25/05/2026
በመከራ ላሉት ጸጋና ሰላም ይብዛ!
ክፍል 2
1ኛዼጥሮስ 1:2
እግዚአብሔር አብ አስቀድሞ ካወቃቸው፣ ኢየሱስ ክርስቶስን ለመታዘዝ በደሙ ለተረጩትና በመንፈስ አማካይነት ለተቀደሱት፤
ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ።
✝️ሐዋሪያው ዼጥሮስ ይህን መልዕክት የጻፈው በተለያየ ፈተናና ስደት ለሚኖሩ አይሁድና አህዛብ አማኞች ሲሆን በሚያልፉበት ፈተና ሊያበረታታቸውና መከተል ስላለባቸው መርህ ሊያሳስባቸው ይጥራል። የተለያየ ምድራዊ ፈተናዎችን እየተጋፈጡ ቢሆንም አይናቸውን በሰማያዊና ዘላለማዊው ተስፋ ላይ እንዲያማትሩ ይጎተጉታል። በተለየ መንገድ ይህን ሰማያዊ ተስፋ የሚጎናፀፉት በጌታችን ዳግም መምጣት ስለሆነ ለምጽዓቱ ጉጉት እና ናፍቆት እንዲያድርባቸው አይናቻውን ከምድር ያላቅቃል።
👉ምንም እንኳ እነዚህ አማኞች በሰው አይን ሲታዪ ስደተኞችና ሀገር አልባ ቢመስሉም ዼጥሮስ ግን በአስደናቂ ማንነት ገላጭ በሆነ ሃሳብ ይጠራቸዋል። ይኸህም “የእግዚአብሔር ምርጦች” ይላቸዋል። ይህ አጠራር ለአይሁድ አማኞች የተለየ ስሜት ይፈጥርባቸዋል። ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን ዘመን እስራኤል በዓለም ላይ ካሉ ህዝቦች ሁሉ የተመረጠች ነበረች። እግዚአብሔር የድነት ሃሳቡን ለመግለጥ የተጠቀመበት ህዝብ ነበር። ይህም የኪዳኑ ህዝብ አድርጓታል። ዘጸ 19:5-6 ዘዳ 7:6 ዘዳ 14:2
✍️ልክ እንዲሁ በአዲስ ኪዳን በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን የነበሩትን አይሁድና አህዛብ ክርስቲያኖች “የተመረጡ ህዝቦች” እንደሆኑና በክርስቶስ ደም አማካይነት በጋራ ተሳታፊ እንደሆኑ በመንገር የምስራችን በማወጅ ይጀምራል።
ይህ ህዝብ በስደትና በመከራ ውስጥ እያለፈ ቢሆን በእግዚአብሔር የተመረጠ ምርጥ ህዝብ እንዲሆን ያደረገው ምንድነው ስንል:- በስላሴ የተሰራ ስራ እንደሆነ ይገልጻል። ይኸውም:-
1. በእግዚአብሔር አብ አስቀድሞ የታወቀ
ይህ አስቀድሞ መታወቅ የሚለው በግሪክ “ፕሮግኖሲስ” ሲባል ትርጓሜውም “አስቀድሞ መታወቅ” ብቻ ሳይሆን “ጥልቅ ግንኙነትንና መለኮታዊ ንድፍን” ያመለክታል። ይህ ግንኙነት የተመሰረተው በክርስቶስ በማመንና በመስቀል ላይ በፈሰሰው ደም ነው።
2. ኢየሱስ ክርስቶስን ለመታዘዝ በደሙ የተረጨ
የአዲስ ኪዳን ማህበረሰብ አይሁድ ይሁን አህዛብ በክርሰቶስ በመስቀል ላይ በተሰራ ስራ በደሙ የተረጨ ነው። በደሙ ወደ አብ መቅረብን ብቻ ሳይሆን ክርስቶስን ለመታዘዝም ጭመር ነው። ይህ የደም መርጨት የተከናወነው በእንስሳት ደም (ዘጸ 24:3-7) ሳይሆን በሚልቀው በኢየሱስ የአዲስ ኪዳን ደም ነው። (ሉቃ 22:20)
3. በመንፈስ አማካኝነት መቀደስ
እነዚህ የአዲስ ኪዳን አማኞች በደሙ ስለተረጩ በመንፈስ ቅዱስ ተቀድሰዋል ይላል። ስለዚህ ያለምንም ኩነኔና ክስ በአብ ፊት የመቆም ድፍረት አላቸው። ከዚህ የተነሳ እንዚህን አማኞች “የእግዚአብሔር ምርጦች” ይላቸዋል።
⚓️ እንግዲህ እነዚህን አማኞች ነው በአንድነት “ጸጋና ሰላም ይብዛላችሁ” የሚለው። ጸጋና ሰላም ማለቱ በጉባኤዎቹ ውስጥ አህዛብና አይሁድ መኖራቸውን ያመለክታል። ምክንያቱም አይሁድን የሚወክለው ሰላምታ “ሻሎም” የሚለው ሲሆን አህዛብን የሚወክለው ደግሞ “ጸጋ” የሚለው ነው።
የህይወት ተዛምዶ
ይህ ክፍል ለዛሬ አንባቢዎች ምን ያስተምረናል?
1. በየትኛውም የህይወት ፈተና ውስጥ ብንሆንም በእግዚአብሔር መመረጣችንን ዘወትር እናስብ 1ኛቆሮ 1:26
2. በአብ አስቀድሞ መታወቃችን፣በጌታ ደም መረጨታችን እንዲሁም በመምፈስ ቅዱስ መቀደሳችን ከማጉረምረም አውጥቶ በየዕለቱ ለክርስቶስ ለመታዘዝ ይምራን።
3. ፈተናው እንደማያጠፋን በስላሴ ምክር ውስጥ እንደተያዝን እና በጸና ህይወት እንደተመሰረትን በማወቅ እንበርታ
ክፍል 3 ይቀጥላል…!
ጸጋ ከሁላችሁ ጋር ይሁን!
መጋቢ ወንድወሰን ለማ