29/05/2026
🕊️ በደብረ ምጥማቅ የአምላክ እናት የድንግል ማርያም መገለጥ ከግንቦት 21–25
✍ በመጋቤ ሐዲስ ዶ/ር ሮዳስ ታደሰ
📖✨ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት በመዝሙር ፵፬፥፲፪ ላይ፦
🌿 “ወለገጽኪ ይትመሐለሉ ኲሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር” 🌿
👑 “የምድር ባለጠጎች አሕዛብ ኹሉ በፊትሽ ይማለላሉ” 👑
🌹 በማለት ትንቢትን እንደተናገረላት፣ ብዙዎች ቅዱሳን ቅድስት ድንግል ማርያምን ተገልጻላቸው የአምላካቸውን እናት ለማየት ተመኝተዋል።
✨ ብዙዎቹም ልመናቸው ተሰምቶላቸው፣ የአምላክ እናት ተገልጻላቸው፣ እጅግ አስደናቂ ውበቷን አይተዋል።
⛪ ከነዚኽ ውስጥ በደብረ ምጥማቅ የነበሩ ምእመናን፣ ሌሎችም ብዙዎች ንጹሓን ክርስቲያኖች ይገኙበታል።
🌍 ልጇ አስቀድሞ በዘመነ ሥጋዌዉ በደብረ ምጥማቅ እንደምትገለጽ በገባላት ቃል ኪዳን መሠረት፣ ከኢትዮጵያ፣ ከግብጽ፣ ከአርመንያ፣ ከሶርያ፣ ከሮም፣ ከጽርዕ፣ ከፋርስ ሀገራት ተሰብስበው፣ በደብረ ምጥማቅ ድንኳን ተክለው፣ አጐበር ጥለው፣ ከግንቦት 21 ቀን ጀምረው እስከ 25 ቀን ድረስ በፍጹም ደስታ የድንግልን በዓሏን ያከብሩ ነበር።
🕊️ “ወድንግልሂ ታስተርእዮሙ በእሉ ኀምስ መዋዕል ዘእንበለ ጽርዐት ምስለ መላእክት ወጻድቃን ወሰማዕት ምስሌሃ” 🕊️
🌟 እመቤታችን ከግንቦት 21–25 ያለማቋረጥ፣ ከመላእክት፣ ከሊቃነ መላእክት፣ ከነቢያት፣ ከሐዋርያት፣ ከጻድቃን፣ ከሰማዕታት፣ ከደናግል፣ ከመነኮሳት ጋራ ኹና ትገለጽላቸው ነበር።
💧 አማኒውም ኢአማኒውም ያያት ነበር። ክርስቲያኖች ይህንን ድንቅ ተአምር እያዩ እምነታቸው ሲጸናላቸው፣ ያላመኑት ደግሞ እያመኑ በመጠመቅ ሀብተ ውልድና ስመ ክርስትናን ይቀበሉ ነበር።
🌞 በጒልላቱ ላይ ስትገለጽ፣ በውስጥ፣ በአፍአ፣ በነፍስ፣ በሥጋ ንጽሕት የኾነችው የቅድስት ድንግል ማርያም የፊቷ ውበትና ብርሃን እጅግ ድንቅ ነበር።
🙏 ካህናቱም ሕዝቡም ኹሉ ልክ እንደ ኤልሳቤጥ፦ “የጌታችን እናት ለእኛ ትገለጪ ዘንድ እኛ ምንድን ነን?” እያሉ ይጮኹ ነበር። ርሷም ያለማቋረጥ ትባርካቸው ነበር።
🌺 የእመቤታችን ፍቅር በእጅጉ የበዛለት አባ ጽጌ ድንግልም በማሕሌተ ጽጌ መጽሐፉ ላይ፦
📜 “አመ ትበርቂ በደብረ ምጥማቅ ኀምሰ ዕለታተ
ትእምርተ ገጽኪ ይርአይ እስከ ይትነሣእ ዘሞተ
ሚ መጠነ ማርያም ታሥተፌሥሒ ትፍሥሕተ
ኅድጊሰ ጽጌ ፍቅርኪ በጊዜ ንቃሑ መዓልተ
ብፁዕ ዘርእየኪ በሕልሙ ሌሊተ” 📜
🌹 “የፊትሽን መልክ ያይ ዘንድ የሞተ ሰው እስኪነሣ ድረስ፣ በደብረ ምጥማቅ ለዐምስት ቀናት ያኽል በተገለጽሽ ጊዜ፣ ማርያም ምን ያኽል ደስ ታሰኚ ኖሯል! በቀን የታየው የፍቅርሽ አበባ ይቅርና፣ ሌሊት በሕልሙ ያየሽ ምስጉን ነው” 🌹
