29/11/2025
✟-እንኳን ለእናታችን ጽዮን ማርያም ዓመታዊ በዓል አደረሰን-✟
______የታቦተ ጽዮን ወደ ኢትዮጵያ መምጣት______
ኢትዮጵያ ከአርባ ሁለት ጊዜ በላይ ስሟ ተደጋግሞ የተጠቀሰው ሀገረ እግዚአብሔር ቅድስት ኢትዮጵያ የተወደደችለመሆኗ ነቢያቱ መስክረዋል፡፡ ከነቢያት አንዱ አሞፅም፤ «የእስራኤል ልጆች ሆይ ለእኔ እንደ ኢትዮጵያ ልጆች አይደላችሁምን ?» ብሎ እግዚአብሔር መናገሩን ጽፏል /9÷7/፡፡ ከሁሉም ከፍ ባለመልኩ ነቢዩ ቅዱስዳዊት፤ «ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች» ብሎ ሕዝበ ኢትዮጵያ እደ ሕሊናውን እና እደልቡናውን ዘወትር በአምልኮተ እግዚአብሔር፣ በጾምና በጸሎት፣ በምጽዋትና በትሩፋት፣ ዘርግቶ በሃይማኖት ጸንቶ፣ ምግባር ቀንቶ የሚኖር ሕዝብ በመሆኑ፤ ሕዝበ እግዚአብሔር ምድሪቱ ሀገረ እግዚአብሔር ተብለዋል፤/መዝ.68÷31/፡፡ለታቦተ ጽዮን ወደ ኢትዮጵያ መምጣት ዋናው ምክንያት በእስራኤል እና በኢትዮጵያ መካከል የነበረውየሠመረ ግንኙነት ነው፡፡ ይኽም በመሆኑ የንግሥት ሳባ እና የንጉሥ ሰሎሞን ግንኙነት ሰፊውን ታሪክ ይዞይገኛል፡፡የንግሥተ ሳባ ዕቃ ግምጃ ቤት የነበረው ታምሪን ወደ ኢየሩሳሌም ሔዶ ንጉሥ ሰሎሞን ያሠራውን ቤተ መቅደስ ዓይቶ፣ የሰሎሞንን ጥበባዊ ዝና ሰምቶ በፍጹም መደነቅ ወደ ሀገሩ ተመለሰ፡፡ ያየውንና የሰማውንለንግሥቲቱ አጫወታት፡፡ እሷም የሰማችውን ለማየት ወደ ኢየሩሳሌም ሔዳ የሰሎሞንን መንፈሳዊና ሥጋዊ ጥበብ ተመልክታ እግዚብሔርን አመስግና ተመለሰች፡፡ከንጉሥ ሰሎሞን ምኒልክን ፀንሳ ከኢየሩሳሌም ተነሥታ ባሕረ ኤርትራን ተሻግራ፣ ሐማሴን አውራጃ ስትደርስ አሥመራ ከተማ በሚገኘው ማይበላ ከተባለው ቦታ ወንድ ልጅ ወለደች፡፡ የሕፃኑንም ስም የንጉሥ ልጅ ስትል «እብነ መለክ» አለችው፡፡ ይኽ ስም በዘመን ሒደት ምኒልክ ተብሎ ተለወጠ፡፡ምኒልክ ተወልዶ በአእምሮ እያደገ ሲሔድ አባቴ ማን ነው ? አድራሻውስ ወዴት ነው ? እያለ ጥያቄ ቢያበዛባት በሃያ ሁለት ዓመቱ ወደ ኢየሩሳሌም ላከችው፡፡ ምኒልክም አባቱ ንጉሥ ሰሎሞንን አግኝቶ ሕገ ኦሪትንና የዕብራይስጥ ቋንቋ ሲያጠና ከቆየ በኋላ፤ ዐሥራ ሁለት ሺሕ እስራኤላውያንን አስከትሎ ከምድረ እስራኤል ወደኢትዮጵያ ጉዞውን አቀና፡፡ ከቀዳማዊ ምኒልክ ጋር ለጉዞ የተነሡ ዕብራውያን ከቤተሰቦቻቸው መለየታቸው ሳያሳዝናቸው ከታቦተ ጽዮን መለየታቸው እጅግ ከበዳቸው፡፡ ወዲያው በፈቃደ እግዚአብሔር ታቦተ ጽዮንን ከመንበሯ አንሥተው በሊቀመላእክት በቅዱስ ሚካኤል መሪነት ወደ ኢትዮጵያ ገቡ፡፡ቀዳማዊ ምኒልክ እና እስራኤላውያን ታቦተ ጽዮንን ይዘው አክሱም የደረሱት ኅዳር 21 ቀን ነበር፡፡ ንግሥተ ሳባም የታቦተ ጽዮን ወደ ኢትዮጵያ መምጣት በጣም ስላስደሰታት በክብር ተቀበለቻቸው፡፡ «ወአንበርዋ ውስተ ሕፅነ ደብረ ሀገረ ማክዳ» እንዲል በአክሱም ከተማ መካከል ደብረ ማክዳ /ዛሬ ቤተ ጊዮርጊስ ከሚባለው/ ላይ ደብተራ ኦሪት ሠርተው አስቀመጧት፡፡አሁን ያለው ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን በዘመናዊ ዐቅድ የታነፀው የአክሱም ጽዮን ገዳም ቅዳሴ ቤቱ ጥር 30 ቀን1957 ዓ.