15/07/2026
የርእሰ ገዳማት ወአድባራት ጣና ቅዱስ ቂርቆስ የአባቶችና የእናቶች አንድነት ገዳም የ፫ ሺ ዓመት ታሪኩን ሊያከብር ነው።
ገዳሙ ክብረ በዓሉን አስመልክቶ የሰጠውን ሙሉ መግለጫ እንደሚከተለው እናቀርባለን።
“ወተዘከር መዋዕለ ትካት ወሐሊ ዓመተ ለትውልደ ትውልድ ተሰአሎ ለአቡከ ወይነግረከ ወለሊቃውንቲከ ይዜንዉከ - የዱሮውን ዘመን አስብ፥
የብዙ ትውልድንም ዓመታት አስተውል፤
አባትህን ጠይቅ፥ ያስታውቅህማል፤
ሽማግሌዎችህን ጠይቅ፥ ይነግሩህማል።” ዘዳ ፴፪፥፯
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት የርእሰ ገዳማት ወአድባራት ጣና ቅዱስ ቂርቆስ የአባቶቾና የእናቶች አንድነት ገዳም የሦስት ሺ ዓመታትን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ ።
በኢትዮጵያና በመላው ዓለም ለምትገኙ ኢትዮጳውያንና ኤርትራውያን በሙሉ፦
ገዳማችን ርእሰ ገዳማት ወአድባራት ጣና ቅዱስ ቂርቆስ የአባቶችና የእናቶች አንድነት ገዳም ታሪክን፣መንፈሳዊነትን፣ አምልኮተ እግዚአብሔርን አዋሕዶ በዘመናት ከነሙሉ ክብሩ የተሻገረ የበረከት ምንጭ ነው።ከብዙ ጸጋዎቹና በረከቶቹም ውስጥ ዋና ዋናዎቹን ለመግለጽ እንሞክራለን ፦
፩.ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከመወለዱ ፱፻፹፪ ዓ/ዓ ቀድሞ ታቦተ ጽዮን ያረፈችበት ከአራቱ መናብርተ ጽዮን ከመርጡለ ማርያም፣ ከተድባበ ማርያም ፣ከአክሱም ጽዮን ጋር አንዱ የሆነና የሊቀ ካህናቱ መንበር የነበረ፣ የሊቀ ካህናቱ አዛርያስ መቃብር የሚገኝበት፣እስከ ጌታ ልደት መሥዋዕተ ኦሪት ያልተቋረጠበት የሕግና የነቢያት ማኅደር የሆነ ገዳም ነው።
፪.በሐዲስ ኪዳን ዓለምን ቤዛ ሆኖ ያድን ዘንድ ጌታችን በእኛው ሥጋ ተወልዶ ከኢየሩሳሌም ወደ ግብጽ ከእናቱ ጋር በተሰደደ ጊዜ በደቡባዊው ግብጽ በኩል አድርገው ኢትዮጵያ መጥተው የኢትዮጵያ አድባራትና በረሃዎችን ከባረኩ በኋላ ደሴተ ጣና ሲደርሱ አንሥእ ኃይለከ ወነዓ አድኅነነ የሚለውን የኦሪቱ ሊቃ ካህናት ሲተረጉም ከመድረሳቸውም በላይ የታመመ ልጁንም ቡሩኩ ሕጻን ፈውሶለት ፣ደሴቱ ዙሪያ ያሉ ሕዝቦችም ተአምራቱን ዓይተው በክብር ተቀብለዋቸዋል።እመቤታችንም ከልጇ ጋር መቶ ቀናትን ደሴቲቱን በመባረክ በቋይታ ስትመለስ ለኢትዮጵያውያን የበረከት የአሥራት እናትነት ቃል ኪዳን ሰጥቷት በደመና ተጭና ስትመለስ ጸዓና በደመና እያሉ የቆሙ መላእክት ስላመሰገኑ በዚያው ስሙ ጸንቶለት ቀርቷል። ይኽውም ይታወቅ ዘንድ የሕጻኑ መድኅነዓለም ክርስቶስና የእናቱ የእመቤታችን እንዲሁም የአህያው እግረሰኮናቸው ያረፈበት ከአዓለት ደንጌያው ላይ የዓይን ምሥክር ሆኖ እስከአሁን ድረስ ይገኛል
፫. የኢትዮጵያን የመጀመሪያው ጳጳስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ከአክሱም ተነሥተው በመምጣት መሥዋዕተ ኦሪትን አሳልፈው መሥዋዕተ ሐዲስን ተክተው ባርከው ያጠመቁበት ሲሆን ያጠምቁበት የነበረው የእጅ መስቀላቸውና ካባቸውም በገዳሙ ይገኛል።
፬.እግዚአብሔር አምላካችን ሰውን ለማዳን ምክንያት ይሻልና ለቅዱሳን ብዙ ቃል ኪዳን ሰጥቷቸዋል። በመሆኑም ለቡሩኩ ሕጻን ሰማዕት ለቅዱስ ቂርቆስ ከረኀብና ከቸነፈር የመጠበቅ ቃል ኪዳን ስለሰጠው በደሴቱ የቅዱስ ቂርቆስ መታሰቢያ ታቦት ተባርኮ ሲገባ በደሴቱ ዙሪያ የነበረው መቅሰፍት በመጥፋቱ የቀደመ የቦታው ስም ሰሐፍ ጽዮን (መካነ ሣህል) እየተባለ የጠራ የነበረ ቢሆንም ከዚያ ቀን ጀምሮ በቅዱስ ቂርቆስ ስም እየተጠራ ሰማዕቱም እየባረከው እስከዘ ዛሬ ጸንቶ ኖሯል።