🔥 ዳግመኛም ይኸው ኢትዮጵያዊ ሊቅ በተመስጦ፦
📜 “ሥዕልኪ ጽግይተ ላሕይ ዘከመዝ ትኤድም በዓለም
እፎ ይሤኒ በሰማይ ላሕየ ገጽኪ ማርያም
ሐሤተ ትእምርትኪ እጽገብ አስተርእዪኒ በሕልም
እስመ አውዐየኒ ነደ ፍቅርኪ ፍሕም
አጥፍኦቶ ዘኢይክል ዝናም” 📜
🌧️🔥 “ማርያም ሥዕልሽ በዓለም እንዲኽ የምታበራ ከኾነ፣ በሰማይ የፊትሽ መልክ ምን ያምር! አንቺን ከማየት የሚገኘውን ደስታ እጠግብ ዘንድ በሕልም ተገለጪልኝ፤ ዝናብ ሊያጠፋው የማይቻለው የፍቅርሽ እሳት አንድዶኛልና” 🔥🌧️
👑 ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም በእንዚራ ስብሐት መጽሐፉ ላይ በአድናቆት፦
📜 “ኦ ንግሥት ይገንዩ ለኪ ነገሥት ወለኪ ንግሥታት ይትቀነያ
ወኪያኪ የአኲታ ወለስምኪ ይገንያ
ወለኪ ይሰግዳ ወለክብርኪ የሐልያ
ጢሮስ ወሲዶና ሰብአ ግብጽ ወኢትዮጵያ
ፊንቂ ወሮምያ ማሮን ወአርማንያ
በሥነ ጸዳልኪ ይትፌሥሓ ወበላሕይኪ ይትሐሠያ” 📜
🌍👑 “ንግሥት ሆይ፣ ነገሥታት ለአንቺ ያገለግላሉ፤ ንግሥታትም አንቺን ያመሰግናሉ፤ አንቺንም ያሞግሳሉ፤ ለስምሽም ያጐነብሳሉ፤ ለአንቺ የጸጋ ስግደትን ይሰግዳሉ፤ ለክብርሽም ምስጋናን ያቀርባሉ። ጢሮስና ሲዶና፣ የግብጽና የኢትዮጵያ ሰዎች፣ ፊንቄና ሮምያ፣ ማሮንና አርማንያ በወጋገንሽ ውበት ደስ ይሰኛሉ፤ በደም ግባትሽም እሰይ ይላሉ” 🌍👑
🎶 ቅዱስ ያሬድ አባታችንም በማይ ኪራሕ ሳለ፣ እመቤታችን ተገልጻለት ፊቷን ለማየት ታድሏልና፣ ይኽነን በዐይኑ ያየውን ውበቷን በድጓው ላይ እንዲኽ ሲል ጽፎታል፦
☀️ “አይ ይእቲ ዛቲ እንተ ትወርድ እምሰማይ፤ ብርህት ከመ ፀሓይ፤ አዳም ቆማ ወክሣዳ ከመ አርማስቆስ፤ መዐዛ አፉሃ ከመ ኮል” ☀️
🌞 “ከሰማይ የምትወርደው፣ እንደ ፀሐይም የምታበራው ርሷ ማን ናት! አንገቷ እንደ ግንብ ቀጥ ያለ ነው፤ የአፏም መዐዛ እንደ እንኮይ ነው” 🌞
🎼 ይኽ የቤተ ክርስቲያን ጌጥ ቅዱስ ያሬድ፣ በዚኽ ሳያበቃ፣ በመላእክት እየተመሰገነች ስለተገለጸችለት ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ያየውን የውበቷን ነገር ሲናገር፦
🕊️ “እምኀበ መላእክት ትሴባሕ አዳም ሥና፤ መዐርዒር ቃላ ወኲሉ ነገራ በሰላም … እምወርኅ ወእምፀሓይ ይሤኒ ላሕያ … ከመ ፍሕሶ ቀይሕ ከናፍሪሃ ወከመ ኮል መዐዛ አፉሃ ወከመ ሮማን ቂሐተ መላትሒሃ …” 🕊️
🌙☀️ “በመላእክት ትመሰገናለች፤ ደም ግባቷ ያማረ ነው፤ ቃሏ እንደ ማር የጣፈጠ፣ ነገሯ ኹሉ በሰላም የተመላ ነው፤ ውበቷ ደም ግባቷ ከጨረቃና ከፀሓይ ይልቅ ያምራል፤ ከንፈሮቿ ፍሕሶ እንደሚባል አበባ ቀይ ናቸው፤ የጒንጯ ቅላትም እንደ ሮማን ቅርፍት ነው” 🌙☀️