ም ግርማዊ ንጉሠ ነገሥት ቀዳማዊ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ፣ ግርማዊት ንግሥት ኤልሳቤጥ /የታላቋ ብሪታንያ ንግሥት/ እና ልዑል ፊልፕ ከክብር ባለሟሎቻቸው ጋር በተገኙበት ተከብሯል፡፡ኅዳር ጽዮን በአክሱም አክሱም ማርያም ጽዮን በኢትዮጵያ ውስጥ ለሚገኙት አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ መሠረታቸው ስትሆን ከተማዋም የኢትዮጵያ ሥልጣኔ መነሻ ናት፡፡ አክሱም በሕገ ልቡና የጸናች፣ ሕገ ኦሪትን የፈጸመች፣ በሕገወንጌል ያመነች ናት፡፡ ለዚህም ነው «ሕግ ይወጽእ እምጽዮን፤ ከጽዮን ሕግ ይወጣል» የሚለው ጥቅስ የሚነገረው፡፡ በዓለ ልደትን በላሊበላ፣ ጥምቀትን በጎንደር፣ ኅዳር ጽዮንን በአክሱም ጽዮን ሲያከብሩት ልዩ የሆነ ሥርዓት ስለሚቀርብባቸው ምእመናን መንፈሳዊ ደስታ ይሰማቸዋል፡፡ኅዳር 21 ቀን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ዓመታዊ በዓል ነው ብለን በተለየ መልኩየምናከብርበት ምክንያት፡-
1. በብሉይ ኪዳን ታቦተ ጽዮን የፈጸመችውን ልዩ ልዩ ገቢረ ተአምራትን ለማሰብ
2. ቀዳማዊ ምኒልክ ከዐሥራ ሁለቱ ነገደ እስራኤል የበኲር ልጆች ጋር ሊቀ ካህናቱን አዛርያስንና ታቦተጽዮንን ይዞ አክሱም የደረሰበት ዕለት በመሆኑ
3. በሦስት መቶ ሠላሳ ዓመተ ምሕረት በአብርሃ ወአጽብሃ ዘመነ መንግሥት ክርስትና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሃይማኖት ይሁን ተብሎ ዐዋጅ የታወጀበት
4. ዘካርያስ በተቅዋመ ወርቅ ምሳሌ ራእይ ያየበት
5. ነቢዩ ሕዝቅኤል በተቆለፈች ቤተ መቅደስ
6. ዕዝራ በቅድስት ሀገር ምሳሌ ራእይ ያየበት
7. አብርሃና አጽብሃ በወርቅና በዕንቁ ያሠሩት ባለ አሥራ ሁለት ክፍል ቤተመቅደስ ለመጀመሪያ ጊዜ ቅዳሴቤቱ የተከበረበት
8. በዘጠነኛው መቶ ክፍለ ዘመን ዮዲት ጉዲት አብያተ ክርስቲያናትን ስታቃጥል ታቦተ ጸዮንን ይዘው ወደዝዋይ ሐይቅ ከተሰደዱ በኋላ ዘመነ ሰላም ሲጀመር አክሱም በነበሩ ካህናት አስታዋሽነት ከዝዋይ ወደ አክሱም የገባችበት ዕለትበመሆኑ በርእሰ አድባራት ወገዳማት አክሱም ጽዮን ከፍ ባለ መንፈሳዊ በዓል እናከብራለን፡፡ ይኽ ሲባል ግን በዓሉ የሚከበረው በአክሱም ጽዮን ማርያም ብቻ ነው ማለት ሳይሆን፤ ታቦተ እግዝእትነ ማርያም ባለችበት ቦታ ሁሉ መከበሩን ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ከዚሁ ጋርም የመመኪያችን ዘውድ፣ የመዳናችን ምክንያት፣የንጽሕናችን መሠረት ስለሆነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ያልተነበየ ነቢይ፣ ያልሰበከ ሐዋርያ፣ያልተቀኘ ባለቅኔ ከቶ የለም፡፡ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማየ ሰማያት ወረደ፣ በቤዛነቱ ዓለምን አዳነ፣ ዳግመኛም በክበበ ትስብእት፣ በግርማ መለኮት ለፍርድ ይመለሳል ብንል ከቅድስት ድንግል ማርያም በነሣው ሥጋ በመሆኑ ያለ ወላዲተ አምላክ ምስጢረ ሥጋዌን፣ ነገረ ድኅነትን፣ ነገረ ምጽአትን ማሰብ ከቶ የማይቻል ነው፡፡ «ዕግትዋ ለጽዮን፤ ጽዮንን ክበቧት» እንዳለ ነቢዩ፤ ዐሥርቱ ቃላት የተጻፈባትን የእስራኤል አምባና መጠጊያየሆነችውን ታቦተ ጽዮንን ሌዋውያን ከበዋት ውዳሴ ያቀርቡላት እንደነበረው፤ ዛሬም እመቤታችን ቅድስትድንግል ማርያምን ካህናትና ምእመናን ከሩቅ እና ከቅርብ ተሰብስበው በማኅሌት፣ በዝማሬ፣ በቅዳሴና በውዳሴያከብሯታል፡፡በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም እና በቃል ኪዳኑ ታቦት