21/05/2026
+++በሚንቦገቦግ የደመና ተን ዐረገ+++
ጌታችን ከማረጉ አስቀድሞ ለደቀ መዛሙርቱ በተገለጠላቸው ጊዜ መንፈስ ያዩ መስሏቸው ፈርተው ነበር። ጌታችንም "ስለ ምን ትደነግጣላችሁ? ስለ ምንስ አሳብ በልባችሁ ይነሣል? እኔ ራሴ እንደ ሆንሁ እጆቼንና እግሮቼን እዩ ፤ በእኔ እንደምታዩት፥ መንፈስ ፤ ሥጋና አጥንት የለውምና እኔን ዳስሳችሁ እዩ" በማለት ምትሐት አለመሆኑን ፤ ከዚህ ቀደም የሚያስተምራቸው መምህራቸው መሆኑን አይተው ዳሰው እንዲያምኑ ፤ እርሱ ከሞት ከተነሣም በኋላ ሥጋና አጥንት እንዳለው ፍጹም ሰውነቱ እንዳልራቀበት ይነግራቸው ነበር። ነገር ግን ይህን ብሏቸው እንኳን ልባቸው አለማረፉን ተመልክቶ ፤ "በዚህ አንዳች የሚበላ አላችሁን?" አላቸው። (ሉቃ. 24: 41)
ደቀ መዛሙርቱም "ከተጠበሰ ዓሣ አንድ ቁራጭ፥ ከማር ወለላም ሰጡት ፤ ተቀብሎም በፊታቸው በላ" ፤ በእውነት ይገርማል!!! ኦርቶዶክሳውያን ሊቃውንት የደቀ መዛሙርቱን ዓሣ መሥጠት እንዲሁ ያለ ምሥጢር በቀላሉ አላለፉትም። ከቀደምት ሊቃውንት አንዱ ፤ ዓሣ በውኃ ውስጥ እንዲኖር ፤ ክርስቶስም ስለሰው ልጆች ፍቅር ወደ ሰው ልጆች ዓለም ወረደ በዚያም ተመላለሰ። ዓሣ በሰዎች በመንጠቆ ተይዞ ከውኃ ወጥቶ እንደሚሞትና እንደሚጠበስ ፤ ጌታችንም ስለ ሰው ፍቅር ፤ በሰዎች ተይዞ እሳት የተባለ መከራን ተቀብሎ ነፍሱን ከሥጋው ለየ ፤ በማለት ያስተምራል።
ዓሣ በቀደምት ክርስቲያኖች ዘንድ የተለመደ ምልክት ነበር። ዓሣ በላቲን Icthus ይባላል። የዚህ የላቲን ቃል እያንዳንዱ ፊደል ራሱን የቻለ ትርጉም አለው። Icthus የሚለው ቃል በግሪክ ቃላት I=Iota; C=Chi; T=Theta; U=Upsilon; S=Sigma ወይም Iesous CHristos THeou Uiou Soter ተብሎ ይተነተናል። ትርጉሙም "መድኃኒት የሆነ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ" ማለት ነው። [1]
ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ ደግሞ "በቀደመው ሕግ በብሉይ ኪዳን እስራኤል ፋሲካን መራራ ቅጠል በመብላት እንዲፈጽሙት መታዘዛቸው ፤ ከባርነት ቀንበር ገና አለመውጣታቸውን እንዲዘከሩ ነው። እውነተኛው ትንሣኤ ግን እውነተኛውን ፋሲካ ከሠጠን በኋላ መራራውን ፤ ጣፋጭ በሆነው ማር ለወጠልን" ይላል። [2]
መድኃኔ ዓለም ምትሐት እንዳልሆነ እርሱነቱን ያምኑ ዘንድ እዩኝ ፣ ዳስሱኝ ከማለት በላይ በልቶ አሳያቸው። ከሞት ከተነሣ በኋላ መብላት መጠጣቱ የሚጠቅመው ሆኖም አይደለም ፤ ምትሐት አለመሆኑን ሊያሳያቸው እንጂ። (after His resurrection eat part of a broiled fish and of a honey-comb, not to allay hunger and to gratify His palate, but to show the reality of His own body. For whenever He raised anyone from the dead He ordered that food should be given him to eat, lest the resurrection should be thought a delusion.) [3]
አስተውለን ከሆነ ጌታችን የሞቱ ሰዎችን ከሞት ካስነሣቸው በኋላ ምግብ እንዲበሉ በማድረግ ሰውነታቸውን ሌሎች እንዳይጠራጠሩ ያደርግ ነበር፡፡ ለምሳሌ፡ አልዓዛርን ከሞት ካስነሣው በኋላ ከጌታ ጋር እራት ለመብላት አብሮ እንደተቀመጠ ተጽፏል፡፡ ‹‹ከዚያም እራት አደረጉለት፤ ማርታም ታገለግል ነበር፤ አልዓዛር ግን ከእርሱ ጋር ከተቀመጡት አንዱ ነበረ።›› (ዮሐ. 12፡2) ፤ በሌላም ክፍል የምኩራብ አለቃውን ልጅ ከሞት ካስነሣት በኋላ ‹‹የምትበላውን ስጡአት›› (ማር. 5፡43) ሲል እናገኘዋለን፡፡ [4]
የጌታችን መብላት ሊቃውንት "ከኃይሉ የተነሣ በላ እንላለን እንጂ ምግቡ ሊጠቅመው ሊረባው አይደለም"(He ate indeed by His power, not from necessity) ይላሉ። በምሳሌ ሲገልጹት ፤ ውኃ የጠማው ደረቅ መሬትም ውኃን ሲያገኝ መጥጦ ውኃውን ይወስደዋል ፤ ውኃ የማይሻ ቦታ ላይ ያቆረ የተቀመጠን ውኃም ፀሐይ አትንኖ ያጠፋዋል። በሁለቱም መንገድ ውኃው ይጠፋል። የደረቀው መሬት ውኃ ስለሚያሻው ውኃውን የመጠጠው ሲሆን ፤ ፀሐዩ ደግሞ ከኃይሉ የተነሣ ውኃውን አትንኖታል። የጌታችንም መብላት ልክ እንደ ፀሐዩ ከኃይሉ የተነሣ እንደሆነ አበው ያስተምራሉ!!!
+++
"ወልደ እግዚአብሔርሰ ዐርገ እንበለ ሰዋስው በሳሕወ ደመና ዘያነበለብል" "የእግዚአብሔር ልጅ ግን ያለ መሰላል በሚንቦገቦግ የደመና ተን ዐረገ።" [5]
አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ
(መጽሐፈ ምሥጢር ፤ ምንባብ ዘዕርገት)
ስብሐት ለእግዚአብሔር
©ዲያቆን ደረጀ ድንቁ
+ ሀ/ደ/ም/ቅ/ገ/ገ መራሔድኅነት ሰ/ት/ቤት