✨ እያለ ሊቁ ማሕሌታይ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ይመሰክርላታል።
🌹 አይ መታደል! አይ መባረክ! 🌹
❤ የእመቤታችን ጣዕመ ውዳሴዋ የበዛለት ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም በእንዚራ ስብሐቱ ላይ ስለ ውበቷ በተመስጦ ኾኖ ያቀረበላትን ውዳሴ እነሆ፦
“ኦ ፍቅርት ውዕየ ልብየ በእሳተ ፍቅርኪ ወነደ ኅሊናየ እምኀልዮትኪ …”
🔥🌹 “ውዲቱ ሆይ፣ በፍቅርሽ እሳት ልቤ ተቃጠለ፤ አንቺንም ከማሰብ የተነሣ ኅሊናዬ ነደደ፤ ለምስጋናሽ ቃሌን ከፍ ከፍ አደርጋለኊ፤ አንቺን ለማመስገንም አንደበቴን አከፍታለኊ።
👑 ንግሥት ሆይ፣ አንደበቴ ቅንነትሽን በመናገር ደስ ይለዋል፤ ከንፈሮቼም በቸርነትሽ ጣዕም ነገር ደስ ይሰኛሉ፤ ሰላም እያልኹሽም ለስምሽ አጠራር እኔ እሰግዳለኊ።”
🖤🌿 ንግሥት ሆይ፣ የራስሽ ክፍክፋት ተፈጥሮ እንደ አሞራ ጥቁር የኾነ ጠጒርሽም እንደ ሐር የሚመስል ነው።
👑 የራስ ወርቅሽ የቃል ኪዳን ምልክት ነው፤
✨ የንጽሕናሽ ብርሃንም እንደ ጧት ወገግታ ነው።
⚡🌙 ግርምቲቱ ሆይ፣ የቅንድቦችሽ ነበልባል የመብረቅ ፍንጣቂ ነው፤
👁️ ዐይኖችሽም እንደ ጨረቃ ምላት ብርሃንን የተመሉ ናቸው፤
👂 ጆሮችሽም የደስታ በሮች ናቸው፤
🌺 የጒንጮችሽ ቅላትም እንደ ሮማን ቅርፍት ነው።
🌸🪟 ንግሥት ሆይ፣ አፍሽ የበጎ መዐዛ መስኮት ነው፤
💋 ከንፈሮችሽም የደስታ መፍሰሾች ናቸው፤
🍃 የአፍንጫሽ መዐዛም የበረሓ እንኮይ ነው፤
❄️ የጥርሶችሽ ንጣትም እንደሚያምር በረዶ ነው።
🍯🥛 ምርጢቱ ሆይ፣ የአንደበትሽ ሥር የወተት ምንጭ ነው፤
🍯 የንግግርሽ ቃልም እንደ ማር የጣፈጠ ነው፤
🌿 የእስትንፋስሽ ቃልም የሽቱ ቅመም ብናኝ ነው፤
🍯 ጒረሮሽም የማር ወለላ አረፋ ነው።
👰✨ የተሸለምሽ ያጌጥሽ ሙሽሪት ሆይ፣
🏅 የአንገትሽ መገናኛ እንደ ወርቅ ዘንግ ነው፤
🕊️ ትከሾችሽም የሰላምና የቅንነት ማረፊያዎች ናቸው፤
✨ የጀርባሽ ልብስም የብርሃን ሐር ነው፤
📖 ደረትሽም የዕውቀት አዳራሽ ነው፤
☦️ ጉያሽ የመለኮት ማረፊያ ናቸው፤
🤲 እጆችሽም በንጽሕና አንባር የተሸለሙ ናቸው።
🔥 ክንዶችሽም የንጉሥ መጠጊያዎች ናቸው፤
💪 ክርንሽም የኀይል ረድኤት ቦታ ነው፤
🔥 ክንዶችሽም የእሳት ምሳግ ናቸው፤
🤲 መኻል እጆችሽም ለመስጠት የተዘረጉ ናቸው፤
🏵️ በጥፍሮችሽ የተጋረዱ ጣቶችሽ እንደ ወርቅ ፍቅፋቂ ናቸው።
🍇🌿 ሙሽሪት ሆይ፣ ጡቶችሽ እንደ ወይን ፍሬ የተወደዱና ያማሩ ናቸው።
🌾 ጐኖችሽም በወርቅ ሐመልማል ያጌጡ ናቸው።
🌸 የማሕፀንሽ መቅደስ በአበባ የታጠረ ነው፤
💗 የልቡናሽ ጥልቀትም በቸርነት ቃል የተሞላ ነው፤
📜 ኲላሊቶችሽ የትእዛዝ ጽላት ናቸው፤
🧠 ኅሊናሽም የጥበብ መሠረት ነው፤
