29/05/2026
ወንጌል — ለእውነተኛይቱ ቤተ ክርስቲያን አንገብጋቢ የሆነው ተግባር የምሥራቹን መልዕክት ለዓለም ማዳረስ ነው
ወንጌል ለእውነተኛይቱ ቤተ ክርስቲያን እጅግ አንገብጋቢ የምሥራች መልዕክት ነው። ምክንያቱም፦
1. ክርስቶስ አዝዟታል
«ኢየሱስም ቀረበና እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፦ “ሥልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ። እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤ እነሆም እኔ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ሁልጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ።”»
(ማቴዎስ 28፡18-20)
ይህ ትእዛዝ ለቤተ ክርስቲያን የተሰጠ ታላቅ ተልዕኮ ነው። ስለዚህ ወንጌልን መስበክ አማራጭ ሳይሆን የጌታ ትእዛዝ ነው።
2. ክርስቶስ ለመዳን ብቸኛው መንገድ ነው
መንግሥተ ሰማይን የሚያስገባ ወይም ሰው ከኃጢአቱ ይቅርታ አግኝቶ ከእግዚአብሔር ጋር እርቅ የሚያደርግበት ሌላ መንገድ የለም። በሌላ መንገድ ወደ አብ መድረስ አይቻልም። ድነት በኢየሱስ ክርስቶስ ብቻ ይገኛል።
«ኢየሱስም፦ “እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም።”» (ዮሐንስ 14፡6)
3. ክርስቶስ ስለ ዓለም ሞቷል
ክርስቶስ የሞተው በኃጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር የተለየው የሰው ልጅ በእርሱ በማመን እንዲድን ነው።
«በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ፥ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።» (ዮሐንስ 3፡16)
4. ለወንጌል ሥራ ቅድሚያ የማትሰጥ ቤተ ክርስቲያን ታላቁን ተልዕኮ እየተላለፈች ነው
ብዙ መሪ አገልጋዮች ስለ ወንጌል መጽሐፍ ቅዱሳዊ እውነት ቢያስተምሩም፣ በተግባር ግን የሚቀድሙት ምድራዊና ቁሳዊ ጉዳዮች መሆናቸውን በግልጽ ማየት ይቻላል።
ወንጌል ለእውነተኛይቱና ታዛዥ ቤተ ክርስቲያን ከጌታዋ የተሰጣት “ታላቅ ተልዕኮ” ነው። ስለዚህ በጌታችን ፊት ከመቆማችን በፊት ራሳችንን በጊዜ መመርመርና እየታዘዝን መሆናችንን ማረጋገጥ ይገባናል።
5. ወደ ውጭ ለወንጌል ሥርጭት የማትወጣ ቤተ ክርስቲያን ውስጣዊ ጤናዋን ልትመረምር ይገባታል
በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የተሞሉ ደቀ መዛሙርት ያሏት ቤተ ክርስቲያን ከወንጌል ሥራ የምታስቀድመው ሌላ ነገር አይኖራትም። የጌታቸውን መሥዋዕትነት የተረዱ ቅዱሳን ለነፍሳት መዳን ከፍተኛ ትኩረት ይሰጣሉ።
በምዕመናኗ ቁጥር ብቻ የረካች እና ወደ ጥፋት የሚሄዱትን ለማየት ያልተጨነቀች ቤተ ክርስቲያን የእግዚአብሔርን መንግሥት ሥራ ችላ ትላለች።
«ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በወረደ ጊዜ ኃይልን ትቀበላላችሁ፥ በኢየሩሳሌምም በይሁዳም ሁሉ በሰማርያም እስከ ምድር ዳርም ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ።» (የሐዋርያት ሥራ 1፡8)
«ወንጌልን ብሰብክ እንኳ የምመካበት የለኝም፤ ግድ ደርሶብኝ ነውና፤ ወንጌልንም ባልሰብክ ወዮልኝ።» (1ኛ ቆሮንቶስ 9፡16)
«እንዲህም አላቸው፦ “ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ፤ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ። ያመነና የተጠመቀ ይድናል፤ ያላመነ ግን ይፈረድበታል።”» (ማርቆስ 16፡15-16)
ታላቁ ተልዕኮ በእውነት ለተረዱት ለኢየሱስ ክርስቶስ ተከታዮች መተኪያ የሌለው ታላቅ መልዕክት ነው!
#ምንጭ፦ አገልጋይ ወርቅነህ አብርሃም ዋንዳሮ