15/03/2026
የሺንሺቾ ምስራቅ መሠረተ ክርስቶስ ቤተ-ክርስቲያን የአምልኮ አዳራሽ ተመረቀ ።
የሺንሽቾ ምሠራቅ መሠረተ ክርስቶስ ቤተ-ክርስቲያን በ 35 ዓመታት የፅናት ጉዞ ውስጥ ተሻግራ ዘመናዊ የአምልኮ አዳራሽ በድምቀት አስመረቀች።
በ 1980 ዓ.ም በአንድ ግለሰብ መኖሪያ ቤት በአራት ልጆች ህብረት የተጠነሰሰችው የሺንሺቾ ምስራቅ መሠረተ ክርስቶስ ቤተ-ክርስቲያን የሦስት አስርተ ዓመታት የፅናትና የዕድገት ጉዞዋን የሚያበስር ታላቅ የዘመናዊ አምልኮ አዳራሽ የምረቃ መርሃ-ግብር በዛሬው ዕለት በደመቀ ሁኔታ አከናውናለች።
ቤተ-ክርስቲያኒቱ ላለፉት 32 ዓመታት ስትጠቀምበት የነበረውን አሮጌ አዳራሽ በዘመናዊ ህንፃ ለመተካት በሚያዝያ 17 ቀን 2015 ዓ.ም ግንባታዋን መጀመሯ የሚታወስ ሲሆን በእግዚአብሔር ረዳትነትና በምዕመናን ያላሰለሰ ጥረት ተገንብቶ የተጠናቀቀው ይህ ዘመናዊ የአምልኮ አዳራሽ ዛሬ መጋቢት 6 ቀን 2018 ዓ.ም በታላቅ የምስጋና ስነ-ስርዓት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።
ግንባታው ሁለት ዓመት ከ አስር ወር የፈጀ ሲሆን በዋንኛነት በምዕመናን የገንዘብ፣ የጉልበትና የቴክኒክ ድጋፍና እገዛ የተገነባ ነው። ሕንፃው ከ 27 ሚልየን ብር በላይ በ ገንዘብ፣ በአይነት እና በጉልበት እንደወጣበት አቶ ሙሉጌታ ወዖሜ የሕንፃው አሰሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ ገልፀዋል።
በምረቃው ስነ-ስርዓቱ ላይ የሺንሺቾ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ክቡር አቶ መለሰ ገብሬ ፣ የቃጫ ቢራ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ክቡር አቶ ማቴዎስ ኤርቃሎ ፣ የሺንሺቾ ከተማ አስተዳደር የመንግሥት ዋና ተጠሪ ኢ/ር ቢኒያም ጴጥሮስን ጨምሮ የከተማ አስተዳደሩ የፊት አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት ፣ የከተማ አስተዳደሩ አመራሮች ፣ የቤተክርስቲያኒቱ መስራች አባቶችና እናቶች፣ የተለያዩ አቢያተ ክርስቲያናት ተወካዮችና በርካታ ምዕመናን በተገኙበት የምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ተከናውኗል።
ቤተ ክርስቲያኒቱ ካለፈችባቸው ዋና ዋና ታሪካዊ ክንውኖች መካከል በ1980 ዓ.ም በአራት ልጆች ህብረት የተጀመረች ሲሆን ግንቦት 19 ቀን 1981 ዓ.ም በሰባት አማኞች ወደ ስርጭት ጣቢያነት በማደግ በ1986 ዓ.ም ሙሉ አጥቢያ ለመሆን በቅታለች።
ባለፉት 35 ዓመታት የእምነቱ አባቶች በብዙ መከራና ተጋድሎ ውስጥ በማለፍ የክርስቶስን ወንጌል ለትውልድ እያስተላልፉ የቆዩ ሲሆን ይህም ጥረት ፍሬ አፍርቶ ዛሬ ላይ ዱራሜ፣ ሀደሮ፣ ሙዱላ እና የሺንሽቾ ምዕራብን ጨምሮ ከ18 በላይ አጥቢያዎችንና የስርጭት ጣቢያዎችን ማፍራት መቻሏ ተገልጿል።
ይህ የምረቃ መርሃ-ግብር ቤተ ክርስቲያኒቱ ለደረሰችበት ከፍተኛ የዕድገት ደረጃ ምስክርነት የሰጠ ሲሆን በቀጣይም ለማህበረሰቡ የምታበረክተውን ሁለንተናዊ አገልግሎት አጠናክራ እንደምትቀጥል አመላክቷል።