🕊️ አንጀትሽም የይቅርታ ሣጥን ነው፤
⛪ የውስጥ ሰውነትሽም የቅዱሳን ቅድስት ምልክት ነው፤
🔘 የዕንብርትሽ ዙሪያም እንደ ማኅተም ቅርጽ ነው፤
👑 ማሕፀንሽም የምስጋና ዙፋን ነው።
📖🔒 የድንግልናሽም ምሳሌ የታተመ የነቢያት መጽሐፍ ነው፤
✨ የወገብሽ ትጥቅም የቅድስና ጸጋ ነው፤
☁️ ጒልበትሽም የአርያም ወገን ናቸው፤
🏛️ የጭኖችሽ አነዋወርም እንደ እብነ በረድ ምሶሶች ነው፤
👣 እግሮችሽም ምሕረትን ለማድረግ የተፋጠኑ ናቸው፤
🌿 የማይታበዩ ጫማዎችሽም የጥበብ መድረክ ናቸው፤
🛤️ እግርሽም በቅንነት ጐዳና የጸኑ ናቸው፤
💎 የእግርሽ ጣቶችም በጥፋት ደንጊያ የማይሰነካከሉ ናቸው፤
✨ ጥፍሮችሽም በላያቸው እንደ ብርሃን ብልጭ የሚሉ ናቸው።
🌴🌹 የቁመናሽ አካልም እንደ ዘንባባ ያማረ ነው፤
🌺 የመልክሽ ደም ግባትም ለዐይን የተወደደ ነው።
🌷 ድንግል ሆይ፣ እጅግ በጣም አማርሽ፤
🕊️ ከራስሽ እስከ እግርሽ ክፉ ነገር የለብሽም።
✨ ደም ግባትሽን የሚመስለው የለም፤ ኹለንተናሽንም የሚተካከለው የለም።
🌹 ምርጢቱ ሆይ፣ መልካም በኾነውና በጎም በኾነው ኹሉ መሰልኹሽ፤ ነገር ግን ምስጋናሽን መጨረሽ አልቻልኹም።
— አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ
🌞✨ የመልክአ ማርያም ደራሲም የአምላኩን እናት ቅድስት ድንግል ማርያምን ፊቷን ለማየት ሽቶ፣ በናፍቆት ኾኖ፦
📜 “ሰላም ለመልክእኪ ዘተሠርገወ አሜረ ዘያበርህ ወትረ ፍቅርትየ አንቲ እንተ ታበድሪ ፍቅረ አርእዪኒ ገጸ ዚኣኪ ማርያም ምዕረ ዘኢይሰምዖ ካልእ እንግርኪ ነገረ” 📜
☀️ “ኹልጊዜ የሚያበራ ፀሓይን ጌጥ ላደረገ መልክሽ ሰላምታ ይገባል።
💞 ፍቅርን የምትመርጪ አንቺ ፍቅረኛዬ ማርያም፣
🙏 ሌላ የማይሰማው ነገርን እነግርሽ ዘንድ፣ አንድ ጊዜ ያንቺን ፊት ግለጪልኝ”
በማለት ተማፅኗታል።
⛪🕯️ በመኾኑም በደብረ ምጥማቅ የተገለጠችላቸው ምእመናን የአምላክን እናት አይተው እንደተደሰቱ፣ ዛሬም ለእኛ በመስቀል ሥር ከልጇ ለተቀበለችን ለአደራ ልጆቿ በረድኤት ትገለጽ ዘንድ፣ አበው ካህናት ሌሊቱን በሰዓታት ምስጋና፦
🙏 “ንዒ ኀቤየ ኦ ድንግል ምስለ ወልድኪ ፍቁርኪ ኢየሱስ ክርስቶስ ከመ ትባርኪ ላዕሌነ” 🙏
🕊️ “ድንግል ሆይ፣ ከተወዳጅ ልጅሽ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋራ ወደ እኔ ነዪ፤ እኛን ትባርኪ ዘንድ፣ በእኛ ላይ በረከትን እንድታሳድሪ” 🕊️
🌹✨ የአምላክ እናት ሆይ፣ ዛሬም ለእኛ በረድኤት ተገለጪልን፤ በልጅሽ ፊት አማልጂን፤ በረከትሽም ከእኛ አይለይ። ✨🌹
✍ ከመጋቤ ሐዲስ ዶ/ር ሮዳስ ታደሰ
👉 በመስቀል ሥር ስጦታችን የተጽናናችኹ የብርሃን ልጆች፣ በአስተያየት መስጫው ላይ እናታችኹን አወድሷት።