21/05/2026
በኤነር ደብረ መንክራት ቅዱስ አማኑኤል ገዳም የዕርገት በዓል በድምቀት ተከበረ
➺➺➠➺➺➺➠➠➠➠➠➠➠➠➠
በጉራጌ ሀገረ ስብከት በሚገኘው በኤነር ደብረ መንክራት ቅዱስ አማኑኤል ገዳም፣ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የዕርገት በዓል ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ዜና ማርቆስ መንፈሳዊ ኮሌጅ መሥራችና የበላይ ኃላፊ በተገኙበት በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ-ሥርዓት ተከብሯል።
የቅዳሴው ፍጻሜን ተከትሎ የታቦተ ሕጉ ዑደት በብፁዕነታቸው አባታዊ ምሪት በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ በካህናትና በመነኮሳት፣ በሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራንና በምዕመናን ታጅቦ ተከናውኗል። በመቀጠልም የገዳሙ ሰንበት ተማሪዎች ዕለቱን የሚዘክሩ ያሬዳዊ ዝማሬዎችን አቅርበዋል።
ብፁዕ አቡነ መልከጼዴቅ በሰጡት ትምህር ወንጌል፤ የዕርገት በዓል ከዘጠኙ ዓበይት በዓላት አንዱ መሆኑን ገልጸው፤ ዕርገት የሚለው ትርጉሙም "ወደ ላይ መውጣት፣ ከፍ ከፍ ማለት" እንደሆነ አስረድተዋል። ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መጥቶ፣ ተሰቅሎ ዓለምን ካዳነና ከትንሣኤው በኋላ ለሐዋርያት በተለያየ ጊዜ እየተገለጠ ካስተማራቸው በኋላ፣ በ40ኛው ቀን እየባረካቸው ማረጉን አብራርተዋል።
ደቀ መዛሙርቱ በአካል ሲለያቸው መጀመሪያ ላይ ቢፈሩም፣ ጌታ ግን አስቀድሞ *"ልባችሁ አይፍራ፤ እኔ ከሄድኩ በኋላ ቦታ አዘጋጅላችኋለሁ"* በማለት የሰጣቸውን ተስፋ አስታውሰዋል። በዚህም ምክንያት ዕርገቱ በሰማይ በመላእክት፣ በምድርም በሰው ልጆች ዘንድ ታላቅ ደስታን ያመጣና ተጎሳቁሎ የነበረው የሰው ሥጋ በአብ ቀኝ በአምላካዊ ክብር የተቀመጠበት መሆኑን ገልጸዋል።
ብፁዕነታቸው በዋናነት ከበዓሉ የምንማራቸውን ዝርዝር ትምህርት ያስተማሩ ሲሆን። የገነት በር ተዘግቶበት ለነበረው የሰው ልጅ ክርስቶስ የሰውን ሥጋ ለብሶ በማረጉ ሰብአዊ ክብር የተገለጠበትና የከበረበት በዓል ነው፤ አምላካችን ሞትን ድል አድርጎ መነሣቱ የሰው ልጅ ሞትን ድል ማድረጉንና ድኅነቱ መጠናቀቁን የሚያሳይ ነው፤ ክርስቶስ በማረጉ፣ በጎ ለሠሩ ሰዎች የሰው ዓይን ያላየው መንግሥተ ሰማያት መዘጋጀቱን ያረጋገጥንበት ነው ብለዋል።
ብፁዕነታቸው ሲቀጥሉ መንግሥተ ሰማያት የቅዱሳንና የተመረጡት መኖሪያ እንጂ ምግባር ለሌላቸው ስላልሆነች፣ ምእመናን ምግባራቸውን ሊያቀኑና በበጎ ሥራ ሊተጉ እንደሚገባ አስገንዝበዋል። በተጨማሪም ጌታ ሲያርግ ሐዋርያትን "ኃይል እስክትለብሱ ድረስ ከኢየሩሳሌም አትውጡ" ማለቱን በማንሳት፣ እዚህ ላይ የተጠቀሰችው ኢየሩሳሌም ቤተክርስቲያን መሆንዋንና ምእመናንም መዳናቸው እስኪረጋገጥ ድረስ ከቤተክርስቲያን መራቅ እንደሌለባቸው መክረዋል።
ብፁዕነታቸው ትምህርታቸውን ሲያጠቃልሉም፦ "‘ላዕለ ይኩን ሕሊናክሙ’ (ልባችሁ/ሐሳባችሁ በሰማይ ይሁን) የተባለው መንግሥቱን እያሰብን እንድንኖር ነው፤ ዓለም እንደ እንስሳ አቀርቅሮ የምድርን ነገር ብቻ በሚያስብበት በዚህ ዘመን፣ እኛ ግን ሐሳባችንና ልባችን ሰማያዊ ሊሆን ይገባል"* በማለት አባታዊ ምክርና ቃለ ምዕዳን አስተላልፈዋል።
በተያያዘ ዜና፣ በገዳሙ በአዲስ መልክ ሊገነባ የታሰበውንና በ1,500 ካሬ ሜትር ቦታ ላይ የሚያርፈውን ዘመናዊ የሕንጻ ቤተክርስቲያን ግንባታ የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠዋል። ብፁዕነታቸው አያይዘውም፣ ይህ ታሪካዊ ገዳም ጥንታዊ ይዘቱንና ታሪኩን ጠብቆ እንዲሠራ በትኩረት እንደሚሠራ ገልጸዋል።
ግንቦት ፲፫/፳፻፲፰ ዓ.ም ወልቂጤ
ለፈጣን መረጃ ሳሌም የጉራጌ ሀገረ ስብከት ሚዲያ። ቤተሰብ ይሁኑ። የማኅበራዊ ሚዲያዎቻችን።
Facebook; https://www.fb.com/GurageDiocese
Telegram; https://t.me/GurageDiocese
Tiktok; tiktok.com/
Instagram; instagram.com/gurage_diocese
YouTube; https://youtube.com/