መካከል ጥልቅ የሆነ ምስጢራዊ ትምህርትአለ፡፡ /ዘፀ. 25÷9-20/፡፡ ይህቺ የቃል ኪዳን ታቦት በደብተራ ኦሪት በቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ የኖረች፣የዮርዳኖስን ባሕር የከፈለች /ኢያ. 3÷14-17/፤ ቅጽረ ኢያሪኮን ያፈረሰች /ኢያ 6÷1-21/፤ ዳጎን የተባለ የፍልስጥኤማውያንን ጣዖት የቆራረጠች /1ሳሙ 5÷1-5/፤ በድፍረት ሊነካ የሞከረውን ኦዛን የቀሰፈች/1ሳሙ 6÷6/፤ በአቢዳራ ቤት ሦስት ወር ተቀምጣ ቤቱን በበረከት የመላች /2ሳሙ 6÷12/፣ ዳዊትየዘመረላት /2ሳሙ 6÷14/፤ ጠቢቡ ሰሎሞን በቤተ መቅደስ በክብር ያኖራት /1ነገ 8÷1/፤ የእግዚአብሔርየክብር መገለጫ ናት፡፡በታቦተ ጽዮን እና በዘመነ ሐዲስ በተገለጠችው በቅድስት ድንግል ማርያም መካከል ያለውን ረቂቅ እና ድንቅ ምስጢራዊ ንጽጽር አስመልክቶ ሦርያዊው ሊቅ ቅዱስ ኤፍሬም፤ «ታቦት በወርቅ ልቡጥ እምኩለሔ ዘግቡር እምዕፅ ዘኢይነቅዝ፤ ከማይነቅዝ እንጨት የተቀረጸ በውስጥ በአፍአ በወርቅ የተለበጠ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ንጽሐ ጠባይዕ ሳያድፍባትና የቅድስና ባሕርይ ሳይጎድፍባት በማየት፣ በመስማት፣ በመዳሰሰ፣ በማሽተት አንዳችም እድፍ ጉድፍ ሳያገኛት በንጽሕናና በቅድስና ጸንታ በኃጢአት ሳትለወጥ ኖራለች፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞንም፤ «አልብኪ ነውር ወኢምንትኒ ላዕሌኪ፤ ምክንያታዊ ነውር ኃጢአት የሌለብሽ የኃጢአት ሸታ ያልደረሰብሽ ንጽሕት በድንግልና ሥርጉት በቅድስና ክብርት በልዕልና አንቺ ነሽ» /መኃ 4÷7/ ሲል ተናግሯል፡፡ ታቦተ ጽዮን በከበረ ወርቅ እንደተሸለመች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም በንጽሐ ሥጋ፣ በንጽሐ ነፍስ እና በንጽሐ ልቡና የተሸለመች ያጌጠች መሆኗን ያጠይቃል፡፡ታቦተ ጽዮን የቃለ እግዚአብሔር ማደሪያ እንደሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያምም ለአካላዊ ቃል ለእግዚአብሔር ወልድ ማደሪያ ሆናለች፡፡ ይኽንንም ቅዱስ ኤፍሬም ሲያስረዳ፤ «ኮንኪ ታቦቶ ለፈጣሬ ሰማያት ወምድር ፆርኪዮ በከርስኪ ተሰዓተ አውርኃ አንቲ ማእምንት ለዘኢያገምርዎ ሰማያት ወምድር፤ ድንግልማርያም ሆይ ሰማይና ምድርን ለፈጠረ አምላክ ለእርሱ ማደሪያ ሆንሽ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅፀንሸቻልሽው ተሸከምሽው ሰማይና ምድር የማይወስኑትን ለመወሰን የታመንሽ አንቺ ነሽ» ብሎ ተቀኝቶላታል፡፡ስለሆነም ከብሉይ ኪዳን እስከ ሐዲስ ኪዳን እግዚአብሔር ራሱን የገለጠበትን የቸርነት በዓል እግዚአብሔር በፈቀደልን ቦታ ሆነን ስናከብር ከእኛ የሚጠበቀውን በጎ ነገር እያሰብን በተግባርም እየገለጥን ከበዓሉ ረድኤትና በረከት ተሳታፊ እንሆን ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት የእናቱ የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡የቅዱሳን ሁሉ ጸሎት እና ምልጃ አክሊልና ጉልላት በሆነው በእናታችን በወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት ሁላችንንም ይማረን፡፡
•✙•ወስብሐት ለእግዚአብሔር
•✙•ወለ ወላዲቱ ድንግል
•✙•ወለ መስቀሉ ክቡር