፭.ኢትዮጵያዊዉ ማኅሌታዊ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ መጥቶ ያስተማረበት ቀለም በጥብጦ ብራና ዳምጦ ድጓ እንደ ጻፈ በገዳማውያን ዘንድ የሚነገር ሲሆን ቀለም የበጠበጠባቸው ድንጋዮች ታሪክን አጽንተው በገዳሙ ይገኛሉ።በተጨማሪም የቅዱስ ያሬድ የበረከት የእጅ መስቀልና ካባው ለበረከት ያለ ሲሆን ይህም መስቀል ጠፍቶ ወደ ፈረንሳይ ሀገር ከሄደ በኋላ በ፳፻፮ ዓም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት እጅ በክብር ወደ ገዳማችን ተመልሷል።
፮.በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የምሥጢርና የትርጓሜ ድልድይ የሆኑት መምህር ኤስድሮስ ፫፻ መጻሕፍትን በቃል አጥንተው ምሥጢረ መጻሕፍትን የቀመሩበት የትምህርተ ሃይማኖት ፈለግ የሆነ ገዳም ነው።
፯ ፤ አቡነ አፍቅረነ እግዚእ ቅድስት ወለተ ጴጥሮስ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራና ብዙ ቅዱሳን
ገዳማችን እነዚህንና እግዚአብሔር የሚያውቃቸው የማይመረመሩ ምሥጢራትን በማይናወጥ መሠረት ይዞ እያበራ አነሆ ባለንበት ዘመን ሦስት ሺ ዓመታት ሞልቶት።የተገባን ባንሆንም የዚህ ሦስት ሺ ዓመታት ዘውድ የሆነ ዓመት በገዳማችን በመገኘታችን አምላከ ቅዱስ ቂርቆስ ወቅዱስ ያሬድ እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን። ሁላችሁም ኦርቶዶክሳውያን እንኳን ደስ አላችሁ!
ይህ የሦስት ሺህ ዓመት አክሊል በቀላል የማይገኝ ጸጋ በመሆኑ የገዳሙን ሦስት ሺኛ ዓመት በዓል በማክበር እግዚአብሔርን ለማመስገን የ፴፻ ዓመቱ ሕያው ገዳም ጣና ቂርቆስና የነገ ልዕልናው በሚል መሪ ቃል በዓሉን ለማክበር እየተዘጋጀን እንገኛለን ።በዓሉን የምናከብረውም፦
ሀ. ሦስት ሺ ዓመት ሙሉ ገዳማችንን በበረከት ያጸና እግዚአብሔርን ለማመስገን።
ለ.የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን የሦስት ሺ ዓመታት የአምልኮተ እግዚአብሔር ጉዞና የሀገር መሠረትነቷን ለመግለጽ።
ሐ.ገዳማችን በሦስት ሺ ዓመታት ውስጥ የታሪክና የመንፈሳዊነት ምልክትነት ለትውልድ ቆጥሮ ሰፍሮ ለማሳወቅ።
መ.ከሦስት መቶ በላይአባቶችና እናቶች መነኮሳትና ከመቶ ሀያ በላይ ደቀመዛሙርት ያሉት ይህ ገዳም በመንፈሳዊነትና በልማት ጠንክሮ በቀደመ ልዕልናውና ክብሩ መጪ ዘመናትን እንዲሻገር የተቀረጹ ፕሮጀክቶችን አስተዋውቆ ለመተግበር።
ይህ የሦስት ሺ ዓመት ታሪካዊ በዓል እግዚአብሔር ቢፈቅድና ብንኖር መስከረም አሥር ቀን ፳፻፲፱ዓም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስታያን፣ ምእመናን በተገኙበት የሚከበር ሲሆን እስከዚያ ግን ክረምቱን ሙሉ በዐደውደ ርእይና በጉባኤያት በተለያዩ መድረኮች ስናከብር እንቆያለን።
በመሆኑም በመላው ዓለም ያላችሁ ኦርቶዶክሳውያን ሁሉ እግዚአብሔር ፈቅዶ ከገዳማችን ጋር እንኳን ለሦስት ሺ ዓመት በሰላም አደረሳችሁ እያልን እስከዚያው በሚተላለፉ ጉባኤያትና ዐውደ ርእዮች አብራችሁን እንድትከርሙ፣ገዳማችንን በመንፈሳዊነትና በሥርዓት እንዲሁም በልማት አጽንተን ልዕልናውን ጠብቀን ለትውልድ እንድናስተላልፍ ኦርቶዶክሳዊ ድርሻችንን እንድንወጣ በእግዚአብሔር ስም ጥሪያችንን እናስተላልፋለን ።
አምላከ አበው እግዚአብሔር ሀገራችንን ኢትዮጵያን በፍጹም ሰላም ይጎብኝልን።
© eotc