአርሲ ኦርቶዶክሳውያንን ግድያ አስመልክቶ የተሰጠ የሐዘን መግለጫ፣

በኢ.ኦ.ተ.ቤ. የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት

💠 የሰኔ ቅዱስ ሚካኤል ክብረ በዓል ጥሪ በዳርምሽታድት📍በጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት በዳርምሽታት ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ዓመታዊው የሰኔ ቅዱስ ሚካኤል በዓል 🗓  እ...
01/06/2026

💠 የሰኔ ቅዱስ ሚካኤል ክብረ በዓል ጥሪ በዳርምሽታድት
📍በጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት በዳርምሽታት ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ዓመታዊው የሰኔ ቅዱስ ሚካኤል በዓል

🗓 እሁድ ሰኔ ፲፬ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም.
Sonntag, June 21, 2026
በደመቀ ሁኔታ ይከበራል፡፡


🟢 ቅዳሜ ከ14:00 - 19:00 ሰዓት ዋዜማ ይቆማል
🟡 ከ19:00 - 22:00 ትምህርተ ወንጌል እና ዝማሪው ሰዓት ጀምሮ ሥርዓተ ማኅሌት ይቆማል
🟡 ከ22 ሰዓት ጀምሮ ሥርዓተ ማኅሌት ይቆማል
🟠 እሁድ ከጥዋቱ 06 ሰዐት ጀምሮ ሥርዓተ ቅዳሴ፣ ስብከተ ወንጌል፣ ዝማሬ፣ ሥርዓተ ዑደት ተከናውኖ የበዓሉ ፍጻሜ ይሆናል፡፡

📍በዓሉ የሚከበርበት ቦታ፡ Heildelberger Landstraße 155, 64297 Darmstadt

የበዓሉ በረከት ተካፋዮች ትሆኑ ዘንድ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ትጋብዛችኋለች።

የደብሩ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ጽ/ቤት

 !የሱባኤ ፣ ምክረ አበው እና ሥልጠና መርሐ ግብር ሊገዛ በታሰበው ገዳምከውድ ሀገራቸው እና ቤተሰቦቻቸው ርቀው በስደት በተለያዩ ችግሮች ውስጥ ላሉ 36 ምእመናን ብቻ፤ ሊገዛ በታሰበው ገዳም...
31/05/2026

!
የሱባኤ ፣ ምክረ አበው እና ሥልጠና መርሐ ግብር ሊገዛ በታሰበው ገዳም
ከውድ ሀገራቸው እና ቤተሰቦቻቸው ርቀው በስደት በተለያዩ ችግሮች ውስጥ ላሉ 36 ምእመናን ብቻ፤ ሊገዛ በታሰበው ገዳም የተዘጋጀ የሁለት ሳምንት ልዩ የሱባኤ ፣ ምክረ አበው እና ሥልጠና መርሐ ግብር።
አሁኑኑ ይመዝገቡ።
+49 152 5496 0289
[email protected]

የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት

ወርኃዊ ጉባኤ ካሉበት ሆነው በዙም ይሳተፉ፤ ላልሰሙትም ያሰሙ*የገዳም ፍለጋ ድጋፍ ሰጭ የስብከተ ወንጌል ጉባኤ (የእመቤታችን ጽዋ ማኅበር) ወርሐዊ መርሐ ግብር**ዛሬ ዐርብ ግንቦት ፳፩ ቀን ...
28/05/2026

ወርኃዊ ጉባኤ ካሉበት ሆነው በዙም ይሳተፉ፤ ላልሰሙትም ያሰሙ

*የገዳም ፍለጋ ድጋፍ ሰጭ የስብከተ ወንጌል ጉባኤ (የእመቤታችን ጽዋ ማኅበር) ወርሐዊ መርሐ ግብር*

*ዛሬ ዐርብ ግንቦት ፳፩ ቀን || May 29, 2026*
*Berlin 19:00 CET*
London 18:00
በኢትዮጵያ ከምሽቱ 3 ሰዓት
❖ ትምህርት
* መምህር ኃ/ሚካኤል ገላሳ /ከኢትዮጵያ

❖መዝሙር
* በዘማሪ ዲያቆን ዳንኤል አሰሌ ከፖላንድ

*ወደ መርሐ ግብሩ መግቢያ የZoom ሊንክ*
https://us06web.zoom.us/j/91971943219
Meeting-ID: 919 7194 3219
*ያጋሩ፣ ላልሰሙት ያሰሙ።*
በጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት የገዳም አፈላላጊ ክፍል

Adresse

E. O. T. C./Germany And Surroundings Archdiocese Abune Dionasiyos C/o Street Immanuel Aethiopisch-Orthodoxe Kirchengemeinde
Frankfurt

Webseite

Benachrichtigungen

Lassen Sie sich von uns eine E-Mail senden und seien Sie der erste der Neuigkeiten und Aktionen von EOTC Germany Archdiocese ፤ የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት erfährt. Ihre E-Mail-Adresse wird nicht für andere Zwecke verwendet und Sie können sich jederzeit abmelden.

Die Kultstätte Kontaktieren

Nachricht an EOTC Germany Archdiocese ፤ የጀርመንና አካባቢው ሀገረ ስብከት senden:

Teilen